ወልቃይት ላለፉት ሺህ ዓመታት በትግራይ ስር ተዳድራ አታውቅም – የታሪክ ማስረጃዎች
(Ze Addis)
የኢትዮጵያ መንግስት (ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ) አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኋላ ከወሰዳቸው ዓብይ ኩነታት አንዱ፤ የሀገሪቱን የፖለቲካን የአስተዳደር ካርታን መቀየሩ እንደሆነ ይታወቃል:: የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገራት ካርታ እ.ኤ.አ. በ1994 ቢቀየርም፤ አዲሱ ካርታ ብዙ የማንነት ጥያቄዎችን አስነስቷል:: ይህ የዳግም መካለል ጥያቄ ከሚነሳባቸው ቦታዎች ውስጥ ወልቃይት አንዱ ነው።
እንዲህ አይነት የማንነትና የመካለል ጥያቄ ሲቀርብ ዋና መፍትሄ የሚሆኑት የታሪክ ሰነዶች ናቸው:: የታሪክ ሰነዶች ስለ ወልቃይት ግን ምን ይላሉ? ላለፉት ብዙ መቶ ዓመታት የተጻፉ የታሪክ ሰነዶች ምን እንደሚሉ እንመርምር::
1/ ወልቃይት ጠገዴና አላማጣ ኮረም በአጼ ዮሓንስ ዘመን በትግራይ ሥር አልነበሩም – የታሪክ ሰነድ ማስረጃ
አጼ ዮሓንስ ከ 1871 ዓ.ም እስከ 1889ዓ.ም (እ.ኤ.ኣ) ኢትዮጵያን የመሩ ንጉስ ናቸው:: ንጉሰ በንግሥና ዘመናቸው የራሳቸው ጠንካራና ደካማ ጎን ቢኖራቸውም፣ ከጠላት ደርቡሽ ጋር በመፋለም ለሀገራቸው ክቡር ሕይወታቸውን የሰጡ ንጉሰ ናቸው:: ጥቂት የማይባሉ የሕወሀት ሰዎች፣ ከወልቃይትና ጠገዴ ጋር በተያያዘም የሚጠቅሱት እሳቸውን ነው:: “ወልቃይት እና ጠገዴ ፣ ጥንት በአጼ ዮሓንስ ዘመነ መንስግት በትግራይ ስር ነበረች” በማለት እንደ ዋና መከራከርያ ሲያቀርቡት ይደመጣል:: እውነታውን የዘገቡት የታሪክ ሰነዶች ናቸውና የታሪክ ሰነዶችን እንመርምር::
በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረው የትግራይ ግዛትና፣ አጠቃላዩ የኢትዮጵያ ግዛት ምን እንደሚመስል በዝርዝር በሀገር ውስጥና በውጭ ሊቃውንት ተጽፏል:: ስለ ወልቃይትም አስተዳደር በማን ስር እንደነበረ በዝርዝር ጽፈውታል:: ለዚህም የእውቁን የፈረንሳዊ የጂኦግራፊ ፕሮፌሰር ኤሊስ ሬክለስ መጽሓፍን በዋቢነት መጥቀስ ይቻላል::
በዩንቨርሲቲ ኦፍ ብረስልስ የኮምፓራቲቭ ጂኦግራፊ (University of Brussels, Professor of Comparative Geography) ፕሮፌሰርና የዴፓርትመንቱ ሀላፊ የነበረው ይሄው ፕሮፌሰር ፤ በ1880 ጀምሮ በርካታ መጽሓፎችን በዓለም ጂኦግራፊ ላይ ጽፏል:: እነዚህም መጽሓፍቱ ከለንደንና ፓሪስ ጆኦግራፊካል ሶሳይቲ የወርቅ ሜዳሊያ ተሸላሚ አድርገውታል::
ከነዚህ መጻሕፍት አንዱ በ 1880 የተጻፈው The Earth and its Inhabitants የሚለው ሲሆን፤ ዘጠኝ ተከታታይ ክፍሎች አሉት። የዚሁ መጽሓፍ ክፍል አራት በገጽ 443 ላይ የሰሜን እና ምስራቅ አፍሪካን የወቅቱን ጂኦግራፊ በዝርዝር ይተነትናል:: በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረውንም የኢትዮጵያን ክፍላተ ሀገራት በዝርዝር ቁልጭ አድርጎ እንዲህ ጽፎታል::
“The Amhara government provinces are: Dembia, Chelga, Yantangera, Dagossa, Kuarra, Begemidir, Guna, Saint, Wadla, Delanta, Woggera, Simen, Tselemt, Armachiho,Tsegede, Kolla Wogerra፣ Waldiba and Wolkait”
Table – Tigray territories from the book – The Earth and its Inhabitants
ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት ይህ ጽሁፍ የተጻፈው በ1880ዎቹ አጼ ዮሃንስ የሀገሪቱ ንጉስ በነበሩበት ዘመንና የተጻፈውም በግዜው ከነበሩ ከተለያዩ የጂኦግራፊካል ሶሳይቲዎች የወርቅ ሜዳይ ተሸላሚ በሆነ ባለሙያ ፕሮፌሰር ነው:: ይህ በ1880ዎቹ የተጻፈው መጽሓፍ እንደሚያስረዳው በአጼ ዮሓንስ ዘመን ወልቃይት: ጠለምት : ዋልድባ : አላማጣ : በሙሉ በትግራይ ስር አልነበሩም:: እነዚህን ቦታዎች በስም ጠቅሶ እንደሚነግረን በትግራይ ስር ሳይሆን በጎንደር ስር ነበሩ::
“በአጼ ዮሓንስ ዘመን ወልቃይትና ጠግዴ በትግራይ ስር ስለነበሩ ነው አሁን ወደ ትግራይ የጠቀለልናቸው ” የሚለው መሰረት የሌለው መሆኑን ይሄ መረጃ ያሳየናል:: ከአጼ ዮሓንስ በፊትስ እነዚህ ቦታዎች ይተዳደሩ የነበሩት በማን ነው? የሚለውን እንመልከት። ወደ አጼ ቴዎድሮስ ዘመን እንጓዝ፡፡
2/ በኣጼ ቴዎድሮስም ዘመን ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች
በኣጼ ቴዎድሮስ (1818 – 1868 እ.ኤ.አ) የነበሩ ስመ ገናና ኢትዮጵያዊ ንጉስ ነበሩ:: በየቦታው የነበሩ መሳፍንትን አሸንፈው፣ ማዕላዊ መንግስት ከመሰረቱ በኋላ፣ ቀጣይ ራዕያቸው የምዕራብያውያንን ቴክኖሎጂ እዚሁ ኢትዮጵያ እንዲመረት ማድረግ ነበር:: ለዚህም ከበርካታ አውሮፓ ሀገራት ጋር ግንኙነት መስርተው ነበር:: የአውሮፓውያን ጥበበኞችን ኢትዮጵያ ለማስቀረት እና ጥብቅ ግንኑነት ለመመስረት፣ አጼ ቴዎድሮስ ልጃቸውን ለአንድ ስዊስ ኢንጂነር እስከመዳር ደርሰው ነበር:: በዚህም ምክንያት በርካታ አውሮፓውያን ጠቢባን በአጼ ቴዎድሮስ ዘመን ኢትዮጵያ መጥተዋል:: እነዚህም ባለሙያዎች ኢትዮጵያ መጥተው ስለ ሀገሪቱ በዝርዝር ጽፈዋአል:: የእንግሊዝ መንግስትና የኢትዮጵያ ግንኑነት መሻከር ሲጀምር፣ እንግሊዞች ስለኢትዮጵያ ይበልጥ የማወቅ ፍላጎታቸው ጨመረ::
የእንግሊዝ መንግስት የintelligence ሰዎችም የእንግሊዝ መንግስት ፓርላማና የጸጥታው ኃይል ኢትዮጵያን በሚገባ ያውቃት ዘንድ ትዕዛዝ ወጣ:: የእንግሊዙ Topographical and Statistical Department of The War Office ኤ . ሲ ኩክ (A. C. Cook) በተባለ እንግሊዛዊ ኮሎነል አማኻኝነት ስለ ኢትዮጵያ ከ15ኛው ክፍለ ዘመን ጀመሮ በተለያዩ እውሮፓውያን ተጻፉ መጻሕፍት ባንድ ላይ እንዲጠርዘ ተደረገ:: የሚደንቀው ይሄ መጽሓፍ በ 1867 ዓ.ም እ.ኤ.ኣ የታተመው በግስቲቷ ጥያቄ ለእንግሊዝ ሀውስ ኦፍ ኮመን ሎወር ሀውስ ግብአት (House of Common lower House) ይውል ዘንድ መሆኑ ነው:: በዚሁ መጽሓፍ ውስጥ፤ የወቅቱ የኢትዮጵያ ዝርዝር ጉዳይ ተጽፏል:: ይሄውም መጽሓፍ ስለ ወልቃይትና ጠገዴም በኣጼ ቴዎድሮስም ይሁን ከሳቸው በፊት በማን ስር ይተዳደሩ እንደነበር በዝርዝር ያትታል::
“The Provinces of Amhara are : Simen, Waldibba, Wolkait,Wogera,Chilga, Kuara, Belesa, Fogerra, Damot, Gojjam, Begemidir, Beshilo ….. Waldiba situated to the NW of Semein between the Tekeze and the Angereb, extends as far as the junction of the two rivers. Welkait is to the west Of Waldiba it is intersected through its whole length by the two river tekuar and guang. It is more wooded than waldiba..” (Routes in Abyssinia (printed in 1867 G.C) page 188)
ይሄው ታሪካዊ መጽሓፍ በወቅቱ የነበረውንም የትግራይ ክፍለሀገር ድንበር እና ግዛት እነማን እንደነበሩ በማያሻማ ቋንቋ እንዲህ ይነግረናል፡፡
“The territory of Tigre whose capital is Adwa, is bounded on the West by Shire, on the Southwest by Temben and Adet on the South by Geralta on the South –East by Haramat, on the East by Agame, and on the North by the rivers of Mereb and Belessa”
የትግራይ ግዛትስ? ብሎ ለሚጠይቅ ወገን ፤ ይሄው መጽሓፍ በወቅቱ የነበርቸው ትግራይ ምን እንደምትመስል እንዲህ ሲል አስፍሮታል በዚሁ መጽሓፍ ላይ ገጽ 187 – 188 የትግራይን ግዛት እንዲህ ሲል ይገልጸዋል
“The territory of Tigray whose capital is Adwa is bounded on the west by Shire, on the south west by Temben and Adet, on the south by Geralta, on the South East by Haramat, on the East by Agamae, and on the North by the Rivers Mereb and Belessa”
Map – northern Ethiopia areas
እዚህ ላይ በ 18ተኛው ክፍለ ዘመን የትግራይን ወሰኖች በማያሻማ ሁኔታ በግልጽ አስቀምጦታል:: የትግራይ ወሰን በምዕራብ – ሽሬ ፤ በምዕራብ ደቡብ – ተምቤን እና አዴት ፤ በደቡብ – ገር አልታ ፤ በምስራቅ – አጋሜ ፤በሰሜን – መረብና በለሳ ናቸው:: የታሪክ ሰነዶች በአጼ ቴዎድሮስም ዘመን እንደሚነግረን ፤ ወልቃይትና ጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም::
ከዛስ በፊት ወልቃይትና ጠገዴ በትግራይ ስር ነበሩን? አሁንም የታሪክ ሰነድ እንመርምር::
3/ በዘመነ መሳፍንት ዘመንም ወልቃይትጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች
እንደሚታወቀው ከአጼ ኢዮአስ ሞት ጀምሮ ፤ አጼ ቴዎድሮስ እስኪነሱ የነበረው ዘመን ዘመነ መሳፍንት ይባላል:: በዚህ ዘመን ኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግስት አልነበራትም:: መሳፍንቶች የገነኑበትና በሀገሪቱ ማዕከላዊ አስተዳደር የጠፋበት ዘመን ነበር:: በዚህ ማዕከላዊ የመንግስት ሕግ በሌለበት ወቅት እንኳን ወልቃይት፥ጠገዴ፥ ዋልድባ ፥ አላማጣ፥ ኮረም እና የመሳሰሉ ቦታዎች በትግራይ ስር አልነበሩም:: አሁንም ማስረጃ እነሆ!
ጀምስ ብሩስ የተባለው ስኮትላንዳዊ ፥ በዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያ መጥቶ ኢትዮጵያ በዘመነ መሳፍንት ምን ትመስል እንደበረ፥ ቁልጭ አድርጎ አስቀምጦታል:: እያንዳንዱ መስፍን ግዛቱ የት ድረስ እንደነበረ፥ የትኛው መስፍን ማንን ይገዛ እንደነበረ በሰፊው ተንትኖታል:: በዚህም መሰረት ስለ ትግራይ ግዛትና እንዲህ ሲል ምስክርነቱን ይሰጣል :: Travel to discover source of the Nile Volume 3 page 582 ላይ
“Tigre is bounded by the territory of the Bahirenegash that is by the river Mereb on the East and Taccazze upon the west. It is about one hundred and twenty miles broad from E. to W. and two hundred from N. to S. “
ጀምስ ብሩስ በዚሁ መጽሓፉ Chapter 10 ላይ Geographical division of Abyssinia into province በሚለው አንቀጹ ላይ በይበልጥ ቁልጭ አድርጎ እንዲህ ያስቀምጠዋል
The first division is called Tigre, between Red Sea and the river Tekeze. Between that River (Tekeze) and the Nile Westwards where it bounds the Oromo, it is called Amhara.
ካለ በኋላ ወረድ ብሎ ይበልጥ ጉዳዩን ሲያስረዳ “Tekezze is the natural boundary between Tigre and Amhara”
ከላይ ለአብነት ያስቀመጥኳቸው ሊቃውንት በግዜ፣ በቦታና በዜግነት አይገናኙም:: ለምሳሌ በአጼ ዮሓንስ ዘመን የነበረው አሊስ ሬክለስ ፈረንሳዊ (French) ነው:: በአጼ ቴዎድሮስ ዘመን የነበረውን የኢትዮጵያ ግዛት የጻፈው ደግሞ እንግሊዛዊ ነው (British):: ጀምስ ብሩስ ደግሞ ስኮትሽ (Scottish)ነው:: ግን ሁሉም በተለያየ ግዜ መጥተው ያዩትና የተገነዘቡትን ጽፈዋል:: የሚናገሩት አንድ ና ተመሳሳይ ነው:: እውነት ምን ግዜም አንድ ናትና!
4/ ወልቃይት በ1630ዎቹስ በማን ስር ነበረች?
በ16ኛው መቶ አጋማሽ ላይ ያሉ ያታሪክ መዛግብትም የሚናገሩት ተመሳሳይ ነገር ነው:: በተለያዩ ወገኖች ተደጋግሞ የሚጠቀሰው የ ማኑኤል በሬዳም መጽሓፍ የሚተነትነው ያንኑ ነው:: ይሄ መጽሓፍ የተጻፈው በ1634 ሲሆን ጸሓፊውም ኢማኑኤል በሬዳ ይባላል:: በወቅቱ የነበረውን የትግራይ ግዛት በዝርዝር አስቀምጧል:: እሱም እንደሌሎቹ ጸሓፍት የትግራይ ድንበር ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ ናቸው አይልም::
«Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634» መጽሀፍ የመጀመሪያ ምዕራፍ ስለ ትግራይ ግዛት እንዲህ ይላል::
“Among all the kingdoms that the Emperor of Ethiopia possesses today one of the greatest if not the greatest and the most important is the kingdom Tigre. From north to south, that is from the limits of the Hamasen to Enderta, it covers an areas of from ninety to one hundred leagues (3.2 miles); and from the east, which is besides Dancali, located at the entrance to the Red sea to the southern end of the Red Sea, to the west bounded by the Tekezze River beside the Semen, it covers an area of similar size, so that the Kingdom has a nearly circular shape.”
አሁንም ወደኋላ እየራቅን እንሂድና ወልቃይት ጠገዴ በነ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመን በማን ስር ነበርች? የሚለውን እንመልከት
5/ በኣጼ ዘርዓ ያዕቆብ ( 14ኛው ክፍለ ዘመን) ዘመንም ወልቃይትጠገዴ በትግራይ ስር አልነበሩም – የታሪክ ማስረጃ ሰነዶች
አጼ ዘርዓ ያዕቆብ በኢትዮጵያ ታሪክ ከተነሱ ሃያልና ሊቅ ነገስታት ውስጥ አንዱ ነበሩ:: በቀድሞ ስሙ ፈጠጋር በአሁን ስሙ ኦሮሚያ አዋሽ ወንዝ አካባቢ የተወለዱት አጼ ዘርዓ ያዕቆብ፥ የሀድያ ሲዳሞ ንጉስ ልጅ የሆነችውን እሌኒን አግብተው፥ በ37 ዓመታቸው ከነገሱ ጀምሮ በርካታ ዓበይት ስራዎችን አከናውነው አልፈዋል:: እኒሁ ንጉስ ከፍተኛ የጥበብ ፍቅር የነበራቸውና ከመሆናቸው ባሻገር፥ ራሳቸው ብዙ መጻሕፍትን ጽፈዋል:: በሳቸው ዘመንም ብዙ መጻሕፍት እንዲጻፉ ድጋፍ በመስጠታቸው አያሌ መጻሕፍት በሳቸው ዘመን ተጽፈዋል:: ከነዚህ መጻሓፍት አንዱ በአክሱም ንቡረ ዕድ የተጻፈው ዜና አክሱም መጽሃፍ አንዱ ነው:: ዜና አክሱም ከሃይማኖያትዊ ሐተታው ባለፈ ስለ 14ኛዋ ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ በዝርዝር ጽፎታል:: ይህ መጽሓፍ የኢትዮጵያን አጠቃላይ ወሰንና ታሪክ ብቻ ሳይሆን የክፍላተ ሀገራቱንም ድንበር ጥንቅቅ አድርጎ ዘግቦታል:: የትግራይንም ክልል በካርታና በጽሁፍ ከዚህ እንደሚከተለው ይገልጸዋል::
Chart – List of Tigrai areas on Zena Axum book
ይህም መጽሓፍ በተመሳሳይ መልኩ የሚነግረን፣ ወልቃይትና ጠገዴ በፍጹም ፣ የትግራይ አካል አንዳልነበሩ ነው::
ዮሓንስ መኮንን Ethiopia: the land, its people , History and Culture በሚለው መጽሓፉ Page 351 በአጼ ዘርዓ ያ ዕቆብ ዘመነ መንግስት የነበረውንና በመጽሓፍ አክሱም የተተነተውን የትግራይን ካርታ እንዲህ ያቀርበዋል
“The Book of Axum.. Shows a traditional schematic map of Tigray with its city Axum at its center surrounded by the thirteen principal provinces: Tembein, Shire, Seraye, Hamasen, Bur, Sama, Agame, Amba Senait, Geralta, enderta, Sahart and Abergele”
በተመሳሳይ ሁኔታም The World through Maps: A History of Cartography (ገጽ 352 ይመልከቱ)፡፡ በJohn R. Short የተጻፈው የዓለም ጂኦግራፊን የሚተርከው መጽሓፍ በ15ኛው ክፍለዘመን የነበሩ የትግራይ ግዛቶች ከላይ የተጠቀሱት መሆናቸውን መጽሓፈ አክሱምን በመጥቀስ ያስረዳል:: ይህም መጽሓፍ በተመሳሳይ መልኩ የሚነግረን፣ ወልቃይትና ጠገዴ በፍጹም የትግራይ አካል አንዳልነበሩ ነው::
6/ ቋንቋን መሰረት ወዳደረገ ክለላን አንመልከት
የኢትዮጵያውያን ወጣቶችና አርበኞች ቁጣ ያሳሰበው ጣልያን፣ ኢትዮጵያን በቋንቋና በዘር በትኖ ለመግዛት ያቀደውን መርዝ ይፋ አወጣ:: የዚህ እቅድ ፊታውራሪ ከሆኑት አንዱ ፋሺስቱ Baron Roman Prochàzka አቢሲንያ ዘ ፓውደር ባረል (Abyssinia: the Powder barrel) በሚል መጽሓፉ ላይ እንዳስቀመጠው፣ ኢትዮጵያውያንን ለመግዛት በዘር መከፋፈልና በመሀከላቸውም ጥላቻን በመዝራት እርስ በርስ ለማናከስ፣ ሀገራቸውን በዘር መከለል የሚለውን እቅድ መተግበር ጀመረ:: በዚሁም መሰረት፣ ዘርንና ቋንቋን መሰረት ባደረገ ሽንሸና ኢትዮጵያን አምስት ቦታ ከፈላት::
እነዚሁም ክልሎች አማራ: ኤርትራ(ትግሬ); ሐረር: ኦሮሞ-ሲዳማ: ሸዋና ሶማሌ ናቸው:: ጣልያን ይሄንን የግዛት ሽንሸና ሲያካሂድ መሰረት ያደርገው ዘርና ቋንቋን ነበር:: የሚከተለውም ሰማንያ በሃያ የሚለውን መርህ ነበር:: ከሰማንያ በመቶ በላይ ሕዝቡ የሚናገረውን ቋንቋ መሰረት በማድረግ ወደየ ክልሉ ይደለደላል:: ሸዋን ግን ለብቻው ለይቶ መቆጣጠር ይገባል ብሎ በማመኑ ሸዋን ና ሀረርን ለብቻ ለይቶታል:: ወደ ነጥባችን ስንመጣ በዚህ የቋንቋ ሽንሸና መሰረት ወልቃትና ጠገዴና ጠለምት ወደ ትግራይና ኤርትራ አልተካተቱም:: በጎንደር ስር ነበሩ::
እዚህ የጣልያን ቋንቋንና ዘርን መሰረት ያደረገ ካርታ ላይ በግልጽ እንደሚታየው ፣ የትግራይ ድንበት ተከዜ እንጂ – ከተከዜ ተሻግሮ አይደለም:: ላልፉት 25 ዓመታት ተቃዎሞ ሲካሄድባቸው የከረሙት ወልቃይት – ጠገዴ – አላማጣ ኮረም በፍጹም በትግራይ ስር እንዳልነበሩ በግልጽ ያሳየናል::
Map – Tigray during Fascist Italy
7/ አንዳንድ ሚድያዎች ደጋግመው የሚያነሱት ነጥብ አለ:: ይሄውም ወልቃይት ጸገዴና ሌሎች ወደ ትግራይ የተካለሉ ቦታዎች ጥንት የትግራይ እንደነበሩና አጼ ኃይለ ሥላሴ የምስራቃዊ ትግራይ ገዥ ከነበሩት ከደጃዝማች ኃይለሥላሴ ጉግሳ አርዓያ ጋር በመጣላታቸው – ወልቃይትና ጠገዴን ወደ ጎንደር ወሰዱት የሚል ነው:: ሌላው የማያስማማው ነጥብ ደግሞ – የቀዳማይ ወያኔን አመጽ ምክንያት በማድረግ ትግራይን ለመቅጣት – ወልቃይትንና ጠገዴን ወደ ጎንደር ከለሉት የሚል ነው::
እስካሁን ከላይ የገለጽኳቸው ሰነዶች ለዚህ ነጥብ በቂ ማስረጃ ቢሆኑም : ካርታን መሰረት ያደረገ መረጃ ለሚጠይቅ ሰው – እነሆ:: ይህ ካርታ በጣልያኖች በ1928 ዓ.ም የተሰራ ነው:: ኢትዮጵያን በደምብ ካጠኑ በኋላ ለያንዳንዱ ክፍለሀግር ካርታ ሰርተዋል:: ያኔ ገና ኃይለሥላሴ ጉግሳ አልከዳም:: ያኔ የቀዳማይ እንቅስቃሴ አልነበረም:: የቀዳማይ እንቅስቃሴ በ1943 ነበር፡፡ ይህ ካርታ ግን ከዛ ብዙ ዓመታት በፊት የተሰራ ነው:: አንባቢው አይቶ ይፍረድ:: ወልቃይት ጠገዴን ነጥለን ስንመለት ካርታው ይሄንን ይመስላል::
Map – north west Ethiopia in 1928
8/ በዘመነ መንግስቱ ኃይለማርያም ወልቃይትና ጠገዴ
በካምብሪጅ ዩንቨርሲቲ በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ ይበልጡንም በኢትዮጵያ ታሪክና ፖለቲካ ላይ ከፍተኛ ምርምር ካደሩት ሰዎች ውስጥ በዋነኝነት የሚጠቀሱት ፕሮፌሰር ክሪስቶፈር ክላፓም: እንደ ኤሮፓ አቆጣጠር 1990 ( ህወሀት አዲስ አበባብ ከመያዙ አንድ አመት በፊት) ድንቅ የሆነ መጽሓፍ አሳትመው ነበር:: በዚሁ መጽሓፋቸው ላይም ስለ ወልቃይትና ጠግዴ እንዲህ ሲሉ ይተርኩታል
“the area concerned (welkait -Tsegede) separated from Tigray by impressive natural barrier of Setit Tekezze river has never been governed as part of Tigray at any period in the past, but has come under Gonder and Semein.” (Christopher Clapham: Transformation and continuity in revolutionary Ethiopia (Cambridge: Cambridge university press 1988 pp 259)
ስናጠቃልለው
1. 1420ዎቹ እንደተጻፈ የሚታመነው መጽሓፈ አክሱም በግልጽ እንደሚያሰረዳን የትግራይ ግዛቶችና ወሰኖች 13 ነበሩ:: እነርሱም Tembein, Shire, Seraye, Hamasen, Bur, Sama, Agame, Amba Senait, Geralta, enderta, Sahart and Abergele ናቸው::
ማስረጃ : መጽሓፈ አክሱም , Ethiopia: the Land, Its People, History and Culture By Yohannes Mekonnen. The World through Maps: A History of Cartography (ገጽ 352 ይመልከቱ) By John R. Short
2. 1634 ዓ.ም የተጻፈው የ እማኑኤል በሬዳ መጽሓፍ Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634» እንደሚያስረዳው የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ አይደሉም
3. በዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያን ጎብኝቶ የነበረው የጀምስ ብሩስ መጽሓፍም በግልጽ የሚናገረው የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠገዴ አይደሉም፡፡ Travel to discover source of the Nile Volume 3 page 582
4. በአጼ ዮሓንስ ዘመንም የታሪክ ማስረጃዎች የሚያስረግጡት ያንኑ ነው:: የትግራይ ደንበር ተከዜ ነው:; ወልቃይትና ጠገዴ በጎንደር ስር እንደነበሩ በግልጽ ፈረንሳዊው ፕሮፌሰረ ሬክለስ ጽፎታል
5. በአጼ ቴዎድሮስ ዘመንም ወልቃይትም ይህን ጠግዴ በትግራይ ስር አልነበሩም::
6. በጣልያን ግዜም የትግራይ ወሰን በደቡብ እንዳምሆኒ, በደቡብ ምስራቅ አበርገሌ ;በም ዕራብ ሽሬና አዲያቦ ነበሩ እንጂ ወልቃይት ጠግዴ ዋጃ ኮረም እና መሰል ቦታዎች በትግራይ ስር አልነበሩም
7. ወልቃይትንና ጠገዴን ወደ ትግራይ የከለሉት አጼ ኃይለሥላሴ ናቸው:; ይህም በ1943 ዓ.ም የተካሄደውን የቀዳማይ ወያኔን አብዮት ለመበቀልና ሕዝቡንም ለመቅጣት ነው የሚለው: መሰረት እንደሌለው እነሆ ይህ ማስረጃ:: ጣልያን ይሄን ካርታ የሰራው በ1928 ዓ.ም ነበር:: ያኔም በአጼው ግዜም የትግራይ ወሰን ያው ነበር
8. የህዝብ ቁጥርና በሚነገሩት ቋንቋ ነው ወልቃይትንና ጠግዴን ወደ ትግራይ የከለልነው ለሚለውም – የዘርና የቋንቋ ክልልን ለመጀመርያ ግዜ ኢትዮጵያ ላይ የመሰረተው ጣልያን ነው:: ጣልያን ይህን ካርታ ሲሰራ የራሱን የዘርና የቋንቋ ጥናት አድርጎ ነበር:: በዚህም መሰረት ወልቃይትና ጠግዴን ወደ ትግራይ ሳይሆን ያካለላቸው ወደ ጎንደር ነበር:: ይሄ ከሆነ አንድ ትውልድ እንኳን አላለፈው:: ታድያ ያኔ አብላጫ የነበረው ቋንቋና ሕዝብ አሁን ወዴት ገባ?
