መፍቀሬ ኢትዮጵያ ወገባሬ ሠናይ: የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ዐረፉ
•ሥርዓተ ቀብራቸው በአሰላ ደብር ቅዱስ ደብረ መዓዛ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ተፈጽሟል
•በታኅሣሥ 1966 ዓ.ም. በንጉሠ ነገሥቱ ትእዛዝ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቻንስለር ኾነው ተሹመው ነበር
•ከአምስተኛው ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ዕረፍት በኋላ ለስድስት ወራት በዐቃቤ መንበርነት አገልግለዋል
* * *
•“በሔዱበት ኹሉ ኢትዮጵያውያን ሃይማኖታቸውን ይጠብቃሉ፡፡ የሚኖሩት ግን ተዋርደው ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት እያሳፈረን ነው፡፡ በእውነት አባትህን ጠይቅ ይነግርሃል፤ ነው፡፡ አፍሪካውያን በሙሉ በቅኝ ግዛት ሲገዙ ኢትዮጵያውያን ለቅኝ ገዥዎች እጃቸውን ያልሰጡት በምን ምክንያት ነው ብለው የዛሬ ክርስቲያኖች በሙሉ ማጥናት አለባቸው፡፡” /ብፁዕ አቡነ ናትናኤል/
* * *

ነገ ቤተ ክርስቲያን ይከፍታልብሎ ያሳደገኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ የአቅሜን ያኽል ተምሬአለኹ፤ ቤተ ክርስቲያን አሳድጋኛለች፤ ባለውለታዬ ነች፤ ውለታዋን አኹንም አልከፈልኩም፤ እስከሞት ቢኾን ውለታዋን ተሸክሜ ወደ መቃብር ከመግባት በስተቀር ውለታዋን አልከፈልኩም፤ ይኼን የምናገረው ከልቤ ነው፤ ኹሉም ውለታ አለበት፤ የቤተ ክርስቲያኑን ውለታ መመለስ አለበት(ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፤ ፲፱፻፳፫ – ፳፻፰ ዓ.ም)
“ነቢዩ ኤርሚያስ፥ ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያዊነቱን አይለቅም፤ ይላል፤ ይህ ሊጠና ይገባል፡፡ እንባችንን እግዚአብሔር እስኪያብስልን ድረስ እኛ አባቶች ስንጸልይ የምናለቅሰው፥ ለነገዪቱ ኢትዮጵያና ለነገው ትውልድ ነው፤ በተለይ አኹን ያለው ትውልድ ያሳዝነኛል፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ እርስ በርሱ መለያየት ምን እንዳስከተለ ተረድቶት ይኾን? ከዚኽ ትውልድ መማር አለበት፡፡ እኛስ ይህን ዓለም እንሰናበተዋለን፤ ጥፋት እንዳይፈጸም፤ ኢትዮጵያ የኢትዮጵያዊነቷን ደርዟን እንዳታጣ በእውነት እያለቀስኩ ነው፡፡” – ለሀገርና ለትውልድ በብዙ ከሚጨነቅ ልባዊ ስሜት የመነጨው የዚኽ ረቂቅና ጥልቅ ንግግር ባለቤት፥ ከሦስት ዐሥርት ዓመታት በላይ የአርሲ ሀገረ ስብከትን በተመሰገነ አባታዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት የመሩት ብፁዕ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ናትናኤል ናቸው፡፡
ብፁዕነታቸው፥“ኢትዮጵያውያን ኹልጊዜ ኢትዮጵያዊ መኾን አለብን፤ የኢትዮጵያን ጠባይ ይዘን መጓዝ አለብን፤” እንዳሉት፣ በሥጋዊ ዝምድና ሳያምኑ፤ “ውለታዋ አለብኝ” ያሏትን ሀገርና ቤተ ክርስቲያን ንቃት በተመላበት ኹለገብነትና በብቃት ለማገልገል እንደጣሩ ተጋድሏቸውን ፈጽመዋል – ብፁዕነታቸው ትላንት፣ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡30 ገደማ ከዚኽ ዓለም ድካም ዐርፈዋል፡፡
በአሰላ መኖርያ ቤታቸው በቅርብ በሚረዷቸው ወዳጆቻቸው እንደተከበቡ በሰላመ እግዚአብሔር ያረፉት ብፁዕነታቸው፣ ከኩላሊትና ስኳር ሕመም ጋር በተያያዘ ሕክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተዋል፤ ከሕመማቸው አገግመው በመልካም ጤንነት ላይ እንደነበሩ የተነገረ ሲኾን፣ ከዕረፍታቸው ሦስትና አራት ቀናት በፊት ምግብ መወሰድ አቁመው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
በፊት ስማቸው ሊቀ ሥልጣናት አባ መዓዛ ቅዱሳን ገብረ ሕይወት የሚባሉት ብፁዕነታቸው፣ በሦስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም. ከተሾሙት 13 ኤጴስ ቆጶሳት አንዱ ሲኾኑ ምድብ ሀገረ ስብከታቸውም በቀድሞው አጠራር ትግራይ ክፍለ ሀገር ነበር፡፡ ብፁዕነታቸው፣ ከዐሥር ዓመት በፊት ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ አብርሃም ቤት ዓምድ በሰጡት ቃለ ምልልስ፥“በመንግሥት ሥራ የባህል ሚኒስቴር(በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር መርሐ ልሳን በሚባለው የቋንቋዎች ጥናት ክፍል) ሲቪል ሰርቫንት ኾኜ እየሠራኹ በመናኙ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘመን ለጵጵስና ታጨኹ፡፡ እኔ ጵጵስና ለመሾም ፍላጎቱ አልነበረኝም፡፡ ያኔ የነበረኝ ዓላማ በመጽሐፍ መምህርነቴ ጉባኤ አስፍቼ እንዳስተምር ነበር የምፈልገው፡፡ ምንኵስናን ተቀብዬ እንኳ ለጵጵስና ጉጉቱም ፍላጎቱም አልነበረኝም፤” ብለዋል፤ ለመምህርነት ሞያ ከፍተኛ ፍቅር እንደነበራቸው ሲያስረዱ፡፡
“አንድ ዕድል አገኘኹና ቅድስት ሥላሴ መምህራን ማሠልጠኛ ገባኹ፤” ያሉት ብፁዕነታቸው፣ በማሠልጠኛው ሳሉ፣ በአባ ሐና ጅማ አቅራቢነትና በቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ፈቃድ በተፈሪ መኰንን ት/ቤት የግብረ ገብ መምህር ኾነው ተቀጥረዋል፡፡ በመምህርነት የመጡ “ኢየሱሳውያን ሚሲዮናውያን” በት/ቤቱ ሥር ሰደው ከጠንካራ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ጋር ግጭት በመፍጠራቸው የተቀጠሩት ብፁዕነታቸው፣ ከ1949 እስከ 1954 ዓ.ም. ድረስ አስተምረዋል፡፡ በምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም አንጋፋውን የተምሮ ማስተማር ሰንበት ት/ቤት ከመሠረቱት አባቶች አንዱ ለመኾን የበቁትም በዚኹ ሥራቸው ላይ ሳሉ ነው፡፡ በወቅቱ ለምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳምም ቋሚ ሰባኬ ወንጌልም ነበሩ፡፡
“የዚያን ጊዜ ገና አልመነኰስኩም፤ ልጅ ነበርኩ፤ ሐዲሳቱንም በቃሌ ስለማውቅ እንደ ብርቅ ድንቅ ኾኜ ነበር የምቆጠረው፤ እውነትም መዓዛ ይሉኝ ነበር፤ መዓዛ የሚለው ስም የወጣልኝ ቅኔ ቤት እያለኹ ነው፡፡ እናቴ ያወጣችልኝ ስም ካሳዬ ነው፡፡ የዚያን ጊዜ ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት የዛሬው ስድስት ኪሎ ዩኒቨርስቲ ነበር፤ የአልጋ ወራሹም ግቢ እዚያው ምስካየ ኅዙናን አጠገብ፣ የልዑል መኰንን ቤትም በአቅራቢያው ነበር፤ ደጀ ጠኚውም በአጠቃላይ የሚመጣው ምስካየ ኅዙናን ነበር፤ ብዙ ሕዝብ ስለሚመጣ ለስብከቱም የተመቸ ነበር::”
