Category Archives: Environment

የአባይ ወንዝ ናፍቆት እና የታላቁ ህዳሴ ግድብ

ካሊድ ኢብራሂም

አባይ ወንዝ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የተፈጥሮ ፀጋ ብቻ ሳይሆን፤ ዜማ፥ ቅኔያችን እና መኩሪያችንም ጭምር ነው። ለግብፅና ለሱዳን ደግሞ ከፈጣሪ በታች የሚያዩት ግን የማያናግራቸው ገዥ ነው። ወንዙ በዓለም ላይ ካሉ ረጅም ጉዞ መዳረሻ ካላቸው ታላላቅ ወንዞች አንዱ ሲሆን፤ በውሃ ሃብት የፖለቲካ ምልከታ ደግሞ ከሩቅ ምስራቁ ጎጀብ እና ከደቡብ አሜሪካው አማዞን ወንዝ ያልተናነሰ ገናና ታሪክ እና እደምታ ያለው ትልቅ ሃብት ነው። በሀገራችን በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በሱዳኖች እና በግብፆችም ለዘመናት የተዜመለት ነው። ይሁን እንጂ ሀገራችን እስካሁን ከወንዙ መጠቀም የቻለቸው ሊሰጥ ከሚችለው አገልግሎት ከ 1% አይበልጥም። ነገር ግን የሚቀርብለት አድናቆት፥ ቅኔ፥ ዜና፥ ስምና መወድስ ግን እንደ አዋሽ ካሉ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት እየሰጡ ካሉ ታማኝ ወንዞች እንኳ የላቀ ሥፍራ የተሰጠው ነው።

እንደ ታሪክ ድርሳናት መረጃ ከሆነ የዛሬዎቹም ሆኑ ጥንታውያን ግብፆች እና የቀድሞ ኑባውያን የስልጣንያቸው ምንጭ ተደርጎ ይወሰዳል። ኢትዮጵያውያን ነገስታት በተለይ ከ12ኛ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ወንዙን ለመጠቀም ፍላጎት ቢኖርም በታሰበው ልክ አገልግሎት ላይ ለማዋል የአቅም ችግር ዋነኛ ምክንያት ነው። ኢትዮጵያ የአባይ ወንዝ አመንጪና ባለቤት ስትሆን ፤ ግብፅ የእና ሱዳን ደግሞ ተጠቃሚ ሆነው ቆይተው ነበር። በተለይ የአባይ ወንዝ ብቻውን ዓመታዊ የአማክይ ፍሰት መጠን 54 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ሲሆን፤ ለናይል ወንዝ 62 % ድርሻ ወይም አበርክቶት አለው።

የተፈጥሮ ሀብትን በአግባቡ ለመጠቀም ፍላጎት በተግባር ካልተደገፈ ብቻውን ምንም ነው። ኢትዮጵያውያን የአባይን ወንዝ ለመጠቀም ፍላጎት ቢኖረንም ዛሬም ድረስ ያለን ተግባራዊ እንቅስቃሴ ግን እዚ ግባ የሚባል አይደለም። በርግጥ እስካሁን ካሉ የኢትዮጵያ መንግሥት መሪዎች የቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴን ያህል ለተግባራዊነቱ የተንቀሳቀሰ መሪ የለም። ወንዙን ለዜጎች ሁለንተናዊ ጥቅም ለማዋል ሳይንሳዊ ጥናት አስጠንተው ለተግባራዊነቱ ረጅም ርቀት የተጓዙትና በተወሰነ መልኩም ቢሆን ተግባር ላይ መዋል የጀመረው በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመን ነው። ለዚህም በአባይ ወንዝ አንዱ ገባር የሆነው የፍንጫ ግድብን ማንሳት ይቻላል።

GERD
ፎቶ፡ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ገፅታ (ጸጋዬ ሐጎስ 2017)

የነበረው የፊውዳል ሥርዓት በዚህ ዘመን በበጎ የማይወሳ ቢሆንም፤ ከስሙ በስተቀር የዛሬውን የአባይን ግድብ ጨምሮ በርካታ የኤሌክትሪክ፥ የመስኖ፥ የመንገድ መሰረተ ልማት እና የዘመናዊ ከተሞች ግንባታና አስተዳደር ጥናቶች የተሰሩት በቀዳማዊ እጼ ኃይለሥላሴ ዘመን ነበር። የአዲስ አበባው የቀለበት መንገድን ጨምሮ ማለት ነው። ተግባር የዋሉት ጥናቶችም እንደዛሬው ለርካሽ ፖለቲካ ፍጆታ ታስበው የሚሰሩ ርካሽና መናኛ ሳይሆኑ ትውልድ የቀጣይ ትውልድን ተጠቃሚነትንም ታሳቢ ያደረጉ ነበሩ። በዛ ኋላቀር ፊውዳላዊ አስተዳደር ውስጥ ትውልድ ተሻጋሪ ስራዎች ዛሬም ህያው ምስክር ናቸው። ከከተማ እቅዶች በደርግ ያልተተገበረውና በኢህአዴግ ለሌቦች የገቢ ምንጭነት ታስቦ ትውልድ እና ታሪክ ነቃይ ተደርጎ በኢህአዴግ የተበለሻሸው የአዲስ አበባ መሪ ፕላን፥ ከሞላ ጎደል ተግባራዊ የተደረጉት የባህርዳርና የአዋሳ ከተማን መሪ እቅድ ጥናትን መጥቅስ ይቻላል። ከመስኖ ግድቦች መካከል ለግማሽ ምዕተ ዓመት ያህል አገልግሎት እየሰጡ ያሉትን የወንጂ፥ መተሐራ እና ፊንጫ መስኖ ግድቦችን ጥናትና ተግባርንም መጥቀስ ይቻላል። ይህ ሲባል ግን የነበረው ሥርዓት በሁሉም ዘርፍ ፍፁም ምሉዕ ነው ማለት አይደለም። በአስተዳደር በኩል እጅግ ኋላቀር ቢሆንም፤ የተሰሩ ፕሮጀክቶችና ጥናቶች ግን ዛሬም ድረስ የምንኮራባቸውና ትውልድ ተሻጋሪ መሆናቸውን ለመጠቆም እንጂ። ምክንያቱም ዛሬ የሌቦች አገዛዝ መፈንጫ የሆነው እና የምንናፍቀው የዛሬው የህዳሴው ግድብም የዛ ዘመን ጥናት ውጤት ነው።

በአሜሪካውያኑ የዘርፉ ባለሙያዎች በ1956 ዓ. ም. .ከነበሩ የአባይ ወንዝ ልማት ጥናቶች መካከል አንዱ የሆነው የዛሬው የህዳሴ ግድብ የወቅቱን የተፈጥሮ ሁኔታ እና አቅምን ከግምት ሳያስገባ ወደተግባር የተገባ ይመስላል። በተለይ የነበውን የአረቡን ዓለም አብዮት ተከትሎ መጋቢት 2003 ዓ. ም. ወደ ስራ እንደተገባ ይፋ የተደረገው እና ብዙ ተስፋ የተጣለበት ይህ የአባይ (የህዳሴ) ግድብ ፕሮጀክት የሀገሪቱን ባለሙያዎችና የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ አልነበረም። ከዛ ይልቅ ከፕሮጀክቱ ተቋራጮች እስከ ግብዓት አቅራቢዎች በሙሉ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ በሥልጣን ላይ የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ የኔ ከሚሏቸው አካላት በስተቀር ሌላው ማኅበረሰብ ገንዘብ ከማዋጣት ባለፈ ሌላ ተሳትፎ የለውም። በብዙ መልኩ የፕሮጀክቱ ሂደት በኢኮኖሚ ደረጃ በቀጥታ የህወሓት አገዛዝ እና የኔ የሚሏቸውን የጥቅም ተጋሪዎቻቸውን ተጠቃሚ ማድረጉ ግልፅ ነው። ከአዋጭነት፥ ጥቅል አካባቢያዊ ተፅዕኖ ግምገማ ላይም ግልፅነት የጎደለው ነው። በመሆኑም ከተግባራዊ ሥራው ይልቅ የፖለቲካ ፍጆታ ጫጫታው በብዙ ዕጥፍ ይልቃል። ለዚህም ይመስላል። በ 5 ዓመት ተጠናቅ አገልግሎት ይሰጣል ሲባል የነበረውና በርካታ ፖለቲካዊ ፍጆታ ሲባል ብቻ ይገለፁ ከነበሩ ይህን ያህል % ተጠናቀቀ ከሚል የመረጃ ጋገራ ሰለባ መሆኑ እሙን ነው። ይሄ ሁሉ ወቅቱን ባገናዘበ መልኩ ትውልድ ተሻጋሪ አሳታፊ ጥናት ተደርጎበት የተጀመረ ፕሮጀክት አልነበረምና።

የህዳሴው ግድብ ሥራው ሲጀመር ለሀገራችን ኢትዮጵያ ያለው አዋጭነት እና አገልግሎቱን በሚመለከት በንጉሱ ዘመን ወቅቱን ታሳቢ ደርጎ የተጠናውን ጥናት ከብተመንግሥት ዶሴ መዞ ከመተግበር ባለፈ አሁን ያለውን የመልከዓምድር፥ አቅም እና ነባራዊ ሁኔታውን ታሳቢ ያደረገ ተጨማሪ ጥናት ሳይካሄድ ተግባራዊ መደረጉን የሚያሳብቁ ጥቂት ምሳሌዎችን ማንሳት ይቻላል። የግድቡ ፕሮጀክት ይፋ ሲደረግ ሥራው ሲጠናቀቅ ግድቡ 5,250 ሜጋ ዋት ያመነጫል ተባለ። ከሶስት ዓመታት በኋላ ፕሮጀክቱ ተሻሽሎ 6,000 ሜጋ ዋት ነው የሚያመነጨው በሚል አገዛዙ ብዙ ተደሰኮረ። በዚህ ሳያበቃ ለምን እና እንዴት እንደሆን ነጋ በሌለበት ሁኔታ ባለፈው 2010 ዓ.ም. ደግሞ ግድቡ ሲጠናቀቅ 6,540 ሜጋ ዋት ኤሌክትሪ ያመነጫል ተባለ። የጉድ ሀገር። ነግስ ሌላ ማሻሻያ አዲስ “ጥናት” ዕቅድ ይነገረን ይሆን? ከተቻለማ ግድቡ በስኬት ተጠናቆ ከዚህም በላይ ቢያመነጭ ደስተኞች ነን። መልካም ነገርን ማን ይጠላል? በተለይ 70 % ያህሉ የሀገራችን ዜጋ የኤሌኬትሪክ አገልግሎት ለማግኘት በሚናፍቅበት ሀገር የተባለው እውን ሆኖ በርካታ ወላጆቻችን በተለይ እናቶቻችን ከዱር እንጨት ለቀማና በጭስ ከመታፈን ቢገላግልልን ደስታውን አንችለውም ነበር። ነገር ግን ግድቡ በተባለው ጊዜ አልተጠናቀቀም። ኽረ እንደውም ሆድ ይፍጀው ተብሎ እንጂ ግድቡ የኤሌክትሪክ ግድብ እንኳ በቅጡ የማያውቁ፥ የፕሮጀክ ምንነትና አስተዳደር ከተራ ስርቆትና ዝርፊያ መለየት የተሳናቸው ሁሉ ያለከልካይ የሚናኙበት የ “ልማት‘” መርሃ ግብር ተደርጎ እንደነበር የቀድሞ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ኃላፊዎች ገመና ህያው ምስክር ነው።

ግድቡ ከፍተኛ የውሓ መጠንን በማከማቸት የሀገራችን ትልቁን እና ተፈጥሯዊውን ጣና ሐይቅ በሁለት እጥፍ የሚበልጥ ሰው ሰራሽ ሐይቅ እንደሚፈጥር ነው የተነገረው። ከአገልግሎቱ አኳያ ስናይ ኤሌክትሪ ማመንጨቱ ጥሩ ነው። ይበረታታል። ከዓሳ ምርትና መዝናኛ በስተቀር ሌላ ተጨማሪ አገልግሎት እንዳለው የሚያመለክት ጥናትም ሆነ መረጃ የለም። ግን ለምን? የፕሮጀክቱ አንዱ ክፍተት የተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት ያልተሳተፉበት ብቻ ሳይሆን ግድቡ አጠቃላይ አዋጭነቱ ላይ በርካታ የተሸፋፈኑ ነገሮች ይስተዋላል። ምናልባት ከብሔራዊ ጥቅምና ደህንነት አኳያ የተወሰኑ ነገሮች በአመራሮችና በፕሮጀክቱ መሪዎች ሊያዙ ይችል ይሆናል። ነገር ግን ከብሔራዊ ጥቅምና ደህንነት ውጭ ዜጎቼ ሊያውቁት የሚገባ ጉዳይ ዛሬም የሚነሳ አይመስልም።

