Tag Archives: Ogaden Ethiopia

የቀድሞ የሶማል ክልል ፕሬዘዳንት አቶ አብዲ መሐመድ ዑመር ን ጭምሮ 47 ተጠርጣሪዎች ክስ ተመሰረተባቸው

በጅጅጋና አካባቢው በተፈጠረው ብጥብጥና ሁከት አብዲ መሀመድ ዑመር (አብዲ ኢሌ)ን ጨምሮ 47 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ተመሰረተባቸው።
abdimehommedumer28abdiilley29
የቀድሞ የሶማሌ ክልል ፕሬዘዳንት (ፎቶ፤ ናሆም ተስፋዬ_ሪፖርተር)

በ1ኛ ክስ ከ1-26 ያሉ ተከሳሾችን ሚመለከት ሲሆን ለጊዜው ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን በቀጥታ ወይም በመላ አሳባቸውና አድራጎታቸው የወንጀሉ ድርጊትና የሚሰጠውን ውጤት ሙሉ ተካፋይ በመሆን ድርጊቱን የራሳቸው በማድረግ በህብረትና በማደም በሶማሌ ክልል ከሰኔ ወር 2010 ዓ.ም እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ቀናቶች በክልሉ ውስጥ አንዱ ወገን በሌላው ነዋሪ ላይ ጥቃት በመፈፀም እና አለመረጋጋት በመፍጠር ተሳትፈዋል በሚል በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየታየ ይገኛል። ተጠርጣሪዎቹ በአካባቢው በተለምዶ ሀበሻ በሚል በሚጠሯቸው የክልሉ ነዋሪዎችና በሶማሌ ማኅበረሰብ መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር ተንቀሳቅሰዋል በሚል ክስ ቀርቦባቸዋል።

ተከሳሾቹ በግጭቱ ውስጥ የሚሳተፉ ሄጎ በሚል ስያሜ ወጣቶችን በማደራጀት፤ የተደራጀውን የሄጎ ቡድን በገንዘብ እና በተለያዩ ቁሳቁሶች በመደገፍ፣መሳሪያ በማስታጠቅ፣ ግጭቱ የሚመራበትና መልዕክት የሚተላለፍበት ሄጎ ዋሄገን (Heego waaheegan) የሚል በፌስቡክ ገጽ በመክፈትና በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ ሰዎችን ለግጭት ሊያነሳሳ የሚችሉ ይዘት ያላቸው መልእክቶችን በማሳተም እንዲሁም በክልሉ ውስጥ የጥቃቱ ዒላማ የተደረጉ ነዋሪዎችን መግደል ፣ንብረታቸውንም መዝረፍ እና ማውደም፣ባንኮችን እና ኢንሹራንሶችን መዝረፍ ፣ቤተክርስቲያኖችን እና ነዳጅ ማደያዎችን ማቃጠል አለብን በማለት በየቦታው ተንቀሳቅሰው ትእዛዝ በመስጠት በክልሉ ውስጥ ግጭት እንዲነሳ በማድረግ፥ የሰው ህይወት እንዲጠፋ ፣ በመንግስት እና በእምነት ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ ፣ ሴቶች እንዲደፈሩና እና በርካታ የከተማው ነዋሪ እንዲፈናቀሉ ማድረጋቸው በክሱ ላይ ተገልጿል፡፡

በ2ኛ ክስ ደግሞ ከ27-47 ያሉ ተከሳሾች በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በጠተቀሰው ቀን በክልሉ ውስጥ አንዱ ወገን በሌላው ወገን ላይ የጦር መሳሪያ እንዲያነሳ ለማድረግ በማሰብ በሶማሌ ብሔር ተወላጆች እና በሶማሌ ክልል የሚኖሩ ከሶማሌ ብሔር ተወላጅ ውጭ በተለምዶ በአካባቢው አጠራር ሀበሻ በሚል በሚጠሯቸው የክልሉ ነዋሪዎች መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር በማሰብ ሄጎ በሚል ስያሜ ወጣቶችን በማደራጀት ፣መሳሪያ በማስታጠቅ ሰዎችን ለአመፅ ሊያነሳሱ የሚችሉ መልእክቶችን በመቅረጽ እና የሄጎ አደረጃጀት ውስጥ አባል እና አመራር በመሆን ከሐምሌ 28 ቀን 2010 እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2010 ዓ.ም በክልሉ በተፈጠረው ግጭት ውስጥ የተለያዩ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ መሳሪያዎችን በመያዝ በግጭቱ በመሳተፍ የሰው ህይወት እንዲጠፋ ፣ በመንግስት እና በእምነት ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ ፣ሴቶች እንዲደፈሩና እና በርካታ የከተማው ነዋሪ እንዲፈናቀል አድርገዋል፡፡

የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎትም ተጠርጣሪዎች አቃቤ ህግ የመሰረተባቸውን ክስ በእጃቸው አንዲደርሳቸው መደረጉም ተጠቁሟል። ፍርድ ቤቱም ተከሳሾቹ በጉዳዩ ላይ ከጠበቆቻቸው ጋር ተነጋግረው መልስ ይዘው እንዲቀርቡ ጥር 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል። ተጠርጣሪዎቹም አዲስ አበባ በሚገኘው ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የደህንነት ችግር እንዳይገጥማቸው ለፍርድ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን፤ ፍርድ ቤቱም ወደፊት ከጠበቆቻቸው ጋር በመነጋገር በሚቀርቡ አቤቱታዎች ተመስርቶ ውሳኔ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡

በተለይ ባለፉት 27 ዓመታት ሶማሌ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ በርካታ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችና ጥቃቶች በመንግሥት አመራር አካላት ትዕዛዝና እውቅና ይፈፀሙ እንደነበር መዘገቡ ይታወሳል። መረጃው የፍደራሉ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ነው።

በርካቶችን ለሞት የዳረገው የኦሮሚያ – ሶማሌ ግጭት እስከ ትናንት አለመቆሙን መንግስት አስታውቋል

አለማየሁ አንበሴ
Abdi,kassa & Lemma
አቶ አብዲ መሐመድ፥ እቶ ካሳ ተክለብርሃን እና አቶ ለማ መገርሳ

በኦሮሚያ እና በሱማሌ ክልሎች መካከል የተፈጠረው ግጭት እንደቀድሞ የወሰን ጉዳይ እንዳልሆነ የተጠቆመ ሲሆን፣ ትክክለኛ መንስኤው እየተጣራ መሆኑን ያስታወቁት የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ፤ ግጭቱ እስከ ትናንት አርብ ድረስ በተለያዩ ቀበሌዎች መቀጠሉንና በርካቶች ተገድለው፣ ከ20 ሺህ በላይ ዜጎች መፈናቀላቸውን አስታውቀዋል፡፡

ለበርካታ ቀናት በቀጠለ ግጭት፤ የሠው ሕይወት ጠፍቷል፣ ንብረት ወድሟል፣ ዜጎች ተፈናቅለዋል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ግጭቱ በቅርቡ እንዲገታ ይደረጋል፤ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎችም በመሃል ገብተው የማረጋጋት ስራ ይሠራሉ ብለዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለ ማርያም ደሣለኝ፤ ከሁለቱ ክልል አመራሮች ጋር በግጭቱ ላይ በስልክ ውይይት ማድረጋቸውንና ግጭቱ እንዲቆም ማሣሠቢያ መስጠታቸውንም ሚኒስትሩ አስታውቀዋል፡፡
በአካባቢው ለግጭቱ መባባስና ለሠው ህይወት መጥፋት ምክንያት የሆኑ ለህግ እንዲቀርቡ ይደረጋል ያሉት ሚኒስትሩ፤ የመሳሪያ ትጥቅ የማስፈታት ስራም ይሰራል ብለዋል፡፡

የመከላከያ ሰራዊትና የፌደራል ፖሊስ በግጭቱ መሃል ገብቶ ለማረጋጋት ለምን ዘገየ ተብለው የተጠየቁት ሚኒስትሩ፤ ክልሎቹ ችግሮቹን በራሳቸው ይፈቱታል የሚል እምነት በመጣሉ ነው ብለዋል፡፡
በግጭቱ የሶማሊያ ሪፐብሊክ ኃይሎችና የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል መሳተፋቸው ተጣርቶ ህጋዊ እርምጃ ይወስዳል ብለዋል – ሚኒስትሩ፡፡ ግጭቱ በታጠቁ አካላት የታገዘ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትሩ፤ እነዚህ የታጠቁ አካላት እነማን ናቸው የሚለው ግን እስካሁን ምላሽ አለማግኘቱንና በማጣራት ሂደቱ እንደሚታወቅ ተናግረዋል፡፡ ግጭቱ የህዝብ ለህዝብ አለመሆኑን ግን አስረግጠው በመግለፅ፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የሁለቱ ክልሎች የመንግስት ኮሚኒኬሽን ኃላፊዎች ጉዳዩን አስመልክቶ በየሚዲያው የሚያስተላልፏቸው መግለጫዎች፣ ግጭቱን ሊያባብሱ የሚችሉ በመሆኑ ከእንግዲህ በኋላ ግጭት አባባሽ መግለጫዎችን ከመስጠት እንዲቆጠቡ ዶ/ር ነገሪ አሳስበዋል፡፡