አንደበተ ርቱዕና ጥልቅ አሳቢው ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ቤተ ክርስቲያናችን በብሥራተ ወንጌል ሬዲዮ ጣቢያ በነበራት ፕሮግራም ያስተምሩ ነበር፤ በሕይወት ዘመናቸው ካከናወኗቸው ተግባራት ለምእመናን በሬዲዮ ስብከተ ወንጌልን በማስተላለፍ የሰጡት አገልግሎት ከፍተኛ ደስታ እንደፈጠረላቸው ይናገራሉ – “ቤተ ክርስቲያናችን በሬዲዮው ለ12 ሰዓት ትምህርት ትሰጥ ነበር፡፡ እኔ በሳምንት አንድ ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እና ማኅበራዊ ኑሮ በቤተ ክርስቲያን በሚል የማስተላልፈው ዝግጅት ነበረኝ፤ ሬዲዮ ጣቢያውን ደርግ እስከወረሰው ድረስ የሰጠኹት አገልግሎት በሕይወቴ የተደሰትኩበት ነው፡፡”
ዛሬ በየአድባራቱ የተስፋፉት ዘመናዊ ት/ቤቶች ትልም፣ በብፁዕነታቸው ሐሳብ አመንጪነት የተቋቋመው የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ት/ቤት ነው፡፡ ሐሳቡን እንዴት እንዳመጡት ሲናገሩ፣ “በወቅቱ በውጭ ሀገር የሚሰጠውን የትምህርት ዘዴና ዘመናዊ ት/ቤትን ከቤተ ክርስቲያን አቅራቢያ የማቋቋም ብልሃት ቀስሜ ስለመጣኹ የምስካየ ኅዙናን ት/ቤት እንዲቋቋም ሐሳብ አቅርቤ የተምሮ ማስተማር እና የመድኃኔዓለም ጽዋ ማኅበርተኞች እንዲገናኙ አደረግኹ፤” ብለዋል፡፡

በአብነት ትምህርቱ፣ በትውልድ አጥቢያቸው ምሥራቅ ትግራይ ክለተ አውላሎ አውራጃ አውዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር አለቃ መብራህቱ ካስተማሯቸው ፊደል ጀምሮ፤ ወደ ጎንደር/በጌምድር/ ተሻግረው፣ በወሎ/ላስታም እየተዘዋወሩ ድጓውን ጾመ ድጓውን፤ ቅኔውን ከነአገባቡ ልቅም አድርገው ከተለያዩ መምህራን ቀጽለው፣ ወደ አዲስ አበባም ዘልቀው በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም በሐዲስ ኪዳንና በፍትሐ ነገሥት መምህርነት ተመርቀዋል፡፡ ማዕርገ ክህነት የተቀበሉበት ኹኔታም ከትምህርት ዝግጅታቸው ጋር የተጣጣመ ነበር፡፡
“ክህነት የተቀበልኩት ምዕራፍና ጾመ ድጓ ኹለት ጊዜ ዘልቄ፣ ቅኔ ዘይእዜ ከቆጠርኩ በኋላ ነው፤” የሚሉት ብፁዕነታቸው፣ ዲቁና የተቀበሉት በ1938 ዓ.ም. ከብፁዕ አቡነ ይሥሓቅ ሲኾን እርሱም ከጎንደር አዲስ አበባ ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ድረስ በእግራቸው በመምጣት እንደነበር ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም፤ “ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ በጾመ ፍልሰታ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ይዘውኝ ሔደው ውዳሴ ማርያም እና ቅዳሴ ማርያም እየተረጎምኩ እዚያው ከርሜ ቅስና፣ ምንኵስና፣ ቁምስና በ1954 ዓ.ም. ከቅዱስነታቸው ተቀብያለኹ፤” ሲሉ ክህነቱን በተገቢው የትምህርት ዝግጅት መቀበላቸውን ገልጸዋል፡፡
እንደዚኹም ኹሉ በዘመናዊው ትምህርት ዐሥረኛ ክፍል ሲደርሱ፣ በንጉሡ ጥያቄና በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ አስፈጻሚነት ወደ ኢየሩሳሌም አንግሊካን ሴንት ጆርጅ ኮሌጅ ከሌሎች ወንድሞቻቸው ጋር ተልከው ለኹለት ዓመት ተኩል የቤተ ክርስቲያን ታሪክና አስተዳደር ተምረው ዲፕሎማ ይዘው ተመልሰዋል፡፡ ዲፕሎማቸውን ለትምህርት ሚኒስቴር አቅርበውና አስገምግመው ዕውቅና እንዲሰጣቸውና ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነትም እንዲተላለፍ በማድረጋቸው፣ “ለቤተ ክርስቲያኗ ትምህርት ዋጋ እንዲሰጠው በር ከፍቼ ነበር” ይላሉ፤ ብፁዕነታቸው፡፡
ከዚኽ በኋላ ብፁዕነታቸው፣ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በካህናት አስተዳደር ምክትል አስተዳዳሪ ኾነው በ1958 ዓ.ም. ቢሾሙም ወደ ምስካየ ኅዙናን ገዳምም በበጎ ፈቃድ እየተመላለሱ ማስተማራቸውን አላቋረጡም ነበር፤ ይህም ከብሥራተ ወንጌል ሬዲዮ ጣቢያ የስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸው ጋር ተደማምሮ በ1961 ዓ.ም. በትምህርት ሚኒስቴር በኩል ወደ እንግሊዝ ኦክስፎርድ ኦስሄትሮፕ ኮሌጅ ለከፍተኛ ትምህርት ተልከዋል፡፡ ትምህርታቸውን ለአራት ዓመታት ተከታትለው በ/Bachelor of Divinity Basic Philosophy Super mental and Developmental Psychology/ የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝተው ተመልሰዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ በብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ አቅራቢነት በንጉሠ ነገሥቱ ትእዛዝ በታኅሣሥ 1966 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቻንስለር ኾነው እንዲያገለግሉ በወቅቱ የጽሕፈት ሚኒስቴር ተሹመው የነበረ ቢኾንም ከተማሪው እንቅስቃሴና ከአብዮቱ ለውጥ ጋር ተያይዞ “ርእዮተ ዓለሙ አይፈቅድም” በመባሉ ወደ ቤተ ክህነቱ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡
ቀደም ሲል የነበሩት የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት ለውጡን ተከትሎ በመታሰራቸው በቦታቸው የተተኩት ብፁዕነታቸው፣ የሐዋርያዊ ድርጅት ሓላፊና የሰበታ ቤተ ደናግል የበላይ ሓላፊ እንዲኾኑ በጽሕፈት ሚኒስቴር ቢሾሙም የለውጡ ማዕበል በሥራቸው ለመቀጠል አስቸጋሪ አድርጎባቸዋል – በስብከታቸው፣ “ደርግ አረማዊ ነው ብሏል” በሚል ተከሠው ጉዳያቸው እስከ ጦር ፍ/ቤት ደርሶ ለአንድ ዓመት ከሥራ ውጭ መደረጋቸውን ያስታውሳሉ፤ “በእኔ ላይ በሐሰት የሚመሠክር በመጥፋቱ ተለቀቅኹ፤ እኔ ያስተማርኩት ለሰላም እንጸልይ እያልኩ ነበር፤ ልታሰር የሚገባኝ በሥራ ፈትነቴ እንጂ በትምህርቴ አልነበረም፤” የሚሉት ብፁዕነታቸው፣ በሐዋርያዊ ተልእኮ መፈተን አይቀሬ መኾኑንና ይህም ከሐዋርያት በረከት እንደሚያሳትፍ ይመክራሉ፡፡
ሰው ችግር አይገጥመውም አይባልም፤ ፈተናም አይጠፋም፡፡ ጠንካራ ማርክሲስቶች ነበሩ፡፡ እነርሱም ቤተ ክርስቲያንን ለመጣል ይታገሉ ነበር፡፡ እኛ ደግሞ ቤተ ክርስቲያን እንዳትወድቅ፤ ሕዝቡም ሃይማኖቱም እንዲጠበቅ ትግል ውስጥ ነበርን፡፡ ይህ ደግሞ ለእኔ ሐዋርያዊ ግዴታዬ ስለነበር እንደ ችግር አላየውም፤ ምክንያቱም ቅዱሳን ሐዋርያት ከደረሰባቸው ጽዋ መካፈል ስለነበረብኝ ነው፡፡