ግድቡ ወደፊት በሀገራችን ላይ ተጨማሪ ወጪ እንዳያስከትል ከወዲሁ በቂ የሆነ የአካባቢ ጥበቃ ስራ አልተከናወነም። ለዚህም ማሳያ ግድቡ ከመጀመሩ በፊት ጀምሮ በጣና ሐይቅ ላይ በከፍተኛ ደረጃ እየተራባ ያለው ባዕድ የውሃ አረም “እንቦጭ” ከጣና ሐይቅ በተጨማሪ የህዳሴው ግድብ ላይ ዋነኛ ስጋት ሊሆን እንደሚችል የፔሮጀክቱ ባለቤት የኢትዮጵያ ኤልክትሪ ኃይልን ጨምሮ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ቦታ የሰጡት አይመስልም። ምክንያቱም ዋነኛው አባይ ወንዝ ምንጭ ከግሽ አባይ ተራራ ይነሳ እንጂ አቋርጦ የሚያልፈው ጣና ሐይቅን ነው። በዛ ላይ ጣና ሐይቅ ለአባይ ወን 10 % ውሃ ያበረክታል። እንቦጭ አረሙ ደግሞ በከፍተኛ ደረጃ ውሃ በመያዝ በተፈጥሮ ያለውን የውሃ ፍሰት መጠን ከመቀነስ በተጨማሪ የግድቡን ኤሌክትሮ ሜካኒካል ሥራ የማስተጓጎል አቅም አለው። የጣና በለስ ግድብም ላይም ተመሳሳይ አደጋ ነው የተጋረጠው። ይሁን እንጂ ከሚምመለከተው መንግሥትና የፕሮጀክቱ ባለቤት ይልቅ ምስኪን ገበሬዎችና የአካባቢው የመብት ተሟጋቾች በስተቀር ትኩረት አልተሰጠውም። ስለዚህ በአባይ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለው የህዳሴ ግድብ ቀጣይት ከወዲሁ አደጋ ተጋርጦበታል። መንግሥት በበኩሉ በሐሰት የተጋገረ መረጃን በማሰራጨት ተጠምዶ ባለፈው ዓመት ይህ ከታሰበለት ጊዜ በላይ የዘገየው ፕሮጀክት “63%” ተጠናቋል ተብሏል። ምድር ላይ ያለው መረጃ ግን ይህን አያሳይም። እውነት ነው፤ ብሳሊኒ ኩባንያ እየተሰራ ያለው የሲቪል ምህንድስና ግድቡ ግንባታ የተባለውን ያህል ባይሆንም ጥሩ በሚባል ደረጃ ቢሆንም ከግድቡ ጋር የተያያዙ የተለያዩ ሥራዎች ግን ዛሬም ምን ላይ እንዳሉ አይታወቅም። ምክንያቱም ትኩረቱም ሆነ እንቅስቃሴው ሁሉ ይታይ የነበረው የኃይል ማመንጫ ተርባይኖች የሚገጠሙበት የምህንድስና ግንባታ ብቻ ነውና። ይሁን እንጂ ሰው ሰራሽ ሐይቅ /ውሃ ማጠራቀሚያ ያለው የውሃ ኃይል ፕሮጀክት ግንባታ የአገልግሎቱ ጥራቱ ቀጣይነት ይኖረው ዘንድ የተለያዩ ባለሙያዎች የሚሳተፉበት በርካታ ሥራዎች ያሉት ዘርፍ ነው።

አሁንም ቢሆን መንግሥት ቢዘገይም ግድቡ ቢያንስ በታሰበለት ጊዜ ባይጠናቀቅም፤ በተሻላ ጥራት በተሳካ ሁኔታ ይጠናቀቅ ዘንድ ከግድቡ ባለቤት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በተጨማሪ ሌሎች የሚመለከታቸው ባለሙያዎች ቢጎበኝና ምክረ ሐሳብ ቢታከልበት የበለጠ ስኬታማ ይሆናል። በተለይ ዘርፍ ያሉ ኢትዮጵያውያን የምህንድስና፥ የውሃ ሃብት፥ የአካባቢና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና እንክብካቤ፥ የማኅበራዊና ኢኮኖሚ ባለሙያዎችን በውጭም ይሁን በሀገር ውስጥ ያሉ ቢያንስ አንጋፋ ባለሙያዎችን ጋብዞ ቢያስጎበኝ፥ ከዛም አጋዥ/ደጋፊ ተጨማሪ ጥናትና ምክረ ሐሳቦች ቢታከሉበት የበለጠ ውጤታማ መሆን ይችላል። እስካሁን የተሰበሰበውና ጥቅም ላይ የዋለው የህዝብ ገንዘብም ቢሆን በተወሰነ ደረጃ በግልፅ ለህዝብ ቢገለፅ (ዝርፊያ እንደተፈፀመበት ቢታወቅም) ተጨማሪ ድጋፍ ለማግኘት ጥሩ ዕድል ሊፈጥር ይችላል። ግድቡ ለሀገሪቱ ያለው ጠቀሚታ ዘርፈ ብዙ ከመሆኑ አኳያ በፕሮጀክቱ ዙሪያ ያሉ ግልፅነትና ተጠያቂነት ጉዳይ ግን በጊዜ ሊፈተሽና ሊታረም ይገባዋል። ምክንያቱም የአባይ ወንዝ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥ ያለ ግን ደግሞ በቁጭት የሚወሳ ተናፋቂ ወንዝ በመሆኑ ግድብ ሃብት ብቻ ሳይሆን የዘመናት በወንዙ ውሃ አልምቶ የመጠቀም ቁጭት የመፍትሄ አካል ተደርጎ የሚወሰድም ጭምር ነውና።

ARE WE SELLING THE NATION OUT?

kebour-ghenna

Kebour Ghenna

You won’t believe this….we hardly believe it ourselves… The Federal Democratic Republic of Ethiopia has put the Ethiopian Shipping Lines (ESL) S.C. on sale (apparently for minority stake…). Is the government so short of money to run its business and service its loans that it has to look for such a short cut? Or is this a matter of “privatization” or “economic efficiency”? By the way, I read that privatization increase neither efficiency nor competition, but do lead to price increases for consumers, higher costs for government, corruption, embezzlement and the destruction of democracy.
But this is a deeper subject …let me leave it for another day.

Now, how does one explain a situation where, one good morning, the Federal Government announces the sale of one its prized assets, which has taken almost three generations to build? Should we applaud the government for this daring move? Should we be grateful for its flair. No debate, no contest, no explaining to the public what other options were considered that could have avoided the sale of this national treasure. What’s more disappointing is the fact that policymakers, in the last couple of months, have been promising to be transparent, open, and inclusive but judging from events on the ground, we have not moved an inch in that direction.

Still believe in democracy?
Many years ago, 1964 G.C to be exact, Emperor Haile Selassie’s government established the ESL with two share holders: the government (49%) and a US firm (51%). In the late sixties the government bought back the 51% of the shares (with real money, if you know what I mean) owned by the US firm. Half a century later we’re back to square one. Selling our hard earned stake, this time to a Chinese company! The Emperor would have screamed!
This is not good news. It tells us there is far more problem in the horizon than potential upside.

From where I sit the proposal to sell the ESL is outrageous. It amounts to disinheritance of future Ethiopians. National assets like the ESL are strategic investments for not just economic but security reasons as well. I don’t know about you, but I can’t bear the idea that a Chinese company may soon control the ESL, and who knows, in a not too distant future many of the country’s public assets.

Not long ago the magazine African Business reported:
“In the next five years, the company (meaning ESL) will extend the entire transport and logistics chain, which could make it the largest liner trader in Africa in the next five years. It will extensively build its competitive advantage and outreach in the oil and gas shipment to serve the international market through strategic partnerships. Existing constraints in finance and limited access to foreign credit suppliers is a challenge. However, the company’s performance report shows a positive return that will attract credit suppliers to work with the company: its strict follow-up and implementation of international rules and regulations has enabled Ethiopia to be among the very few IMO white-listed countries.”

Local news outlets have also regularly reported on the profits of the ESL. You try to make out what is going on here.

Now, I really do not have anything against the sales of assets but then it should only be those that are either not profitable or you cannot run efficiently. As I said, my heart was made heavier when I noted the absence of any debate on the issue, and the news was reported as a benign matter of fact. Who can trust a government when its institutions that are meant to ensure economic prosperity and unity through sound policies fail to do so? Isn’t it this type of behavior that triggers more chaos and panic than poor governance? Apart from the economic dimension, how can we ignore that national assets such as the ESL are instruments of unity in a country that is plural like ours? Afar, Amhara, Gambela, Oromo, Somali, Tigray, Welayta and all other groups have the consciousness that national investments unite us, and that gains or otherwise there from are nationally shared.

No doubt the proposal to sale of the ESL makes many Ethiopians uneasy. From talking to ordinary people I get the sense that the ESL deal has made many compatriots uneasy for reasons they couldn’t quite articulate.

In fact I think the uneasiness of the people has more to do with what it says about the peculiar fiscal climate in the country. How is it that in one of the fastest growing nation on earth, the government simply don’t have the cash to maintain such a strategic asset, the political will to raise such funds, or the competence to run such reasonably profitable operations? Why is Ethiopia being forced to sell off long-term cash cows for short-term cash? People sense that the Chinese buyer would take the company and move it to Shanghai, or Hong Kong. I doubt if the contract spells out in detail obligations of the buyers to invest in maintenance or to maintain jobs opportunities for Ethiopians, or to keep a lid on shipping rates.

Remember selling a public asset is a classic one-shot – a short-term measure that bolsters the balance sheet today but that can’t be repeated. While politicians focus on getting through the next few fiscal years with minimum pain, foreign Chinese companies are thinking about how to get rich off of shipping business for the next three-quarters of a century.
Of course, by selling the ESL at high prices, Ethiopia could be taking foreigners for a ride. In the eighties the Japanese famously overpaid for Rockefeller Center in New York, after all. It’s possible that the FDRE just ripped off the Chinese on this deal. But I doubt it.

Ah!… Two more questions:
Think Ethiopian Airlines and Ethiopian Electric Power and ET Telecom are safe? Think again!
And who reaps the commission from the ESL deal?
You may have the same reaction we did: This is crazy!

ወልቃይት ላለፉት ሺህ ዓመታት በትግራይ ስር ተዳድራ አታውቅም – የታሪክ ማስረጃዎች

(Ze Addis)

የኢትዮጵያ መንግስት (ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ) አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኋላ ከወሰዳቸው ዓብይ ኩነታት አንዱ፤ የሀገሪቱን የፖለቲካን የአስተዳደር ካርታን መቀየሩ እንደሆነ ይታወቃል:: የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገራት ካርታ እ.ኤ.አ. በ1994 ቢቀየርም፤ አዲሱ ካርታ ብዙ የማንነት ጥያቄዎችን አስነስቷል:: ይህ የዳግም መካለል ጥያቄ ከሚነሳባቸው ቦታዎች ውስጥ ወልቃይት አንዱ ነው።

እንዲህ አይነት የማንነትና የመካለል ጥያቄ ሲቀርብ ዋና መፍትሄ የሚሆኑት የታሪክ ሰነዶች ናቸው:: የታሪክ ሰነዶች ስለ ወልቃይት ግን ምን ይላሉ? ላለፉት ብዙ መቶ ዓመታት የተጻፉ የታሪክ ሰነዶች ምን እንደሚሉ እንመርምር::

1/ ወልቃይት ጠገዴና አላማጣ ኮረም በአጼ ዮሓንስ ዘመን በትግራይ ሥር አልነበሩም – የታሪክ ሰነድ ማስረጃ

አጼ ዮሓንስ ከ 1871 ዓ.ም እስከ 1889ዓ.ም (እ.ኤ.ኣ) ኢትዮጵያን የመሩ ንጉስ ናቸው:: ንጉሰ በንግሥና ዘመናቸው የራሳቸው ጠንካራና ደካማ ጎን ቢኖራቸውም፣ ከጠላት ደርቡሽ ጋር በመፋለም ለሀገራቸው ክቡር ሕይወታቸውን የሰጡ ንጉሰ ናቸው:: ጥቂት የማይባሉ የሕወሀት ሰዎች፣ ከወልቃይትና ጠገዴ ጋር በተያያዘም የሚጠቅሱት እሳቸውን ነው:: “ወልቃይት እና ጠገዴ ፣ ጥንት በአጼ ዮሓንስ ዘመነ መንስግት በትግራይ ስር ነበረች” በማለት እንደ ዋና መከራከርያ ሲያቀርቡት ይደመጣል:: እውነታውን የዘገቡት የታሪክ ሰነዶች ናቸውና የታሪክ ሰነዶችን እንመርምር::

በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረው የትግራይ ግዛትና፣ አጠቃላዩ የኢትዮጵያ ግዛት ምን እንደሚመስል በዝርዝር በሀገር ውስጥና በውጭ ሊቃውንት ተጽፏል:: ስለ ወልቃይትም አስተዳደር በማን ስር እንደነበረ በዝርዝር ጽፈውታል:: ለዚህም የእውቁን የፈረንሳዊ የጂኦግራፊ ፕሮፌሰር ኤሊስ ሬክለስ መጽሓፍን በዋቢነት መጥቀስ ይቻላል::

በዩንቨርሲቲ ኦፍ ብረስልስ የኮምፓራቲቭ ጂኦግራፊ (University of Brussels, Professor of Comparative Geography) ፕሮፌሰርና የዴፓርትመንቱ ሀላፊ የነበረው ይሄው ፕሮፌሰር ፤ በ1880 ጀምሮ በርካታ መጽሓፎችን በዓለም ጂኦግራፊ ላይ ጽፏል:: እነዚህም መጽሓፍቱ ከለንደንና ፓሪስ ጆኦግራፊካል ሶሳይቲ የወርቅ ሜዳሊያ ተሸላሚ አድርገውታል::

ከነዚህ መጻሕፍት አንዱ በ 1880 የተጻፈው The Earth and its Inhabitants የሚለው ሲሆን፤ ዘጠኝ ተከታታይ ክፍሎች አሉት። የዚሁ መጽሓፍ ክፍል አራት በገጽ 443 ላይ የሰሜን እና ምስራቅ አፍሪካን የወቅቱን ጂኦግራፊ በዝርዝር ይተነትናል:: በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረውንም የኢትዮጵያን ክፍላተ ሀገራት በዝርዝር ቁልጭ አድርጎ እንዲህ ጽፎታል::

“The Amhara government provinces are: Dembia, Chelga, Yantangera, Dagossa, Kuarra, Begemidir, Guna, Saint, Wadla, Delanta, Woggera, Simen, Tselemt, Armachiho,Tsegede, Kolla Wogerra፣ Waldiba and Wolkait”

Table-Tigray-territories-from-the-book-The-Earth-and-its-Inhabitants-768x363

Table – Tigray territories from the book – The Earth and its Inhabitants

ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት ይህ ጽሁፍ የተጻፈው በ1880ዎቹ አጼ ዮሃንስ የሀገሪቱ ንጉስ በነበሩበት ዘመንና የተጻፈውም በግዜው ከነበሩ ከተለያዩ የጂኦግራፊካል ሶሳይቲዎች የወርቅ ሜዳይ ተሸላሚ በሆነ ባለሙያ ፕሮፌሰር ነው:: ይህ በ1880ዎቹ የተጻፈው መጽሓፍ እንደሚያስረዳው በአጼ ዮሓንስ ዘመን ወልቃይት: ጠለምት : ዋልድባ : አላማጣ : በሙሉ በትግራይ ስር አልነበሩም:: እነዚህን ቦታዎች በስም ጠቅሶ እንደሚነግረን በትግራይ ስር ሳይሆን በጎንደር ስር ነበሩ::

“በአጼ ዮሓንስ ዘመን ወልቃይትና ጠግዴ በትግራይ ስር ስለነበሩ ነው አሁን ወደ ትግራይ የጠቀለልናቸው ” የሚለው መሰረት የሌለው መሆኑን ይሄ መረጃ ያሳየናል:: ከአጼ ዮሓንስ በፊትስ እነዚህ ቦታዎች ይተዳደሩ የነበሩት በማን ነው? የሚለውን እንመልከት። ወደ አጼ ቴዎድሮስ ዘመን እንጓዝ፡፡

2/ በኣጼ ቴዎድሮስም ዘመን ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች

በኣጼ ቴዎድሮስ (1818 – 1868 እ.ኤ.አ) የነበሩ ስመ ገናና ኢትዮጵያዊ ንጉስ ነበሩ:: በየቦታው የነበሩ መሳፍንትን አሸንፈው፣ ማዕላዊ መንግስት ከመሰረቱ በኋላ፣ ቀጣይ ራዕያቸው የምዕራብያውያንን ቴክኖሎጂ እዚሁ ኢትዮጵያ እንዲመረት ማድረግ ነበር:: ለዚህም ከበርካታ አውሮፓ ሀገራት ጋር ግንኙነት መስርተው ነበር:: የአውሮፓውያን ጥበበኞችን ኢትዮጵያ ለማስቀረት እና ጥብቅ ግንኑነት ለመመስረት፣ አጼ ቴዎድሮስ ልጃቸውን ለአንድ ስዊስ ኢንጂነር እስከመዳር ደርሰው ነበር:: በዚህም ምክንያት በርካታ አውሮፓውያን ጠቢባን በአጼ ቴዎድሮስ ዘመን ኢትዮጵያ መጥተዋል:: እነዚህም ባለሙያዎች ኢትዮጵያ መጥተው ስለ ሀገሪቱ በዝርዝር ጽፈዋአል:: የእንግሊዝ መንግስትና የኢትዮጵያ ግንኑነት መሻከር ሲጀምር፣ እንግሊዞች ስለኢትዮጵያ ይበልጥ የማወቅ ፍላጎታቸው ጨመረ::

የእንግሊዝ መንግስት የintelligence ሰዎችም የእንግሊዝ መንግስት ፓርላማና የጸጥታው ኃይል ኢትዮጵያን በሚገባ ያውቃት ዘንድ ትዕዛዝ ወጣ:: የእንግሊዙ Topographical and Statistical Department of The War Office ኤ . ሲ ኩክ (A. C. Cook) በተባለ እንግሊዛዊ ኮሎነል አማኻኝነት ስለ ኢትዮጵያ ከ15ኛው ክፍለ ዘመን ጀመሮ በተለያዩ እውሮፓውያን ተጻፉ መጻሕፍት ባንድ ላይ እንዲጠርዘ ተደረገ:: የሚደንቀው ይሄ መጽሓፍ በ 1867 ዓ.ም እ.ኤ.ኣ የታተመው በግስቲቷ ጥያቄ ለእንግሊዝ ሀውስ ኦፍ ኮመን ሎወር ሀውስ ግብአት (House of Common lower House) ይውል ዘንድ መሆኑ ነው:: በዚሁ መጽሓፍ ውስጥ፤ የወቅቱ የኢትዮጵያ ዝርዝር ጉዳይ ተጽፏል:: ይሄውም መጽሓፍ ስለ ወልቃይትና ጠገዴም በኣጼ ቴዎድሮስም ይሁን ከሳቸው በፊት በማን ስር ይተዳደሩ እንደነበር በዝርዝር ያትታል::

“The Provinces of Amhara are : Simen, Waldibba, Wolkait,Wogera,Chilga, Kuara, Belesa, Fogerra, Damot, Gojjam, Begemidir, Beshilo ….. Waldiba situated to the NW of Semein between the Tekeze and the Angereb, extends as far as the junction of the two rivers. Welkait is to the west Of Waldiba it is intersected through its whole length by the two river tekuar and guang. It is more wooded than waldiba..” (Routes in Abyssinia (printed in 1867 G.C) page 188)

ይሄው ታሪካዊ መጽሓፍ በወቅቱ የነበረውንም የትግራይ ክፍለሀገር ድንበር እና ግዛት እነማን እንደነበሩ በማያሻማ ቋንቋ እንዲህ ይነግረናል፡፡

“The territory of Tigre whose capital is Adwa, is bounded on the West by Shire, on the Southwest by Temben and Adet on the South by Geralta on the South –East by Haramat, on the East by Agame, and on the North by the rivers of Mereb and Belessa”

የትግራይ ግዛትስ? ብሎ ለሚጠይቅ ወገን ፤ ይሄው መጽሓፍ በወቅቱ የነበርቸው ትግራይ ምን እንደምትመስል እንዲህ ሲል አስፍሮታል በዚሁ መጽሓፍ ላይ ገጽ 187 – 188 የትግራይን ግዛት እንዲህ ሲል ይገልጸዋል

“The territory of Tigray whose capital is Adwa is bounded on the west by Shire, on the south west by Temben and Adet, on the south by Geralta, on the South East by Haramat, on the East by Agamae, and on the North by the Rivers Mereb and Belessa”

Map-northern-Ethiopia-areas-768x362

Map – northern Ethiopia areas

እዚህ ላይ በ 18ተኛው ክፍለ ዘመን የትግራይን ወሰኖች በማያሻማ ሁኔታ በግልጽ አስቀምጦታል:: የትግራይ ወሰን በምዕራብ – ሽሬ ፤ በምዕራብ ደቡብ – ተምቤን እና አዴት ፤ በደቡብ – ገር አልታ ፤ በምስራቅ – አጋሜ ፤በሰሜን – መረብና በለሳ ናቸው:: የታሪክ ሰነዶች በአጼ ቴዎድሮስም ዘመን እንደሚነግረን ፤ ወልቃይትና ጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም::

ከዛስ በፊት ወልቃይትና ጠገዴ በትግራይ ስር ነበሩን? አሁንም የታሪክ ሰነድ እንመርምር::

3/ በዘመነ መሳፍንት ዘመንም ወልቃይትጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች

እንደሚታወቀው ከአጼ ኢዮአስ ሞት ጀምሮ ፤ አጼ ቴዎድሮስ እስኪነሱ የነበረው ዘመን ዘመነ መሳፍንት ይባላል:: በዚህ ዘመን ኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግስት አልነበራትም:: መሳፍንቶች የገነኑበትና በሀገሪቱ ማዕከላዊ አስተዳደር የጠፋበት ዘመን ነበር:: በዚህ ማዕከላዊ የመንግስት ሕግ በሌለበት ወቅት እንኳን ወልቃይት፥ጠገዴ፥ ዋልድባ ፥ አላማጣ፥ ኮረም እና የመሳሰሉ ቦታዎች በትግራይ ስር አልነበሩም:: አሁንም ማስረጃ እነሆ!

ጀምስ ብሩስ የተባለው ስኮትላንዳዊ ፥ በዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያ መጥቶ ኢትዮጵያ በዘመነ መሳፍንት ምን ትመስል እንደበረ፥ ቁልጭ አድርጎ አስቀምጦታል:: እያንዳንዱ መስፍን ግዛቱ የት ድረስ እንደነበረ፥ የትኛው መስፍን ማንን ይገዛ እንደነበረ በሰፊው ተንትኖታል:: በዚህም መሰረት ስለ ትግራይ ግዛትና እንዲህ ሲል ምስክርነቱን ይሰጣል :: Travel to discover source of the Nile Volume 3 page 582 ላይ

“Tigre is bounded by the territory of the Bahirenegash that is by the river Mereb on the East and Taccazze upon the west. It is about one hundred and twenty miles broad from E. to W. and two hundred from N. to S. “

ጀምስ ብሩስ በዚሁ መጽሓፉ Chapter 10 ላይ Geographical division of Abyssinia into province በሚለው አንቀጹ ላይ በይበልጥ ቁልጭ አድርጎ እንዲህ ያስቀምጠዋል

The first division is called Tigre, between Red Sea and the river Tekeze. Between that River (Tekeze) and the Nile Westwards where it bounds the Oromo, it is called Amhara.

ካለ በኋላ ወረድ ብሎ ይበልጥ ጉዳዩን ሲያስረዳ “Tekezze is the natural boundary between Tigre and Amhara”

ከላይ ለአብነት ያስቀመጥኳቸው ሊቃውንት በግዜ፣ በቦታና በዜግነት አይገናኙም:: ለምሳሌ በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረው አሊስ ሬክለስ ፈረንሳዊ (French) ነው:: በአጼ ቴዎድሮስ ዘመን የነበረውን የኢትዮጵያ ግዛት የጻፈው ደግሞ እንግሊዛዊ ነው (British):: ጀምስ ብሩስ ደግሞ ስኮትሽ (Scottish)ነው:: ግን ሁሉም በተለያየ ግዜ መጥተው ያዩትና የተገነዘቡትን ጽፈዋል:: የሚናገሩት አንድ ና ተመሳሳይ ነው:: እውነት ምን ግዜም አንድ ናትና!

4/ ወልቃይት በ1630ዎቹስ በማን ስር ነበረች?