የኮሚኒኬሽን ኃላፊዎቹ ከዚህ ድርጊታቸው የማይቆጠቡ ከሆነ፣ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድም ሚኒስትሩ ጠቁመው፤ በሁለቱም የሚገለፁ አሃዛዊ መረጃዎችንም ገና ያልተጣሩ መሆናቸውንና መንግስት ሁኔታውን አጣርቶ እንደሚገልፅ አስታውቀዋል፡፡

የሶማሌ ክልል ግጭቱን አስመልክቶ ለቪኦኤ በሰጠው መግለጫ፤ በአወዳይ ከተማ 50 ሠዎች መገደላቸውን ሲገልፅ፣ የኦሮሚያ ክልል በበኩሉ፤ በአወዳይ ከተማ 18 ሰዎች መገደላቸውን፣ ከነዚህ ውስጥ 12ቱ የሶማሌ ተወላጆች፣ ቀሪዎቹ የኦሮሞ ጃርሶ ጎሣ አባላት መሆናቸውን አስታውቋል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋ ትናንት ምሽት ባሰራጩት መረጃ፤በሰሞኑ ግጭት ከተፈናቀሉት ከ22ሺ በላይ ዜጎች በተጨማሪ አጠቃላይ የድንበር ግጭቱ ከተከሰተበት ከ2009 ጀምሮ 416ሺ807 ዜጎች መፈናቀላቸውን አስታውቀዋል፡፡

በአወዳይ የደረሠውን ግጭት ተከትሎ፣ ከሶማሌ ክልል ከ21 ሺህ በላይ ዜጎች ተፈናቅለው በጭናቅሠን፣ ባቢሌና ሐረር ከተሞች ተጠልለው እንደሚገኙ የኦሮሚያ ክልል ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋንና ምንጮቹን ጠቅሶ ቪኦኤ ዘግቧል፡፡

የሱማሌ ክልል የመንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ኢንድሪስ አህመድ በበኩላቸው፤ “ሰዎች ከአካባቢው የተፈናቀሉት በግዴታ ሳይሆን በፍቃዳቸው ነው፤ ጥቃት አልተፈፀመባቸውም” ብለዋል፡፡ ምንጮች በበኩላቸው፤ የግዳጅ ማፈናቀል መፈፀሙንና በዜጎች ላይ ድብደባና እንግልት እንደደረሰባቸው ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል፡፡

የሱማሌ ክልል መንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ኢንድሪስ አህመድ፤ በአወዳይ ከተማ የደረሰውን ግድያ ተከትሎ ባስተላለፉት መግለጫ፣ የኦሮሚያ ክልል መንግስትን “የአሸባሪነት አላማ አራማጅ” በሚል የፈረጀ ሲሆን የኦሮሚያ ክልል ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ ፍረጃውን አጣጥለው፣ ከአንድ ክልልን ከሚያስተዳድር አካል የማይጠበቅ ነው ብለዋል፡፡

የሶማሌ ክልል መንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ ለቪኦኤ በሰጡት መረጃ፤ በአስራ አንድ የሶማሌ ወረዳዎች፣ ማንነታቸው ባልታወቀ አካላት በተሠነዘሩ ጥቃቶች፣ ከሁለት መቶ አስራ ሶስት ሰዎች በላይ ህይወት ማለፉን አስታውቀዋል፡፡ ይሄን ተከትሎም የሶማሌ ክልላዊ መንግስት፣ ለ5 ቀናት የሚቆይ ብሄራዊ የሃዘን ቀናት በክልሉ ማወጁንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ፣የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን የግጭቱን መነሻና የደረሰውን ጉዳት የሚያጣራ ቡድን ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ወደ አካባቢው መላኩንና ማጣራት መጀመሩን የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደምሰው በንቲ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡

ሰሞኑን የሁለቱ ክልሎች የመንግስት ኮሙኒኬሽን ኃላፊዎች በማህበራዊ ድረ-ገፆቻቸው የሚያሰፍሯቸው የእርስ በርስ ውንጀላዎች አስደንጋጭና ግጭቱን የሚያባብሱ መሆናቸውን አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡ ክልላዊ መንግስታቸውን ወክለው መልዕክት የሚለዋወጡ እንደማይመስሉና ኃላፊነት የጎደሏቸው እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ምንጭ፡ አዲስ አድማስ

%d bloggers like this: