Tag Archives: TPLF/EPRDF Ethiopia

የቀድሞ የሶማል ክልል ፕሬዘዳንት አቶ አብዲ መሐመድ ዑመር ን ጭምሮ 47 ተጠርጣሪዎች ክስ ተመሰረተባቸው

በጅጅጋና አካባቢው በተፈጠረው ብጥብጥና ሁከት አብዲ መሀመድ ዑመር (አብዲ ኢሌ)ን ጨምሮ 47 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ተመሰረተባቸው።
abdimehommedumer28abdiilley29
የቀድሞ የሶማሌ ክልል ፕሬዘዳንት (ፎቶ፤ ናሆም ተስፋዬ_ሪፖርተር)

በ1ኛ ክስ ከ1-26 ያሉ ተከሳሾችን ሚመለከት ሲሆን ለጊዜው ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን በቀጥታ ወይም በመላ አሳባቸውና አድራጎታቸው የወንጀሉ ድርጊትና የሚሰጠውን ውጤት ሙሉ ተካፋይ በመሆን ድርጊቱን የራሳቸው በማድረግ በህብረትና በማደም በሶማሌ ክልል ከሰኔ ወር 2010 ዓ.ም እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ቀናቶች በክልሉ ውስጥ አንዱ ወገን በሌላው ነዋሪ ላይ ጥቃት በመፈፀም እና አለመረጋጋት በመፍጠር ተሳትፈዋል በሚል በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየታየ ይገኛል። ተጠርጣሪዎቹ በአካባቢው በተለምዶ ሀበሻ በሚል በሚጠሯቸው የክልሉ ነዋሪዎችና በሶማሌ ማኅበረሰብ መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር ተንቀሳቅሰዋል በሚል ክስ ቀርቦባቸዋል።

ተከሳሾቹ በግጭቱ ውስጥ የሚሳተፉ ሄጎ በሚል ስያሜ ወጣቶችን በማደራጀት፤ የተደራጀውን የሄጎ ቡድን በገንዘብ እና በተለያዩ ቁሳቁሶች በመደገፍ፣መሳሪያ በማስታጠቅ፣ ግጭቱ የሚመራበትና መልዕክት የሚተላለፍበት ሄጎ ዋሄገን (Heego waaheegan) የሚል በፌስቡክ ገጽ በመክፈትና በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ ሰዎችን ለግጭት ሊያነሳሳ የሚችሉ ይዘት ያላቸው መልእክቶችን በማሳተም እንዲሁም በክልሉ ውስጥ የጥቃቱ ዒላማ የተደረጉ ነዋሪዎችን መግደል ፣ንብረታቸውንም መዝረፍ እና ማውደም፣ባንኮችን እና ኢንሹራንሶችን መዝረፍ ፣ቤተክርስቲያኖችን እና ነዳጅ ማደያዎችን ማቃጠል አለብን በማለት በየቦታው ተንቀሳቅሰው ትእዛዝ በመስጠት በክልሉ ውስጥ ግጭት እንዲነሳ በማድረግ፥ የሰው ህይወት እንዲጠፋ ፣ በመንግስት እና በእምነት ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ ፣ ሴቶች እንዲደፈሩና እና በርካታ የከተማው ነዋሪ እንዲፈናቀሉ ማድረጋቸው በክሱ ላይ ተገልጿል፡፡

በ2ኛ ክስ ደግሞ ከ27-47 ያሉ ተከሳሾች በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በጠተቀሰው ቀን በክልሉ ውስጥ አንዱ ወገን በሌላው ወገን ላይ የጦር መሳሪያ እንዲያነሳ ለማድረግ በማሰብ በሶማሌ ብሔር ተወላጆች እና በሶማሌ ክልል የሚኖሩ ከሶማሌ ብሔር ተወላጅ ውጭ በተለምዶ በአካባቢው አጠራር ሀበሻ በሚል በሚጠሯቸው የክልሉ ነዋሪዎች መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር በማሰብ ሄጎ በሚል ስያሜ ወጣቶችን በማደራጀት ፣መሳሪያ በማስታጠቅ ሰዎችን ለአመፅ ሊያነሳሱ የሚችሉ መልእክቶችን በመቅረጽ እና የሄጎ አደረጃጀት ውስጥ አባል እና አመራር በመሆን ከሐምሌ 28 ቀን 2010 እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2010 ዓ.ም በክልሉ በተፈጠረው ግጭት ውስጥ የተለያዩ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ መሳሪያዎችን በመያዝ በግጭቱ በመሳተፍ የሰው ህይወት እንዲጠፋ ፣ በመንግስት እና በእምነት ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ ፣ሴቶች እንዲደፈሩና እና በርካታ የከተማው ነዋሪ እንዲፈናቀል አድርገዋል፡፡

የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎትም ተጠርጣሪዎች አቃቤ ህግ የመሰረተባቸውን ክስ በእጃቸው አንዲደርሳቸው መደረጉም ተጠቁሟል። ፍርድ ቤቱም ተከሳሾቹ በጉዳዩ ላይ ከጠበቆቻቸው ጋር ተነጋግረው መልስ ይዘው እንዲቀርቡ ጥር 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል። ተጠርጣሪዎቹም አዲስ አበባ በሚገኘው ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የደህንነት ችግር እንዳይገጥማቸው ለፍርድ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን፤ ፍርድ ቤቱም ወደፊት ከጠበቆቻቸው ጋር በመነጋገር በሚቀርቡ አቤቱታዎች ተመስርቶ ውሳኔ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡

በተለይ ባለፉት 27 ዓመታት ሶማሌ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ በርካታ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና ጥቃቶች በመንግሥት አመራር አካላት ትዕዛዝና እውቅና ይፈፀሙ እንደነበር መዘገቡ ይታወሳል። መረጃው የፍደራሉ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ነው።

ቦምብ በመወርወር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድን ለመግደል የሞከሩ ተጠርጣሪዎች ክስ ተመሠረተባቸው

ታምሩ ጽጌ

PM Abiy Ahmed
ሰኔ 16 ቀን 2010ዓ.ም. መስቀል አደባባይ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የድጋፍ ሰልፍ

ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. በመስቀል አደባባይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ላይ ግድያ ለመፈጸም፣ ቦምብ በመወርወር ተጠርጥረው ከታሰሩት መካከል በአምስቱ ላይ ክስ ተመሠረተ፡፡

በፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ረቡዕ መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም. የተጻፈውና ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አራተኛ ተረኛ ወንጀል ችሎት ዓርብ መስከረም 18 ቀን 2011 ዓ.ም. የቀረበው ክስ እንደሚያመለክተው፣ በወንጀል ድርጊት ተጠርጥረው ክስ የተመሠረተባቸው አምስት ግለሰቦች ናቸው፡፡ ተከሳሾቹ አቶ ግርማ ቶሎሳ፣ አቶ ብርሃኑ ጃፋር፣ አቶ ጥላሁን ጌታቸው፣ አቶ ባህሩ ቶላና አቶ ደሳለኝ ተስፋዬ መሆናቸውን ዓቃቤ ሕግ አስታውቋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ አራቱ ተከሳሾች የወንጀል ሕግ ቁጥር 32(1ሀ) 35 እና 38ን፣ እንዲሁም የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 3(1) ሥር የተደነገገውን በመተላለፍ በፈጸሙት የሰው ሕይወት ማጥፋት፣ ከባድና ቀላል አካል ጉዳት ማድረስና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ጥቃት ለማድረስ በፈጸሙት ሽብርተኝነት ድርጊት ወንጀል መከሰሳቸውን አስረድቷል፡፡ አቶ ደሳለኝ ተስፋዬ የተባለው ተጠርጣሪ ደግሞ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (12) ሥር የተደነገገውን በመተላለፍ፣ የሽብርተኝነት ድርጊት የፈጸሙ ተጠርጣሪዎችን ባለማሳወቅ ወንጀል መከሰሱንም ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡

የዓቃቤ ሕግ ክስ እንደሚያስረዳው ተጠርጣሪዎቹ በጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ መንግሥት መኖር እንደሌለበት፣ በስመ ሕዝበኝነት የራሳቸውን ዓላማ የሚራምዱ መሆናቸውንና መገደል እንዳለባቸው መዶለታቸውን ያስረዳል፡፡ ጥቃቱ መፈጸም ያለበት ቀድሞ በተደራጀ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ስም በሚንቀሳቀሱና ቦምብ በመወርወር ጥቃት ማድረስ በሚችሉ አባላት መሆን እንዳለበትም፣ ከግብረ አበሮቻቸው ጋር መመካከራቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በኦሮሞ ብሔር ዘንድ የማይፈለጉ መሆኑን ለማሳየት በሚረዳ መንገድ ጥቃቱ መፈጸም እንዳለበት፣ የመኖሪያ አድራሻዋ ኬንያ መሆኑ በተገለጸው ገነት ታምሩ (ቶለሺ ታምሩ) አማካይነት ዕቅድ ወጥቶና ስምምነት ላይ ተደርሶ ተልዕኮው መተላለፉንና በዕቅዱ መሠረት ወደ ትግበራ መገባቱን ክሱ ያብራራል፡፡

Meskel Square Bombering
ሰኔ 16 ቀን 2010ዓ.ም. መስቀል አደባባይ በነበረው ህዝባዊ ሰልፍ ላይ ቦንቡ ከፈነዳ በኋላ

አቶ ጌቱ የተባለው ተከሳሽ ቀኑ ባልታወቀበት ሰኔ ወር 2010 ዓ.ም. ከቶለሺ ታምሩ ጋር በስልክ በመገናኘት፣ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. የጠቅላይ ሚኒስትሩ የድጋፍ ሠልፍ መካሄድ እንደሌለበት መክረዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ መሠረታዊ ለውጥ አለመምጣቱና ሠልፉን የጠራው ኢሕአዴግ መሆኑ እንደሆነ፣ የዓቃቤ ሕግ ክስ ይጠቁማል፡፡ በተጨማሪም ኤችአር 128 የተባለውና የአሜሪካ ኮንግረስ ያስተላለፈው ውሳኔ ተግባራዊ እንዳይሆን ያደርጋል የሚልም መሆኑንም ያክላል፡፡ በመሆኑም አቶ ጌቱ ሰኔ 15 ቀን 2010 ዓ.ም. ከአቶ ብርሃኑ ጃፋር ጋር ሱሉልታ ከተማ በመገናኘት ቦምብ እንዲዘጋጅና የሚወረውር ሰው እንዲያፈላልግ፣ ለሦስተኛ ተከሳሽ አቶ ጥላሁን ጌታቸው ስልክ በመደወል ተልኮ እንደሰጡት ክሱ ያስረዳል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሽ አቶ ብርሃኑ ሁለት ኤፍዋን እና አንድ የጭስ ቦምቦች ያሉት መሆኑን ለአንደኛ ተከሳሽ አቶ ጌቱ ነግሮት ሰኔ 15 ቀን 2010 ዓ.ም. ሱሉልታ ከተማ በመገናኘት፣ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. በድጋፍ ሠልፉ ቦታ ተገኝተው ጥቃቱን ለመፈጸም ከተስማሙ በኋላ፣ አቶ ብርሃኑ ቦምቡን የሚወረውር ሰው እንዲያዘጋጅ ለአቶ ጌቱ ተልዕኮ እንደሰጠውም በክሱ ተብራርቷል፡፡