በ16ኛው መቶ አጋማሽ ላይ ያሉ ያታሪክ መዛግብትም የሚናገሩት ተመሳሳይ ነገር ነው:: በተለያዩ ወገኖች ተደጋግሞ የሚጠቀሰው የ ማኑኤል በሬዳም መጽሓፍ የሚተነትነው ያንኑ ነው:: ይሄ መጽሓፍ የተጻፈው በ1634 ሲሆን ጸሓፊውም ኢማኑኤል በሬዳ ይባላል:: በወቅቱ የነበረውን የትግራይ ግዛት በዝርዝር አስቀምጧል:: እሱም እንደሌሎቹ ጸሓፍት የትግራይ ድንበር ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ ናቸው አይልም::

«Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634» መጽሀፍ የመጀመሪያ ምዕራፍ ስለ ትግራይ ግዛት እንዲህ ይላል::

“Among all the kingdoms that the Emperor of Ethiopia possesses today one of the greatest if not the greatest and the most important is the kingdom Tigre. From north to south, that is from the limits of the Hamasen to Enderta, it covers an areas of from ninety to one hundred leagues (3.2 miles); and from the east, which is besides Dancali, located at the entrance to the Red sea to the southern end of the Red Sea, to the west bounded by the Tekezze River beside the Semen, it covers an area of similar size, so that the Kingdom has a nearly circular shape.”

አሁንም ወደኋላ እየራቅን እንሂድና ወልቃይት ጠገዴ በነ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን በማን ስር ነበርች? የሚለውን እንመልከት

5/ በኣጼ ዘርዓ ያዕቆብ ( 14ኛው ክፍለ ዘመን) ዘመንም ወልቃይትጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች

አጼ ዘርዓ ያዕቆብ በኢትዮጵያ ታሪክ ከተነሱ ሃያልና ሊቅ ነገስታት ውስጥ አንዱ ነበሩ:: በቀድሞ ስሙ ፈጠጋር በአሁን ስሙ ኦሮሚያ አዋሽ ወንዝ አካባቢ የተወለዱት አጼ ዘርዓ ያዕቆብ፥ የሀድያ ሲዳሞ ንጉስ ልጅ የሆነችውን እሌኒን አግብተው፥ በ37 ዓመታቸው ከነገሱ ጀምሮ በርካታ ዓበይት ስራዎችን አከናውነው አልፈዋል:: እኒሁ ንጉስ ከፍተኛ የጥበብ ፍቅር የነበራቸውና ከመሆናቸው ባሻገር፥ ራሳቸው ብዙ መጻሕፍትን ጽፈዋል:: በሳቸው ዘመንም ብዙ መጻሕፍት እንዲጻፉ ድጋፍ በመስጠታቸው አያሌ መጻሕፍት በሳቸው ዘመን ተጽፈዋል:: ከነዚህ መጻሓፍት አንዱ በአክሱም ንቡረ ዕድ የተጻፈው ዜና አክሱም መጽሃፍ አንዱ ነው:: ዜና አክሱም ከሃይማኖያትዊ ሐተታው ባለፈ ስለ 14ኛዋ ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ በዝርዝር ጽፎታል:: ይህ መጽሓፍ የኢትዮጵያን አጠቃላይ ወሰንና ታሪክ ብቻ ሳይሆን የክፍላተ ሀገራቱንም ድንበር ጥንቅቅ አድርጎ ዘግቦታል:: የትግራይንም ክልል በካርታና በጽሁፍ ከዚህ እንደሚከተለው ይገልጸዋል::

Chart-List-of-Tigrai-areas-on-Zena-Axum-book

Chart – List of Tigrai areas on Zena Axum book

ይህም መጽሓፍ በተመሳሳይ መልኩ የሚነግረን፣ ወልቃይትና ጠገዴ በፍጹም ፣ የትግራይ አካል አንዳልነበሩ ነው::

ዮሓንስ መኮንን Ethiopia: the land, its people , History and Culture በሚለው መጽሓፉ Page 351 በአጼ ዘርዓ ያ ዕቆብ ዘመነ መንግስት የነበረውንና በመጽሓፍ አክሱም የተተነተውን የትግራይን ካርታ እንዲህ ያቀርበዋል

“The Book of Axum.. Shows a traditional schematic map of Tigray with its city Axum at its center surrounded by the thirteen principal provinces: Tembein, Shire, Seraye, Hamasen, Bur, Sama, Agame, Amba Senait, Geralta, enderta, Sahart and Abergele”

በተመሳሳይ ሁኔታም The World through Maps: A History of Cartography (ገጽ 352 ይመልከቱ)፡፡ በJohn R. Short የተጻፈው የዓለም ጂኦግራፊን የሚተርከው መጽሓፍ በ15ኛው ክፍለዘመን የነበሩ የትግራይ ግዛቶች ከላይ የተጠቀሱት መሆናቸውን መጽሓፈ አክሱምን በመጥቀስ ያስረዳል:: ይህም መጽሓፍ በተመሳሳይ መልኩ የሚነግረን፣ ወልቃይትና ጠገዴ በፍጹም የትግራይ አካል አንዳልነበሩ ነው::

6/ ቋንቋን መሰረት ወዳደረገ ክለላን አንመልከት

የኢትዮጵያውያን ወጣቶችና አርበኞች ቁጣ ያሳሰበው ጣልያን፣ ኢትዮጵያን በቋንቋና በዘር በትኖ ለመግዛት ያቀደውን መርዝ ይፋ አወጣ:: የዚህ እቅድ ፊታውራሪ ከሆኑት አንዱ ፋሺስቱ Baron Roman Prochàzka አቢሲንያ ዘ ፓውደር ባረል (Abyssinia: the Powder barrel) በሚል መጽሓፉ ላይ እንዳስቀመጠው፣ ኢትዮጵያውያንን ለመግዛት በዘር መከፋፈልና በመሀከላቸውም ጥላቻን በመዝራት እርስ በርስ ለማናከስ፣ ሀገራቸውን በዘር መከለል የሚለውን እቅድ መተግበር ጀመረ:: በዚሁም መሰረት፣ ዘርንና ቋንቋን መሰረት ባደረገ ሽንሸና ኢትዮጵያን አምስት ቦታ ከፈላት::

እነዚሁም ክልሎች አማራ: ኤርትራ(ትግሬ); ሐረር: ኦሮሞ-ሲዳማ: ሸዋና ሶማሌ ናቸው:: ጣልያን ይሄንን የግዛት ሽንሸና ሲያካሂድ መሰረት ያደርገው ዘርና ቋንቋን ነበር:: የሚከተለውም ሰማንያ በሃያ የሚለውን መርህ ነበር:: ከሰማንያ በመቶ በላይ ሕዝቡ የሚናገረውን ቋንቋ መሰረት በማድረግ ወደየ ክልሉ ይደለደላል:: ሸዋን ግን ለብቻው ለይቶ መቆጣጠር ይገባል ብሎ በማመኑ ሸዋን ና ሀረርን ለብቻ ለይቶታል:: ወደ ነጥባችን ስንመጣ በዚህ የቋንቋ ሽንሸና መሰረት ወልቃትና ጠገዴና ጠለምት ወደ ትግራይና ኤርትራ አልተካተቱም:: በጎንደር ስር ነበሩ::

እዚህ የጣልያን ቋንቋንና ዘርን መሰረት ያደረገ ካርታ ላይ በግልጽ እንደሚታየው ፣ የትግራይ ድንበት ተከዜ እንጂ – ከተከዜ ተሻግሮ አይደለም:: ላልፉት 25 ዓመታት ተቃዎሞ ሲካሄድባቸው የከረሙት ወልቃይት – ጠገዴ – አላማጣ ኮረም በፍጹም በትግራይ ስር እንዳልነበሩ በግልጽ ያሳየናል::

Map-Tigray-during-Fascist-Italy-768x664 (1)

Map – Tigray during Fascist Italy

7/ አንዳንድ ሚድያዎች ደጋግመው የሚያነሱት ነጥብ አለ:: ይሄውም ወልቃይት ጸገዴና ሌሎች ወደ ትግራይ የተካለሉ ቦታዎች ጥንት የትግራይ እንደነበሩና አጼ ኃይለ ሥላሴ የምስራቃዊ ትግራይ ገዥ ከነበሩት ከደጃዝማች ኃይለሥላሴ ጉግሳ አርዓያ ጋር በመጣላታቸው – ወልቃይትና ጠገዴን ወደ ጎንደር ወሰዱት የሚል ነው:: ሌላው የማያስማማው ነጥብ ደግሞ – የቀዳማይ ወያኔን አመጽ ምክንያት በማድረግ ትግራይን ለመቅጣት – ወልቃይትንና ጠገዴን ወደ ጎንደር ከለሉት የሚል ነው::

እስካሁን ከላይ የገለጽኳቸው ሰነዶች ለዚህ ነጥብ በቂ ማስረጃ ቢሆኑም : ካርታን መሰረት ያደረገ መረጃ ለሚጠይቅ ሰው – እነሆ:: ይህ ካርታ በጣልያኖች በ1928 ዓ.ም የተሰራ ነው:: ኢትዮጵያን በደምብ ካጠኑ በኋላ ለያንዳንዱ ክፍለሀግር ካርታ ሰርተዋል:: ያኔ ገና ኃይለሥላሴ ጉግሳ አልከዳም:: ያኔ የቀዳማይ እንቅስቃሴ አልነበረም:: የቀዳማይ እንቅስቃሴ በ1943 ነበር፡፡ ይህ ካርታ ግን ከዛ ብዙ ዓመታት በፊት የተሰራ ነው:: አንባቢው አይቶ ይፍረድ:: ወልቃይት ጠገዴን ነጥለን ስንመለት ካርታው ይሄንን ይመስላል::

Map-north-west-Ethiopia-in-1928

Map – north west Ethiopia in 1928

8/ በዘመነ መንግስቱ ኃይለማርያም ወልቃይትና ጠገዴ

በካምብሪጅ ዩንቨርሲቲ በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ ይበልጡንም በኢትዮጵያ ታሪክና ፖለቲካ ላይ ከፍተኛ ምርምር ካደሩት ሰዎች ውስጥ በዋነኝነት የሚጠቀሱት ፕሮፌሰር ክሪስቶፈር ክላፓም: እንደ ኤሮፓ አቆጣጠር 1990 ( ህወሀት አዲስ አበባብ ከመያዙ አንድ አመት በፊት) ድንቅ የሆነ መጽሓፍ አሳትመው ነበር:: በዚሁ መጽሓፋቸው ላይም ስለ ወልቃይትና ጠግዴ እንዲህ ሲሉ ይተርኩታል

“the area concerned (welkait -Tsegede) separated from Tigray by impressive natural barrier of Setit Tekezze river has never been governed as part of Tigray at any period in the past, but has come under Gonder and Semein.” (Christopher Clapham: Transformation and continuity in revolutionary Ethiopia (Cambridge: Cambridge university press 1988 pp 259)

ስናጠቃልለው

1. 1420ዎቹ እንደተጻፈ የሚታመነው መጽሓፈ አክሱም በግልጽ እንደሚያሰረዳን የትግራይ ግዛቶችና ወሰኖች 13 ነበሩ:: እነርሱም Tembein, Shire, Seraye, Hamasen, Bur, Sama, Agame, Amba Senait, Geralta, enderta, Sahart and Abergele ናቸው::

ማስረጃ : መጽሓፈ አክሱም , Ethiopia: the Land, Its People, History and Culture By Yohannes Mekonnen. The World through Maps: A History of Cartography (ገጽ 352 ይመልከቱ) By John R. Short

2. 1634 ዓ.ም የተጻፈው የ እማኑኤል በሬዳ መጽሓፍ Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634» እንደሚያስረዳው የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ አይደሉም

3. በዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያን ጎብኝቶ የነበረው የጀምስ ብሩስ መጽሓፍም በግልጽ የሚናገረው የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ አይደሉም፡፡ Travel to discover source of the Nile Volume 3 page 582

4. በአጼ ዮሓንስ ዘመንም የታሪክ ማስረጃዎች የሚያስረግጡት ያንኑ ነው:: የትግራይ ደንበር ተከዜ ነው:; ወልቃይትና ጠገዴ በጎንደር ስር እንደነበሩ በግልጽ ፈረንሳዊው ፕሮፌሰረ ሬክለስ ጽፎታል

5. በአጼ ቴዎድሮስ ዘመንም ወልቃይትም ይህን ጠግዴ በትግራይ ስር አልነበሩም::

6. በጣልያን ግዜም የትግራይ ወሰን በደቡብ እንዳምሆኒ, በደቡብ ምስራቅ አበርገሌ ;በም ዕራብ ሽሬና አዲያቦ ነበሩ እንጂ ወልቃይት ጠግዴ ዋጃ ኮረም እና መሰል ቦታዎች በትግራይ ስር አልነበሩም

7. ወልቃይትንና ጠገዴን ወደ ትግራይ የከለሉት አጼ ኃይለሥላሴ ናቸው:; ይህም በ1943 ዓ.ም የተካሄደውን የቀዳማይ ወያኔን አብዮት ለመበቀልና ሕዝቡንም ለመቅጣት ነው የሚለው: መሰረት እንደሌለው እነሆ ይህ ማስረጃ:: ጣልያን ይሄን ካርታ የሰራው በ1928 ዓ.ም ነበር:: ያኔም በአጼው ግዜም የትግራይ ወሰን ያው ነበር

8. የህዝብ ቁጥርና በሚነገሩት ቋንቋ ነው ወልቃይትንና ጠግዴን ወደ ትግራይ የከለልነው ለሚለውም – የዘርና የቋንቋ ክልልን ለመጀመርያ ግዜ ኢትዮጵያ ላይ የመሰረተው ጣልያን ነው:: ጣልያን ይህን ካርታ ሲሰራ የራሱን የዘርና የቋንቋ ጥናት አድርጎ ነበር:: በዚህም መሰረት ወልቃይትና ጠግዴን ወደ ትግራይ ሳይሆን ያካለላቸው ወደ ጎንደር ነበር:: ይሄ ከሆነ አንድ ትውልድ እንኳን አላለፈው:: ታድያ ያኔ አብላጫ የነበረው ቋንቋና ሕዝብ አሁን ወዴት ገባ?