9. በዚህ ዘመን ያሉ እውቅ የኢይዮጵያ ነክ ፕሮፌሰሮችም ምስክርነታቸው ያው ነው:: የካምብሪጅ ዩኒቨርስቲው ክሪስቶፈር ክላፕማን እንዳጠቃለሉት
“the area concerned ( welkait -Tsegede) separated from Tigray by impressive natural barrier of Setit Tekezze river has never been governed as part of Tigray at any period in the past, but has come under Gonder and Semein.
10. የአጼ ዮሓንስ የልጅ ልጅ ልዑል ራስ መንገሻ ስዩምም እንዳረጋገጡት ” የትግራይ ወሰን ተከዜ እንጂ ተከዜን ተሻግረው ያሉት ወልቃይትና ጠግዴ አይደሉም”
አሁንም ቢሆን የወልቃይት የማንነት ጠያቂዎች የ ሃምሳ ሺህ ሰው ፊርማ አሰባስበው ነው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ የሄዱት:: እንግዲህ ይሄ ሁሉ ጫና: ወከባና ግድያ ባለበት በዚህ ወቅት ሃምሳ ሺህ ሰው ፊርማ ማሰባሰብ ከቻሉ ነጻነት አግኝተው ሁሉም ቦታ ቢንቀስቀሱ የምን ያህል ሰው ፊርማ ማሰባሰብ እንደሚችሉ መገመቱ ቀላል ነው:: ያለው እውነታ ይሄው ነው::
ማጠቃለያ
አሁንም ከላይ የጠቀስኳቸውን የፕሮፌሰር ክላፕማንን ቋንቋ ልጠቀምና ” ወልቃይትና ጠግዴ በኢትይኦጵያ ታሪክ በትግራይ ስር ሆነው አያውቁም”:: ለመጀመርያ ግዜ በትግራይ ስር : እንዲካተቱ የተደረገው በ1994 ነው::
እኔን የሚያሳሰበኝ ግን ሌላ ነው:: በአንድ ሀገር ውስጥ ሆነን ስለ ድንበር እያወራን ነው:: ከዚህ የማንነት ጥያቄም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች መገደላቸውን የሰባዊ መብቶች ጉባኤ አሳውቋል:: ወዴት እየሄድን ይሆን?
———–
ዋቤ መጻሕፍትና ሊንኮች
1. ‘ልዝብን ምኽሪን ጥራሕ’ያ መድሓኒታ’ ኢሎም ዶ/ር ገላዴዎስ ኣርኣያ
2. The Earth and its Inhabitants, Africa: South and east Africa, by Elisée Reclus 1890
3. Routes in Abyssinia (printed in 1867 G.C)
4. Travels to Discover the Source of the Nile: In the Years 1768 …, Volume 3. By James Bruce
5. Tractatus tres historico-geographici (1634): A seventeenth century historical and geographical account of Tigray, Ethiopia (Aethiopistische Forschungen) 1634
6. Ethiopia: the Land, Its People, History and Culture, By Yohannes Mekonnen
7. Christopher Clapham: Transformation and continuity in revolutionary Ethiopia (Cambridge: Cambridge university press 1988 pp 259
8. The World through Maps: A History of Cartography : John R Short
9. https://archive.org/details/liberaxumae00pari (the Book of Axum part one)
10. Library of Congress የኢትዮጵያ ካርታ 1955 ዓ.ም (በ1963 እ.ኤ.ኣ)
11. የኢትዮጵያ ካርታ 1966 ዓ.ም (በ1974 እ.ኤ.ኣ ወይም) Library of Congress
12. Library of Congress የኢትዮጵያ ካርታ 1979-81 ዓ.ም
13. በ1928 ዓ.ም ( 1933 እ.ኤ.አ) ጣልያን የሰራው የኢትዮጵያ ካርታ
14. በ1928 ዓ.ም (1933 እ.ኤ.አ) ጣልያን የሰራው የኢትዮጵያ ካርታ
15. CIA maps 1961 E.C and 1969 G.C
Source:- http://hornaffairs.com/am/2016/06/08/tigray-wolkait-historical-accounts
ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
• ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች ነው
• አዳም የተፈጠረው ጎጃም፤ ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው
• ስለ ኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አጥንቼ አለሁ ይላሉ …
ኑሮአቸውን በአሜሪካ ያደረጉት ታዋቂው የሥነፅሁፍ ምሁር ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ፤ የፃፉት‹‹የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ›› የተሰኘ አዲስ አነጋጋሪ የታሪክ መፅሐፍ ዛሬ ለገበያ ይቀርባል፡፡ የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ ማን እንደሆነ በጥናት ደርሼበታለሁ የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ እስከ ዛሬ የተለያዩ የታሪክ ምሁራን ከተናገሩት ፍፁም የተለየና አዲስ የጥናት ውጤት ማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ የሁለቱ ቋንቋዎች አመጣጥም በጥናቱ ተካቷል ብለዋል፡፡ በሊንከን ዩኒቨርሲቲ በሂዩማኒቲስ የትምህርት ዘርፍ የሚያስተምሩት ፍቅሬ ቶሎሳ ፤ከዚህ ቀደም ‹‹Heaven to Eden›› እና ‹‹The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉ መጽሐፍትን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሙ ሲሆን ሁለቱም በኢንተርኔት
“አማዞን” በተባለ የመፅሃፍ ሽያጭ ድረገፅ ላይ ከተፈላጊ መፃህፍት ተርታ ተሰልፈዋል፡፡ በሙያቸው
ፀሃፌ-ተውኔትና የሥነ ፅሁፍ ምሁር ሲሆኑ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥልቅ ጥናትና ምርምሮችን
በማድረግም ይታወቃሉ፡፡
አንጋፋው ምሁር ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም በቅርቡ ለንባብ ባበቁት
“አዳፍኔ” የተሰኘ መፅሃፋቸው ላይ፤“የኦሮሞን ታሪክ ሙሉ አደርጎ ሊፅፍ የሚችለው ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ ብቻ ነው” ሲሉ ለብቃታቸው ምስክርነትና ዕውቅና መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡ ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በርካታ ቲያትሮችን ለደረክ ያበቁ ሲሆን ከእነዚህም መካከል “ጓደኛሞቹ”፣ “ፍቅር በአሜሪካ” እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ በቅርቡም ‹‹ላሟ›› የተሰኘ ባለ ሁለት ገቢር ቲያትር ፅፈው ማጠናቀቃቸውንም ተናግረዋል፡፡ ፕሮፌሠሩ ለአጭር ጊዜ ዕረፍት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የነበረ ሲሆን ወደ አሜሪካ ከመመለሳቸው በፊት ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በታሪክ ጥናቶቻቸው ዙሪያ ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡
በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሟቸው “Heaven to Eden” እና “The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉት መፃህፍት በአለማቀፍ ደረጃ ሰፊ ተቀባይነት ያገኙበት ሚስጥር ምንድነው? በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነው የሚያተኩሩት?
የመፅሐፍቱ ይዘት ነው ወሳኙ፡፡ ተቀባይነት ያገኙት በቋንቋ አጠቃቀም ለአንባቢያን ምቹ ስለሆኑ ይመስለኛል፡፡
በአይሁዶች ታሪክ ላይ የሚያተኩረው መፅሐፍ፤በጉዳዩ ላይ ከተጻፉ ሌሎች መጻህፍትና በተለምዶ ስለ አይሁዶች ከሚታወቀው ምን የተለየ ነገር ይዟል?
ብዙ ጊዜ ስለ አይሁዳውያን ሲወራ፣ቀዳማዊ ሚኒልክ የዛሬ 3ሺህ ዓመት፣ 40ሺህ አይሁዳውያንን ይዞ መጣ የሚለውን ነው የምናውቀው፡፡ ከመጡት መካከል 12ሺህ ያህሉ ንፁህ እስራኤላውያን ናቸው። 28ሺህ ያህሉ እነሱን በሥራ ያገለግሉ የነበሩ ኢያቡሳውያን የሚባሉ ነገዶች ናቸው፡፡ ቀዳማዊ ሚኒልክ ለ12 ሺህዎቹ ልዩ ቦታ ሰጥቷቸው፣ በሀገሪቷ ላይ ካህናት አድርጎ ታቦት እያስቀረፀ፣ ኢትዮጵያ ላይ በዚህ መልክ ሾሟቸው ነበር፡፡ ኢያቡሳውያን ደግሞ ንጉሱን በእጅ ስራና በውትድርና ያገለግሉት ነበር፡፡ ይሄ እንግዲህ አይሁዳውያን ወደ ኢትዮጵያ ያደረጉት ሁለተኛው ፍልሰት ነው፡፡
የመጀመሪያውና ብዙም የማይነገረው የአይሁዳውያን ፍልሰት፣ የእስራኤላውያኑ መሪ ሙሴ በህይወት እያለ አባ ብሄር የሚባል ልኡል ነበር። የሙሴ አማች ነው፡፡ አባ ብሄር የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ሊሆን ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣አይሁዳውያን ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡ ምክንያቱም አባ ብሄር ያገባት ልጅ የሙሴ እህት ነበረች፡፡ ሙሴ በወቅቱ ለአባ ብሄር ፅላት ቀርፆ እንዲሁም ቀይ ባህርን የከፈለባትን በትር ሰጥቶት፣ወደ ሳባ ከተማ መጥቶ ነግሷል፡፡ በወቅቱ ብዙ አይሁዳውያንም ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡
ሶስተኛው ፍልሰት የምንለው፣የኢራቁ ናቡከደነፆር አሸንፏቸው በሚያሳድዳቸው ጊዜ፤ “ኢትዮጵያ ውስጥ አይሁዳውያን ወገኖች አሉን” ብለው ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡ አይሁዳውያን በነዚህ መንገዶች ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡
ትክክለኛዎቹ አይሁዳውያን በኢትዮጵያ ያሉት ናቸው የሚሉ ወገኖች አሉ…?