አንደኛ ተከሳሽ አቶ ጌቱ ለሦስተኛ ተከሳሽ አቶ ጥላሁን ደውሎለት ቦምቡን እንዲወረውርና እንዲያፈነዳ ሲነግረው፣ አቶ ጥላሁንም ለአራተኛ ተከሳሽ አቶ ባህሩ ቶላ ደውሎ በድጋፍ ሠላማዊ ሠልፉ ላይ ቦምብ ለመወርወር ማቀዱን እንደገለጸለትና ለመመካከር በቡራዩ ከተማ በሚገኘው አምስተኛ ተከሳሽ አቶ ደሳለኝ ተስፋዬ ቤት መገናኘታቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡ አቶ ደሳለኝ ቤት ሲመካከሩ ካደሩ በኋላ አንደኛና ሁለተኛ ተከሳሾች ማለትም አቶ ጌቱና አቶ ብርሃኑ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት፣ አቶ ብርሃኑ በሚያሽከረክረው የሰሌዳ ቁጥሩ 02-26235 (አ/አ) በሆነ ተሽከርካሪ ሁለት ኤፍዋን ቦምቦችና አንድ የጭስ ቦምብ ለአቶ ጥላሁን ጌታቸውና ለአቶ ባህሩ ቶላ መስጠታቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡ ሁለቱ ተከሳሾች የጠቅላይ ሚኒስትሩ ምሥል ያለበትን ቲሸርት ገዝተው በመልበስና ፍተሻውን በማለፍ ከሕዝቡ ጋር ተቀላቅለው በመግባት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር አድርገው ሲጨርሱ ከመድረኩ በቅርብ ርቀት ላይ ቦምቡን ጥለው ማፈንዳታቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አስረድቷል፡፡

በደረሰው ፍንዳታም ሙሳ ጋዲሳና ዮሴፍ አያሌው የተባሉ ሁለት ግለሰቦች ሕይወት ሲያልፍ፣ ከ163 በላይ ሰዎች ከባድና ቀላል የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸውም ተገልጿል፡፡ አንድ ኤፍዋን ቦምብ ግዮን ሆቴል መግቢያ አጠገብ ናኒ ሕንፃ ፊት ለፊት በሚገኘው ትንሹ ስታዲዮም ውስጥ ቢወረውርም ሳይፈነዳ መቅረቱን፣ አራተኛ ተከሳሽ ለአንደኛ ተከሳሽ በስልክ ሪፖርት ማድረጉም በክሱ ተጠቅሷል፡፡

ተከሳሾቹ በቡድን በመደራጀት በግብረ አበሮቻቸው በተሰጣቸው ተልዕኮ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ላይ ጥቃት ለማድረስና ሠልፉን ለመበተን በወረወሩት ቦምብ፣ የሰው ሕይወት በማጥፋትና አካል በማጉደል የሽብርተኝነት ድርጊት መፈጸማቸውንና ክሱን እንደመሠረተባቸው ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡

የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራተኛ ተረኛ ወንጀል ችሎትም ክሱን ለተከሳሾች በችሎት አንብቦላቸዋል፡፡ ክሱን ካነበበ በኋላ በራሳቸው ጠበቃ ማቆም ስለመቻላቸውና በክሱ ላይ ተቃውሞ ካላቸው ለመስማትና የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ተለዋጭ ቀጠሮ ለጥቅምት 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ሰጥቷል፡፡ ሁለት ተከሳሾችን በቤቱ ያሳደረው አምስተኛ ተከሳሽ አቶ ደሳለኝ የተከሰሰበት አንቀጽ ዋስትና እንደማይከለክል ተናግሮ የዋስትና መብቱ እንዲከበር ቢጠይቅም፣ ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ ዘገባው የሪፖርተር ነው። Abiy Ahmed

ድብቁ የኢትዮጵያ እስር ቤት ግፍ እና የወልቃይቱ ተወላጅ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ

ለገሠ ወልደሃና

Ethiopian General Attorney

አቶ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ የወልቃይት ጠገዴ ተወላጅ ነው። በአዲስ አበባ በንግድ ስራ ተሠማርቶ ውጤታማ ነገዴ መሆን የቻለ ሰው ነበር። በአዲስ አበባ ላይ ጎጆ ቀልሶ ንግዱን እያከናወነ ይኖር የነበረው አቶ ዘካርያስ ነሐሴ 14 ቀን 2000 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ በደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ። በቁጥጥር ስር ያዋሉት ግለሰቦች መጀመሪያ አዲስ አበባ ፓሊስ ኮሚሽን (በተለምዶ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ)አሰሩት። ከተወሰነ ወራት በኋላ ወደ ቦሌ ፓሊስ መምሪያ ቀየሩት። እንደገና ከወራት በኋላ አራዳ ክ/ከተማ የሚገኝ ፓሊስ ጣቢያ አዛወሩት። ከዚህም ከወራት በኋላ ልደታ ክ/ከተማ የሚገኝ ፓሊስ ጣቢያ ያዛወራል። ከልደታ ወደ ቃሊቲ ተወስዶ ለወራት ከታሰረ በኋላ ወደ ቅሊንጦ በመጨረሻም አሁን ወደሚገኝበት ቃሊቲ አዛውረው ያስሩታል።

ከእስር ቤት እስር ቤት እያዘዋወሩ ያሰሩት አቶ ዘካርያስ ከሶስት አመት ክርክር በኋላ ፍርድ ቤት ነፃ ይለዋል። “እስካሁን ያሰረኝን ሳላውቅ። ሶስት አመት ተንገላታሁ። አሁን ነፃ ተብያለሁ። ፍቱኝ” የሚል ጥያቄ ያቀርባል። “አዎ! በዚህ ነፃ ተብለሃል። ግን ተጠይቆብሃል ተብሎ ፍች ሲጠብቅ በይግባኝ እስር ቤት ሆኖ ለ2 ዓመት በክርክር ያሳልፋል። ከ5 ዓመት እስር በኋላ ነፃ ይወጣል። “አሁን ነፃ ወጥቻለሁ ፍቱኝ!” የሚል ጥያቄ ያቀርባል። “አዎ በዚህ ክስ ነፃ ተብለሃል!ግን ሌላ የ17 ዓመት ፍርድ አለብህ!” ይባላል። 

አቶ ዘካርያስም “ማን ከሶኝ? መቼስ ክስ ደረሰኝ? በየትኛው ፍርድቤት ቀርቤ ተከራክሬ ነው የተፈረደብኝ? የፈረደብኝ ፍርድ ቤት ውሰዱኝ!” የሚል ጥያቄ ያቀርብና ፍርድ ይወስዱታል። ፍርድ ቀርቦ “17 ዓመት የተፈረደብኝ በምን ወንጀል ነው? ክስ አልደረሰኝ። የመሳሰለውን ጥያቄ ያቀርባል። ዳኛው “እኛ አልፈረድንም። የምናውቀው ነጻ መውጣትህን ነው።” ይለዋል። “ታዲያ ማነው 17 ዓመት የፈረደብኝ ማነው? እኔ ተከራክሬ ነፃ ወጥቻለሁ መፍቻ ፃፉል!! የሚል ጥያቄ ለዳኛ አቅርበ። ዳኛው “ያንተ ጉዳይ አስቸጋሪ ነው። መፍቻ አልፅፍም” የሚል መልስ ይሰጠዋል። ዘካርያስ ከዳኛ ጋር ሰጣ ገባ ይጀመራል። ዳኛው ለዘካርያስ መፍቻ ከመጻፍ ይልቅ 6 ዓመት ቅጣት ጨምሮ በድምሩ የ24 ዓመት ፍርድ ተፈርዶበት ወደ ቃሊቲ እስር ቤት በልዩ ቅጣት ኮንቴነር ቤት ወደሚባለው ጨለማ ቤት ይወረወራል።

ዘካርያስ ጉዳዩን የሚከታተሉለት ጠበቆች ቢያቆምም በስውሩ እጅ የሱን ጉዳይ እንዲተው በማስፈራራት 8 ጠበቆች አባረውበታል። በዚህ ሁኔታም ሆኖ ዘካርያስ ተስፋ ሳይቆርጥ ለፍትህ ሚኒስትር አቤቱታ ያቀርባል። ፍትህ ሚኒስቴር በዚህ የመዝገብ ቁጥር ዘካርያስ ገ/ፃዲቅ የሚባል ሰው አናውቅም። “በዚህ መዝገብ ቁጥር አማን ከሊፋ የሚባል ሰው ነበር የተከሰተው እሱም በሽምግልና ጉዳዩ በማለቁ መዝገቡ ተዘግቷል” የሚል መልስ ፍትህ ሚኒስትር ለዘካርያስ ገ/ፃዲቅ ደብዳቤ ይልካል። 

ዘካርያስም አቤት የሚልበት ተቋም በማጣቱ ከነሐሴ 14 ቀን 2000 ዓ.ም. ጀምሮ በልዩ ልዩ እስር ቤት ዛሬም ድረስ የመከራ ጊዜውን እየገፋ ይገኛል። በተለይ ቃሊቲ እስር ቤት ከገባበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ሰኔ 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ከሰው ተለይቶ መታሰሩን ገልጿል። ከሰኔ 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ቃሊቲ ዞን 6 ከሰው ተቀላቅሎ ማን እንዳሰረው ማን እንዳሳሰረው ለምን እንደታሰረ ሳያውቅ 11 ዓመታት አስቆጥሯል። የግፍ እስረኛው ምንም እንኳ ከተመሰረተበት ክስ በተደጋጋሚ በፍርድ ቤት ነፃ ቢባልም ይህ እስከተዘገበበት መስከረም 20 ቀን 2011 ዓ ም ቃሊቲ ወህኒ ቤት አልወጣም። ዘካርያስ ገብረፃዲቅ አሁንም ፍትህ ይሻል።

ለመንግሥት ሀላፊዎች 

ላለፉት 27 ዓመታት ልክ እንደ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ በግፍ የታሰሩ በርካታ ዜጎች በማንነታቸው እና በአገዛዙ ሰዎች ቀጭን ትዕዛዝ በርካታ ዜጎች በግፍ ታስረው እንደሚገኙ የታወቀ ነው። በአሁኑ ሰዓት የመንግስትነት ስልጣን የጨበጣችሁ ሰዎች በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ እስር ቤቶች ላይ ፍተሻ በማድረግ ያለ አግባብ የታሰሩ ሰዎች ነፃ እንዲወጡ ታደርጉ ዘንድ ጥሪየን አቀርባለሁ።
ለሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች 

ዘካርያስ ገብረፃዲቅ እና እንደሱ በግፍ የታሰሩ ወገኖችን ጉዳይ በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ እስር ቤት የተወረወሩ ወገኖችን ጉዳዩ በማጣራት ከግፍ እስር ነጻ እንዲወጡ ጥረት እንድታደርጉ ጥሪ አስተላልፋሁ።

የአዲስ አበባው “ለውጥን እንደግፍ፣ ዴሞክራሲን እናበርታ” ታሪካዊ የድጋፍ ሰልፍ እና ክስተቶቹ

ብስራት ወልደሚካኤል

ቅዳሜ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ ም ከጠዋቱ 1፡0 ጀምሮ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሁሉን ያሳተፈ ታሪካዊ ሰልፍ ተከናውኗል። ህዝባዊ ሰልፉም በኢትዮጵያ ታሪክ ተደርጎ በማይታወቅ መልኩ፥ የትኛውም የፖለቲካ ድርጅት ወይም የሲቪክ ተቋም ውጭ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እየወሰዷቸው ባሉ በጎ የለውጥ ርምጃዎች ደስተኛ በሆኑ እና ለውጡ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በሚፈልጉ ግለሰቦች ተነሳሽነት የተጠራ ህዝባዊ ሰልፍ ሲሆን፤ መሪ ቃሉም “ለውጥን እንደግፍ፥ ዴሞክራሲን እናበርታ” በሚል በሪ ቃል የተዘጋጀ ህዝባዊ ትዕይንት ነበር።

Abiy Ahmed

ዶ/ር አብይ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሰልፍ በከፊል (ፎቶ፡ ከዕለቱ ማኅበራዊ ገፆች የተወሰደ)