9. በዚህ ዘመን ያሉ እውቅ የኢይዮጵያ ነክ ፕሮፌሰሮችም ምስክርነታቸው ያው ነው:: የካምብሪጅ ዩኒቨርስቲው ክሪስቶፈር ክላፕማን እንዳጠቃለሉት

“the area concerned ( welkait -Tsegede) separated from Tigray by impressive natural barrier of Setit Tekezze river has never been governed as part of Tigray at any period in the past, but has come under Gonder and Semein.

10. የአጼ ዮሓንስ የልጅ ልጅ ልዑል ራስ መንገሻ ስዩምም እንዳረጋገጡት ” የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠግዴ አይደሉም”

አሁንም ቢሆን የወልቃይት የማንነት ጠያቂዎች የ ሃምሳ ሺህ ሰው ፊርማ አሰባስበው ነው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ የሄዱት:: እንግዲህ ይሄ ሁሉ ጫና: ወከባና ግድያ ባለበት በዚህ ወቅት ሃምሳ ሺህ ሰው ፊርማ ማሰባሰብ ከቻሉ ነጻነት አግኝተው ሁሉም ቦታ ቢንቀስቀሱ የምን ያህል ሰው ፊርማ ማሰባሰብ እንደሚችሉ መገመቱ ቀላል ነው:: ያለው እውነታ ይሄው ነው::

ማጠቃለያ

አሁንም ከላይ የጠቀስኳቸውን የፕሮፌሰር ክላፕማንን ቋንቋ ልጠቀምና ” ወልቃይትና ጠግዴ በኢትይኦጵያ ታሪክ በትግራይ ስር ሆነው አያውቁም”:: ለመጀመርያ ግዜ በትግራይ ስር : እንዲካተቱ የተደረገው በ1994 ነው::

እኔን የሚያሳሰበኝ ግን ሌላ ነው:: በአንድ ሀገር ውስጥ ሆነን ስለ ድንበር እያወራን ነው:: ከዚህ የማንነት ጥያቄም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች መገደላቸውን የሰባዊ መብቶች ጉባኤ አሳውቋል:: ወዴት እየሄድን ይሆን?

———–

ዋቤ መጻሕፍትና ሊንኮች

1. ‘ልዝብን ምኽሪን ጥራሕ’ያ መድሓኒታ’ ኢሎም ዶ/ር ገላዴዎስ ኣርኣያ

2. The Earth and its Inhabitants, Africa: South and east Africa, by Elisée Reclus 1890

3. Routes in Abyssinia (printed in 1867 G.C)

4. Travels to Discover the Source of the Nile: In the Years 1768 …, Volume 3. By James Bruce

5. Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634

6. Ethiopia: the Land, Its People, History and Culture, By Yohannes Mekonnen

7. Christopher Clapham: Transformation and continuity in revolutionary Ethiopia (Cambridge: Cambridge university press 1988 pp 259

8. The World through Maps: A History of Cartography : John R Short

9. https://archive.org/details/liberaxumae00pari (the Book of Axum part one)

10. Library of Congress የኢትዮጵያ ካርታ 1955 ዓ.ም (በ1963 እ.ኤ.ኣ)

11. የኢትዮጵያ ካርታ 1966 ዓ.ም (በ1974 እ.ኤ.ኣ ወይም) Library of Congress

12. Library of Congress የኢትዮጵያ ካርታ 1979-81 ዓ.ም

13. በ1928 ዓ.ም ( 1933 እ.ኤ.አ) ጣልያን የሰራው የኢትዮጵያ ካርታ

14. በ1928 ዓ.ም (1933 እ.ኤ.አ) ጣልያን የሰራው የኢትዮጵያ ካርታ

15. CIA maps 1961 E.C and 1969 G.C

Source:- http://hornaffairs.com/am/2016/06/08/tigray-wolkait-historical-accounts

አብዮት የሚናፍቀው የኢትዮጵያ መሬት

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

መሬት ለኢትዮጵያውያን የሕልውና ጉዳይ ነው። አገሪቱ ከመንግሥት ስርዓት ጋር ከተዋወቅችበት ከክ.ል.በ. 2545 ጀምሮ ለነገሥታቱም ይሁን ለቀሪው ዜጋ መሬት የመኖርና ያለመኖር ጉዳይ ነበር። የመሬቶቹ ባለቤትነትም ከመደበኛው ከነዋሪው ይልቅ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የገዥው መደብ አባላት እና አጋሮቻቸው እንጂ የአራሹ ሆኖ አያውቅም ነበር። ይህ መሬት ለየአካባቢው የጭፍራ አለቆችም ሆነ ለመኳንንቱ የርስበርስ መቃቃርና ግጭት ዋነኛ ምክንያት ነበር። ይህ ሁሉ ታሪክ በሀገሪቱ ዘመናዊ የመንግሥት ስርዓት መሥራች በነበሩት ዳግማዊ ዐፄ ቴዎድሮስ አማካኝነት በተወሰነ ደረጃ ለውጥ የታየበት ቢሆንም፤ ሕጋዊና ሁሉንዐቀፍ አልነበረም።

በተለይ በዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ ከመኳንንቱ በተጨማሪ በርካታ ሰዎች መሬትን ለማግኘት ከቤተክርስቲያን ይጠጉም ነበር። ይሁን እንጂ ይህ ሁሉ ሲወርድ ሲወራረድ የመጣው ኋላ ቀር የመሬት ይዞታ ፊውዳላዊ ስርዓት በዐፄ ቴዎድሮስ ስላልተወደደ፣ በዜጎች መካከል ከመሬት ጋር በተያያዘ የነበረው የገዥና ተገዥ ስሜት ያበቃ ዘንድ የመኳንንቱን እና በክሕነት ሥም በየቤተክርስቲያኑ ተጠግተው በርካታ መሬቶችን በመያዝ ገበሬውን ያንገላቱ የነበሩ ባላባቶች ሁሉ አብዛኛው መሬቶቻቸው እየተወሰደ መሬት ለሌለውና ሲያርስ ለነበረው እንዲከፋፈል፤ በቤተከርስቲያንም የሚያገለግሉ ካሕናት ቁጥር ውስን እንዲሆን እና ቀሪዎቹ ወደ ግብርና ሥራ እንዲገቡ አዘዙ። ይህ ሁሉ የነበረው በዛው በጎንደርና አቅራቢ አጎራባች አካባቢ በነበሩት ወሎ፣ ጎጃምና ትግራይ እንጂ በሌላ የአገሪቱ አካባቢ በገዥ ሥም ባሉ የጎበዝ አለቆች የተለመደው የመሬት ብዝበዛ ሲያከናወን ነበር። የተጠቀሱ ቦታዎችም ቢሆኑ የተሳካ ወጥ የመሬት ክፍፍልና አዋጅ ተፈፃሚ አልሆነም፤ ምክንያቱም የነበረው ስርዓት የተረጋጋና በሰነድ የታገዘ አልነበረም።

በመጨረሻም በዐፄ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በ1966 ዓ.ም. በነበረው የተማሪዎች እንቅስቃሴ የዜጎች በተለይም የገበሬዎች የመሬት ባለቤትነት መብት ይረጋገጥ ዘንድ በይፋ ጥያቄ መቅረብ ጀመረ። ከዓመት በኋላም ለዓመታት የሕዝቡ ጥያቄ የነበረው የመሬት ባለቤትነት መብት ከዘውዳዊ ስርዓት ስንብት ጋር አብሮ ተበሰረ። ይህ የመሬት ባለቤትነት መብት በተለይም የ“መሬት ላራሹ” መብት ጥያቄ የካቲት 25 ቀን 1967 በዘመነ ደርግ ምላሽ አገኘ። ያ ወቅት ለኢትዮጵያ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ከፋች ነበር። ምክንያቱም ለረጅም ዘመናት መሬት የኢትዮጵያውን የመብትም የሕልውና ጥያቄ ነበርና። ያ አዋጅም ሆነ የተማሪዎች ጥያቄ ትኩረት የእርሻ መሬት ላይ እንጂ ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ በነጻነት በእንሰሳት እርባታ የሚተዳደሩትን በተመለከተ ነበር ለማለት አያስደፍርም። ምክንያቱም ከቦታ ቦታ በመንቀሳቀስ በእንስሳት እርባታ ይተዳደሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን መሬታቸውን ማንም ከልካይና የሚቀማ ወይም የባለቤት መብት የነፈጋቸው አካል አልነበረም። በተለይ አርብቶ አደሮች የመሬት እና የውኃ ሀብትን በሚመለከት በአነስተኛ ደረጃ እርስበርስ ከሚኖራቸው አለመግባባት በስተቀር የሚንቀሳቀሱበት ቦታ ሁሉ በነጻነት የሚጠቀሙና የባለቤትነት መብቱም ቢሆን ቢበዛ በጎሳ ይሆን እንጂ እንደ እርሻው መሬት በመኳንንቱና በመንደር የጎበዝ አለቆች ባለቤትነት የሚተዳደር አልነበረም።

ዛሬ ግን ሁሉም ነገር ተቀይሯል። የካቲት 25 ቀን 1967 የታወጀው የመሬት ላራሹም ሆነ የመሬት ባለቤተነት መብት ከሕዳር 1987 ጀምሮ በዘመነ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ ተሽሯል። የመሬት ባለቤትነት በእርሻ፣ በእንስሳ እርባታ እና በከተማ ኑሮ የሚተዳደረውን ሁሉ መብት ነው የቀማው። ምክንያቱም የግለሰብ የመሬት ባለቤትነት መብት መነጠቁን 4ኛው እንደሆነ በሚነገርለት የአገሪቱ ሕገ መንግሥት አንቀፅ በግልጽ አረጋግጧል። በዚህ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 40 ‹የንብረት መብት› በሚለው ሥር ንዑስ አንቀፅ 3 “የገጠርም ሆነ የከተማ መሬት እና የተፈጥሮ ሀብት ባለቤትነት መብት የመንግሥትና የሕዝብ ብቻ ነው። መሬት የማይሸጥ የማይለወጥ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የጋራ ንብረት ነው” ይላል።

እዚሁ አንቀፅ ላይ በንዑስ አንቀፅ 6 የመሬት ባለቤትነት የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ መንግሥት ‹ለግል ባለሀብቶች በሕግ በሚወሰን ክፍያ በመሬት የመጠቀም መብታቸውን ያስከብርላቸዋል› ይላል። በንዑስ አንቀፅ 4-5 “የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች መሬት በነጻ የማግኘትና ከመሬታቸው ያለመነቀል መብታቸው የተከበረ ነው። የኢትዮጵያ ዘላኖች ለግጦሽም ሆነ ለእርሻ የሚጠቀሙበት መሬት በነጻ የማግኘት፣ የመጠቀምና ከመሬታቸው ያለመፈናቀል መብት አላቸው። ዝርዝር አፈፃፀሙ በሕግ ይወሰናል” ይላል።
በመጀመሪያ ደረጃ ሕገ መንግሥቱም ሆነ ሕጉን ያወጡት እና ያፀደቁት እንዲሁም አገሪቱን እየመሩ ያሉ አካላት ሊመልሱት ያልቻሉት፤ ነገር ግን ሊመልሱ የሚገባቸው በርካታ ጥያቄዎችን ማንሳት ይቻላል። ከነዚህም መካከል፦