የሃይማኖታቸውን ስርአት፣ መፅሃፍትና ህግጋት ከመጠበቃቸው አንፃር ከሌላ ህዝብ ጋር ስላልተደባለቁ ትክክለኛው ያለው እነሱ ጋ ነው፡፡ ሌሎቹ ወደ አውሮፓ፣ እስያ፣ አሜሪካ የተሰደዱት እነዚህን ነገሮች በተለያዩ ጫናዎች የተነሳ ሙሉ ለሙሉ ጠብቀው አላቆዩትም፡፡ ወደዚህ የመጡት ግን በግድ ባህላችሁን ሃይማኖታችሁን ለውጡ ተብለው በኢትዮጵያውያን አልተረበሹም፤ነፃነት ነበራቸው፡፡ መሬትና ሁሉ ነገር የተመቻቸላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነበር፡፡ ሌላ አገር ላይ ቦታ እንዳይኖራቸው ተደርገው በየጊዜው ይሰደዱ ነበር፡፡ እንደውም በሩሲያ ውስጥ በድንገት አይሁዳውያንን የመግደል ድርጊት ይፈፀም ነበር። ሩሲያውያኑ ተሰባስበው፤“ዛሬ አይሁዳውያንን ገድለን እንምጣ” እያሉ ይዘምቱባቸው ነበር፡፡ ወደ መንደራቸው ሄደው አውድመዋቸው ይመለሳሉ፡፡ ማንም ስለማይበቀልላቸው ደማቸው ደመ ከልብ ሆኖ ነበር የሚቀረው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ከተሰጣቸው ክብር የተነሳ በትንንሽ ንጉስነት ጭምር ይሾሙ ነበር፡፡ በርካቶቹም ካህናትና ሊቀ-ካህናት ተደርገው ለአይሁድ እምነት ተሹመል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ የሰለሞን ዘር ነን በሚሉት ውስጥም ገብተው፣ ስርወ መንግስት እስከ መመስረት የደረሱ ነበሩ፡፡ በዓለም ላይ አይሁዳውያን ደልቷቸው የኖሩት ኢትዮጵያ ላይ ብቻ ነው፡፡ በጠቅላላው በኢትዮጵያ ሀገራት ማለትም፡- በግብፅ፣ የመን፣ ኑቢያ—ኢትዮጵያ ባስተዳደረቻቸው አካባቢዎች በሙሉ በክብር ተይዘው ነው የኖሩት፡፡ ትልቁ ማስረጃ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ፣ እናቱ ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ በስደቱ ዘመኑ እኛ ጋ ብቻ ነው ጥገኝነት ያገኙት። በወቅቱ ግብፅ ለሁለት ተከፍሎ ነበር፡፡ አንዱ ክፍል በሮማውያን ቁጥጥር ስር ነበር፡፡ ሁለተኛው የኢትዮጵያ ክፍል ነው፡፡ ኢየሱስ ከመወለዱ ከ880 ዓመት በፊት አማራዎች፤ አማሩላ ደልታ ወደሚባል ቦታ ሄደው፣ አክሱማይት የተባለውን ህፃን ልጅ ዙፋን በመጠበቅ ያገለግሉ ነበር፡፡ በኋላ በ800 ዓመታት ውስጥ አማሩላ ደልታ የሚባል መንደር መስርተው ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ጋርና ከቅዱስ ዮሴፍ ጋር ሲሸሹ፣ እዚያ ነው ማረፊያ ያገኙት፡፡ ይሄ መፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ የለም፤እኛ ግን ከተለያዩ መዛግብት እናገኘዋለን፡፡ በወቅቱ የአካባቢው ንጉስ አማናቱ ተትናይ ይባላሉ፡፡ ከጎጃም ከጣና አካባቢ ነው ወደዚያ የሄደው፡፡ ሌላው አይሁዳውያኑ መፅሐፍ ቅዱሳቸው ሲጠፋባቸው ከኛ ነው የወሰዱት፡፡ አፄ ደንቀዝ የተባለው ንጉሰ ነገስት ነው ከግዕዝ ወደ እብራይስጥ አስተርጉሞ የሰጣቸው፡፡
ትክክለኛውን የአይሁድ ባህልና እምነት በመጠበቅ በኢትዮጵያ ያሉት አይሁዳውያን ብቸኞቹ ናቸው ማለት ይቻላል?
አዎ! ኦሪትን ይዘዋል፡፡ ግን በደማቸው ከኛ ተደባልቀዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ሃበሻ የተባሉት። ሃበሻ ማለት የተደባለቀ ነው፡፡ “አበሳ” ያለበት ወይም እንከን ያለበት ማለት ነው፤ ሃበሻ ማለት፡፡ በቀዳማዊ ሚኒልክ ጊዜ የመጡት ከኛ ጋር ተደባልቀው 560 ዓመት ከቆዩ በኋላ በባቢሎን ስደት ጊዜ ሶስተኛዎቹ ሲመጡ፣ነባሮችን ሲያዩአቸው በመልካቸው አይሁዳውያንን አልመስል አሏቸው። ስለዚህ፤“እናንተማ ክልስ ናችሁ፤አበሳ አለባችሁ” ብለው ይሰድቧቸዋል፡፡ ነባሮቹ አይሁዶች ደግሞ፤ “እናንተ ፈላሾች፤እኛ ሀገር አለን” እያሉ ይሰድቧቸው ነበር፡፡ በዚህም “አበሻ” እና “ፈላሻ” የሚለው መጠሪያቸው ሆነ፡፡ “ሀበሻ” የሚለው ቃል እኛን አይወክለንም የምለው ለዚህ ነው፤ሀበሻ አይሁዳውያኑን ነው የሚወክለው፡፡ እኛ የኢትዮጰያ ልጆች ነን፤ ኢትዮጵያውያን ነን፡፡
“በሃበሻነቴ እኮራለሁ” ስንል የከረምነውስ—–ቀለጠ ማለት ነው?
አዎ! እኔ ኢትዮጵያዊ እንጂ ሀበሻ አይደለሁም። ሀበሻ የሚለው ቃል የስድብ ቃል ነው፡፡ እኛን አይወክለንም፡፡ አይሁዳዊ ካልሆነ በስተቀር አንድ ሰው ራሱን “ሀበሻ ነኝ” ብሎ ሊጠራ አይገባውም። ስድብ አያኮራም፡፡ ብዙ ሰው ስለማያውቅ ነው በሀበሻነቴ እኮራለሁ የሚለው፡፡ በአረብኛም ብናየው “የተደባለቀ”፤ “ንፁህ ያልሆነ” ማለት ነው። ይሄ መልካም ቃል አይደለም፡፡ ግን ሀበሻ የሚለው “አበሳ” ከሚለው እንጂ ከአረብኛ የመጣ አይደለም። ሁለቱ አይሁዳውያን መሃል ያለ የመሰዳደቢያ ቃል ነው እንጂ እኛ ኢትዮጵያውያንን አይመለከተንም፡፡
‹‹ኢትዮጵያ›› የሚለውስ ከየት የመጣ ነው?
ኢትዮጵያ የሚለው ‹‹ኢትዮጵ›› ከተባለው ሰው የመጣ ነው፡፡ ኢትዮጵ ማን ነው ካልን፣ በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ የተጠቀሰው መልከፀዴቅ የሚባል የሳሌም ንጉሰ ነገስትና ሊቀካህን ነበር፡፡ ይህ ሰው ሃገር ያስተዳድራልም፤ሃይማኖትም ይመራል፡፡ እሱም የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነበር፡፡ ይሄ እንዴት ይሆናል ከተባለ፣ኢየሱስ በምፅአት ቀን ሲመጣ፣ የንጉስ ንጉስ፣ የካህን ካህን ሆኖ ነው፤መልከፀዴቅም የዚህ ምሳሌ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ከዚሁ ጋር ምን ያገናኛታል ሊባል ይችላል፡፡ በጣም የሚያኮራ ግንኙነት አለው፡፡ የመልከፀድቅ ልጅ ኢትኤል ይባል ነበር፡፡ እግዚአብሔር ኢትኤልን ካለህበት የሳሌም ምድር ለቀህ ጣና ላይ ስፈር አለው፡፡ ‹‹ከዚያም ያንተ የልጅ ልጆች፣ እኔ ከ2000 አመታት በኋላ በምወለድበት ጊዜ በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ስለ መወለዴ ኮከብ አሳይሃለሁ” ይለዋል (እንደኔ ምርምር፤ይሄ ኮከብ የተባለው መልአኩ ገብርኤል ነው) በዚህ ሁኔታ ኢትኤል አሁን ወዳለችው ኢትዮጵያ ሲደርስ እግዚአብሔር፤‹‹ኢትዮጵ›› ተብለህ ተጠራ አለው፡፡ ‹‹ኢት›› – ስጦታ ማለት ነው፡፡ ‹‹ዮጵ” – ማለት ደግሞ ቢጫ ወርቅ ነው፡፡ ስለዚህ “ቢጫ ወርቅ ስጦታ” ተባለ፡፡ በኋላ ሃገሪቷን ኢትዮጵያ አሠኛት፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ በተደጋጋሚ ኢትዮጵያ ተብሎ የሚጠቀሰው ስም የትኛዋን ኢትዮጵያ ነው የሚወክለው?
እሱ አሁን ያለችውን ኢትዮጵያን ነው የሚወክለው፡፡ ግን ኢትዮጵያ የሚለው መጠሪያ እስከ 13ኛው ክ/ዘመን ድረስ ለመላዋ አፍሪካ መጠሪያ ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፡፡ በኋላም የመጣው አፍሪካ የሚለው ስም ከዚሁ ከኢትዮጵያ የተገኘ ነው፡፡ ከአፋሮች ነው አፍሪካ መጠሪያዋን ያገኘችው፡፡ በመፅሃፈ እዝራ ምዕራፍ ስድስት ላይ፤‹‹አፍሪካንሳውያን›› ይላል፡፡ ይሄ አፋሮችን ነው የሚወክለው፡፡ በመርከብ ስራ በቀይ ባህር ላይ የተራቀቁ ሰዎች ነበሩ፡፡ የዛሬ 3ሺህ አመት ንጉስ ሰለሞን ቤተመቅደሱን ሲሰራ፤ልዩ እንጨት፣ እጣን፣ ወርቅ (ኦፊር የተባለ ታዋቂ ወርቅ- በነሱ የተሰየመ) ጭምር ይነግዱና ለንጉሡ ያቀርቡ ስለነበር፣ስማቸው የገነነ ሆኖ አፍሪካንሳውያን የተባሉት፡፡ በሳይንሱም አፋር የሰው ዘር መገኛ እያልን ነው፡፡ ኢስያውያንም ስያሜያቸውን ያገኙት ከሣባ ቀድሞ ከነገሰው ‹‹ኢስአኤል›› ከተባለው ንጉስ ነው፡፡ ምድሪቱን ያስተዳድር ስለነበር ኢስያ ተባለች፡፡ ‹‹አፄ” የሚለውም ከዚህ የመጣ ነው፡፡
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለውስ —?
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለው ውሸት ነው፡፡ ይሄን አጣርቻለሁ፡፡ በነሱ መዝገበ ቃላት ውስጥ ይሄ ቃል የለም፡፡ ‹‹ፊቱ የተቃጠለ›› የሚለው ቃል በግሪክ ቋንቋ ኢትዮጵያ የሚለውን ሳይሆን ሌላ ትርጉም ነው የሚኖረው፡፡ ግሪኮቹ ከኛው ሰምተው ነው መልሠው ኢትዮጵያ ያሉን፡፡ እኛ ከነሱ በፊት ነበርን እንጂ እነሱ ከኛ በፊት አልነበሩም፤ ስማችንን ሊያወጡልን አይችሉም፡፡
በምርምርዎ አዳምና ሄዋን የተፈጠሩበት ቦታ የት ሆኖ አገኙት?
ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፡፡ ጎጃም፤ ዳሞትና ጣና አካባቢ ያለ ቦታ ነው፡፡
ለዚህ ድምዳሜ ማስረጃዎ ምንድን ነው?
አንደኛ ኤደንን ከሚያጠጡ አራት ወንዞች ውስጥ አባይ የምንለው ነው ኤፌሶን የሚባለው። በኦፌር ወርቅ ዙሪያ የሚዞር መሆኑ ተፅፏል፡፡ በኔ ድምዳሜ፣የኤፌሶን ወንዝ የአሁኑ ዋቢ ሸበሌ ነው። ጤግሮስና ኤፈራጥስ ደግሞ ጊዮን ራሱ ጥንት ሜዲትራኒያን ባህር ይገባ ነበር፡፡ ድሮ ሜድትራኒያን “ኪቲ” ይባል ነበር፡፡ ጥንት ጊዮን ወንዝ ሜድትራኒያን ሲደርስ ተራራ ስለነበር ተጋጭቶ ይመለስ ነበር፡፡ ከዚያ ነው መሬት ተነቃንቆ፣ቦታው ተቆራርጦ አሁን ወዳለበት ኢራቅ የሄደው እንጂ አካባቢው እዚሁ ነበር፡፡
አዳም የት ተፈጠረ ለሚለው በመፅሃፈ ሄኖክ ላይ “ኤልዳ” በሚባል ቦታ ተፈጠረ ይላል፡፡ ኤልዳ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም አስሌዳውያን ወይም ኤልዳውያን የሚባሉ አሁንም ድረስ ጎጃም ውስጥ አሉ፡፡ ሄኖክ በመፅሃፉ ኤልዳ ነው የተፈጠረው ይላል፡፡ ከዚያ ወስዶ ነው እግዚአብሄር በ40 ቀኑ ወደ ኤደን ገነት የከተተው ይላል፡፡ ሄዋንን ደግሞ ከአዳም ጎን አውጥቷት ነው በ80 ቀኗ ወደ ኤደን ገነት የከተታት፡፡ ከዚህ ተነስቶ ነው ወንድ በ40፣ ሴት በ80 ቀን ክርስትና የሚነሱት። ይሄ አይነቱ ስርአት በዓለም ላይ የትም የለም፤እና ይሄ በሄኖክ መፅሃፍ የተፃፈውና አሁን ያለው እውነታ ይገኛል፡፡
ሌላው ኮሬብ የሚባል ዋሻ ውስጥ አዳም ተቀበረ ይላል፡፡ በእርግጥ በሲናይ በረሃ አካባቢ ኮሬብ የሚባል ቦታ አለ፤ ግን በተመሳሳይ ይህ ቦታ ኢትዮጵያ ውስጥም አለ፡፡ ሌላው ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው ይላል፡፡ አራራት ተራራን ለመፈለግ ወደ ቦታው ሄጄ ነበር፤ በታንኳ ጣናን አቋርጬ፡፡ አራራት ተራራ የሚባለውን ሳገኘውና አቀማመጡን ሳጠናው፣ ለመርከብ ማሳረፊያነት በአናቱ ላይ ምቹ ሜዳ አለው፡፡ ኖህ ወይን ጠጅ ጠጥቶ ሰክሮ ነበር ይላል፤መፅሃፍ ቅዱስ፡፡ በእርግጥም ቦታው የወይን ጠጅ ፍሬ ለማብቀል ተስማሚ ነው፡፡ አሁንም አትክልቶችና ጌሾ ይበቅልበታል፡፡ ከዚሁ ማስረጃ ሳልወጣ፣አዲስ አመትን አበቦች አብበው አከበረ፤የእንጨት መስዋዕትም አደረገ ይላል፡፡ ይሄ እንግዲህ ዛሬ በመላ ኢትዮጵያ ያለው የአዲስ ዓመት መቀበያ ስርአት፣ ከየት መጣነትን ሊያስረዳ ይችላል። በኋላ ወደ ክርስትናው የመስቀል በዓል ደመራነት ተለወጠ እንጂ በፊት ደመራ የሚነደው በአዲስ ዓመት መጀመሪያ ላይ ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃው አሁንም ድረስ ክርስቲያን ያልሆኑ የሀገራችን ሰዎች የደመራ ስርአት አላቸው። ይሄ የአባታቸው የኖህ ትዝታ (ማስታወሻ) ነው ሲወረስ ሲዋረስ የመጣው፡፡ በዚህና በኖህ ጉዳይ ሰፊ ጥናት እያደረግሁ ነው፤ወደፊት ይፋ ይሆናል፡፡ አንድ እዚህ ላይ ልጠቅሰው የምፈልገው፣ሌላ አራራት የሚባል ተራራ አርመን ውስጥ አለ፡፡ ተራራው ግን በረዶ ያለበት፣ ገደላገደል፣ እንኳን መርከብ ሊያሳርፍ ለሰው ልጅ የማይመችና የማያብብ ቦታ ነው፤ ስለዚህ ያ ሊሆን አይችልም፡፡
በሰንደቅ አላማው ላይም የተለየ መከራከሪያ ያቀርባሉ፡፡ ለኢትዮጵያ የተሰጠ ስጦታ ነው ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
ሰንደቅ አላማው ለኖህ ከተሰጠው ምልክት የመጣ ነው፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የጎሉበት ቀለማት ሰማይ ላይ ታይተዋል፡፡ እነዚያ ቀለማት ናቸው ዛሬ ያሉት፡፡ ከንግስት ሳባ በፊት የነገሰው አፄ ኢሲአኤል ነው ሰንደቅ አላማ እንዲውለበለብ ያደረገው፡፡ ሰንደቅ አላማ የሚለው የመጣው የኢስአኤል መንግስት “ሰንደቅ አለማ” ከሚለው ነው፡፡ ከዚያ የመጣ ነው። እሱ በወቅቱ የመረጠው፡- አረንጓዴ ቢጫ፣ቀይና ሰማያዊ ቀለማት ነበር፡፡ ለሰንደቅ አላማው ያልተገዛና ያላውለበለበ ይቀጣል ብሎ ለመጀመሪያ ጊዜ አስገዳጅ ህግ ያወጣውም እሱ ነበር፡፡ በሰንደቋ አናት ላይ ኮከብ ነበር የሚቀመጠው፡፡ ኢየሱስ ሲወለድ የሚጠቁመውን ኮከብ ለማስታወስ ይጠቀም ነበር፡፡ በዓለም ላይ ሰንደቅ አላማን የፈለሰፈ የመጀመሪያው ሰውም ሊሆን ይችላል፡፡
የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነው ኢስአኤል ከፈለሰፈው ሰንደቅ አላማ ነው፣ዛሬ ያሉት የሰንደቅ አላማ ቀለማት የመጡት፡፡ ስለዚህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሰንደቅ አላማው ላይ ከዚህ ተነስቶ አንድ አይነት አቋም ቢይዝ መልካም ነው፡፡ ኢስአኤል ለኦሮሞውም፣ ለአማራውም፣ ለትግሬውም፣ለአፋሩም ለሌላውም ብሄረሰብ ሁሉ አባት ነው፡፡ ከአባቶቻችን የወረደ ሰንደቅ አላማ እንጂ ከባዕድ የመጣ አይደለም፡፡
ሰውየው እጅግ ጠቢብ ነበር፤ልእለ ሰብዕ (superman) ነበር፡፡ 150 አንበሳ መግደሉን ለማስታወስ ጭምር አፄ ኢስአኤል የሰብዕ እና የአውሬዎች ንጉሰ ነገስት ብሎ ነበር ራሱን የሚጠራው፡፡ ሰውየው እጅግ ጠቢብ ከመሆኑ የተነሳ የጀነቲክ ኢንጅነሪንግን የፈለሰፈውም እሱ ነው፡፡ እንስሳን ከእንስሳ፣ ዘርን ከዘር እየቀላቀለ የፈለሰፈ የመጀመሪያው የጀነቲክ ኢንጅነር ነበር። በቅሎን የፈጠረውም እሱ ነው፡፡ አህያንና ፈረስን አዳቅሎ፡፡ ይህ ሰው የሁሉም ኢትዮጵያውን አባት ነው፡፡ የኢትዮጵ ልጅ ነው፡፡ የኢትዮጵ 10 ወንዶች ልጆች ናቸው፤ አሁን የምናያቸውን የኢትዮጵያውያን ጎሳዎች ሁሉ የፈጠሩት፡፡
ሰሞኑን ለአንባቢያን የሚቀርብ መፅሃፍ እንዳዘጋጁም ሰምቼአለሁ፡፡ የመፅሐፉን ይዘት በአጭሩ ሊነግሩኝ ይችላሉ?