በሰልፉ ላይ ከ2 እስከ 3 ሚሊዮን ተሳታፊዎች ሊገኙ ይችላሉ ተብሎ ቢጠበቅም፤ እንደ አዲስ አበባና ፌደራል ፖሊስ ግምት ግን ከ4 ሚሊዮን በላይ ህዝብ እንደታደመበት ሙያዊ ግምታቸውን ሰጥተዋል። ይህም ከተጠበቀው በላይ መሆኑ ነው። ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፉም ከአዲስ አበባ ነዋሪዎች በተጨማሪ የአጎራባች ከተሞች ነዋሪዎችም ታድመውበታል። በሰልፉ ላይም ህዝቡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጎን እንደሚቆም በተለያዩ መፈክሮች እና ህብረ-ዜማዎች በመግለፅ ለውጡ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ድጋፋቸውን ሲቸር ታይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም ህዝባዊ ድጋፉ ለስራቸው ተጨማሪ ጉልበትና አቅም እንደሚፈጥርላቸውና በድጋፉ ሳይታበዩ ህዝቡን በቅንነትና በታማኝነት እንደሚያገለግሉ በመግለፅ ትህትናን በሚያሳይ መልኩ ራሳቸውን ዝቅ በማድረግ ለህዝቡ ያላቸውን አክብሮት ሲያሳዩ ተስተውሏል። የጠቅላይ ሚኒስትሩና በጎ የለውጥ ርምጃቸው የተለያየ የፖለቲካ አመለካከትና ፍላጎት ባላቸ አካላትንም ጭምር በማካተት የተደረገ ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝቡ ያደረጉት ንግግር እና ያሳዩት ትህትና፤ በታዳሚው ዘንድ የተቸራቸው የአደባባይ አድናቆትና ድጋፍ በኢትዮጵያ ያልተለመደ አዲስ ክስተት ነበር።

Abih Ahmed at Meskel square

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ መስቀል አደባባይ ለህዝቡ ምስጋና እና አክብሮቱን ሲገልፅ

Addis Ababa rally
የአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሰልፍ በከፊል (ፎቶ፡ ከዕለቱ ማኅበራዊ ገፆች የተወሰደ)

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ ገና 82ኛ ቀናቸው ቢሆንም በየዕለቱ በሚተገብሯቸው ስራዎችና ተግባራዊ እንቅስቃሴያቸው ላለፉት 27 ዓመታት በርካቶችን ለእስር፥ግድያ፥ ስደትና መከራ የዳረገውን የሚመሩት ኢህአዴግ ድርጅት ተፎካካሪዎችን ሳይቀር ይሁንታ ያገኘ ያልተለመዱ በጎ ርምጃዎች ለድጋፉ ዋነኛ ምክንያቶች ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ የሀገሪቱን መሪነት ከተረከቡ ጀምሮ በተለይ በአዲስ አበባ ፥ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል የታሰሩ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ ተደርጓል። በተለይ የርስ በርስ ሽኩቻና ግጭቶችን በይፋ በማውገዝ ከመከፋፈል ና ልዩነት ይልቅ “መደመር” በሚል የሚታወቁበት አብሮነት ቃል ፍቅር፥ ይቅርታ፥ ሰላምና ኢትዮጵያዊ አንድነት ጥሪያቸው የህዝቡን ቀልብ የሳቡ ንግግሮቻቸው ተጠቃሽ ናቸው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምንም እንኳ ላለፉት 27 ዓመታት ገዥ የነበረው ኢህአዴግ አመራር ሆነው የመጡ ቢሆንም፤ ከዚህ ቀደም በነበሩ የገዥው አመራሮች ሲፈፀሙና ሲቀነቀኑ የነበሩና በህዝቡ የተወገዙ ተግባራት፥ የሀገሪቱን እና የህዝቡን አንድነት የሚፈታተኑ እጅግ ለጆሮ የሚቀፉ ቃላቶችና ትርክቶችን ሁሉ በመተው በአዲስ ማንነት ራሳቸውን ሆነው በመምጣት መልካም የሚባሉና በህዝቡ የተወደዱ ተስፋ ሰጭ እንቅስቃሴዎችን ማከናወናቸው ለድጋፉ አንዱ ምክንያት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በርግጥም ከ3 ወር ላልበለጠ የሥልጣን ጊዜያቸው ይበል የሚያሰኙ በጎ ተግባራትን እያከናወኑ መሆኑ እሙን ነው።

ዶ/ር አብይ ካከናወኗቸው በጎ ሥራዎች መካከል በፖለቲካዊ አመለካከታቸውና ሐሳባቸው፥ በነፃነት በመግለፃቸውን እና መብታቸውን በመጠየቃቸው ብቻ በአስከፊ እስር ላይ የነበሩ ጋዜጠኞች፥ የተፎካካሪ ፖለቲካ ድርጅት መሪዎች፥ የመብት ተሟጋቾች፥ የኢንተርኔት ጦማሪዎች እንዲሁም ገዥውን ሥርዓት ሲያገለግሉ የነበሩና የመንግሥትን የሰብዓዊ መብት ጥሰትና አድሏዊ የሆነ ብልሹ አሰራርን በመቃወማቸው የታሰሩ የጦር መኮንኖች ለዓመታት በግፍ ከሚማቅቁበት ወህኒ ቤቶች ከእስር በነፃ እንዲለቀቁ ማድረጋቸውን እና የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብት ላይ ገደብ የጣለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲነሳ ማድርብጋቸው በበጎ ጎን ማንሳት ይቻላል። ሌላው ላለፉት 27 ዓመታት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ እና በቅርቡ ሥልጣናችውን በለቀቁት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥልጣን ዘመን ሲከናወኑ የነበሩ የመብት ጥሰቶችን በማመን እና ድርጊቱን በመኮነን ህዝቡን በይፋ ይቅርታ በመጠየቅ፤ መንግሥት በህዝቡ ላይ የሽብር ተግባር ይፈፅም እንደነበር ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመረጃ ናሙና በመግለፅ አረጋግጠዋል። ለዚህም ህዝቡን በድጋሚ ይቅርታ ጠይቀዋል።