ለቤተ ክርስቲያን የፖሊቲካ ጫወታ እንደማይጠቅማት አሠልሰው የሚናገሩት ብፁዕነታቸው፣ በየጊዜው በመንበሩ የሚቀመጡ አባቶችን ለመቃወም ሲባል በሀገር ውስጥም ኾነ በውጭ ቤተ ክርስቲያኒቱን ከፖሊቲካ ጋር ኾኖ የመታገል መንፈስ መቀየር እንዳለበት ያሳስባሉ፡- “አቡነ ቴዎፍሎስ በነበሩበት ወቅት በግል ቅራኔ የነበራቸው ሰዎች እርሳቸውን እንጎዳለን ብለው ቤተ ክርስቲያኗን ይቃወሙ ነበር፡፡ አቡነ መርቆሬዎስም በነበሩበት ወቅት እንዲኹ ይታገሏቸው ነበር፡፡ እንደዚኹ ኹሉ ሕዝቡ በአባቶች ላይ ቅሬታ ኖሮት አባቶችን ሲቃወም በአንድ ላይ አብራ የምትመታው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ስለዚኽ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህን መንፈስ መቀየር አለበት፡፡”
ከአባታቸው ከአቶ ገብረ ሕይወት ፀዓዱ ከእናታቸው ከወ/ሮ ወለተ ክርስቶስ ቢሻው በ1923 ዓ.ም. የተወለዱት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ከትውልድ አገራቸው ለትምህርት የወጡት ገና የ13 ዓመት ብላቴና ሳሉ ነበር፡፡ “ኢትዮጵያዊነቴን እንጂ ስለ ትግራይ ብዙ የማውቀው ነገር የለም፤ የትግራይ ጓደኛ አልነበረኝም፤” ያሉት ብፁዕነታቸው፣ የትምህርት ቤት ሕይወታቸውም ይህንኑ ሀገራዊ ስሜት እንዳጠናከረላቸው ይመሰክራሉ፡- “የትምህርት ቤት ሕይወት ምናኔ ነው፤ የመጣነው ተማሪዎች የተማሪ ቤት ጓደኝነት እንጂ የእርስ በርስ የሥጋ ዝምድና የለንም፤ ኹለቱ ጓደኞቼ ቤጌምድሮች ናቸው፤ አንዱ የላስታ ላሊበላ ልጅ ነው፤ እኔ የተወለድኩት ትግራይ ነው፤ ኹላችንም ከተለያየ ቦታ ብንመጣም እንደ አንድ እናትና አባት ልጆች፣ እንደ ወንድማማቾች ነው የምንተያየው፤ እርስ በርሳችን ልዩ ፍቅር ነበረን፡፡ እንደ ጊዜው ኹኔታ ምግባችንን ሰብስበን አንድ ላይ እንቆርሳለን፤ በአንድነት እንማራለን፡፡ በበሽታ እናስታምማለን፤ ሲድኑ ወደሚያገግሙበት ቦታ እንወስዳለን፤ ሲሞቱ እንቀብራለን፡፡”
ብፁዕነታቸው ዐቃቤ መንበር በነበሩበት ወቅት ከግብጹ ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ጋር ይታያሉ
ብፁዕነታቸው፣ ኤጲስ ቆጶስነት በተሾሙበት በትግራይ ሀገረ ስብከት ለስድስት ዓመታት በሰጡት ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ መተዳደርያ ይዞታቸውን ተነጥቀው ለነበሩት ጥንታውያን ገዳማት ትኩረት በመስጠት በችግር እንዳይፈቱ ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ርዳታ እየተቀበሉ ሥራ ጀምረው ነበር፡፡ “ሶሻሊስት ነን ብላችኋል፤ ማኅበራዊ ኑሮ ያለው በገዳማት ነው፡፡ ገበሬው በነዚያ ቢታቀፍ ይጠቀማልና የገዳማቱን መሬት አትውሰዱባቸው፡፡ ለአካባቢው የልማት ኣርኣያ ይኾናሉ፡፡ እያንዳንዱን ገዳም እንደ አንድ ገበሬ ማኅበር ቁጠሩት፡፡ መሬቱ ለካህናቱ፣ ለመነኰሳቱ ይኹን፤ ሕዝቡን ገንዘብ እንዳይጠይቁት፡፡ ለዘለቄታው ራሳቸውን የሚችሉበት የልማት ሥራ ያስፈልጋቸዋል፤” ብለው ከኮሚሽኑ ስለተቀበሉት ርዳታ አፈጻጸም ከትግራይ ግብርና ቢሮ ጋር ተፈራርመው ሥራ ቢጀምሩም በክፍለ ሀገሩ እየገፋ በነበረው የእርስ በርስ ጦርነት ዕቅዶቻቸውን ሳይተግብሩ ቀርተዋል፡፡
“ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን ካለኝ ቀናዒነት የተነሣ የማይኾን ነገር ሳይ እናገራለኹ፤ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ኾኖ ዕድሜዬን ለማራዘም ወደ አርሲ ሀገረ ስብከት አመጣኝ፤” ይላሉ፤ በ1975 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ ወደ አርሲ ተዛወረው ስለመመደባቸው ሲናገሩ፡፡ ምደባቸውን በአኰቴት ቢቀበሉትም ችግሩ ግን በሌላ ገጽታው በአርሲም ቆይቷቸው ነበር፤ እንዲኽ ያስረዱታል፡-
“ያኔ ከትግራይ ወደ አርሲ የመጣኹት በእውነት እግዚአብሔር ባወቀ ነው እንጂ በጥናት አልነበረም፤ መመደቤንም በአኰቴት ተቀብዬዋለኹ እንጂ በጣም ችግር ነበር፤ ምክንያቱም ገና የደርግ መዋቅር የሚዘረጋበት ወቅት ነበር፤ የወዛደር ዓለም፤ የአብዮት ምሥረታ የሚባሉ በርካታ እንቅስቃሴዎች የተጀመሩት ባሌ እና አርሲ ላይ ይመስል ነበር፤ እንደ ቀልድ ፕሮፓጋንዳ፥ ሌኒን የተወለደው ጭላሎ ተራራ ላይ ነው፤ ይባል ነበር፡፡ የመንግሥት ሠራተኞች በአየዳራሹ ይሰበሰቡ ነበር፤ በርእሰ ከተማው አሰላ በነበረ የኅብረት አዳራሽ ለአንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ እንኳ እንድንሰበሰብ አይፈቀድም ነበር፡፡ በወቅቱ የሰንበት ት/ቤት አባላት ይገረፉ ነበር፤ በዚያን ወቅት ወጣቶች ከፍተኛ ችግር ነበረባቸው፤ ወጣቶቹ እንዳይገረፉ ሰበካ ጉባኤም እንዲቋቋም ከፍተኛ ትግል እናደርግ ነበር፤ የዘመኑ ሰዎች ግን ወጣቱንም እኔንም ያስሩን ነበር፤ እስር ቤት አልገባኹም እንጂ በቁም እስር እስከ ግማሽ ቀን እንዳልንቀሳቀስ ተደርጌአለኹ፡፡ መታወቂያኽ የቀበሌ አይደለም፤ የቤተ ክህነት ነው እያሉ ብዙ እንግልት ደርሶብኛል፡፡
ለዚኽ ዘዴው ጉባኤ ማድረግ ነበር፡፡ ጉባኤ ለማካሔድ ገንዘብ ከልማት ኮሚሽን አገኘን፡፡ የመምሪያ ሓላፊዎችን ሰብስበን አዳራሽ ከማዘጋጃ ቤት ተከራይተን በ1976 ዓ.ም. ጉባኤ አደረግን፡፡ ጉባኤ ማድረጋችን በመላው ሀገሪቱ ተሰማና ሃይማኖት ተፈቀደ፤ ተባለ፡፡ በእግዚአብሔር አጋዥነትም በርካታ አብያተ ክርስቲያናትን ከምእመናን ጋር በመተባበር ለማሳነፅ ችለናል፡፡ አርሲ ተመድቤ ስመጣ የነበሩት 215 አብያተ ክርስቲያናት ብቻ ነበሩ፤ አኹን ግን(ቃለ ምልልሱ በተካሔደበት በ1998ዓ.ም.) 436 አብያተ ክርስቲያናት እንዲታነፁ አድርጌአለኹ፤ እኔ ከመጣኹ ከ200 በላይ አዲስ አብያተ ክርስቲያናት ታንፀዋል ማለት ነው፡፡”
ብፁዕነታቸው፣ ከሀገረ ስብከቱ አሰላ ከተማ 60 ኪ.ሜ ርቆ በሚገኘው የዝዋይ ሐይቅ ደሴቶች ላይ በታሪክ የሚዘከር ሥራ ሠርተዋል፡፡ በቀደሙት ብፁዓን አባቶች ተጀምሮ ፍጻሜ ያላገኘውን የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በ1978 ዓ.ም. ተጀምሮ በ1986 ዓ.ም. ሥራው ተጠናቆ በቅዱስ ፓትርያርኩ አቡነ ጳውሎስ ተመርቋል፤ የተገነባበትን ድንጋይ፣ ከቦታው 68 ኪ.ሜ ርቀት ቁሉልታ ከሚባል ቦታ በማመላለስ እንደተሠራ ብፁዕነታቸው ጠቅሰዋል፤ የአብርሃምንና የአርባእቱ እንስሳ አብያተ ክርስቲያናትንም በበጎ አድራጊ አካላትና ምእመናን ድጋፍ አሠርተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ በአሰላ ምእመናን ዘንድ በልዩ ኹኔታ የሚታወሱት፣ ከከተማው ወጣ ብሎ የመንግሥት ሹማምንት ቤተ መንግሥት የነበረውን ቦታ ተከራክረው በማስመለስ የቤተ ክርስቲያን ይዞታና ንብረት እንዲኾን ማድረጋቸው ነው፡፡ ቦታውንም፣ ደብር ቅዱስ ደብረ መዓዛ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም እና የሕፃናት ማሳደጊያ ብለው ሰይመው ወላጆቻቸው የሞቱባቸውን ልጆች ሰብስበው አስተምረውበታል፤ መነኰሳትንም በአባታዊ ጥሪ ሰብስበው ማደርያ አሠርተው ሥርዓተ ገዳምን አስፈጽመውበታል፡፡
ቦታውን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ድጋፍ ከተረከብኩ በኋላ በወቅቱ በነበረው የሃይማኖት ቅራኔ መልሰው ወስደውት ነበር፤ የክፍለ ሀገሩ ኢሠፓ ተጠሪ ስለሺ መንገሻ ወደ ትግራይ ተቀይሮ ሲሔድ አስተዳደሩ እንደገና ተረከብ አለኝ፡፡ በእጅጉ አደከመኝ፡፡ ቦታው ዘረፋ ሲፈጸምበት ስለቆየ ከጥቅም ውጭ ኾኗል፡፡ ባለቤት አጥቶ ደኑ ይወድማል በማለት መንፈሴ ይታወክ ነበር፡፡ ዳግመኛ ከተረከብኩ በኋላ፣ ቤቱን በምን እሠራዋለኹ እያልኩ እጨነቅ ነበር፡፡
ተፈሪ መኰንን ት/ቤት ያስተማርኩት ልጄ የቢትወደድ ዘውዴ ገብረ ሕይወት ልጅ ዶ/ር ዳዊት ዘውዴ ቀይ መስቀል ሓላፊ ኾኖ ይሠራ ስለነበር እርሱን ጠይቄ መንገዱ ጥገና ተደረገለት፡፡ ከዚያ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን ጠርቼ ቦታውን እንዲጎበኙ አደረግኹ፡፡ ቅዱስነታቸው ብር 390‚000 ርዳታ ሰጥተውኝ ቦታውን በአዲስ መልክ አሠርቻለኹ፡፡ በውስጡ 120 የሙት ልጆችን አሳድጌበታለኹ፡፡ እኒኽ ልጆች አብዛኛዎቹ ኢንጅነሮች፣ ሜዲካል ዶክተሮች ኾነዋል፡፡ ታላላቅ ባለሞያዎች አድገውበታል፤ አኹንም እያደጉበት ይገኛሉ፡፡
ቦታው የቤተ ክርስቲያን ኾኖ እንዲቀጥል ዘወትር መንፈሴ ይጨነቃል፡፡ ስለዚኽ በጭላሎ ተራራ ሥር የሚኖሩ ሰዎች ከከተማው ርቀው በበሽታ ስለሚሠቃዩ ከአውሮፓ ኅብረት ርዳታ ጠይቄ በጤና ጥበቃ ደረጃ ለልጆቹም ኾነ በገዳሙ ለሚያድጉት ለአካባቢው ኅብረተሰብ የሚያገለግል ጤና ጣቢያ/ክሊኒክ አቋቁሜ ከ25‚000 በላይ ለኾነ ነዋሪ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ በርግጥ ክሊኒኩ የመድኃኒት እጥረት አለበት፡፡ ለማሟላት መድኃኒት አምራች ድርጅቶችን እየለመንኩ ነው፡፡
የቦታው የደን ሀብት እና የዱር እንስሳት እንዳይጠፉ ከአውሮፓ ኅብረት ባገኘኹት ርዳታ ዙሪያውን በሽቦ አሳጥሬ የጥበቃ ሠራተኛ ተቀጥሯል፡፡ የጎኑ ስፋት 16 ሜትር የኾነ የዛፎች አባት አለ፡፡ የዛፎቹ ዕድገትና ደኑ ጥብቅ ኾኖ እንዲዘልቅ እንዲኹም የዱር እንስሳቱ ክብካቤ እንደ ጥንቱ አስተማማኝ የሚኾነው ቤተ ክርስቲያን ጠባቂ ስትኾን ነው፡፡ ባለሞያዎች፣ በርሓማነት የተስፋፋው ደኖቻችን ስለተመነጠሩ ነው፤ ይላሉ፡፡ ስለዚኽ የደን ባለአደራ ቤተ ክርስቲያን ስለኾነች ደብር ቅዱስ ደብረ መዓዛ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳምን የተከልኩበት ምክንያቱ፣ ደኑ ሳይመነጠር ቦታው ጠፍ ሳይኾን እንዲዘልቅ በማሰብ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሰጧትን አደራ ጠባቂ ስለኾነች ከእኔ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ትረከባዋለች ብዬ እየደከምኩ ነው፡፡
ብፁዕነታቸው፣ ወላጆቻቸውን በሞት ተነጥቀው አሳዳጊ አልባ ለኾኑ ሕፃናት የመመገቢያና የማደርያ ሕንፃ ካስገነቡ በኋላ በመንፈሳዊ ሕይወት ተኮትኩተው እንዲያድጉ የጻድቁን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አሳንፀዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ቅጽር ለዐሥራ ኹለት መናኞች የሚኾን ቤትም አሠርተዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያኑ መንቀሳቀሳሻ ከራሳቸው ብር 50 ሺሕ እና ከበጎ አድራጊ ምእመን ተውጣጥቶም እየተገለገለ ነው፡፡ “ዘይመጽእ እም ድኅሬየ ያጸንዕ እምኔዬ” እንደተባለ፣ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ሰው ድካሜን አይቶ ከዚኽም አስፍቶ እንደሚሠራው እምነት አለኝ፤ ይላሉ ብፁዕነታቸው፡፡
በበቆጂ የደብረ ቁስቋም የሴቶች አንድነት ገዳምን የመሠረቱት ብፁዕነታቸው፣ የሴት መነኰሳዪያት ት/ቤት ለመክፈት በዝግጅት ላይ እንዳሉም በቃለ ምልልሱ ወቅት ጠቁመው ነበር፡፡ “ት/ቤቱን ልከፍት ያሰብኩት ቀድሞ በሰበታ ቤተ ደናግል የቦርድ አባልና የገዳሙ ሓላፊ ኾኜ በመሥራቴ ብዙ ልምድ ስላገኘኹ ነው፤” ሲሉ መነሻቸውን አውስተዋል፡፡ በበቆጂ ከሚገኙ እናቶች መካከል ወደ ሰበታ ቤተ ደናግል እየተላኩ ሠልጥነዋል፡፡
ከከተማው ወጣ ብሎ እንደ ሸንኮራ ዮሐንስ ያለ የመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ የጠበል ቦታ ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን በተገኘ 48 ሺሕ ያኽል ብር በጥሩ ኹኔታ አሠርተዋል፡፡ ለምእመናኑንም የመጠጥ ውኃ፣ ለከብቶቻቸው ገንዳና ሌሎችም የልማት ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡ የኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያንም አሳንፀዋል፡፡ ሁሩታ ላይ ለፋብሪካ የሚኾን ቦታ ተገዝቶ ከደብር ቅዱስ የሚወጡ አዳጊዎች በሠርቶ ማሳያ እንዲሠማሩበት ለማድረግ ያላቸውንም ዕቅድ በወቅቱ ገልጸው ነበር፡፡
በሀገረ ስብከቱ ኮፈሌ ወረዳ ልዩ ስሙ አንሻ በሚባል ቦታ፣ ኢአማንያን ለምእመኑ ብቸኛ የኾነችውን የቅድስት ማርያምን ቤተ ክርስቲያን ባቃጠሉበት ወቅት ብፁዕነታቸው ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ ምእመኑን አጽናንተዋል፤ ጥቃት አድራሾቹ በሕግ ቁጥጥር ሥር እንዲውሉ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱም በሕዝቡ ትብብር ዳግመኛ እንድትታነፅ አድርገዋል፡፡
የውስጥ ችግሮችን በሰላም በመፍታት የውጭ ተግዳሮትን ለመመከት፣ በተለይ ኦርቶዶክሳዊው ወጣት መለያየትን አቁሞና ልብ ገዝቶ አንድነቱንና ትብብሩን ማጥበቅ እንደሚኖርበት ብፁዕነታቸው ያሳስባሉ፤ “በእውነት፥ ጸሎት፣ ምሕላ፣ ትምህርት የሚያስፈልገው ነው፤” ያሉትን ጥልቅና ረቂቅ ምክራቸውንም እንደሚከተለው አስተላልፈው ነበር፡-