‹መንግሥት እና ሕዝብ የሚባለው ማነው የሚለው ግልጽ አይደለም። ሌላው ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሚል የቃላት ክምር ልዩነታቸውና አንድነታቸው (ካለ) ምንድነው? እነሱስ እነማን ናቸው? በማንስ ይወከላሉ፣ መብቶቻቸውና ግዴታቸውስ? የሚሉ ጥያቄች እስካሁን በየትኛውም ሕዝባዊ መድረክም ሆነ የመንግሥት ሕጋዊ መዝገበ ቃላት ፍቺም ሆነ ትርጉም ያልተሰጣቸው፤ ግን ደግሞ መልስ የሚያሻቸው ናቸው። ምክንያቱም በድፍኑ የቃላት ድርደራ ከመሆን በዘለለ ለሕዝቡ በሚገባ መልኩ በግልጽ የተቀመጠ ትርጉም የለውም።
ሌላው መሬት የማይሸጥ የማይለወጥ… የጋራ ንብረት ነው ይልና ወረድ ብሎ ደግሞ መንግሥት ለግል ባለሀብቶች በሕግ በሚወሰን ክፍያ በመሬት የመጠቀም መብታቸውን ያስከብርላቸዋል ይላል። ይህ የሚያሳየው የማይሸጥ የማይለወጥ የተባለው መሬት መንግሥት መሬት ቸርቻሪ እንዲሆን መብት ሰጥቶታል። አሁን ባለው በሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ መንግሥት የሚለውም ትርጉም የሚያስፈልገው ዐብይ ጉዳይ ነው። በአንቀፅ 40 (7-8) ላይ ደግሞ ዜጎች የግል ንብረት ባለቤትነት መብት ያላቸው በመሬቱ ላይ በሚገነቡትና በቋሚነት ለሚያሻሽሉት ቁስ እንጂ መሬቱ ላይ የባለቤትነት መብት እንደሌላቸው ያመለክታል። ይህም ከቦታው በግድ የሚፈናቀል ሰው ካሳ እንኳ ቢያስፈልገው፤ በመሬቱ ሳይሆን መሬቱ ላይ ባለው የተጠቃሚነት መብት ባፈራው ንብረት ብቻ መሆኑን ያመለክታል።

የመሬት ባለቤትነት መብት ያለመኖር ያስከተለው ችግር

በርግጥ ሕገ መንግሥቱ ሥራ ላይ ባያውላቸውም በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ዓለም አቀፍ የዴሞክራሲና ሰብኣዊ መብት ድንጋጌዎችን ያካተተ ቢሆን ግልጽ ያልሆኑ፣ ጥያቄ የሚያስነሱ በርካታ ግግር ጉዳዮችንም ይዟል። ይበልጥ ግን የገዥውን ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. በተለይም የሕ.ወ.ሓ.ት.ን የፖለቲካ ፕሮግራምና ፍላጎት በስፋት ይገኝበታል። ለዚህም ይመስላል፤ ሕገ መንግሥቱ ከተወሰኑ አንቀፆች (ላለፉት 21 ዓመታት ሥራ ላይ ያልዋሉ) ዓለምዐቀፍ ድንጋጌዎች በስተቀር የሕ.ወ.ሓ.ት./ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. የፖለቲካ ፕሮግራምና ፍላጎት የሰፈረበት ሰነድ ነው የሚል ጥያቄ የሚነሳው። በተደጋጋሚ ከሚነሱ ጥቄዎችና ቅሬታዎች መካከል የመሬት ጉዳይ ዋነኛው ነው።

በተለይ ሕ.ወ.ሓ.ት. መሬትን በተመለከተ የሚከተለው የፖለቲካ ፕሮግራም (ፖሊሲ) እና ሕገ መንግሥቱ ላይ የሰፈረው አንድ ነው። ከሕ.ወ.ሓ.ት. ውጭ ያሉ ሌሎቹ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. አባላት (ብ.አ.ዴ.ን.፣ ኦ.ሕ.ዴ.ድ. እና ደ.ኢ.ሕ.ዴ.ን.) የተሰጣቸውን ከማስፈፀም በቀር የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን ተመሳሳይ ከማድረግ ውጭ ሥልጣኑም ሆነ ሞራሉ ያላቸው አይመስልም። አጋር ድርጅቶች የተባሉት የጋምቤላ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ሶማሌ፣ አፋር እና ሐረሪ ክልል ፓርቲዎች ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.ን. ከማጀብና የሚለውን ከመቀበል ውጭ በየትኛውም አገራዊ ጉዳይ ላይ የመወሰን፣ የመጠየቅም ሆነ ላሉበት ማኅበረሰብ መብትና ጥቅም የመቆም ሕልውናም ሆነ አቅም የላቸውም። ምክንያቱም አጋር እንጂ የገዥው ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. አባል ስላልሆኑ የተሰጣቸውን ሥራ ከማከናወን ባለፈ በፖሊሲም ሆነ በፖለቲካ ፕሮግራማቸው የተለየና የራሳቸውን ነገር ይዘው መቅረብ አይችሉም። በዚህም ምክንያት ከመሬት ባለቤትነት መብት ጋር በተያያዘ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ መሆናቸው አልቀረም።

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ በፌደራሉ መንግሥት ፍላጎትና ሥልጣን ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶች ከገበሬዎቹ በግድ ተነጥቀው ለባለሀብቶች እንዲተላለፉ ተደርገዋል። ከባለሀብቱ በተጨማሪ ስርዓቱ ለሚከተለው መንግሥታዊ ባለሀብትነት (state capitalism) ትግበራ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችን ከገበሬዎች ነጥቋል። ይሁን እንጂ ከገበሬዎች ያለምንም አካባቢያዊና ማኅበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ (Environmental and social impact assessment) ሰፋፊ ለም መሬታቸው ወደ መንግሥታዊና ግል ባለሀብቶች በመተላለፉ አንዳቸውም ፕሮጀክቶች ውጤታማ አልሆኑም። ይልቁንም ያለበቂ ምክክር፣ ካሣና ምትክ ቦታ የተፈናቀሉ በርካታ ገበሬዎች ዛሬም ድረስ ሕይወታቸውን በጉስቁልና እንዲመሩ አስገድዷቸዋል። ከገበሬዎች ማኅበራዊ ችግር በተጨማሪ በአካባቢያዊ የአየር ጠባይ እና የአየር ንብረት ላይ የሚኖረው ጉዳት አገሪቱ በቀላሉ የምታካክሰው አይደለም። ይህ ሁሉ በሕገ መንግሥቱ የሰፈረው የመሬት ባለቤትነት መብትና ስርዓቱ የሚከተለው የመሬት ፖሊስ ምክንያት የተፈጠረ ችግር ነው።

Ethiopian land grabbing sample

በሰንጠረዡ ላይ እንደሚታየው በደቡብ ክልል ደቡብ ኦሞ እና ቤንች ማጂ ዞን አካባቢ ለስኳር ፕሮጀክት መንግሥት የወሰደውን 335,000 ሔክታር መሬት፣ የወልቃይት፣ የከሰም፣ የተንዳሆ ሰፋፊ እርሻዎችን፣ 2,000 ሔክታር እና ከዛ በታች ስርዓቱ የኔ ለሚላቸው ሰዎች የሰጠውን ሳያካትት ነው። መሬቱ ለግል ባለሀብቶች የተላለፈው ከ30-50 ዓመት በሚቆይ ኪራይ ነው። በዚህም ምክንያት በአንድ ሔክታር በዓመት ከ14-135 ብር የሊዝ ኪራይ የተላለፉና መንግሥት በነጻ የወሰዳቸው መሬቶች ላይ የኖሩ ዜጎች ያለ በቂ ምክክር፣ ካሣና ምትክ ቦታ ተፈናቅለዋል። በተለይ በጋምቤላ ክልል ብቻ 225 ሺሕ ዜጎች ሲፈናቀሉ፣ ከ8-10 ሺሕ የሚሆኑ ተፈናቃዮች ደግሞ አገር ጥለው ሲሰደዱ፤ ከ424 ያላነሱ ተገድለዋል። በተመሳሳይ በደቡብ ክልል በሚገኘው ደቡብ ኦሞ ዞን 200 ሺሕ ያህል ዜጎች ተፈናቅለዋል።

መንግሥት ለስኳር ልማት፣ ለማዳበሪያ ፋብሪካና ተያያዥ ግንባታዎች ልማት በሚል የወሰዳቸው ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶችና ለግል ባለሀብቶች ከተላለፉት ውስጥ ለአገሪቱም ሆነ ለዜጎች ያመጡት ጥቅም የለም። ከጥቅማቸው ይልቅ በተለይ በምዕራብና ደቡብ ኢትዮጵያ ለዘመናት የቆዩ ደኖችና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች ከጥቅም ውጭ ሆነዋል። ይህም ማኅበራዊ ሕይወት ላይ ካስከተለው ችግር በተጨማሪ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እና አካባቢ ጥበቃ ላይ ያስከተለው ጉዳት ቀላል የሚባል አይደለም። እዚህ ላይ በቅርቡ የገባበት ያልታወቀውን 77 ቢሊዮን ብር የስኳር ልማት ፕሮጀክት ገንዘብ እና የኢሉ አባቦራ ያዩ ማዳበሪያ ፋብሪካ የደን ጭፍጨፋን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል።

ሌላው ችግር ባለሀብቶች ውጤታማ መሆን ባልቻሉበት መሬት ላይ የተጠቀሟቸው ኬሚካሎች በተፈጥሮ ሀብት ላይ በተለይም በአፈሩ፣ በውሃውና በአካባቢው አየር ላይ የሚኖረው አሉታዊ ተፅዕኖ እንደቀላል የሚታይ አይደለም። ገበሬው መሬቱን በሚመለከት ለሚያቀርባቸው ጥያቄዎችም ሆኑ ቅሬታዎች ከመንግሥት ወገን የሚሰጠው መልስ “መሬት የመንግሥት ነው፤ ወደህ ሳይሆን ተገደህ ትነሳለህ” የሚል ሲሆን፤ ያለበቂ ካሳና ምትክ ቦታ ከቀዬያቸው መፈናቀላቸውን የተቃወሙ ደግሞ የእስርና ግድያ ሰለባ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። ይሄ በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የመሬት ሕጉና ፖሊሲው ካስከተሏቸው ችግሮች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው።

በከተማው ያለው የመሬት ችግር ከገጠሩ እጅጉን የባሰ ሲሆን፣ ሕዝቡ በኢኮኖሚው፣ በማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የስርዓቱ ጥገኛ እንዲሆን ካስገደዱት ነገሮች መካከል የመሬት ሕጉና ፖሊሲው ዋነኞቹ ናቸው።

‹መሬት አይሸጥም አይለወጥም›፣ ‹የመሬት ፖሊሲው የሚቀየረው በኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. መቃብር ላይ ነው›… የሚሉ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. መፈክሮች ይበልጥ የሚሰሙት በከተማ ነው። ምንም እንኳ መሬት አይሸጥም አይለወጥም ቢባልም የአገሪቱን የከተማ መሬቶች እንደጉሊት ንግድ በአደባባይ የሚቸረችረው ደግሞ ራሱ መንግሥት መሆኑን ላስተዋለ፣ መሬትን በተመለከተ በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጠውና የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ፖሊሲ እርስበርስ ሲጋጭ ይታየዋል። ከዛም አልፎ የሕጉና የፖሊሲው ዓላማ እንዲሁ በቀላሉ እንደተራ ነገር በትዝብት የሚያልፍ ጉዳይ አይደለም። ምክንያቱም መሬት ለኢትዮጵያውን መነሻ ካፒታል ብቻ ሳይሆን፣ የሕልውና ጉዳይም ነው። ነገር ግን አሁን የመሬት ጉዳይ ሌላ አብዮት የሚናፍቅ ጉዳይ የሆነ ይመስላል። አለበለዚያ በተለይ ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬት ያለባቸው አካባቢዎች፣ በከተማ የሚኖሩ ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች እንደሰው የመቆጠራቸውም ጉዳይ ጥያቄ የሚገባ ይመስላል። ምክንያቱም በከተሞች ያለው የመሬት የሊዝ ጨረታ ዋጋ እንኳን በወር ደመወዝ በተቋማት ተቀጥሮ የሚተዳደር ቀርቶ በቂ ገንዘብ አለው የሚባለውን ነጋዴውንም ቢሆን እጅግ የሚፈታተን ጉዳይ ሆኗል። ይህ ታቅዶ፣ ዓላማና ግብ ኖሮት የሚፈፀም ያልተጻፈ ፖሊሲ አካል እንጂ በድንገት እየተከናወነ ያለ የሚመስለው ካለ ተሳስቷል።