ሌላው በህዝብ ላይ ላለፉት 27 ዓመታት በደል ሲፈፅሙና ሲያስፈፅሙ የነበሩ አመራሮችን ከሥልጣን አሰናብተዋል። ለዓመታት በሀገር ውስጥና እንዳይነበቡና እንዳይደመጡ ታፍነው የነበሩ 246 የኢትዮጵያውያን የመረጃ ድረ-ገፆች እና ብሎጎች እንዲለቀቁ እና አማራጭ የመረጫ ምንጭ ሆነው እንዲያገለግሉ አድርገዋል። ከዚህ በፊት የመንግሥትን የሰብዓዊ መብት ጥሰትና ብልሹ አሰራር የሚኮንኑትን በመወንጀል፥ የተሳሳተ መረጃ ለህዝቡ በማሰራጨትና የባለሥልጣናትን ገመና ለመሸፈን ሲውሉ የነበሩ የህዝብ መገናኛ ብዙኃን አሁን ሙያዊ ስነምግባርን የተከተለ ትክክለኛ መረጃ ለህዝቡ እንዲያሰራጩ አድርገዋል። ላለፉት 18 ዓመታት ሻክሮ የነበረውን እና በኢትዮጵያ ታሪክ ከ70 ሺህ በላይ ሰዎች ያለቁበት አስከፊ ደም አፋሳሽ ጦርነት መንስኤ በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት አልባ ጦርነት ያሉት የኢትዮጵያና እርትራ ግንኙነት እልባት እንዲያገኝ የወሰዱት የሰላም ርምጃ ህዝቡን ካስደሰቱት መካከል ዋነኞቹ ናቸው።

Addis Ababa rally 2
የአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሰልፍ በከፊል (ፎቶ፡ ከዕለቱ ማኅበራዊ ገፆች የተወሰደ)

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ እየወሰዷቸው ካሉ በጎ ርምጃዎች በተጨማሪ የዴሞኬራሲ የሰብዓዊ መብት አጠባብቅ በተግባር እንደሚረጋገጥ፥ በእርሳቸው የሥልጣን ዘመን ማንም ኢትዮጵያዊ አሳዳጅና ተሰዳጅ እንደማኖር፥ የዜጎች እኩልነት፥ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት፥ በነፃነት የመሰብሰብና የመደራጀት እናንዲሁም ዴሞክራሲ መብቶች እንደሚያረጋገጡ ቃል በመግባት ተግባራዊ ርምጃዎችን መውሰድ በመጀመራቸው ህዝቡን እያስደሰተው እንደሆነ ይስተዋላል። በተቃራኒው ያለፉት 27 ዓመታት ህዝቡን ለመከራ፥ ሀገሪቱን ለከፋ ውድቀት የዳረጉ የገዥው ህወሓት/ኢህአዴግ አመራሮች ምክንያት የተበሳጨው ህዝብ አገዛዙና ሥርዓቱ እንዲወገድ በተለይም ላለፉት ሶስት ዓመታት በኦሮሚያ፥ በአማራ እና በከፊል በደቡብ ክልል በተነሳው ህዝባዊ ተከታታይ አስገዳጅ ተቃውሞ ምክንያት ከሥልጣን የተወገዱ አካላት በጠቅላይ ሚኒስትሩ በጎ ርምጃዎች ደስተኛ ባለመሆናቸው በጎ ርምጃዎቹ “የፓርቲውን ህገ ደንብ የተከተለ አይደለም፥ ሕገ መንግሥቱም እየተጣሰ ነው” በሚል ከሚነሳው ውስጣዊ የሥልጣን ሽኩቻ እስከ አደባባይ የተቃውሞ መግለጫ ማውጣታቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ የተጀመረው በጎ ለውጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እና እንዳይደናቀፍ በመፈለግ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. “ለውጥን እንደግፍ ፥ ዴሞክራሲን እናበርታ” በሚል መሪ ቃል የተደረገ ታላቅ ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ ነው። በተጨማሪም በጎንደር፥ ደብረ ማርቆስ፥ ደሴ፥ ዱራሜ ከተሞች ተመሳሳይ የድጋፍ ሰልፎች የተደረጉ ሲሆን፤ እሁድ ሰኔ 17 ቀን 2010 ዓ ም ደግሞ በድሬዳዋ፥ ሰመራ፥ አሳይታ እና ጅግጅጋ ከተሞች ተመሳሳይ የለውጡና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የድጋፍ ሰልፎች ተከናውነዋል።

በተለይ የአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ የተደረገው ህዝባዊ ሰልፉ እጅግ የደመቀ፥ ብዙ ህዝብ የተገኘበት፥ የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከት እና ፍላጎች ያላቸው አካላት በአንድነት በመሆን የተለያዩ ሐሳቦች የተንፀባረቁበት ልዩ ህዝባዊ ሰልፍ በመሆኑ በኢትዮጵያ ታሪክ አዲስ ክስተት ነው። ከዚህ ቀደም ዛሬም ድረስ ሥልጣን ላይ ያለውን እና በምርጫ ሥልጣን ለመልቀቅ ፈቅደኛ ያልሆነውን ገዥውን ኢህአዴግን በመቃወም እና ተፎካካሪውን ፓርቲ ቅንጅት በመደገፍ የተደረገው የሚያዝያ 30 ቀን 1997 ዓ.ም. ሰልፍ በርካታ ህዝብ የተገኘበት ሆኖ የተመዘገበ ነበር። ይሁን እንጂ ቅዳሜ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ ም የተደረገው ሰልፍ ግን በበጎ ፈቃድ ግለሰቦች ተነሳሽነት የተከናወነ፥ በኢትዮጵያ ታሪክ ብዙ ህዝብ የተሳተፈበት፥ የትኛውምን የፖለቲካ ፓርቲ ፍላጎት ምክንያት ወይም ተገን ያላደረገ፥ ይልቁንም ሁሉንም የፖለቲካ ኃይሎች ያካተተ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድን በመደግፍ የተደረገ ታላቅ ህዝባዊ ሰልፍ በመሆኑ በሀገሪቱ ታሪክ ልዩ ሥፍራ ይኖረዋል ተብሎ ይታሰባል። በሰልፉ ላይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ተገኝተው ንግግር ያደረጉ ሲሆን፥ በዕለቱም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን፥ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ የሆኑት ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል እና ሌሎች ባለሥልጣናትም ተገኝተው ነበር።

ይሁን እንጂ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ለደጋፊዎቻቸው የሰልፉ ታዳሚዎች እንደወትሮ ህዝቡን ያስደመሙና ያስደሰቱ ንግግሮችን አድርገው ጨርሰው በተቀመጡ በሁለት ደቂቃዎች ውስጥ በቅርብ ርቀት የቦንብ ፍንዳታ ተሰማ። የቦንብ ፍንዳታው የተከሰተው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ካሉብት መድረክ በስተቀኝ በአማካይ 40 ሜትር ርቀት አካባቢ እንደሆነ የዓይን እማኞች የገለፁ ሲሆን፤ ድርጊቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ የተቃጣ የግድያ ሙከራ እንደነበር ታምኗል። በወቅቱም በፍንዳታው አቅራቢያ ሌላ ተጨማሪ ፍንዳታ ሊያከናውኑ ነበር የተባሉ ተጠርጣሪዎች መካከል ሁለት ሴቶች ራሳቸውን የአዕምሮ ህሙማን በማስመሰልና ራሳቸውን የጣሉ ሰዎች አለባበስ በመልበስ ተጨማሪ ቦንብ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደሚገኙበት መድረክ ለመወርወር ከቦርሳችው ውስጥ ቦንብ ሲያወጡ ከነፖሊስ የደንብ ልብስና የትጥቅ መያዣ በሰልፉ ታዳሚዎች እጅ ከፍንጅ ተይዘው እንዳስጣሏችውና ደብድበው ለፖሊስ አሳልፈው እንደሰጧቸው እማኞች በፎቶና ቪዲዮ የታገዘ መረጃ አስደግፈው ይፋ አድርገዋል።

Police car at Meskel square incident
አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ የአደጋው ተጠርጣሪዎች የፖሊስ ባልደረባ አካላት ነበሩበት በሚል በህዝቡ የተያዘና ጉዳት የደረሰበት የፖሊስ ተሽከርካሪ (ፎቶ፡ ከዕለቱ ማኅበራዊ ገፆች የተወሰደ)

ከአደጋው ጋር በተያያዘ ከተያዙ ሴቶች በተጨማሪ በተመሳሳይ ቦታና ሰዓት አንድ የፖሊስ ባልደረባ አባል ከመድረኩ በስተጀርባ ባለ ህንፃ ላይ በፍጥነት በመውጣት ተጨማሪ ቦንብ ሊያፈነዳ ሲሞክር አካባቢው ላይ ሰልፉን እንዲያስተባብሩ እና የህንፃውን መግቢያና መውጫ እንዲቆጣጠሩ በተመደቡ የአዲስ አበባ ወጣቶች መያዙ ታውቋል። በኤግዥቢሽን ማዕከል አካባቢ ደግሞ የወታደራዊ መገናኛ ሬዲዮ በወጣቶች ተይዞ ለሚምለከተው የፖሊስ አካል ተላልፎ መሰጠቱ ተሰምቷል። በሰልፉ በቅርብ ርቀት የነበረና የአንዱ ተጠርጣሪ ፖሊስ ይዞት የነበረው የፖሊስ መኪና ባልታወቁ ሰዎች ወዲያው እንዲቃጠል የተደረገ ሲሆን፤ ከውስጡም የቦንብና ፈንጅ ማስቀመጫ ሳጥን መሰል ሻንጣ በሰልፉ ታዳሚዎች መያዙ ታውቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ፍንዳታው መድረኩ አቅራቢያ ከመከሰቱ አስቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሰልፉ ከመምጣታቸው በፊት ህዝቡ በብዛት ከሚገኝበት የአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ባለ የሰልፉ መግቢያ በር ላይ ከአንድ ወጣት ጋር የነበረች አንዲት ሴት ተለቅ ባለ የእጅ ቦርሳ ይዛ ያልተለመደ እንቅስቃሴ በማድረጋቸው ጥርጣሬ ባደረባቸው የሰልፉ ታዳሚ ወጣቶች ተይዛ ስትፈተሽ ቦርሳዋ ውስጥ ቦንቦችን የያዘ ሸራ ጋር ይዛ በመገኘቷ አብሯት ከነበረ ወጣት ጋር አንድ ላይ ለፖሊስ ማስረከባቸው ተጠቁሟል።

በዕለቱ ወደ ሰልፉ ስፍራ ለመግባት እንደከዚ ቀደሙ በሁሉም የአደባባዩ መግቢያ እያንዳንዱ ሰው በአማካይ ለሶስት ጊዜ ያህል በተለያየ ርቀት በፖሊስ ተደጋጋሚ ጥብቅ ፍተሻ እንደተደረገ የተገለፀ ሲሆን፤ አደጋውን ያደረሱ አካላት እንዴትና በምን ያንን ተደጋጋሚ ጥብቅ ፍተሻ አልፈው መድረኩ አቅራቢያ እንደተገኙ የብዙዎች ጥያቄ ሆኗል። ከዚህ ቀደም በዛ መድረክ በየዓመቱ መሪዎች በሚገኙበት የተለያዩ ፖለቲካዊና ኃይማኖታዊ ዝግጅቶች ቢደረጉም፤ በሀገሪቱ ታሪክ ተመሳሳይ አደጋ ተከስቶ አያውቅም ነበር። በዕለቱ በደረሰ የቦንብ ፍንዳታ አደጋ እስካሁን የ2 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ 135 ሰዎች ከባድና ቀላል የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መረጃ አመልክቷል።