መፅሐፉ፤“የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ” የሚል ነው፡፡ አሁን ያሉት ኢትዮጵያውያን በሞላ የኢትዮጵ ልጆች መሆናቸውን ከላይ አስረድቻለሁ፡፡
አሁን እንደምናው በሁላችንም ላይ የማንነት ቀውስ አለ፡፡ የማንነት ቀውሱ የመጣውም እኛ ማን እንደሆንን በትክክል ባለማወቃችን ነው፡፡ ስለዚህ ይህ መፅሐፍ እኛ ማን እንደሆንን፣በርካታ ታሪካዊ ማስረጃዎችና ሰነዶችን አስደግፎ፣ግልጥልጥ አድርጎ ያስረዳናል፡፡ ይህ የማንነት ቀውሳችን ከተስተካከለና ራሳችንን ካወቅን፣ በመካከላችን ግጭቶች ሊኖሩ አይችሉም፡፡ መፅሐፉ፤ፍቅር፣ ሰላምና ህብር ሊፈጥር ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኛ የትልቅ ሰው ዘር ነን የሚለውን በማስረጃ የሚያሳየን ነው፡፡ የሰው ዘር ምንጭ ናሙናዎች መሆናችን ይተነትናል፡፡ ማንነታችንን በትክክል ተረድተን፣ አንድ ላይ ለመጓዝ ያስችለናል ብዬ አስባለሁ – ይህ ብዙ የተደከመበት የምርምር ውጤት፡፡
የኦሮሞና የአማራ የዘር ሀረግ አንድ ነው የሚለውን ነው መፅሃፉ የሚያስረዳው?
አማራና ኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ሁሉም በኢትዮጵያ ግዛት ያለው ብሄር፣ ጎሳ ከ10ሩ የኢትዮጵ ልጆች ነው የመጣው፡፡ ዝቅ ሲል ደግሞ የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነ፣ ጎጃም ላይ አዳምና ሄዋን ተፈጥረዋል ብዬ ባልኩት አካባቢ አንድ ጠቢብ ሰው ነበር፡፡ “ደሴት” ወይም “ደሸት” ይባላል፡፡ እሱ ነው የኦሮሞና የአማራ አባት፡፡ የዛሬ 3600 ዓመት 4 ወንዶች ልጆች ወለደ፡- መንዲ፣ መደባይ፣ ማጂ፣ ጅማ የሚባሉ፡፡ እነዚህ 4ቱም አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ የሀገር መጠሪያ ሆነዋል። ማጂ ደግሞ ማራ እና ጀማን ይወልዳል። ዛሬ አማራ የምንለው ማራ ነው፡፡ “ማራ” ማለት “እውነተኛ ብርሃን” ማለት ነው፡፡ አማራ ያሉት አጋዚያን ወይም የግዕዝ ቋንቋ ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ ማጂ ማራን ወለደ ካልን፤ ጀማ እና ማራ ወንድማማቾ ናቸው፡፡ ሁለቱ ወንድማማቾች በአካባቢው ካሉት ጋፋቶች ጋር መዋጋት ሰልችቷቸው፣ ሃገር ለቀው ወደ ሸዋ ሲመጡ አንድ ወንዝ ያገኛሉ፡፡ ወንዙን ጀማ አሉት። አሁን የጀማ ወይም የ“ዠማ” ወንዝ ማለት ነው። ከአካባቢው እየራቁ ሲሄዱ የጥንት አባቶቻቸውን ቋንቋ “ሱባ”ን ትተዉ አማርኛን መፈልሰፍ ጀመሩ፡፡ መደባይ፣ ጅማና መንዲ ደግሞ ግማሾቹ ጎጃም ላይ ቀሩ፤ ግማሾቹ ወለጋ ሄዱ፤ሌሎቹም እየራቁ በምስራቅ አፍሪካ ተሰራጩ፡፡ ኦሮሚኛ ቋንቋ የሚባለውንም ፈጠሩ፡፡ በዚህ ሁኔታ ነው ዛሬ ያሉት ኦሮሞና አማራ የመጡት፡፡ ዘረ ደሸት ይባላሉ፡፡ የደሸት ልጆች ናቸው። የዘር ሀረጋቸው አንድ ነው፡፡ ቋንቋቸው የተለያየ የሆነው በሂደት ነው፡፡
ኦሮሞው የኩሽቲክ፣ አማራው የሰሜቲክ ዘር ናቸው፤ የመጡትም ከውጭ ነው የሚለው ለዘመናት የዘለቀ ታሪክስ …?
እሱ ፈፅሞ ውሸት ነው፡፡ ሁለቱም ከውጭ አልመጡም፡፡ እንዳስረዳሁት እዚሁ የበቀሉ ናቸው። የአማራም የኦሮሞም አባት ደሸትም ሆነ ታላቁ አባት ኢትዮጵ ኩሽ ነው፡፡ መልከፀዴቅም ኩሽ ነው። ኦሮሞና አማራ ሁለቱም ኩሽ ናቸው፡፡ አማራ ሴም አይደለም፤ ኩሽ ነው፡፡
እስከ ዛሬ ሲነገር የነበረው ውሸት ነው። ምናልባት የአማርኛ ቋንቋ ከሌሎች ጋር ሲደበላለቅ ሴሜቲክ ቤተሰብ ውስጥ ተገኝቶ ሊሆን ይችላል። ሁሉም ኢትዮጵያውያን የኩሽ ዘሮች ናቸው። በዚሁ መፅሐፌ ላይ ስለ ቋንቋም አስረድቻለሁ፡፡ በእብራይስጥም ሆነ በአረቢክ የሌሉ እንደ ጨ፣ቀ፣ፀ ያሉ ድምጾች በአማርኛና በኦሮሚኛ ቋንቋ ውስጥ አሉ። ይሄን በዝርዝር በመፅሐፉ አስቀምጫለሁ፡፡
ኦሮሞና አማራ አንድ ነው የሚለው አመለካከት በተለይ በኦሮሞ ምሁራን ዘንድ እምብዛም ተቀባይነት ያገኘ አይመስልም፡፡ በግድ ኦሮሞን አማራ ለማድረግ ነው በሚል ወቀሳ የሚሰነዝሩ አሉ …
እንዲህ የሚሉት ሁሉም ከኢትዮጵ ዘር የመጣው የደሸት ልጆች መሆናቸውን ባለማወቃቸው ነው። ይሄ መረጃ ስለሌላቸው ራሳቸውን እንደ ባዕድ አግልለው ስለሚያዩ ነው እንጂ አሁን ይሄ እኔ ያቀረብኩትን ማስረጃ በቅን ልቦና አገናዝበው ለመረዳት ከሞከሩ፣ የትልቁ ሰው የኢትዮጵ፣ የጠቢቡና የሊቀካህናቱ የደሸት ልጅ እንደሆኑ በሚያውቁ ጊዜ፣ እነሱ እንደተሳሳቱ ተገንዝበው ወደ ማንነታቸው ላይ አተኩረው ይኮሩበታል ብዬ አስባለሁ፡፡ የመጣነው ከትልቅ ዘር ነው፡፡ ኦሮሞውም አማራውም የመጣው ከዚህ ትልቅ ሰው ነው፡፡ በዚህ ሁላችንም ልንኮራ ይገባናል፡፡
የአሁኗ እና የቀድሞዋ ኢትዮጵያ ልዩነታቸውና አንድነታቸው ምንድን ነው?
በግዛት ከሄድን ጥንት መላው አፍሪካ ኢትዮጵያ ነው የሚባለው፡፡ ከየመን አልፎ ሁሉ ይሄዳል፡፡ ግብፅ ውስጥ ፈርኦኖች የሚባሉት ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያውያን ከአባይ ላይ ከመርከብ ወርደው ሜዳ አግኝተው የሰፈሩበት ቦታ ነው፤ ግብፅ፡፡ የአፍሪካ ሁሉ ነገር ከኛ አይወጣም፡፡
የኢትዮጵያ ታሪክ የ3ሺህ ዘመን ነው ይባላል፡፡ እርሶ የደረሱበት የጥናት ውጤት ምን ይላል?-
አዎ፤ በተለምዶ 3ሺህ አመት ይባላል እንጂ ከ7ሺ በላይ ነው፤ የኢትዮጵያ ታሪክ፡፡ ኖህ ኢትዮጵያ ላይ ነግሷል፤ ከዚያ ጀምሮ 7ሺህ አመት ነው፡፡
እስካሁን በነገሩን ታሪክ ውስጥ መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው በማስረጃነት የሚጠቅሱት፡፡ መፅሐፍ ቅዱስን ብቻ የታሪክ ምንጭ ማድረግ ይቻላል?
መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም፡፡ 42 ሰነዶችን አሁን በሚወጣው መፅሐፌ ላይ በግልፅ አስቀምጫለሁ። እነዚህ ሰነዶች በተለያዩ ሰዎች በጥንት ጊዜ የተፃፉ ናቸው፡፡ ኑቢያ ውስጥ ጀበል ኑባ በተባለ ቦታ ተቀብረው የቀሩ፣በጥንት ፍርስራሽ የኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን (ከእስልምና በፊት የነበረ) ድንጋይ ሳጥን ውስጥ ተቀብረው የነበሩ የብራና ሰነዶች አግኝቻለሁ፡፡ በዚያ ላይም የተመሰረተ ነው። ከመፅሐፍ ቅዱስ ውጪ 42 ተጨማሪ የታሪክ ሰነዶችን ተጠቅሜያለሁ፤ይሄን መፅሐፍ ሳዘጋጅ፡፡
ቀጣይዋ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት ይላሉ?
አሁን ማንነታችንን አውቀን፣ የማንነት ቀውሳችንን ፈትተን፣ሁላችንም የኢትዮጵያ ዘር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች—–መሆናችንን ተገንዝበን፤ በፍቅር፣ በሰላም፣ በመከባበር፣ በእኩልነት መኖር አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡ ሁላችንንም ኢትዮጵ ያገናኘናል፡፡
ምንጭ፡- አዲስ አድማስ
የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ…
ከዚህ ቀደም በቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት የነበሩና ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የትግራይ ክልል ስር ያሉት የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ “እኛ አማራ ነን፣ ያለፈቃዳችን ተገደን ነው ወደ ትግራይ የተካለልነው፣ የአማራ ማንነት ጥያቄያችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አማራ እንጠቃለል” የሚል ጥያቄን ቢያነሱም፤ ከመንግሥት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ አባላት ተገደው ያለፈቃዳቸው ወደ ትግራይ እንድንጠቃለል ተደርገናል ከሚለው ጥያቄ በተጨማሪ አማራ በመሆናችን ብቻ በትግራይ ክልል አስተዳደር ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብና፤እየተፈፀመብንም ይገኛል በማለት የቀደመው የአማራ ማንነታችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አስተዳደር አማራ ክልል ለመጠቃለል አንዱ ምክንያታቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ይስተዋላል፡፡
እንደ ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴዎች አገላለፅ፤የነበረው የወልቃይት ጠገዴ አስተዳደር ወሰን ክልልም በሰሜን ተከዜ ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ ኤርትራ፣ በምስራቅ የቀድሞው ትግራይ ጠቅላይ ግዛት ፣ በምዕራብ ሱዳን በደቡብ የቀድሞው ቤጌምድር (የአሁኑ ጎንደር) አስተዳደር አካል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አካባቢውም በአሁን ወቅት በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በሚል አስተዳደር ስር በ3 ወረዳዎች የተዋቀሩት ቃፍታ ሁመራ፣ ወልቃይት እና ጠገዴ ወረዳዎች በቀድሞ ቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት ወልቃይት ጠገዴ አውራጃ አስተዳደር እንደነበርም ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ቀደምት የአስተዳደር ሰነዶችን እና የአማራ ማንነትን ያረጋግጣሉ የሚሏቸው መረጃዎችን አያይዘው በሕገ-መንግሥቱ መሰረት ጥያቄ ቢያቀርቡም ከሚመለከተው አካል እስካሁንም ምላሽ አለማግኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
በተለይ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ ተወካዮች የአማራ ማንነት ጥያቄ ይዘው ላለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ ጥያቄ ያቀርቡ እንደነበር እንደሚያውቁ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲአዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አስታውሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ይህን ያስታወሱት ባለፈው ከኦሮሚያ እና በሌሎች ሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ በተያያዘ መድረክ በዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ላይ ነበር፡፡
የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላቱም በተለያየ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ከሆነ፤ አማራ ሆነው ሳለ ሳይወዱ በግድ ወደ ትግራይ መጠቃለላቸውን፣ ልጆቻቸውም ከአፍ መፍቻ አማርኛ ውጭ ተገደው በትግርኛ እንዲማሩ መደረጉን፣ የአካባቢው ህዝብ ከአማርኛ በተጨማሪ አረብኛ እና ትግርኛም ባላቸው የድንበር ግንኙነት አማካኝነት መናገር ቢችሉም፤ ባህላቸውን እና ማንነታቸውን የሚገልፁበት ቋንቋ አማርኛ መሆኑን እና የማንነት ስነ ልቦናቸውም አማራ እንደሆነ፤ ይህንንም ላለፉት 25 ዓመታት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማት ጥያቄ ሲያነሱ ግድያ፣ እስራት፣ ድብደባ፣ ማስፈራራትና ስደት እንደደረሰባቸው፣ ከጥያቄው ጋር በተያያዘ የትግራይ ክልል መስተዳደር ግድያን ጨምሮ የተለያዩ በደሎችንም ይፈፅም እንደነበርና አሁንም እየፈፀመ እንደሆነ ሲያነሱ ይደመጣል፡፡
የአማራ ማንነት ፈቃዳችን ሳይጠየቅ ተገደን እንድንጠቃለል ተደርገናል ለሚሉት የትግራይ ክልል መስተደዳደርና በፌደራሉ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄን የሚያቀርቡ ተወካዮች በአዲስ አበባም ለተወሰኑ ቀናት በፖሊስና ደህንነት አባላት ታግተው መለቀቃቸው የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን ጨምሮ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን የተዘገበ ሲሆን፤ በተለይ የትግራይ ክልል አስተዳደርና እና የክልሉ ምዕራባዊ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎች አሁንም ከፍተኛ ማስፈራሪያ እና ዛቻ እየፈፀሙ መሆኑን የኮሚቴው አባላት ገልፀዋል፡፡ አዲሱን የአስተዳደር ክልል መዋቅር የመሰረተው ኢህአዴግ መንግሥት እና የትግራይ ክልል መስተዳደር ቀድሞ የነበረውን የአማራ ስነ ህዝብ ስብጥር፣ ባህል እና ማንነትን ለማጥፋትና መቀየር ላለፉት 25 ዓመታት ሙሉ ሲሰሩ ተቃውሞ ብናቀርብም ሰሚም አላገኘንም፣ እንደወንጀለኛም ተቆጥረናል ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ከዛ በተጨማሪ የእኛ የአማራ ማንነት እንደሌለ ተቆጥሮና ተክዶ ልጆቻችን በአማርኛ እንዳይማሩና እንዳይናገሩ፣ በአማራ ማንነታቸው እንዲያፍሩና የነበረውን የአማራ ማንነት ባህል እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ በግድም የትግርኛ ቋንቋ እንዲነገሩ፣ የትግራይ ማንነት ባህልን ብቻም እንዲያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ይህም ህገ-መንግሥቱን እንደሚፃረር ብናነገርም የከፉ በደሎች ተፈፅመውብናል ይላሉ፡፡
በተለይ አካባቢውን በተመለከተ በአጼ ኃይለስላሴ ዘመን የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩትና የአጼ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል መንገሻ ስዩም ወልቃይት ጠገዴ በሳቸው ዘመንም ሆነ ከዛ በፊት ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ አስተዳደር ስር እንዳልነበር እንደሚያውቁ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ገልፀው ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሃላፊ በኩላቸው ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ እንደሆነ እና ከዛ ጋ ተያይዞ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ የህዝቡ እንዳልሆነ ከመግለፃቸው በተጨማሪ የአማራ ማንነት ጥያቄ የሚያነሱ ተወካዮች የሚቃወም ሰልፍም በአካባቢው ተደርጎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአማራ ማንነት ጥያቄን ለሚያነሱ ማኀበረሰብ አባላትና ተወካዮች ጥያቄያቸው መፍትሄ አሊያም ህዝባዊ ውሳኔ ያገኝ ዘንድ ባሉበት ወልቃይት ጠገዴ ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፍ ቢጠይቁም በትግራይ ክልልም ሆነ በክልሉ ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሊፈቀድ ባለመቻሉ የማኀበረሰቡ ተወካዮች ህዝባዊ ስብሰባዎቻቸውን በአጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች ለማድረግ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለ ኦሮሚያው ተቃውሞ እና ስለ ጎንደር የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ቢገልፁም፤ ስለ ወልቃይ ጠገዴ አማራ ማንነት ጥቄን ግን ሳያነሱት ከማለፋቸው በተጨማሪ በጥቅሉ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንነት ጋር በተያያዘ ያልተመለሰ ጥያቄ የለም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ አዲስ ሚዲያ ባለው መረጃ መሰረት የብሔረሰብ ማንነት እና የራስ አስተዳደር ጋ በተያያዘ በትግራይ ወልቃይት ጠገዴን እና በኣማራ ክልል ምላሽ አግኝቷል ከተባለው የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጥያቄ በተጨማሪ በኦሮሚያ፣ በደቡብ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ከክልሎቹ እስከ አዲስ አበባው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ እስካሁንም ምላሽ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