ከሊዝ ጨረታ ውጭ አዲሱ ትውልድም ሆነ ከዚህ በፊት የራሳቸው መኖሪያ ቤት የሌላቸው ዜጎች የከተማ መኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ የማግኘት ዕድላቸው ሙሉ ለሙሉ ከስሟል። በዚህ ምትክ መንግሥት ለፖለቲካ ፍጆታ የሚጠቀምበትን ኮንዶሚኒየም ቤት ደስ ባለው ሰዐትና ራሱ በተመነው ዋጋ ለዓመታት በተስፋ በመጠበቅ የከተሜው ነዋሪ ግዴታ መሆን ከጀመረ እነሆ 10 ዓመት አልፎታል።
በተለይ ከሊዝ አዋጅ በተያያዘ የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣ አዋጅ 721/2004 መሠረት አይደለም መሬት በሊዝ ጨረታ መግዛት በውርስ ያገኘው የቤተሰብ ንብረትም ሆነ በቀድሞ ስርዓት ሠርቶ የቤት ባለቤት የነበረ ሰው መንግሥት በፈለገው ጊዜ እንደሚያስነሳው፣ ካሣውን የሚተምነው ለተሠራው ቤት ጣሪያና ግድግዳ እንጂ ለመሬቱ እንዳልሆነ በግልጽ አስቀምጦታል።

በተለይ ከከተማ ቦታ ይዞታ ጋር በተያያዘ ቤት ያለአግባብ የፈረሰበት ወይም መብቱን የተነጠቀ ማንኛውም ግለሰብ በከተማ አስተዳደሮቹ ውሳኔ ቅር ቢሰኝ እንኳ ወደፍርድ ቤት ሄዶ አቤቱታ ማቅረብ አይችልም። ምክንያቱም የከተማን ቦታ በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ 721/2004 መሠረት፤ ከተማ አስተዳደሩ 5 አባላት ያሉት ራሱ ፖለቲከኛው የመረጠውና የሾመው የጉባዔ አባላት አቋቁሞ እንዲፈርድ ሥልጣን ሰጥቶታል። ለዚህም በአንቀፅ 30 (8-9) “ጉባዔው ሥራውን በሚያከናውንበት ጊዜ በመደበኛው የፍትሐብሔር ሥነ ስርዓት ሕግ አይመራም። ሆኖም በክልሉ ወይም በከተማ አስተዳደሩ በሚወሰን የተቀላጠፈ ሥነ ስርዓት ይመራል። የጉባዔው አባላት የሥራ ዘመን በክልሉ ወይም በከተማ አስተዳደሩ ይወሰናል” በሚል ያስቀመጠውን መረዳት ይቻላል።

በዚህ የሊዝ አዋጅ መሠረት፤ አንድ የከተማ አስተዳደር አካል የሆነና በፖለቲካ የተሾመ ሰው ከመሬት ይዞታ መፈናቀልና መብት ጋር በተያያዘ የትኛውንም በደል ወይም ጥፋት ቢፈፅም፤ ጉዳዩን የሚያየው ጥፋት የፈፀመው የአስተዳደር አካል የሾመው ሌላ የባለሥልጣናት ስብስብ “ጉባዔ” መሆኑ ችግሩን የበለጠ ውስብስብ ያደርገዋል። ይህም መሬት የስርዓቱ የፖለቲካ መቆመሪያ መሣሪያ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። ምናልባት ቤት ንብረት ኖሯቸው መንግሥት በፈለገው ሰዐት ለፈለገው ግለሰብ በስጦታም ይሁን በሊዝ ጨረታ መስጠት ቢፈልግ፤ ከይዞታዬ አልነሳም፣ የካሣ ክፍያውም ሆነ የተሰጠኝ ምትክ ቦታ (ዕድለኛ ሆኖ ከተሰጠው) በቂ አይደለም ቢል፣ አስተዳደሩ የፈለገውን ቤት በፖሊስ ኃይል እንዲፈርስ ማድረግ እንዲችል ሥልጣን ሰጥቶታል።

የመሬት ባለቤትነት መብት ችግር መፍትሔ

የመሬትና የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት የተለያዩ መፍትሔዎችን ማንሳት ይቻላል።
ሕገመንግሥቱ አንቀፅ 40 ላይ የዜጎችን የመሬት ንብረት ባለቤትነት መብትን የሚነጥቁ ድንጋጌዎች መሻሻል አለባቸው። የሚሻሻሉት ድንጋጌዎችም በማያሻማ መልኩ በግልጽ መቀመጥ አለባቸው። በተለይም መንግሥት፣ ሕዝብ፣ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሚሉ የቃላት ድርድሮች ልዩነታቸውና አንድነታቸው (ካላቸው) በግልጽ መቀመጥና መለየት አላስፈላጊ ድግግሞሽ ወይም የትርጉም አቻ ያላቸው ቃላት መወገድ አለባቸው። በመቀጠልም መሬት በነዋሪዎች ይዞታ ሥር ያለ የከተማም ሆነ የገጠር መሬት የንብረት ባለቤትነቱ ለራሱ ለግለሰቡ መሰጠት አለበት። መንግሥትም ሆነ የግል ባለሀብቶች የነዋሪዎቹን መሬት ለተለያየ ፕሮጀክቶች ቢፈልጉ በወቅቱ የመሬትና ተያያዥ የንብረት ዋጋ በቀጥታ ከግለሰቡ ጋር ተደራድረው መግዛት አለባቸው። በዚህም ነዋሪው መሬቱን እንደካፒታል በመጠቀም ይንከባከባል፣ ያለማል፣ ቢሸጥ እንኳ ምትክ ቦታ ገዝቶ ቀሪውን ገንዘብ እንደችሎታው የፈለገውን መጠነኛም ሆነ ዝቅተኛ ኢንቨስትመንት ማካሄድ ይችላል። ለዚህ ደግሞ በንብረቱ ላይ ራሱ እንዲወስን ሙሉ ሥልጣኑ ሊኖረው ይገባል።

በሕዝብ የተያዙ የገጠርም ሆነ የከተማ መሬቶች የንብረት ባለቤትነቱ የአካባቢው ነዋሪ ሕዝብ መሆን አለበት። የአካባቢው ነዋሪ ሕዝብ ሲፈልግ ለልጆቹ መዝናኛ አሊያም ለግጦሽም ሆነ ለሚፈልገው የልማት ፕሮጀክት ማዋል ይችላል። ምናልባት የአካባቢውን ክፍት መሬት መንግሥት ወይም የግል ባለሀብት የሚፈልገው ከሆነ በወቅቱ የመሬት ገበያ ዋጋ ከአካባቢው ነዋሪ ማኅበረሰብ ጋር ተደርድሮ መግዛት ይችላል። መሬቱን የሸጠው የአካባቢው ማኅበረሰብም ገንዘቡን ወደሌላ የገቢ ምንጭ እንዲቀይሩ መንግሥት በነጻ የማማከርና የሙያ ድጋፍ ማድረግ ይችላል፤ ካልሆነ ራሱ ማኅበረሰብ በባለሙያ አስጠንቶ የመረጠውን ሥራ ማከናወን እንዲችል መደረግ አለበት።

በግለሰብም ሆነ በማኅበረሰብ ያልተያዙ መሬቶች የንብረት ባለቤትነት መብቱ ለመንግሥት ቢሆን፤ መንግሥት ለግል ባለሀብቶችም ሆነ ለተለያዩ ማኅበራዊ ተቋማት ግንባታ ወይም ለመንግሥት የልማት ፕሮጀክቶች ማዋል ከፈለገ ተጠያቂነት ባለበት ሁኔታ ለሕዝብ ይፋ ተደርጎ ጥቅም ላይ መዋል አለበት። ነገር ግን ጥቅም ላይ የሚውሉ መሬቶች መጪውን ትውልድ ደኅንነትና የተሻለ ሕይወት ከግምት ያስገባ ሆኖ፣ ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነጻ በሆነ መልኩ ባለሙያዎች የአካባቢ ጥበቃና ማኅበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ጥናትና ምክር ቢያደርጉ፣ ሕዝቡ በሥራው ላይ በዕውቀት፣ በገንዘብም ሆነ በጉልበት ተሳታፊ እንዲሆን፤ ካልሆነ የሞራል ድጋፍ እንዲሰጥ መመቻቸት አለበት።

የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ መሻር ወይም መሻሻል አለበት። ምክንያቱም አዋጁ የግለሰብ የመሬት ንብረት ባለቤትነትን መብት ከመንጠቁ በተጨማሪ መንግሥት ከመደበኛው ሥራው ውጭ የመሬት ቸርቻሪ፣ ካድሬዎችን የሥልጣን መባለጊያ እና የሙስና ምንጭ፣ ለስርዓቱ የመጨቆኛ መሣሪያ፣ ሕዝቡን ደግሞ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ጥገኛ እንዲሆን አስችሎታልና።

ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶችን በርካሽ ዋጋ ለውጭ ባለሀብት መስጠት የሚያስከትለውን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ (የአገር ውስጥ የባንክ ብድር ወስደው ስለማይከፍሉ)፣ የማኅበራዊ እና የአካባቢ ጥበቃ ችግር ለመቅረፍ የአገሪቱ የሰው ሀብት ልማት ላይ ትኩረት መደረግ አለበት። በተለይ በአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች የሚማሩ የግብርና ሳይንስና ተያያዥ ባለሙያዎች በራሳቸው ፈቃድና ተነሳሽነት ተደራጅተው ዘመናዊ የግብርና ሥራን እንዲጀምሩ የባንክ ብድርን ጨምሮ የተለያዩ ድጋፎች ቢደረግላቸው። ምክንያቱም የአገር ውስጥ ባለሙያዎች በግብርና ምርትና ንግድ ዘርፍ ቢሰማሩ፣ የአገሪቱን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ በተጨማሪ የሥራ ዕድል በመፍጠርም ሆነ የውጭ ምንዛሪ በማስገኘት እንዲሁም ፕሮጀክቱን በሚያከናውኗቸው አካባቢ ያሉ ማኅበረሰብን ሕይወት ለማሻሻል እጅግ የተሻሉ ናቸው።

 

የከተማ ቦታን በሚመለከት መንግሥት ከመሬት ችርቻሮ ወጥቶ የመንግሥትን ሥራ ብቻ እንዲሠራ ቢደረግ፤ የከተማ ነዋሪዎች ራሳቸው አቅማቸው በፈቀደ መጠን በሚፈልጉት የሙያ ማኅበርም ሆነ መሥሪያ ቤት ወይም ተቋም ዘመናዊ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ሠርተው እንዲኖሩ መደረግ አለበት። መሬትም ከሊዝ ነጻ ቢመቻችና የመኖሪያ ቤት ግንባታን ሊያግዝ የሚችል በረጅም ጊዜ የሚከፈል የባንክ ስርዓትና ብድር ቢመቻች፣ መንግሥት ግንባታዎቹ የከተማውን ደረጃ በጠበቀ መልኩ አካል ጉዳተኞችን እና የአደጋ ጊዜ መከላከልን ታሳቢ ያደረጉ ግንባታዎች እንዲከናወኑ ወጥነት ያለው መመሪያ ቢያዘጋጅና መሠረተ ልማቶችን በማመቻቸት ብቻ ቢሳተፍ አሁን ያለውን እና ከዚህ በኋላ የሚኖረውን የቤት ችግር ለመቅረፍ ይረዳል። ከዛ በተጨማሪ በግላቸው ቤት መሥራት ለሚፈልጉና ለሚችሉ መንግሥት የግንባታ ደረጃዎችን በማውጣትና በተመጣጣኝ ዋጋ ነጻ መሬት ቢያቀርብ፣ መንግሥት ነጻ መሬት ማቅረብ ካልቻለ፣ ግለሰቦቹ ከሌሎች ነባር ነዋሪ ከሆኑ የመሬት ባለቤቶች ራሳቸው በቀጥታ ተደራድረው ገዝተው እንዲገነቡና እንዲኖሩ ቢደረግ ሁለቱም አካላት ተጠቃሚ ይሆናሉ።