የቦንብ ጥቃቱን ተከትሎም ከህዝባዊ ሰልፉ ውስጥ እጅ ከፍንጅ የተያዙትን ጨምሮ 6 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ውለው የነበረ ቢሆንም፤ በተሳሳተ ጥቆማ አብሮ ተይዞ ነበር የተባለው ዲያቆን በፅሐ ለ10 ዓመታት በቄራ ጎፋ ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል አገልጋይና በአካባቢው ሰዎች በመልካም ስነምግባሩ የሚታወቅ እንደሆነ በመግለፅ በተደረገ ምርመራ የተሳሳተ ጥቆማ መሆኑን በመጥቀስ ፖሊሴ ወዲያው ለቆታል። እጅ ከፍንጅ እንደተያዙ የተገለፁት ቀሪዎቹ 5 ተጠርጣሪዎችን ጨምሮ ከጥቃቱ ጋር ንክኪ አላላቸው በሚል እስካሁን 30 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላችውን የፌደራል ፖሊስ ዋና ኮሚሺነር ዘይኑ ገልፀዋል። ከአደጋው ጋር በተያያዘ ሌሎች ተጠርጣሪዎችም በፖሊስ እየተፈለጉ እንደሆነም ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ከህዝባዊ ሰልፉ ጥበቃ ላይ ክፍተት አሳይተዋል በሚል የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ግርማ ካሳን ጨምሮ 9 የአዲስ አበባ እና የፌደራል ፖሊስ አባላት በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሆነ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ አህምድ ሸዴ ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርገዋል። ዘግይቶ በወጡ መረጃዎች ከአደጋው ጋር በተያያዘ የብሔራዊ ደህንነት አገልግሎት ምክንትል ኃላፊና የሀገር ውስጥ ጉዳይ የደህንነት ኃላፊም በቁጥጥር ስር መዋላቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ በአደጋው ቅንብር እጃቸው አለበት በሚል ሌሎች ተጠርጣሪዎች በተለይም ከፌደራልና ከክልል የፀጥታ አስከባሪ አካላት በቁጥጥር ስር ሊውሉ እንደሚችሉ ይጠበቃል።

በአደጋው ሰለባ ከሆኑ ሰኣላምዊ የሰልፉ ታዳሚዎች በስተቀር ጉዳት የደረሰበት ባለሥልጣን እንደሌለ ለማወቅ ተችሏል። ከአደጋው የተረፉት ጠቅላይ ሚኒስትሩም በዕለቱ በቤተመንግሥት መግለጫ የሰጡ ሲሆን፤ ከሁለት ሰዓታት ቆይታ በኋላም በአደጋው ጉዳት ደርሶባቸው በጥቅር አንበሳ፥ ዘውዲቱ እና ያቤፅ ሆስፒታል ህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው የሚገኙ ተጎጂዎችን ሄደው ጎብኝተዋል። በተመሳሳይም እሁድ ሰኔ 17 ቅቀን 2010 ዓ.ም. የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾሙ የአደጋው ሰለባ የሆኑትን በየሆስፒታሉ በመገኘት ጎብኝተዋቸዋል።

አደጋውንም ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ፥ በቅርቡ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አበይ አህመድ የተደረገውን የሰላም፥ የይቅርታና እርቅ ጥሪን ተከትሎ ሁለገብ ትግል ያደርግ የነበረውና ማንኛውንም የአመፅ እንቅስቃሴ በይፋ ማቆሙን ያወጀው ተቀናቃኙ አርበኞች ግንቦት 7 እንዲሁም ሰማያዊ ፓርቲን ድርጊቱን ኮንነው አውግዘውታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ እና የኢትዮጵያ የሰላም፥ የፍቅር፥ የይቅርታና አንድነት ተስፋ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለጫችው አስታውቅዋል። መንግሥት የአደጋውን ፈፃሚዎችና ተባባሪዎች ተከታትሎ ለህግ እንደሚያቀርብ በመግለፅ ወንጀሉ በማን እና ለምን ዓላማ እንደተቀነባበረ የፖሊስ ምርመራ ሲጠናቀቅ ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ አስታውቋል።

የተፈፀመውን የቦንብ ጥቃት የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጽሐፊ፥ የአፍሪካ ህብረት ፕሬዘዳንትና ኮሚሽነር፥ በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ቢሮ፤ የጅቡቲ፥ የኬንያ፥ የሶማሊያ እና የኤርትራ መንግሥታት በዕለቱ ድርጊቱን ኮንነው አውግዘዋል።

የዋልድባ መነኮሳት ክሳቸው ተቋረጦ ከእስር ተለቀቁ

በፌደራል አቃቤ ህግ በሽብር ወንጀል ተከሰው ለበርካታ ወራት ታስረው የነበሩት የዋልደባ መነኮሳት ከእስር ተፈቱ። መነኮሳቱ ከዋልደባ ገዳም ታፍነው ለበርካታ ወራት ታስረው ጉዳያቸው በፍደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ሲታይ ቆአይቶ በመጨረሻም ክሳቸው ተቋርጦ ተፈተዋል።

Waldeba Monastry arrested monks
መነኮሳቱ ልደታ ፍርድ ቤት ሳሉ

መነኮሳቱ በአዲስ አበባ በሚገኘው ቃሊቲ ፌደራል ወህኒ ቤት ባሉ የጥበቃና የደህንነት አባላት ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈፀምባቸው እንደነበር አብቱታዎቻቸውን ለፍርድ ቤት ሲያቀርቡ እንደነበር ይታወሳል።

መነኮሳቱ አባ ገብረኢየሱስ ኪዳነ ማርያም፥ አባ ገብረሥላሴ ወልደኃይማኖት፥ መርጌታ ዲበኩሉ እንዲሁም አቶ ለገሰ ወልደሐና፥ አቶ ሀብታሙ እንየው ጨምሮ 114 የፖለቲካ እስረኞች ክሳቸው ተቋርጦ ከታሰሩበት ወህኒ ቤት ተለቀዋል።

በመጨረሻም፤ መነኮሳቱ ከእስር በመፈታታቸውን ፈጣሪን በማመስገን አሁንም በርካታ ዜጎች ፍርድ ቤት እንኳ ሳይቀርቡ ለዓመታት በውህኒ ቤት ያሉ እንዳሉ እና ሀገሪቱ ኢትዮጵያ እና ኃይማኖታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እስር ላይ እንዳሉ በማስታወስ ሁሉም ከእስር ነፃ ካልወጡ ራሳቸውን ከእስር እንደተፉ እንደማይቆጥሩ ተነግረዋል።