እርስ በርሷ የተለያየች መንግሥት ትፈርሳለች፤ አትጸናም፡፡ እርስ በእርሷ የተለያየች አገር ትፈርሳለች፤ አትጸናም፡፡ “የሰይጣን መንግሥቱ ተለያየ፤” ሲል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሯል፡፡ እንኳን አንድ አገር ሕዝብና መንግሥት ቀርቶ የሰይጣን መንግሥት እንደሚፈርስ መረዳት ይቻላል፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ጎሳ የለውም፤ ሴሜቲክ፣ ነገደ ካም እና ነገደ ኩሽ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ግዛቷ እስከ ሱዳን ነበር፡፡ ሲናር፣ ከሰላ፣ መቋድሽ(መቅደሶ ማርያም)፣ ማዳጋስካር ደሴት፣ ሕንድ ውቅያኖስ ጠረፏ ወሰኗ፤ ቀይ ባሕር ወሰኗ እንደነበር ይታወቃል፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ እርስ በርሱ መለያየትና መከፋፈል ምን እንዳስከተለ ተረድቶት ይኾን? ከዚኽ ትውልዱ መማር አለበት፡፡ እኛስ እናዝናለን፤ ይህን ዓለም እንሰናበተዋለን፤ ነገር ግን ጥፋት እንዳይፈጸም፣ ኢትዮጵያ የኢትዮጵያዊነት ደርዟን እንዳታጣ በእውነት እያለቀስኩ ነው፡፡ ያለነው ጥቂት አባቶች ለማስተማር ብንወተረተርም ትውልዱ አይረዳም፤ ከወላጆቹ መማር የሚገባው ወጣት እንደ አባቶቹና እናቶቹ አይደለም፡፡ ወደ አውሮፓ፣ ወደ አሜሪካ፣ ወደ ዓረብ አገር ብንሔድ ኢትዮጵያዊ የሚኖረው አምሮበት አይደለም፡፡ ተዋርዶ፣ ተሳቅቆ፣ ሮጦ ነው ያለው፡፡ በሔዱበት ኹሉ ኢትዮጵያውያን ሃይማኖታቸውን ይጠብቃሉ፡፡ የሚኖሩት ግን ተዋርደው ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት እያሳፈረን ነው፡፡
በእውነት አባትኽን ጠይቅ፣ ይነግርሃል ነው፡፡ አፍሪካውያን በሙሉ በቅኝ ሲገዙ ኢትዮጵያውያን ለቅኝ ገዥዎች እጃቸውን ያልሰጡት በምን ምክንያት ነው? ብለው የዛሬ ክርስቲያኖች ማጥናት አለባቸው፡፡ ጣልያን ቢመጣ የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድ ኾኖ ዐድዋ ላይ ድል ሲቀዳጅ የተደሰቱት ኢትዮጵያውያንና አፍሪካውያን ብቻ ሳይኾኑ የጥቁር ሕዝብ በሙሉ ተደስቷል፡፡ ለካስ ነጭ በጥቁር ይሸነፋል፤ ብለው ነፃነታቸውን ለመጠየቅ የተነሡት ከዐድዋ ድል በኋላ ከኢትዮጵያውያን አንፀባራቂ ድል ተነሥተው ነው፡፡ ወጣቱ የአባቶቹ ወኔ ሊኖረው ይገባል፡፡
ኢትዮጵያዊነት ምን ማለት ነው? ወይን ወይንነቱ ጠማማነቱ ነው፡፡ ወይን በቀጥታ ለሞፈርና ለቀንበር አይኾንም፡፡ ወይን ደግነቱ ፍሬው ነው፤ ዕንጨቱ ግን ጠማማ ነው፡፡ ነብር ተፈጥሮው ግራጫ፣ ዝንጉርጉር ነው፤ ኢትዮጵያዊ ደግሞ ጀግና ነው፡፡ ነቢዩ ኤርሚያስ፣ ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያዊነቱን አይለቅም፤ ይላል፡፡ ይህ ሊጠና ይገባል፡፡
እንባችንን እግዚአብሔር እስኪያብስልን ድረስ እኛ አባቶች ስንጸልይ የምናለቅሰው ለነገዪቱ ኢትዮጵያና ለነገው ትውልድ ነው፡፡ በተለይ አኹን ያለው ኹኔታ በጣም ያሳዝነኛል፡፡
ብፁዕነታቸው በመጨረሻም፤ ከ33 ዓመታት በፊት ከትግራይ ሀገረ ስብከት ወደ አርሲ ሀገረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ ሲዛወሩ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ያሏቸውን ለትውስታ በመጥቀስ ምክራቸውንና መልእክታቸውን ያጠቃልላሉ፡-
ከትግራይ ወደ አርሲ የተዛወርኩ ጊዜ፣ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፥ አባታችን አልኋቸው፤ ከእግዚአብሔር አግኝተው አድርገውት ከኾነ እግዚአብሔርም እኔም ደስ ይለናል፡፡ ደስ የሚያሰኝ ሥራ ሠርቼ አስደስትዎታለኹ፡፡ ከሰው አግኝተውት ከኾነ እኔና እግዚአብሔር ደስ ይለናል፡፡ የአቅሜን ያኽል ደስ የሚያሰኝ ሥራ እሠራለኹ፤ ብያቸው ነበር፡፡ የአቅሜን ያኽል ተምሬአለኹ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሳድጋኛለች፡፡ ባለውለታዬ ነች፡፡ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ግን ውለታ አልከፈልኩም፡፡
ተማሪ ሳለኹ በእንተ ስማ ለማርያም፣ ስለ ቸሩ እግዚአብሔር እያልኩ ስማር አቅመ ደካማ፣ አካል ጉዳተኛ ኾኜ አይደለም፡፡ ነገ ቤተ ክርስቲያን ይከፍታል ብሎ ያሳደገኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፡፡ ከቆሎ ት/ቤት ጎጆ ቤት ወጥቼ አዳሪ ት/ቤት ገብቼ ከዚያም ብዙ የትምህርት ዕድል ያገኘኹት፤ ከአንድም ኹለት ጊዜ ወደ ውጭ ልካ ያስተማረችኝ ለእኔ ሳይኾን ለቤተ ክርስቲያን ውለታ ነው፡፡
ኹሉም ውለታ አለበት፤ የቤተ ክርስቲያኑን ውለታ መመለስ አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ውለታ አኹን አልከፈልኋትም፤ እስከ ሞት ቢኾን ውለታዋን ተሸክሜ ወደ መቃብር ከመግባት በስተቀር ውለታ አልከፈልኩም፡፡ ይህን የምናገረው ከልቤ ነው፡፡
እያንዳንዳችን ውለታችንን ለአገር፣ ለቤተ ክርስቲያን መክፈል አለብን፡፡ ኢትዮጵያውያን ኹልጊዜ ኢትዮጵያዊ መኾን አለብን፡፡ የኢትዮጵያንን ጠባይ ይዘን መጓዝ አለብን፡፡ በ1977 ዓ.ም. በረኀብ በተቀጣን ጊዜ ስሙን የማላስታውሰው የምዕራቡ ዓለም መሪ፣ ያ ኩሩ ሕዝብ፤ አገሩንና ሃይማኖቱን ያላስደፈረ ሕዝብ ነው፤ ያለው ቃል ከኅሊናዬ ዘወትር አይጠፋም፡፡ ከዚኽ ውጪ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅማት የፖሊቲካ ጫወታ አይደለም፡፡
* * *
ብፁዕነታቸው፣ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ እንዳሏቸው፣ ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ ተዛውረው በተመደቡበት አርሲ ሀገረ ስብከት ከሦስት ዐሥርት ዓመታት በላይ በብዙ የደከሙበትን ሐዋርያዊ አገልግሎት እግዚአብሔርንም ሰውንም ደስ በሚያሰኝ አኳኋን ፈጽመው በተወለዱ በ85 ዓመት ዕድሜአቸው ዐርፈዋል፤ ሥርዓተ ቀብራቸውም፤ አሳድገው ለቁምነገር ባበቁአቸው ልጆች የቀጣዩን ትውልድ ተስፋና የጥረታቸውን ፍሬ ባዩበት በደብር ቅዱስ ደብረ መዓዛ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም፣ ሐሙስ፣ የካቲት 24 ቀን ብፁዓን አባቶች፣ ማኅበረ ካህናትና ማኅበረ ምእመናን በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡
የብፁዕ አባታችን በረከታቸው ይድረሰን፡፡ አሜን፡፡
ምንጭ፡- ሐራ ዘተዋሕዶ፣ https://haratewahido.wordpress.com/2016/03/01
ሰበር ዜና ፡- ፈቃድ የሌላቸው የኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራሞች በቤተ ክርስቲያን ስም እንዳይጠቀሙ ተወሰነ፤ የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት ይጀመራል
• የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ እና ዕውቅና የሌላቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል
• በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ መሠረት፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
የብዙኃን መገናኛ ቦርድ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው
• በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ላይ የቀረቡ ማስረጃዎች የበለጠ ተጠናክረው አጀንዳው በልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ተወስኗል

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ከማእከል የተሰጠ ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም፣ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ(EBS) የቴሌቭዥን ጣቢያ፣ “ሃይማኖታዊ ትምህርት” የሚያስተላልፉ ፕሮግራሞች፣ የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ ወሰነ፡፡
ምልአተ ጉባኤው በዛሬ፣ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ስድስተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው ያሳለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲኾን፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቭዥን በደብዳቤ እንዲያውቁት ይደረግ ዘንድ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
በውሳኔው÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በስም የተጠቀሱ ሲኾን በፕሮግራሞቹ አዘጋጅነት የሚታወቁት በተለይ የ“ታዖሎጎስ” ግንባር ቀደም ምንደኞች፣ ፕሮግራማቸው“ራሱን የቻለ የሚዲያ ተቋም” እንጂ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ይኹን ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በይፋ በሰጡት መግለጫ ማረጋገጣቸው ይታወሳል፡፡
ምልአተ ጉባኤው ከዚኹ ጋር በማያያዝ፤ በሊቃውንት ጉባኤ ሳይመረመሩ እና በማእከል ሳይፈቀዱ በግለሰቦች እየተዘጋጁ የቤተ ክርስቲያንን ስም ይዘው ስለሚወጡ የስብከት፣ የመዝሙር እና የመጻሕፍት ኅትመቶች እንዲኹም የአዳራሽ ጉባኤያት እና ስብሰባዎች ከተወያየ በኋላ ቀደም ሲል ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች በማጽናት ተመሳሳይ ትእዛዝ መስጠቱ ታውቋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ስብከተ ወንጌል እና ሚዲያን በተመለከተ” በተራ ቁጥር ሦስት በያዘው አጀንዳ፤ ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊነቱን ጠብቆ የራስዋን ድምፅ ለዓለም የምታሰማበት እና ስብከተ ወንጌልን የምታስፋፋበት የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት እንዲጀመርም ወስኗል፡፡
ለቤተ ክርስቲያንየቴሌቭዥን አገልግሎት ስርጭት የሚያስፈልገውና በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አስተባባሪነት የተጠናው በጀት ባለፈው ዓመት ግንቦት በምልአተ ጉባኤው የጸደቀ ሲኾን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር እንደተመለከተው፤ በዚኽ ዓመት በጀቱ በአፋጣኝ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበውን ጥያቄ በመቀበል የፋይናንስ ምንጮቹን ወስኖ ለነገ የሚያቀርብ ሦስት አባላት ያሉት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት(ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ) ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤ ተሠይሟል፡፡
ምልአተ ጉባኤው ባለፈው ዓመት ግንቦት ባጸደቀው የሚዲያዎች (የሬዲዮ እና የቴሌቭዥን አገልግሎት) ሥርጭት ደንብ መሠረት፤ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራ ዘጠኝ አባላት ያሉት የብዙኃን መገናኛ የሥራ አመራር ቦርድ የተቋቋመ ሲኾን ተግባሩን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ለ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ የቀረበው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ሪፖርት ያስረዳል፡፡
በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልን ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በአጽናፈ ዓለም ለማስፋፋት እና ለማጠናከር ስለሚያስፈልጓት ሚዲያዎች፣ በመምሪያው አስተባባሪነት በብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎች የተካሔደውን ጥናት መሠረት አድርጎ መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ/ማኑዋል ተዘጋጅቷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣“የቤተ ክርስቲያኗን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ማየት” በሚል ዐቢይ አጀንዳ ሥር በፊደል ተራ ቁጥር 4/መ፣ “የተሐድሶ እንቅስቃሴን በተመለከተ”፤ የተዘጋጀው ሰነድ በተጨማሪ ማስረጃዎች ተስፋፍቶ እና ተጠናክሮ ራሱን በቻለ ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል፡፡
የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፤ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ግንባር ቀደም መሪዎች በሚሰጣቸው ተልእኮ እና ድጋፍ በቤተ ክርስቲያናችን የአስተዳደር እና የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በመስረግ የኑፋቄውን አስተሳሰብ እና ድርጊት የሚያራምዱ የ66 አካላት እና ግለሰቦች የሰነድ፣ የምስል እና የድምፅ ማስረጃዎች ከኃምሳ ገጾች ማብራሪያ ጋር ተደግፎ ተዘጋጅቷል፡፡
ከቤተ ክርስቲያናችን ዐውደ ምሕረት እና የአስተዳደር መዋቅር ባሻገር፣ የኑፋቄው ግንባር ቀደም መሪዎች እና ምንደኞቻቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን(መንፈሳዊ ኮሌጆች እና የካህናት ማሠልጠኛዎች) ውስጥ በተለያየ ሽፋን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ከፍተኛ ትኩረት እንዲደረግበት ምልአተ ጉባኤው ኮሚቴውን አሳስቧል፡፡