መንግሥትም ከዜጎች በሚሰበስበው ግብርና በዜጎች ሥም ከሚያገኘው ብድርና ዕርዳታ የመሠረተ ልማትና ማኅበራዊ ተቋማትን በመገንባት ብቻ እንዲሳተፍ መደረግ አለበት። በግላቸውም ሆነ በማኅበር ተደራጅተው መሥራት ለማይችሉ በመንግሥት ድጎማ እንደየአቅማቸው እንዲደራጁና እንዲመዘገቡ በማድረግ ለግል የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች በጨረታ እንዲሠሩ ቢደረግ፣ የሚሠሩ ግንባታዎች ደረጃ ላይም ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ቢደረግ፣ የግል የመኖሪያ ቤት ግንባታ ተቋራጭ ድርጅቶች (ሪል ኢስቴቶችም) መሬት በመጠኛ ዋጋ እንዲያገኙ መደረግ አለበት። ድርጅቶቹም በወቅቱ ተመጣጣኝ የገበያ ዋጋ ለቤት ፈላጊዎች እንዲያስተላለፉ ቢደረግ፤ ለዚህም የቤት ግንባታን ብቻ ለማገዝና ለመደጎም የሚችል የባንክ ተቋምና ስርዓት ቢመሠረት ያለውን የቤት ችግር በቶሎ መቅረፍ ይቻላል። መንግሥትም የመኖሪያ ቤት ችግርን የፖለቲካ ፍጆት ከማድረግ ያግደዋል፤ የመንግሥት ግዴታ፣ ኃላፊነትና ተጠያቂነት በግልፅ እንዲሰፍን ያግዛል የሚል እምነት አለኝ።

በአዲስ አበባ አራዳ ፒያሳን ጨምሮ ከ10 ዓመት በላይ ታጥረው ምንም ዓይነት ግንባታ ያልተከናወነባቸው በርካታ ቦታዎች እያሉ የአቅማቸውን ያህል በከተማ ጥጋጥግ ጎጆ ቀይሰው የሚኖሩ ዜጎችን ክረምት ጠብቆ ለጎዳና ሕይወት መዳረግ በየትኛውም መመዘኛ ተገቢ ሊሆን አይችልም። ቢቻል በክረምት መኖሪያ ቤት አጥተው ለጎዳና ሕይወት የሚዳረጉትን መታደግ ሲገባ፤ በአዲስ አበባ ቦሌ ቡልቡላ እና ንፋስ ስልክ ላፍቶ በሁለት ወረዳዎች ብቻ 20 እና 30 ሺሕ ነዋሪዎችን ማፈናቀል ከሰብኣዊ መብትም ሆነ ከሞራል አንፃር የሚያስኬድ አይደለም። መንግሥት እየወሰደ ያለው ኃላፊነት የጎደለውን ተግባር ቆም ብሎ ማሰብ አለበት። ቤቶቻቸው ሕገ-ወጥ እንኳ ቢሆን ያለምትክ ቦታና ካሣ እንዲሁም ክረምት ጠብቆ ማፈናቀል የተሳሳተው የመሬት ፖሊሲ ውጤት መሆኑ መታወቅ አለበት።

ስርዓቱን ብቻ አምነው የሕዝቡን የመሬት ባለቤት መብትና ጥቅም ወደጎን በመተው የመሬት ቅርምቱ ላይ የሚሳተፉ የግል ባለሀብቶች ቆም ብለው ማሰብ አለባቸው። የስርዓት ለውጥ ቢኖርም ሆነ ያለው ስርዓት ቢቀጥል የሕዝቡ መብትና ጥቅም እስካልተጠበቀ ድረስ መዋዕለ ነዋያቸውን አፍሰሰው ለሚሠሩት ኢንቨስትመንት ዋስትና እንደሌላቸው መረዳት አለባቸው። ምክንያቱም ብዙ የተገፋ ሕዝብ በአንድ ሌሊት ተነስቶ የራሱን እርምጃ የማይወስድበት ምክንያት የለም። ስለዚህ ቢቻል በቀጥታ ከነዋሪው ካልሆነ የሕዝቡ መብትና ጥቅም መረጋገጡን ሳያረጋግጡ ሕዝብ በተፈናቀለበት የገጠርም ሆነ የከተማ መሬት ላይ ገንዘባቸውን ከመበተን ይልቅ ሕዝቡን ባሳተፈ፣ አሊያም የጋራ ተጠቃሚነትን መሠረት ያደረገ ፕሮጀክት ስለመተግበራቸው ቀድመው ቢገነዘቡ ይመከራል።

መንግሥት አሁን ከሚከተለው የመንገድ የተለየ መሻሻልም ሆነ የሕዝብን መብትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ ለውጥ ማድረግ ካቃተው ወይንም የመንግሥትን ሚና እና ግዴታ መለየት ከተሳነው ሥልጣኑን ለሕዝብ ማስረከብ ብቸኛው አማራጭ መሆን አለበት። አለበለዚያ አሁን በሚከተለው መንገድ የሚቀጥል ከሆነ ስርዓት በሕዝባዊ ኃይል መፍረስ ብቻ ሳይሆን አገሪቱን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ በመምራት ከፍተኛ ዋጋ ሊያስከፍል እንደሚችል መታሰብ አለበት።

የመሬት ሕጉም ሆነ ፖሊሲው መሻሻል አለበት፤ ካልሆነ ግን መንግሥት ገበሬዎችንም ሆነ የከተማ ነዋሪዎችን ማፈናቀሉ ይቀጥላል። ይህ ደግሞ በአገሪቱ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ላይ አለመረጋጋትን ይፈጥራል። ለዚህ ማሳያ ደግሞ በኦሮሚያ ያለውን ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ በአዲስ አበባ እንደክፉ ጠላት ክረምት ጠብቆ እየፈረሱ ያሉ መኖሪያ ቤቶችን ተከትሎ የሚፈጠረው ቅራኔ ምናልባት ቀኑን እንደነብይ መተንበይ ቢያስቸግርም፤ ወደሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች ተዛምቶ አዲስ የመሬት ባለቤትነት አብዮት ሊፈጠር ይችላል። ያኔ እንደዛሬው እየሳቁና እያስገደዱ፣ እንዳፈረሱና እንዳፈናቀሉ መቀጠል ላይቀል ይችላል። ምክንያቱም የመሬት ጉዳይ ለስርዓቱ የሥልጣኑ መሠረት እንደሆነ ቢታወቅም፣ ለሕዝብ ደግሞ የመኖርና ያለመኖር የኅልውና ጉዳይ ነው።

በአዲስ አበባ የኮሌራ በሽታ አስጊ ደረጃ ላይ መድረሱን የተባበሩት መንግሥታት የውስጥ መልዕክት ልውውጦች አጋላጡ

(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የአካባቢ ንፁህና ጉድለት ችግር ምክንያት ከተከሰተው አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) የከተማዋ ነዋሪዎችን ጤና ማናጋት ከጀመረ ሶስተኛ ሳምንቱን አስቆጥሯል፡፡ በንፁህ የውሃ አቅርቦት እና በአካባቢ ንፁህና ጉድለት ምክንያት የሚከሰተው የኮሌራ በሽታ በከተማው መዛመት፤ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሰራተኞችን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎችን ለከፋ በሽታ መዳረጉ ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በከተማዋ ለሚገኙ ለሌሎች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰራተኞች ባሰራጨው የውስጥ መልዕክት መሰረት፤ ሰራተኞቹ የኮሌራ ክትባት እንዲወስዱ አሳስቧል፡፡ በተለይ ኮሌራ በተበከለ ምግብና ውሃ አማካኝነት የሚዛመትና በንፁህና ጉድለት የሚከሰት በሽታ ሲሆን፤ ወዲያውኑ ተገቢውን ህክምና በጤና ተቋማት ማድረግ ካልተቻለ፤ በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የሰውነትን ፋሳሽ በመሳጣት ለሞት እንደሚዳርግ ይታወቃል፡፡

Addis-Ababa-Water-and-Sewerage-Authority

በሽታውን በተመለከተ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሀገር ቤት በመንግሥት ቁጥጥር ስር ለሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ፤ አተት የተከሰተው የወንዝ ውሃ በሚጠቀሙ ዜጎች ላይ እንደሆነ እና ለዚህም በወንዝ ዳር አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች የመፀዳጃ እና ፍሳሽ ማስወገጃዎቻቸውን ከወንዝ በማገናኘታቸው እንደሆነ በቃል አቀባዩ አህመድ ኢማኖ በኩል አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር የንፁህ የመጠጥ ውሃ ተገቢው ቁጥጥርና ክትትል ባለመደረጉ እና በከተማዋ በተከማቸው ቆሻሻ አማካኝነት እንደሆነ የከተማዋ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ምንጮች ማረጋገጣቸው ተነግሯል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የከተማው የንፁህ መጠጥ ውሃ ጥራት ባልተጠበቀበት ሁኔታ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የከተማው ነዋሪ በመጪው 2009 ዓ.ም. ከዚህ ቀደም ከሚከፍለው የቧንቧ ውሃ ተጨማሪ ክፍያ ማሻሻያ ሊጣልበት እንደሆነም ሪፖርተር ጋዜጣ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የአዲስ አበባ ደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃነት በ1 ቢሊዮን ወጪ በሰንዳፍ ተገንብቷል ቢባልም፤ ሰራ የተባለው ግንባታ ወጪ ከግንባተው ጋር አብሮ ሊድ እንዳይመችል የተጠቆመ ሲሆን፤ ይልቁንም በአካባቢው ያሉ የሰንዳፋ ነዋሪዎች ከአካባቢ ብክለት በሚመጡ በሽታዎች እንዲጋለጥ በማድረጉ፤ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በከፍተኛ ወጪ ተሰራ በሚባለው ሰንዳፋ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ እንዳይደፋ ተቃውሞና እገዳ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአዲስ አበባ አስተዳደር ለደረቅ ቆሻሻ መጣያ ባለመኖሩ መፍትሄ ባለማበጀቱ ከዚህም በኋላ አዲስ አበባን ለውሃና አየር ወለድ በሽታ ሊያጋልጥ እንደሚችል ተሰግቷል፡፡ የከተማው መስተዳደር ከሰንዳፋ ነዋሪዎች ጋር ቀደም ሲል ያለምንም ድርድርና ምክክር አለመገንባቱ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የጥራት ችግር ያለበት በመሆኑ ነዋሪውን ለበሽታ በማጋለጡና ተቃውሞ በመቅረቡ አስተዳደሩ ሌላ መፍትሄ እስኪያዘጋጅ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በየመንደሩ ባለበት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ ይህም ከወቅቱ የክረምት ዝናብ ጋር ተዳምሮ በቀላሉ ወደተለያዩ የከተማው ወንዞችና ጉዳት ወደደረሰባቸው የንፁሃ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች በመቀየጥ፤ አሁን ከተከሰተው የኮሌራ በሽታ በተጨማሪ ለተለያየ ውሃ ወደለድ በሽታ ሊያደርግ እንደሚችል የአስተዳደሩ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ባለሙያዎች ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡

እንደ ከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ ገለፃ ከሆነ፤ በከተማ እየሰሩ ባሉ መሰረተ ልማት እና የተለያዩ የግል ግንባታዎች ምክንያት በርካታ የንፁህ የመጠጥ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች ከጥቅም ውጭ ሆነው ከከተማ ፍሳሽ ማስወገጃ ጋር በመገናኘታቸው እንደሆነ እና ችግሩንም በአጭር ጊዜ ለማስተካከል አስቸጋሪ እንደሆነ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ አስታውቀዋል፡፡ ስለሆነም፤ ችግሩ እስኪቀረፍ የከተማው ነዋሪ አቅሙ የፈቀደ ከከተማው የባንቧ ውሃ ከመጠቀም ተቆጥቦ ሌሎች አማራጮችን አሊያም ውሃን በደንብ አፍልቶ በማቀዝቀዝ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡ በተጨማሪም፤ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ምልክት የታየባቸው ሰዎች በአስችኳይ በአቅራቢያቸው ወዳለ የህክምና ጣቢያ እንዲሄዱና ተገቢውን የህክምና ክትትል እንዲያደርጉ መክረዋል፡፡

በተከሰው የኮሌራ ወረርሽን በሽታ በርካታ ህፃናትና እናቶች ሰለባ ሆነው በከተማዋ ባሉ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ተኝተው ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በበሽታው ታመው የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ከሚገኙ የከተማው ነዋሪዎች በስተቀር ህይወታቸው ያለፈ ስለመኖሩ እስካሁን የተገረጋገጠ መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ መንግሥት በስታውን እና መንስዔውን ከመገናኛ ብዙኃን ለመደበቅ ቢሞክርም፤ ዓለም ተቋማት የሚሰሩትን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎች የችግሩ ሰለባ በመሆናቸው በየ ህክምና ተቋሙ የሚሰጡ ውጤቶች ላይ ኮሌራ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ እንዳይወጣ ያደረገው ጥረት በህክምና ባለሙያዎች ሊጋለጥ ችሏል፡፡ መንግሥት ችግሩን ለመሸፋፈን ከመሞከርና ከማስተባበል ባለፈ እየወሰደ ስላለው የማስተካከያ ርምጃ በግልፅ ያለው ነገር የለም፡፡