(ዳጉ ሚዲያ) የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋች፥ የኢትዮ ቲንክታንክ እና ማኀበራዊ ገፅ ጦማሪ ስዩም ተሾመ ከሚኖርበትና ይሰራበት ከነበረው ወሊሶ ከትማ በፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እስር ቤት ከፍተኛ ስቃይና እንግልት እንደተፈፀመበት ተጠቆመ።
ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ. ም. ጀምሮ በድጋሚ ለ6 ወራት የሚቆይ የአቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ በተደረገ ሳምንት ሳይሞላው ስዩም ተሾመ ከመኖሪያ ቤቱ ታፍኖ ማዕከላዊ በሚባለው የፌደራል ወንጀል ምርመራ ማዕከል ከፍተኛ ምርመራ እየተደረገበት ሲሆን፤ የአገዛዙ መርማሪዎች አካላዊ ጥቃት በመፈፀምና በማስገደድ የሚጠቀማቸውን የኮምፒዩተርና የኢንተርኔት አገልግሎት የይለፍ ቃሎች(ፓስ ወርድ) መወሰዱም ታውቋል። መርማሪ ፖሊሶችም የፍርድ ቤት ክስ በመመስረት ተጨማሪ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ በጠየቁት መሰረት እንደተፈቀደላቸውም ለማወቅ ተችሏል። ስዩም ተሾመን ማዕከላዊ ምርመራ በመሄድ ለመጎብኘት የሞከሩ ወዳጆቹ፥ የመብት ተሟጋቾችና የስራ ባልደረቦቹ እንዳይጎበኙት መከልከላቸውም ታውቋል።
ስዩም ባለፍው ለ10 ወራት ተግባራዊ ተደርጎ በነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተመሳሳይ መልኩ ከመኖሪያ ቤቱ በገዥው ስርዓት የፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በምርመራ ወቅት ከፍተኛ የአካል ጥቃት ተፈፅሞበት እንደነበርና ከተወሰኑ ወራት እስር በኋላ መለቀቁ ይታወሳል።