በመካከለኛው ምሥራቅ አህጉረ ስብከት፣ ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ሳያውቁት ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በተቋቋመው የኑፋቄው መናኸርያ “ዱባይ ሚካኤል” እና “ቤርያ ቲኦሎጂካል ኢንስቲትዩት” በሚል መሪዎቹ የመሠረቱት ሕገ ወጥ ተቋም በከፍተኛ ደረጃ ያነጋገረ ሲኾን በምልአተ ጉባኤው ጥናት ተካቶ እንዲቀርብ መወሰኑ ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይ ኹኔታ ጉባኤውን ያነጋገረው፣ በመንበረ ፓትርያርኩ የውጭ ጉዳይ መምሪያ በሓላፊነት የተቀመጡት መልአከ ሰላም አባ ቃለ ጽድቅ የተባሉ ግለሰብ፣ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቁ አንጻር ያላቸው ሃይማኖታዊ አቋም እና ሥነ ምግባራዊ ኹኔታ ነበር፡፡ የግለሰቡ አመጣጥ እና አመዳደብም ከፓትርያርኩ ልዩ ጸሐፊ ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ጋር ባላቸው የጥቅም ግንኙነት እንደኾነ መጠቆሙ ደግሞ ችግሩ ከግለሰቡም በላይ ልዩ ጽ/ቤቱ እንደ መዋቅር ያለበትን አስከፊ ደረጃ እና አሳሳቢነቱን ለምልአተ ጉባኤው አለብቧል፡፡
ከዚኽ ውስብስብነቱና ከሚያስፈልገው ጠንካራ ቅንጅት አኳያ፤ አጀንዳው ራሱን በቻለ አስቸኳይ እና ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሲወስን ጊዜው በመጪው ወርኃ ጥር ላይ ሊኾን እንደሚችል ከወዲኹ የተጠቆመ ቢኾንም በኮሚቴው ውጤታማ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚመሠረት ነው፣ በብዙኃን የምልአተ ጉባኤው አባላት ዘንድ መግባባት የተደረሰበት፡፡
በሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት መሠረት፤ አስቸኳይ እና ድንገተኛ ጉዳይ ሲያጋጥም ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም ቋሚ ሲኖዶሱ ወይም የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ በሚያደርጉት ጥሪ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሊካሔድ ይችላል፤ ከዐራቱ እጅ ሦስቱ እጅ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት ስብሰባም ምልዓተ ጉባኤ ይኾናል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ በማናቸውም ስብሰባ ላይ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍም፣ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ከኾነ በሙሉ ድምፅ ያልፋል፤ በሃይማኖት እና በቀኖና ጉዳይም ድምፀ ተዓቅቦ ማድረግ አይቻልም፡፡
ምንጭ፡- ሐራ ዘተዋሕዶ
በእስር ላይ የሚገኙት መምህር ግርማ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄም ወድቅ ተደረገ
ጥላሁን ካሳ
ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት መምህር ግርማ ወንድሙ ዛሬ ጥቅምት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፖሊስ መርማሪ ቡድን ዛሬ ግለሰቡን በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት አቅርቧቸዋል።
ፖሊስ ግለሰቡ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ቀሪ የምርመራ ስራ ስላሉብኝ ተጨማሪ 14 ቀን ይፈቀድልኝ ብሏል።
ተጠርጣሪው በራሳቸውና በጠበቃቸው በኩል ፖሊስ የጠየቀውን ተጨማሪ ጊዜ በመቃወም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል።
የፖሊስ የምርመራ ቡድን በበኩሉ እሳቸው ቢለቀቁ ሌሎች ተፈላጊዎችን እና የተለያዩ ሰነዶችን ስለሚያሸሹብን ጥያቄያቸው ውድቅ ይሁን ብሏል።
ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ አብዛኛውን የምርመራ ስራ ያካሄደ በመሆኑ ለቀሪ የምርመራ ስራዎቹ ይረዳል በማለት ከጠየቀው የ14 ቀን ጊዜ ውስጥ 7 ቀን ብቻ ፈቅዷል።
ውጤቱን ለመጠባበቅም ለጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
የወንጀሉ ዝርዝር
ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ.ም ነው ብሏል።
በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው።
እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።
እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል።
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ800 ሺህ ብር ይሸጡታል።
ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው የሚለው የምርመራ መዝገቡ።
ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው።
ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።
የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው።
ተጠርጣሪው እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።
ጠበቃቸውም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል አይደለም፤ ፖሊስም የሚጠበቁ ምርመራዎቹን አጠናቋል፤ ደንበኛዬ የዋስትና መብታቸው ይከበርልኝ በማለት ጠይውቋል።
ይሁን እንጂ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጓል።
ምንጭ፡- ሬዲዮ ፋና (ኤፍቢሲ)
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች ሹመት ፓትርያርኩንና ረዳት ሊቀ ጳጳሱን እያወዛገበ ነው
- ረዳት ሊቀ ጳጳሱ የፓትርያርኩን ምደባዎች በደብዳቤ ተቃውመዋል
- ቋሚ ሲኖዶሱ የጠቅላይ ቤተክህነቱ ሥራ አስኪያጁ ያቀረቡትን አቤቱታ መመልከት ጀምሯል
ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አዲስ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ ስኪያጅ መሾማቸውን ተከትሎ ከሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እና ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ተቃውሞ እንደገጠማቸው ተገለጸ፡፡ኹለቱ ሥራ አስኪያጆች ለሀገረ ስብከቱ መመደባቸው የተገለጸው፣ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ ከፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በደብዳቤ በተሰጠ መመሪያ ነው፡፡የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት እንደኾነና ከረዳት ሊቀ ጳጳሱ ጀምሮ በሀገረ ስብከቱ የሚመደቡ ኃላፊዎችን የመምረጥና የመመደብ ጉዳይ ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋራ መያያዙን፣ በዚህም መሠረት ሲሠራ እንደቆየ በመመሪያው የተጠቀሰ ሲኾን፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ለኹለቱ ሥዩማን ሥራ አስኪያጆች ምደባቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ እንዲያደርሷቸውና ሥራቸውን እንዲጀምሩ ይደረግ ዘንድ ይጠይቃል፡፡ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ በአድራሻ የተጻፈው ይኸው ደብዳቤ፣ በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ለኾኑት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በግልባጭ እንዲያውቁት መደረጉ ተገልጧል፡፡
ረዳት ሊቀ ጳጳሱ የሥራ አስኪያጆቹ ሹመት ከሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቃለ ዐዋዲው እና ከሀገሪቱ የሕግ አሠራር ውጭ መኾኑን በመግለጽ ምደባውን በትላንትናው ዕለት ለፓትርያርኩ በጻፉት ደብዳቤ የተቃወሙ ሲኾን፣ ፓትርያርኩ ከሕግ አግባብ ውጭ የሰጡትን መመሪያ እንደገና እንዲያጤኑት መጠየቃቸውም ታውቋል፡፡ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ አስኪያጅ ተጠሪነታቸው ለረዳት ሊቀ ጳጳሱ እንጂ ለፓትርያርኩ ኾኖ እንደማያውቅና ሊኾንም እንደማይችል የገለጹት አቡነ ቀሌምንጦስ፣ የፓትርያርኩ አካሔድና የሥራ አስኪያጆች ምርጫ “የሕግ ድጋፍ የሌለው፣ ያልተለመደና የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅራዊ አሠራር በእጅጉ የሚፃረር ነው” ብለዋል፡፡ አቡነ ማትያስ የሰጡት መመሪያ ተቀባይነት የሚኖረውም ተሿሚዎቹ በሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ተመርጠው ከቀረቡ በኋላ ምርጫቸው ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ጋር የጋራ ስምምነት ተደርሶበት በፓትርያርኩ ሲሾሙ እንደኾነ በተቃውሟቸው አስረድተዋል፡፡ ፓትርያርኩ ከልዩ ጽ/ቤታቸው በሰጡት መመሪያና በሥራ አስኪያጆች ምርጫዎቻቸው እንደማይስማሙና ምደባውንም ለማስተናገድ እንደሚቸገሩ ያስታወቁት ረዳት ሊቀ ጳጳሱ፣ “ይህ አሠራር ከትዝብት ላይ የሚጥል መኾኑን ተረድተውልን ለቤተ ክርስቲያን ሰላማዊ አሠራርና ለኹላችንም ሰላም ሲባል ውሳኔዎን እንደገና እንዲያጤኑ በታላቅ አክብሮት አሳስባለኹ” ብለዋል – በተቃውሞ ደብዳቤአቸው፡፡
የፓትርያርኩን መመሪያ እንዲያስፈጽሙ በአቡነ ማትያስ መመሪያ የተሰጣቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቡነ ማቴዎስ በበኩላቸው፣ ትላንት ከቀትር በፊት በተደረገው የቋሚ ሲኖዶሱ ሳምንታዊ ስብሰባ መመሪያውን በመቃወም አስተያየታቸውን በቃል ማቅረባቸው ተጠቁሟል፡፡
ስብሰባውን በሊቀ መንበርነት የሚመሩት ፓትርያርኩም አጀንዳው ውሳኔአቸውን የሰጡበት በመኾኑ መታየት የለበትም በሚል ቢቃወሙም ቋሚ ሲኖዶሱ ዋና ሥራ አስኪያጁ ተቃውሟቸውን በጽሑፍ እንዲያቀርቡ ማዘዙ ተገልጧል፡፡ ከትላንት በስቲያ በድንገት ይፋ የኾነው የሀገረ ስብከቱ ተተኪ ሥራ አስኪያጆች ምደባ፥ ‹‹የመልካም አስተዳደር ሒደቱን ማቀላጠፍ›› በሚል ከኹሉ አቀፍ የትምህርት ዝግጅት፣ ከሥነ ምግባርና ከብሔር ተዋፅኦ መስፈርቶች አንጻር ፓትርያርኩንና ረዳት ሊቀ ጳጳሳቸውን ላለፉት ሦስት ወራት ሲያወዛግብ መክረሙን የዜናው ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ምንጭ፡- አዲስ አድማስ ጋዜጣ
የኢሬቻ በዓል በደብረ ዝቋላ እንደሚከበር የተላለፈው ዘገባ ማስተባበያ እንዲሰጥበት ተወሰነ
-
- ለአፈጻጸሙ የወረዳው እና የዞኑ አስተዳደር ባለሥልጣናት ሓላፊነት ወስደዋል
- ከመጋቢት ፭ ክብረ በዓል በፊት ማስተባበያው እንዲተላለፍ ከስምምነት ተደርሷል
- ከኹሉም አካላት የተውጣጣ የሽማግሌዎች ኮሚቴ የችግሩን ቆስቋሾች ያጣራል
- በክብረ በዓሉ ቀን የተጠናከረ ጥበቃ እንዲደረግ መመሪያ ተሰጥቷል
ደብረዘይት/ቢሾፍቱ አካባቢ በሚገኘውና ከ800 ዓመታት ዕድሜ በላይ ባስቆጠረውና በየዓመቱ መጋቢት 5 የሚከበረው ታሪካዊው ደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረመንፈስቅዱስ ገዳም የኢሬቻ በዓል ይከበራል በሚል በክልሉ ፕሬዘዳንት አቶ ሙክታር ከድር በተፃፈና በፀደቀ ደብዳቤ ማስታወቂያና ዜና ተላልፏል መባሉን ተከትሎ በአካባቢው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ኃይማኖት ተከታዮች፣ የሀገረ ስብከቱና የገዳሙ አስተዳዳሪ ለኦሮሚያ ክልል መስተዳደር፣ ለዞኑና ለወረዳው ለሚለከታቸው አካላት ቅሬታ አቅርበው ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ቤተክርስቲያኗን በመወከል ጉዳዩ በህዝቡ መካከል ሆን ብሎ ግጭት ለመቀስቀስና አለመግባባት ለመፍጠር የተደረገ በመሆኑ ቤተክርስቲያኗ ድርጊቱን እንደምትቃወም የሚገልፅ ቅሬታ ለክልሉ መስተዳደር መላካቸው ታውቋል፡፡
ማስታወቂያውና ዜናው እንዲተላለፍ የተደረገው በክልሉ አበገዳ ተወካዮች ስም ቢሆንም፤ አባገዳዎቹ እነሱ ይህንን ማስታወቂያም እንደማያውቁትና እንደማይመለከታቸው በመግለፅ በሁኔታው መገረማቸው ተጠቁሟል፡፡ ስለሆነም የኢሬቻ በዓል በደብረ ከዋክብት ዝቋላ ገዳም እንደሚከበር የተላለፈው ዘገባና ማስታወቂያ ማስተባበያ እንዲሰጥበት መወሰኑ ሰሞኑን ከክልሉ ባህልና ቱሪዝም የወጡ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ሐራ ዘተዋህዶ በአጭሩ የሚከተለውን አጠናቅሮታል፡፡
- “ለእኛ አዲስ ነገር ነው፤ እዚኽ ቦታ ኢሬቻ የለም፤ በአራት ወይም በስምንት ዓመት አንዴ ዝናም እምቢ እንዳይለን ገዳሙን አስፈቅደን ከምንፈጽመው ሥርዐት ውጭ በተነገረው መልኩ የሚከበር በዓል የለም፡፡ ያስተላለፉት መጠየቅ አለባቸው፡፡”–(የአባ ገዳ ተወካዮች)
- “ህብረተሰቡን ከእኛ ጋራ ሊያጣሉ የሚፈልጉ ግለሰብ አመራሮች አሉ፡፡… ለተላለፈው መልእክት ሓላፊነት የሚወስድ አካል ካልተገኘ፣ የመጋቢት ፭ ክብረ በዓል ከመድረሱ በፊት በስሕተት የተላለፈ መኾኑ ይገለጽልን፡፡”–(የገዳሙ አስተዳደር)
- “እናንተ ሰላም ፍጠሩ፤ [በክብረ በዓሉ] ከተለመደው ውጭ አንዳችም የሚደረግ አይኖርም፤ ጥበቃውም እንዲጠናከር ይደረጋል፤የተላለፈውን ዘገባ አጣርተን በኦሮምኛ እና በአማርኛ ማስተባበያ እንዲሰጥበት እናደርጋለን፡፡”–(የዞን የአስተዳደርና ፀጥታ ኃላፊዎች)


