የኮ/ል ደመቀ ዘውዱ የፍርድ ቤት ውሎ

ጌታቸው ሺፈራው

ፍርድ ቤቱ ኮ/ል ደመቀ ያቀረቡትን መቃወሚያ በመቀበል የብሔራዊ ደኅንነት እና መረጃ አገልግሎት ያቀረበው ሪፖርት አልተረጋገጠም ብሏል! በመሆኑም ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ባቀረቡት መቃወሚያ መሰረት የቀረበባቸው ማስረጃ ትክክለኛ መሆኑን ለማረጋገጥ የድምፅ ቅጅ እንዲመጣ ታዟል። ከሌሎች ግለሰቦች ጋር ተደዋውለውባቸዋል የተባሉት የስልክ ቁጥሮችም እንዲጠቀሱና እንዲረጋገጡ ተበይኗል።

ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ጥቅምት 27 ቀን 2010 ዓም ጎንደር ከተማ ላይ ከሚያስችለው የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ለብይን ተቀጥረው እንደነበር ይታወሳል። የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ላይ ባቀረበው የ”ሽብር” ክስ የሰው ምስክሮችን ማሰማቱን እንዲሁም፣ የሰነድ ማስረጃዎችን አጠናቅቄ አቅርቤያለሁ በማለት ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ የቀረበባቸውን ክስ ይከላከሉ ወይም መከላከል አይገባቸውም የሚል ብይን እንዲሰጥ ጠይቆ ነበር። በመሆኑም የአቃቤ ህግ ማስረጃዎችን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት27/2010 ዓም ቀጠሮ ይዞ ነበር።

የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በማስረጃነት ያቀረበው የብሔራዊ መረጃ ደኅንነት አገልግሎት ያዘጋጀውና ከስልክ ምልልስ ተገኘ የተባለ ሪፖርት “ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ የሽብር ወንጀል ለመፈፀም የተለያዩ የስልክ ቁጥሮችን በመጠቀም ለነ መብራቱ ጌታሁን፣ አታላይ ዛፌ እና ለሌሎች ግለሰቦች ስልክ በመደወል ስለ “ወንጀሉ” ሲነጋገሩ ቆይተዋል” የሚል ሰፋ ያለ ይዘት ያለው ማስረጃ እንደነበር ተገልፆአል።

የተከሳሽ ጠበቆች በበኩላቸው ፍርድ ቤቱ ተከሳሹን ተከላከል ወይንም መከላከል አይገባህም በሚል ብይን ከመስጠቱ በፊት የሰነድ ማስረጃዎቹ በሕጋዊ መንገድ ያልተገኙ ናቸው በማለት ሰፋ ያለ መቃወሚያ አቅርበዋል። ካቀረቧቸው መቃወሚያዎች መካከል ዋናው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከስልክ ምልልስ ያገኘሁት ነው ብሎ ያዘጋጀው ሪፖርት ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ያደረጉት የስልክ ንግግር እንዳልሆነ በሰፊው አትቷል። መቃወሚያው የስልክ ንግግር ቀጥተኛ ማስረጃው ድምፅ በመሆኑ ይህ ማስረጃ ከስልክ ንግግር ወደ ፅሑፍ መለወጡ ከተረጋገጠ ወደ ፅሑፍ የተለወጠው የድምፅ ቅጅ ሊቀርብ ይገባው ነበር የሚል ነበር።

በሌላ በኩልም ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ በስልክ አግኝተዋቸዋል የተባሉ ግለሰቦች ስልክ ቁጥር አለመጠቀሱ ሪፖርቱ ከስልክ ምልልስ የተገኘ መሆኑን ስለማያረጋግጥ የሰነድ ማስረጃው ውድቅ እንዲደረግልን በማለት መቃወሚያዎችን አቅርበው የነበር ሲሆን ፍርድ ቤቱ መቃወሚያዎቹን ተቀብሏቸዋል።

ፍርድ ቤቱ ወደ ዋናው ክርክር ገብቶ ብይን ከመስጠቱ በፊት መቃወሚያ የቀረበባቸው የሰነድ ማስረጃዎች ትክክለኛ መሆናቸው ካልተረጋገጠ በፍሬ ጉዳይ ላይ ብይን መስጠት እንደማይችል መግለፁን ጠበቃ አለልኝ ምህረቱ ገልፀዋል። የኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ጠበቆች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ አለልኝ ምህረቱ እንደገለፁት ፍርድ ቤቱ ማስረጃዎቹ ያልተረጋገጡ ስለመሆናቸው ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶችን አስቀምጧል። እነዚህም:_
1) የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ሪፖርቱን አገኘሁት ያለው ከስልክ ምልልስ ነው ከተባለ፣ በተከሳሽና በሌሎቹ ግለሰቦች መካከል ተደረገ የተባለው የስልክ ምልልስ በትክክል ሊኖር ስለሚችል ወደፅሑፍ መቀየሩን ወይም የተቀነሰ እና የተጨመረበት ነገርም ካለ ይህን ማጣራት አስፈላጊ በመሆኑ፣
2)ከኮለኔል ደመቀ ዘውዱ ጋር ስለ “ሽብር ወንጀል” ተነጋገሩ የተባሉ ግለሰቦች ስልክ ቁጥሮች በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ሪፖርት ላይ ስላልተጠቀሱ ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ በስልክ አነጋግረዋቸዋል የተባሉት ግለሰቦች የስልክ ቁጥሮች እና ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ተገናኙባቸው ተብለው በሪፖርቱ የተጠቀሱ ስልክ ቁጥሮች የእርሳቸው ስለመሆናቸው ማረጋገጥ ያስፈልጋል የሚሉ ናቸው።

ፍርድ ቤቱ የብሔራዊ ደኅንነትና መረጃ አገልግሎት ሪፖርትን በማጣራት የሰነድ ማስረጃ ላይ በቀረበው መቃወሚያ ላይ ውሳኔ መስጠት እንዲያስችለውም ሁለት ትዕዛዞችን አስተላልፏል። ትዕዛዞቹም:_
1ኛ) የብሔራዊ ደኅንነትና መረጃ አገልግሎት ለዐቃቤ ሕግ ማስረጃነት በሪፖርት ያቀረበው ከስልክ ምልልስ ተገኘ የተባለ ሪፖርት ያዘጋጀበትን የስልክ ምልልስ የድምፅ ቅጅ እንዲያቀርብ እና፣
2ኛ) ከኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ጋር በስልክ ተገናኙ የተባሉት ግለሰቦች ስልክ ቁጥሮች፣ እንዲሁም እነዚህ ስልክ ቁጥሮች ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ደወሉባቸው ከተባሉት ስልክ ቁጥሮች ጋር ግንኙነት የነበራቸው መሆንን የሚያሳይ ማስረጃ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ዐቃበ ህግ እነዚህን ማስረጃዎች እንዲያቀርብም ለህዳር 19/2010 ዓም ቀጠሮ ተይዟል።

ፍርድ ቤቶች በ”ሽብር ወንጀል” ላይ የብሔራዊ ደኅንነትና መረጃ አገልግሎት ከስልክ ምልልስ ያገኘሁት ነው ብሎ የሚፅፈው ሪፖርትን ለማረጋገጥ የድምፅ ቅጅ በማስመጣት ከማረጋገጥ ይልቅ ሪፖርቱን በቀጥታ እየተቀበሉ ይገኛሉ። በኮ/ል ደመቀ ላይ የቀረበው የደኅንነት ሪፖርቱ ላይ መቃወሚያ ካቀረቡት መካከል አንዱ የሆኑት ጠበቃ አለልኝ በኮ/ል ደመቀ ተቃውሞ ላይ የተሰጠውን ትዕዛዝ ሌሎች መሰል ክሱችን የሚያስችሉ ችሎቶችም ቢጠቀሙበት “ዳኞች ተገዥነታቸው ለህሊናቸውና ለሕጉ ብቻ ነው !” የሚለውን መርህ ማስከበር ይቻል ነበር ብለዋል።

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: