ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ቀንድ

ካሊድ ኢብራሂም
nafkothager@gmail.com

በዓለም አቀፍ ደረጃ የአፍሪካ ቀንድ በርካታ የንግድ እንቅስቃሴ የሚደረግበት የቀይ ባህር እና የሰሜን ምዕራብ ህንድ ውቅያኖስ አካባቢ የሚገኝ ዋነኛ ዓለም አቀፍ የባህር ንግድ እንቅስቃሴ የሚካሄድበት አካባቢ ነው። ቀጠናው በቅርብ ርቀት የአረብ ሀገራት የሚገኙ ሲሆን፤ አካባቢው ከትናንሽ ሀገር በቀል የፖለቲካ ሽኩቻ እስከ ክልላዊ እና ዓለም አቀፋዊ የፖለቲካ ሽኩቻና ፉክክር የሚካሄድበት ሰላም አልባ የግጭት ቀጠና ነው። በቀጠናው ኤርትራ፥ ጅቡቲ፥ ሱዳን፥ ደቡብ ሱዳን፥ ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ ይገኛሉ።

ቀጠናው ባለው የተፈጥሮ ሃብት አይታማም። ውድ ከሆኑ ማዕድናት፥ ነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ፥ በርካታ ወንዞች፥ የቁም እንሰሳት፥ ስራ ፈት የሆኑ ለንግድ ምቹ የሆኑ የባህር በሮች እና በተፈጥሮ ቱሪዝም የበለፀገ አካባቢ ነው። የአየር ፀባዩ የተለያየ ቢሆን ለነዋሪውም ይሆን ከሌላ አካባቢ መጥቶ መዋዕለ ነዋይ አፍስሶ መኖሪያውን እዚህ ማድረግ ለሚፈልግ የተመቸ ነው። ነገር ግን በቀና እና የሰለጠኑ መሪዎችና የፖለቲካ ልሂቃን እጦት በኢኮኖሚ፥ በመሰረተ ልማትም ይሁን በቴክኖሎጂ እጅግ ኋላቀር አካባቢ ነው። ቀውስ የማያጣው የአፍሪካ ቀንድ።

የአፍሪካ ቀንድ በአሁን ወቅት በርካታ ህዝብ የሚኖርበት ሲሆን፤ በተለይም ኢትዮጵያ 105 ሚሊዮን፥ ኤርትራ 5 ሚሊዮን፥ ጅቡቲ 1 ሚሊዮን፥ ሱዳን 40 ሚሊዮን፥ ደቡብ ሱዳን 12 ሚሊዮን 500 ሺህ እና ሶማሊያ 14 ሚሊዮን 500 ሺህ በድምሩ 178 ሚሊዮን አካባቢ ህዝብ ይኖራል። ቀጠናው ርስ በርስ በሚሻኮቱ እና ሐሳብን በጦር መሳሪያ ባሉ አማጺያን እና እብምባገነን መሪዎች ዋሻ ሲሆን፤ ከአቅራቢያው አረብ ሀገራት እስከ ምዕራባውያን ፍላጎቶች የሚርመሰመሱበትም ነው። በተለይ ፍትህ፥ ዴሞክራሲ፥ እኩልነት፥ የፕሬስ ነፃነት፥ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ እና የሰብዓዊ መብት በግልፅ የሚጨፈለቁበት የአምባገነን ጣዖታት መሪዎች ልዩ ግዛት ነው ማለት ይቻላል።

በተለይ በፖለቲካው መድረክ በጦር መሳሪያ ወደ ስልጣን ከመጡት ውጭ የብዙሃን ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፎ የማይስተናገድበት ሲሆን፤ ሐሳብን በነፃነት መግለፅና የፕሬስ ነፃነት ተግባራት በሽብር የሚያስቀጡ ከባድ ወንጀሎች ነው። በአንፃሩ ገዥዎች በይፋ የሚፈፅሙት የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብት ረገጣ፥ ሙስና እና በስልጣን መባለግ እንደልማትም የሚቆጠርበት ልዩ ቀጠና ነው።

የአካባቢው ሰላማዊ ዜጎች ከመንደር የጎበዝ አለቃ እስከ ማዕከላዊ መንግሥት ሹማምንት የሚፈፅሙት ርግጫ ከሞት የተረፉት ሀገራቸውን ጥለው ይሰደዳሉ። ለአምባገነኖቹ ገዥዎች ግን ይህም የልማት አካል ተደርጎ ይወሰዳል። ዜጎቻቸውን ከቀዬአቸው እና ሀገራቸው የበረሃና የባህር ሲሳይ ከሆኑት የተረፉት ብሰቆቃ ውስጥ ላለው ወገናቸው የሚመፀውቱት ገንዘብ በምንዛሪ መልክ ለክፉ መሪዎች ኪስ ማደለቢያ እና ጥይት መግዣ ከመዋል አይድንም።

የቀጠናው የገንዘብ ሀብት ኃላፊነት በማይሰማቸው ጨካኝ መሪዎች አማካኝነት ከደሃው ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቆ የገዥዎች ቤተሰቦችና ወዳጆቻቸው ከሚንደላቀቁበት የተረፈው ብር በሀብታም ሀገራት ባንኮች ወስዶ መሰወርና ማከማቸት የተለመደ ተግባር ነው። ምክንያቱም ተጠያቂነትና ግልፅነት እንዲሁም የህግ የበላይነት የለምና። በተለይ ርሷን እንደ ነፃ ሀገር ከምትታየውና በዓለም አቀፉ ማኅበረስብ የሶማሊያ ፌደራል ግዛት አካል ተደርጋ ከምትቆጠረው ሶማሌ ላንድ በስተቀር ሁሉም ገዥዎች ወደ ስልጣን የያዙት በጦር መሳሪያ አመፅ የቀድሞ ገዥዎችን ገልብጠው ነው አሊያም በውጭ ኃይሎች ድጋፍ ነው። ለዚህም ይመስላል ራሳቸው ከዴሞክራሲ ጋር የየዕለት ተግባራቸው ተራርቆ ስሙን ሲደጋግሙ የሚውሉት። ለዜጎቻቸውም የተስፋ ዳቦን ከመመገብ በተጨማሪ የዕለት ጉርስ የሚቀመስ በሚናፍቅ ዜጎቻቸው ስም ሳይቀር እየለመኑ ልማት በሚዲያ የሚሰራጭ ተስፋ የሚመግቡም አሉ። ግን ምን ዋጋ አለው። ሁሉን ነገር መደበቅና ዋሽቶ ማሳመን አይቻል ነገር።

በኢትዮጵያ ዶ/ር አብይ አህመድ መጋቢት 2010 ዓ ም የጠቅላይ ሚኒስተርነትን መንበር ከያዙ በኋላ ከወትሮ በተለየ መልኩ ብሩህ ተስፋ ይታይባታል። ለዓመታት ያለበደላቸው በሰቆቃ ስር የነበሩ አብዛኛው የፖለቲካ እስረኞች ከስር ነፃ እንዲወጡ ተደርጓል። ዋነኛ የአፈና እና የመጨቆኛ ተቋማትና ዋነኛ ተዋናይ ግለሰቦች ከቦታቸው እንዲነሱ ተደርጓል። በጎ የሆኑ የተለያዩ ማሻሻያዎች ተደርገዋል፤ እየተደረጉም ነው። ለዚህም ይመስላል ለአስርት ዓመታት ሰላምና ዴሞክራሲን ይናፍቅ የነበረ ህዝብ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የድጋፍ ሰልፉን ችሮታል። ይሁን እንጂ አስታዋሽ ያጡ እና ሚዲያ ያላወቃቸው የፖለቲካ እስረኞች አሁንም በትግራይና እና በተለያዩ አካባቢ ወህኒ ቤቶች አሉ። ሌሎች ማሻሻያዎች ይጠበቃሉ። ነገር ግን የአርካ ቀንድን በሚመለከት የዶ/ር አብይ ወደ ሥልጣን መምጣትን ተከትሎ ከሀገር ውስጥ ባልተናንሰ መልኩ በቀጠናው ብሩህ ተስፋ ይታያል። በህዝብ ቁጥር አምስቱ የቀጠናው ሀገሮች ተደምረው ኢትዮጵያን አያህሉም። ስለሆነም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ነባራዊ ሁኔታ በቀጠናው ላይ ያለው ሚና ምን ያህል እንደሆነ በቀላሉ ማየት ይቻላል።

Horn of African Map
የአፍሪካ ቀንድ ሀገሮች ካርታ (ፎቶ ዊኪፔዲያ)

ዶ/ር አብይ ሥልጣን በያዙ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከደቡብ ሱዳን በስተቀር ሁሉንም የቀጠናውን እና የአካቢውን ሀገሮች በመጎብኘትና ያረበበውን ሌላ የግጭትና የስጋት ፖለቲካ ለማረጋጋት ሞክረዋል። በተለይ ላለፉት 21 ዓመታት በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ያለውን የጦርነትና የግጭት ስጋት ወደ ሰላም መቀየራቸው ለቀጠናው ትልቅ ተስፋ ነው። በጎረቤት ደቡብ ሱዳን ውስጥ ያለውንም የርስ በርስ ግጭትና ስጋት ለማረጋጋትና ለማርገብ የወሰዱት ርምጃም የሚበረታታ ነው። በተለይ ተፋላሚዎቹ ሙሉ ለሙሉ ወደ ሰላም ከመጡ ለዶ/ር አብይም እንደ ሀገር ለኢትዮጵያም ትልቅ ድል ነው።

ነገር ግን በጠቅላይ ሚንስትር አብይ እና በፕሬዘዳንት ኢሳይያስ መካከል እንዲሁም በሌሎች የጎረቤት ሀገሮችም ይሁን በቀጠናው መካከል የሚደረጉ ስምምነት እጅግ በጣም ጥንቃቄና ብስለትን ይጠይቃሉ። ምክንያቱም ቀጠናው ከባለቤቶቹ ሀገራት በተጨማሪ ለዘመናት ለውጭ ጣልቃ ገብ ፖለቲካ ክፍት የነበረ በመሆኑ እና በነበሩ ግጭቶች በፖለቲካውም ይሁን በኢኮኖሚው ተጠቃሚ የነበሩ ሶስተኛ ሀገራት ስላሉ በአንድ ግለሰብ ወይም ሀገር ቅንነትና ተነሳሽነት ብቻ ዘላቂ ሰላም ማምጣት አይቻልም። ለጋራ ሰላም የጋራ ተነሳሽነትና የጋራ ተጠቃሚነት ትልቅ ድርሻ አለው።

ላለፉት ጊዜያት ከልክ ባለፈ ራስ ወዳድ በሆኑ ገዥዎች ፍላጎትና ጥቅም ላይ ብቻ ተወስኖ የነበረው በኢትዮጵያና በመካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት መካከል የነበረው ግንኙነትም ከጥርጣሬ ይልቅ ወደ አጋርነት የመሄድ አዝማሚያ ይታይበታል። ይህ የሚበረታታና ጥሩ ጅምር ነው። ይሁን እንጂ የነ አቶ መለስ ዜናዊ ርካሽ የግል ጥቅምንና ፍላጎትን ብቻ ማዕከል አድርጎ የነበረው የፖለቲካ ዲፕሎማሲ ግንኙነት ኢትዮጵያ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሉዓላዊና ህልውና ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ በሌሎች ሀገሮች መልካም ፈቃድ ያውም 1 ሚሊዮን አካባቢ ህዝብ ባላት ጅቡቲ ላይ ሳይቀር ጥገኛ እንዲሆን ተደርጓል። ይህም ሀገሪቱንም ህዝቡን ከፍተኛ ዋጋ አስከፍሏል። ችግሮቹ ተጠንተው፥ ተለይተውና መፍትሄ ተበጅቶላቸው እርምት ካልተወሰደ ችግሮቹ ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይችል ይሆናል። ምክንያቱም የኢትዮጵያ ህዝብ እጅግ በሚያስገርም አሀዝ እየጨመረ ሲሆን፤ የገበያ ፍላጎቱም የዛን ያህል ይጨምራል። ለዚህም ተመጣጣኝ አቅርቦት የሚያስፈልግ ሲሆን፤ ከሀገር ውስጥ ምርት በተጨማሪ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በፍጥነት ለማዳረስና የሀገር ውስጥ ምርትን በነፃነት በውጭ ላሉ ተጠቃሚዎች ለማድረስ መሰረተ ልማት ቁልፍ ድርሻ አለው። በተለይ ነፃ የባህር በር። ምክንያቱም ነፃ የባህር በር ከአንዲት ሀገር ያውም ከባህር 60 ኪሎ ሜትር ቤቻ የምትርቅ ወደብ አልባ ሆና የምትቀጥል ሀገር ከሉዓላዊነቷ በተጨማሪ ኢኮኖሚው ላይ ትልቅ ፈተና ይጋርዳል። ለምሳሌ ፈጣን የንግድ እንቅስቃሴ፥ ፍትሃዊ የንግድ ቁጥጥር ስርዓትና ተጠቃሚነት፥ የሸማቹ ደህንነት እና የአቅርቦት ተጠያቂነትና ግልፅነት ላይ ትልቅ ጫና አለው። ይሄ የተለያዩ አዋጭና ዘላቂ አማራጮችን አይቶ መፍትሄ ካልተወሰደ አሁን ያለው ግን ደግሞ ትኩረት ያልተሰጠው ችግር ከህዝብ ቁጥርና ፍላጎት ጋር እየተባባሰ የሚሄድ በመሆኑ ለቀጠናው ሰላምና መረጋጋት የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በጥሞና ማሰብ አለባቸው።

ስለሆነም ኢትዮጵያ የራሷን ብሔራዊና ታሪካዊ መብትና ጥቅሟን እስካላስጠበቀች ድረስ አሁን ያለው ሰላም መልካም ቢሆንም ዘላቂ የመሆን ዕድሉ ግን አጠራጣሪ ነው። ለዚህም ዋነኛ ምክንያት ያለህዝብ ፍላጎትና ፈቃድ ታሪካዊ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ እጅግ አንገብጋቢና ፈታኝ ሲሆን፤ በዶ/ር አብይ አስተዳደር ወደ ፊት ምን እንደታሰበ እስካሁን ግልፅ የሆነ ነገር ባለመኖሩ፤ ነገስ የሚል ጥያቄን ያጭራል። ሌላው መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ ቢኖር በሀገራቱ መካከል ያለውን ሰላም ወደ ዘላቂ ደረጃ የማሸጋገር ዕድሉ በመሪዎች መልካም ፈቃድ ብቻ የሚወሰን ሳይሆን በእያንዳንዱ ሀገር ብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎትም ጭምር በመሆኑ አሁን ያለውን ሰላም ምሉዕ አያደርገውም።

በርግጥ የአብይ አንድ ጥሩ ጅምር አለ። እሱም ቀጠናውን በኢኮኖሚና በመሰረተ ልማት ማስተሳሰር። ይህ ለጋራ ተጠቃሚነት እጅግ በጣም ጥሩ ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም የነበረውን የርስ በርስ ጥርጣሬ አጥፍቶ ያለውን ሰላም ወደተሻለ ምዕራፍ ሊያሸጋግረው ይችላል። ከዚህ በተጨማሪ በኢኮኖሚው መስክ ሁሉም የቀጠናው ሀገራት በሌሎች ሀገሮች መልካም ፈቃድ ልግስና እና ብድር ጥገኛ በመሆናቸው በቅድሚያ ለፖለቲካው ነፃነት የኢኮኖሚ ደረጃዎቻቸውን በፈጣን ሁኔታ ማሻሻልና መቀየር አለባቸው።

አንዲት ሉዓላዊ ሀገር በርካታ ብድሮችንም ይሁን ርዳታዎችን ከአንድ የተወሰኑ ሀገራት ወይም ተቋማት ወይም የፖለቲካ አጋር ላይ ጥገኛ ከመሆን መላቀቅና አማራጮችን መጠቀም በራስ አስቦ ለመወስን ጉልበት ይሆናል። አለበለዚያ ኢኮኖሚው፥ የሀገር ውስጥ በጀት እና ትብብሩ በሶስተኛው ወገን ላይ ጥገኛ በሆነበት ሁኔታ በራስ ፈቃድ ብቻ ሰላምን አስፍኖ ዘላቂ ማድረግ እጅግ አስቸጋሪና ፈታኝ ነው። ይሄ ለኢትዮጵያም ሆነ ለቀሪዎቹ የቀጠናው ሀገራት ይሰራል። ምክንያቱም ብቻህን ደሴት ሆነህ እስካልኖርክ ድረስ፥ የኢኮኖሚ ነፃነት እስካላረጋገጥክ ድረስ የቱንም ያህል ቅን እና መልካም ሆነህ የፖለቲካ ነፃነት ለማረጋገጥ ብትሞከር ጊዜያዊ ካልሆነ በቀር ከጎረቤት ሀገሮች የሚኖረውን ግንኙነት በሌላ ሶስተኛ ወገን መፈተኑ የማይቀር ነው።

ኢትዮጵያ ያላትን ታሪካዊ ዳራ፥ የህዝብ ብዛት፥ የገበያ ፍላጎትና የፖለቲካ ሚናዋን ታሳቢ በማድረግ ቀጠናዋን በተለያየ አቅጣጫ መመልከትና መመርመር ይጠበቅባታል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይም አንዱና ዋነኛ የአስተዳደራቸው ፈተና ሊሆን የሚችለውም በቀጠናው ያለው የገዥዎች ስግብግብነት እና አምባገነንነት በተጨማሪ የሶስተኛ ወገን ጥቅምና ፍላጎት በቀጠናው ፖለቲካና ማኀበራዊ መስተጋብር ያለውን ሚና መለይት፥ መፍትሄውንም በብዙ አቅጣጫ መቃኘት፤ ለሚወስዷቸው ርምጃዎችም ጥንቃቄ በማድረግ ነገ ሊያስከትል የሚችለውንም ነገር ታሳቢ ማድረግ አለባቸው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ወደ ሥልጣን ከመጡ ጊዜ ጀምሮ በሀገር ውስጥ እየወሰዷቸው ካሉ በጎ ርምጃዎችና ማሻሻያዎች በተጨማሪ በቀጠናው ላይ የወሰዱት ፈጣን ርምጃ ይበል የሚያሰኝ ነው። የሚመሩትን ሀገርና ህዝብ እንዲሁም ታሪክ በሚመጥን መልኩ የወሰዷቸው ርምጃዎች ጥሩዎች ናቸው። ነገር ግን ከኤርትራ የተደረጉ ስምምነቶች ምንም እንኳ በግልፅ የታወቁ ነገሮች ባይኖሩም በኢኮኖሚውና በፀጥታ መስክ ያለውን ግንኙነት ከወዲሁ ፈር ማስያዝ ይጠበቅባቸዋል። ለምሳሌ በሁለቱ ሀገራት መካከል ለሁለት አስርት ዓመታት የነበረው ውጥረት ከረገበ በኋላ ከርስ በርስ ማኅበራዊ ግንኙነት በተጨማሪ በቅርቡ የርስ በርስ ንግድ ልውውጥ ተጀምሯል። በጎ ጅምር ነው። ነገር ግን በሁላቱ ሀገራት መካከል ያለው የገንዘብ አጠቃቀምና የምንዛሪ ተመን በግልፅ መታወቅና መነገር አለበት።

የወደብ አገልግሎትን በሚመለከት ከጅቡቲ ጋር እንደነበረው ፤ ለዜጎች ኑሮና የውጭ ምርት አቅርቦት ዋጋ መናር አንዱ ምክንያት እንደሆነው ልክ እንደ ጅቡቲ ወደብ ኪራይ ነው ወይስ በጋራ ማልማት አሊያም በሰጥቶ መቀበል መርህ ኢትዮጵያን ከዛሬ 27 ዓመታት በፊት እንደነበረው ሀገሪቱን የባህር በር ባለቤት ባደረገ መልኩ? በኪራይ ከሆነስ ለምን ያህል ጊዜ በምን ያህል ዋጋ? የወደብ መሰረተ ልማትና አገልግሎት ዘረፍ አጠቃቀም ጉዳይስ በምን ዓይነት ስምምነት ተካቷል? በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የመሰረተ ልማት ግንባታ በተለይም መደበኛ የየብስ መንገድ፥ የባቡር ትራንስፖርትና ሀዲድ ግንባታ፥ መብራት፥ ሎጅስቲክ፥ የፀጥታ ጉዳይ (በተለይ ወታደራዊ እንቅስቃሴ፥ የባህርና የአየር ኃይል) ለኢትዮጵያ የንግድ እንቅስቃሴና ለአካባቢው የፀጥታ ደህንነት አጠባበቅ ጉዳይ፥ ሌላ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ አካል የወደብ አገልግሎት አልሚና ተጠቃሚ ቢመጣ የኢትዮጵያ የሚኖራት ሚና እና የምትስተናገድበት አግባብ ፥… የመሳሰሉ ጉዳዮች በግልፅ ስምምነት ላይ ተደርሶ ለተጠቃሚው ህዝብ ይፋ መደረግ አለበት።

በሁለት ተራ ግለሰቦች አለመግባባት ወይም የጥቅም ሽኩቻ ግጭት ሀገራቱን ሊያቃቅር እንዳይችል መደረግ ያለባቸው ጥንቃቄዎች ከወዲሁ መታየት አለባቸው። የሚደረጉ ስምምነቶች ምንም እንኳ ዶ/ር አብይ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎትን ለሌላ አካል አሳልፎ በመስጠት ይደራደራሉ ተብሎ ባይታሰብም በፖለቲካ በተለይ በዲፕሎማሲው የአንድ መሪ ወይም ግለሰብ ቅንነት ብቻውን ሰላምን ማስፈን ጉልበት ቢኖረውም በሀገራት መካከል ቅንነትና በየዋህነት የሚደረጉ ስምምነቶች ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው ያመዝናል። ምክንያቱም በፖለቲካም ይሁን በተፈጥሮ አስገዳጅ ሁኔታ የመሪዎች መለዋወጥ አሊያም ከነፍስ ወከፍ ገቢ ጋር ያልተመጣጠነ የህዝብ ብዛትና ፍላጎት ባልተጠበቀ ጊዜ ሁነቶችን የመለወጥ ባህርይ ስላላቸው ቢቻል የሚፈፀሙ ስምምነቶች ዘላቂ ሰላም የሚያስገኙ ቢሆኑ መልካም፤ የውል ስምምነቶች ግን ከአስር ዓመት ባይዘሉ ይመከራል። ምክንያቱም በሁለት ሀገሮች መካከል የሚደረጉ ስምምነቶች ዓለም አቀፍ ሰነድ ሆነው የሚቆዩ በመሆናቸው፥የአካባቢና የሀገር ውስጥ ፖለቲካና ነባራዊ ሁኔታ ሲቀያየር አማራጭ እይታዎች ሊለያዩ ስለሚችሉ አሳሪ መሆን የለባቸውም።

ሌላው ኢህአዴግ ለመቀበል ከወሰነውና አቶ መለስና ስዩም መስፍን በስልጣን ላይ በነበሩበት ጊዜ ፈርመው ካረጋገጡት የአልጀርስ ስምምነት ተፈፃሚ ከማድረግ በስተቀር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይም ሆነ በአስተዳደራቸው ስር ያሉ አካላት የቀድሞ ስምምነቶችና ውሎች ካሉ ተገቢው ምክክር፥ ምርመራና ጥንቃቄ ሳይደረግበት ማፅደቅም ሆነ መስማማት የለባቸውም። ይህ ለሁለቱ ሀገራት ብቻ ሳይሆን ለቀጠናው ሰላምም የራሱ ድርሻ ይኖረዋል።

ከቀጠናው አዋሳኝ አረብ ሀገራት ጋር እየታዩ ያሉ ጥሩ የሚመስሉ መግባባቶች ይበረታታሉ። ይሁን እንጂ ከሌሎች ሀገሮች በተለየ መልኩ ከአረብ ሀገራት ጋር የሚደረግ ወዳጅነትና አጋርነት በጥንቃቄ መታየት አለበት። ምክንያቱም ሁሉም ነዳጅ አምራጅ የቀጠናው አረብ ሀገራት በኢኢኮኖሚ ነፃ ቢመስሉም በፖለቲካውና በፀጥታ ጉዳይ ሌላ ሁለተኛ ወገን ላይ ጥገና የሆኑ ስለሆነ ከእነሱ ፍላጎት ውጭም ሊሆን በሚችል መልኩ በየጊዜው ያልተጠበቁ ተለዋዋጭ ባህርዮች ይታያሉ።

በተለይ የአረብ ሀገራት ዴሞኬርሲ አልባ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን የሀገራቸው ኢኮኖሚም በገዥዎችና ቤተሰቦቻቸው እጅ የተከማቸ፥ የፀጥታ ጉዳዮቻቸውም ምንም እንኳ ጠንካራ ቢሆንም ከብሔራዊ ይልቅ በገዥዎች ፍላጎትና ተክለ ቁመና ላይ የተገነባ በመሆኑ እነሱ ያለ እንቅስቃሴ የአፍሪካ ቀንድ ጋር ቀጥተኛ ትስስር ይኖረዋል። ምክንያቱም በባህል እንዲሁም በተለያዩ ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ የአፍሪካ ቀንድ ሀገሮች ከአረብ ሀገራት ጋር የሚጋሩት ነገር ስላለ እዛ የሚፈጠረው ችግር ከራሳቸው አልፎ የአጋር ሀገሮችንም ሰላም የማናጋት አቅም አለው። ለምሳሌ አሜሪካ 66 % የኃይል አቅርቦት በተለይም ነዳጅ፥ የተፈጥሮ ጋዝና የድንጋይ ከሰል የአሪካ ቀንድ አጎራባች የሆኑ የአረብ ሀገራት ላይ ጥገኛ ስትሆን፤ እነሱም ዋነኛ የውጭ ምንዛሪ፥ የምግብ አቅርቦት ንግድ፥ የጦር መሳሪያ ፥ መሰረተ ልማት ቴክኖሎጂ አገልግሎትና አቅርቦት በዋነኝነት አሜሪካና ሸሪኮቿ ላይ ጥገኞች ናቸው። ርስ በርስ ያላቸው ወዳጅነትም ቢሆን አንዱ ያኩረፈ ቀን ቀጠናውን ማመስ የተለመደ ተግባራቸው ነው። ለምሳሌ የአሁኗን የመንን እንዲሁም ከኳታር ጋር ያላቸውን ግንኙነት ማየት ይቻላል። ስለዚህ አንዱ አጋር ጋር የአደጋ ወይም ችግር ዝናብ ቢያካፋ በኢኮኖሚ የደከሙ ሌሎች ሶስተኛ አጋር ሀገሮችን የሚገጥማቸው የችግር ካፊያ ሳይሆን ጎርፍ ነው። ስለዚህ ከበጎ ርምጃው ጎን ለጎን ጥንቃቄዎችም በደንብ መታየት አለባቸው።

በአጠቃላይ ኢትዮጵያ የምታደርጋቸው ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎችና ርምጃዎች በቀጠናው ላይ ትልቅ ተፅኖ አለው። ሰላሟና ደህንነቷ ከራሷ በተጨማሪ ቀጠናው ላይ የሚኖራት ሚና ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም። ስለሆነም የቀጠናውን ህዝብ ብዛት 59 በመቶ ያህል የያዘች ሀገር መሪ የሆኑት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይና አስተዳደራቸው እየወሰዱት ያሉት ርምጃና ስምምነቶች ቀጠናውንም ታሳቢ ያደረገ መሆን ይኖርበታል። እየወሰዷቸው ካሉ በጎ ርምጃዎች በተጨማሪ በቀጠናውም ሆነ በሌላው ዓለም አቀፍ የፖለቲካው መድረክ ኢትዮጵያ የነበራትን ተሰሚነትና ቦታ እንድትይዝ የሀገር ውስጥ የፖለቲካ መረጋጋት፥ የህግ የበላይነትና የፀጥታ ጉዳይ ሳይዘነጋ ማለት ነው።

በተለይ በአንድ ሀገር ሁለት መንግሥት አሉ ብለው የሚፎክሩትን፥ የመንጋ ፍርድ ሰጪና ትጥቃቸውን አንግበው ሰላማዊ ዜጎች መሃል እየተንቀሳቀሱ የሚያውኩ “ተፎካካሪ” የፖለቲካ ኃይሎች ከወዲሁ በቃችሁ ተብለው እንዲታረሙ መደረግ አለበት። በአንድ ሀገር ሁለት እና ከዚያ በላይ ማዕከላዊ መንግሥት የጦር ሰራዊት የለም ሊኖርም አይችልም። ትንንሽ ተብለው በቸልታ አሊያም በየዋህነት የሚታለፉ ነገሮች በሌላው ወገን እንደ ጅልነትና አላዋቂነት ተቆጥሮ ለሀገርም ለህዝብም ጥቁር ጠባሳ የሚጥል አደጋ እንዳያስከትል ለቀጠናው ሰላም ኢትዮጵያ ቤቷን ማፅዳት ግድ ይላታል። በመጨረሿም ለማንኛውም የሀገር ውስጥ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴም የጦር መሳሪያና የሁለተኛ አካል ወይም ሀገር የፋይናንስ ድጋፍ፥ ዝውውርና ጣልቃ ገብነት ከእንግዲህ እንዳይኖር የፀጥታው ዘርፍ ከመንደር ባለፈ ሀገሪቷንና ቀጠናውን በበቂ ሁኔታ የተረዳ ፥ በቴክኖሎጂ የታገዘና ከነበረው ኋላቀር የገዥዎችን ፍላጎትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ መዋቅር በአዲስ መልክ ተደራጅቶ ብሔራዊ መልክ የያዘ የፀጥታ ኃይል መገንባትና ማሰማራትም ቅድሚያ ሊሰጡ ከሚገቡ አብይ ጉዳዮች አንዱ ተደርጎ ቢወሰድ ለሚታሰበው ሰላም ጉልህ አስተዋፅዖ ይኖረዋል።

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: