የተራራቁት የለውጥ ዕይታዎች

Ethiopian politics ECA August 2019

ነአምን አሸናፊ

ሐሙስ ነሐሴ 16 እና ዓርብ ነሐሴ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የስብሰባ ማዕከል በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያላቸው የፖለቲካና የአካዳሚክ ልሂቃን በአገሪቱ ጅመር የለውጥ ሒደት፣ ዕድሎች፣ ፈተናዎችና ሥጋቶች ላይ የሁለት ቀናት ውይይት አድርገው ነበር፡፡ በዚህ ለሁለት ቀናት በቆየው ውይይት መድረክ ላይ በለውጡ ዙሪያ የተለያየ ሐሳቦች የተሰነዘሩ ሲሆን፣ በተለይ በሁለተኛ ቀን ውሎ ሦስት ፖለቲከኞችን በአንድ መድረክ ያገናኘው ውይይት የብዙዎችን ቀልብ የሳበ ነበር፡፡ በሁለተኛው ቀን ውይይት ሐሳባቸውን ያጋሩት ተወያዮች በለውጡ ላይ ያላቸውን አተያይ ያስረዱ ሲሆን፣ የግለሰቦቹ ምልከታ በራሱ በለውጡ ላይ አንድ ወጥና ተመሳሳይ አቋም፣ እንዲሁም አረዳድ ላይ አለመደረሱን አመላካች ነበሩ፡፡ በምሥሉ ላይ ከግራ ወደቀኝ አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ጌታቸው ረዳና አቶ ልደቱ አያሌው ከአወያያቸው ወ/ሮ ፀዳለ ለማ ጋር ይታያሉ፡፡

ለውጡን አስመልክቶ ያሉ አተያዮች

ሐሙስ ነሐሴ 16 እና ዓርብ ነሐሴ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. በአገሪቱ የፖለቲካ ምኅዳር ተሳታፊ የሆኑ ፖለቲከኞችና በፖለቲካ ሒደቱ ላይ የተለያዩ ምርምሮችን ያካሄዱና ጽሑፎችን ማቅረብ የቻሉ ምሁራን፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ቅጥር ግቢ ውስጥ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት የተከሰተውን ለውጥ አስመልክቶ ለመወያየትና አሁን ያለበትን ደረጃና ፈተናዎች ለመተንተን ለስብሰባ ተቀምጠዋል፡፡

ይህን የውይይት ኮንፈረንስ ያዘጋጁት ኢንተር አፍሪካ ግሩፕ፣ የምክክር የጥናትና ትብብር ማዕከል፣ አማኒ አፍሪካ፣ ቤርጎፍ ፋውንዴሸን፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ስትራቴጂክ ጥናት ማዕከል ሲሆኑ፣ የሁለት ቀናቱን የውይይት መድረክ በንግግር የከፈቱት ፕሬዚዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ ነበሩ፡፡

ከ1960ዎቹ የፖለቲካ ተዋንያን አንስቶ እስከ ቅርብ ጊዜ እስከ ተመሠረቱት ፓርቲ አባላትና አመራሮች በውይይት መድረኩ ላይ የተገኙ ሲሆን፣ አንጋፋ ምሁራን እንዲሁ ‹‹የኢትዮጵያ የለውጥ ሒደት ወቅታዊ ቁመናው፣ መፃኢ ዕድሎቹ፣ ፈተናዎቹና ሥጋቶቹ›› በሚል ርዕስ ለተዘጋጀው መድረክ የልምዳቸውን ለማካፈል ተሰይመዋል፡፡

ከእነዚህ የአገር ውስጥ ምሁራንና ፖለቲከኞች በተጨማሪም፣ የዓለም አቀፍ የለውጥ ተሞክሮዎችን ለማውሳትና ልምዳቸውን ለማካፈል የውይይቱ አካል ነበሩ፡፡ በዚህም መሠረት በቱኒዚያ ሕዝባዊ አመፅ ማግሥት በተቋቋመው ሕዝባዊ የውይይት ምክር ቤት አባል የነበሩ፣ የየመን ሕዝባዊ የውይይት ምክር ቤት አባል የነበሩ ሁለት ተወካዮች በለውጥ ሒደት ውስጥ የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን እንዴት መፍታት እንደሚቻልና እንደሚገባ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከሽግግር አስተዳደር ጋር በተያያዘ በርካታ ምርምሮችን ያደረጉት ማይክል ሉንድ ገለጻ አድርገዋል፡፡

ምንም እንኳን በመጀመርያው ቀን የውይይቱ ውሎ ለውይይቱ ከተሰጠው ርዕስ አንፃር የለውጡን ፈተናዎች፣ ተግዳሮቶችና መልካም ዕድሎችን አስመልክቶ በዝርዝር የቀረበ የውይይት ሐሳብ ባይኖርም፣ በታዋቂው የታሪክ ምሁር ገብሩ ታረቀ (ፕሮፌሰር) አወያይነት፣ እንዲሁም በሌላው ታዋቂው የታሪክ ምሁር ባህሩ ዘውዴ (ፕሮፌሰር) እና የቀድሞው የመኢሶን መሥራችና መሪ በነበሩት በአቶ አንዳርጋቸው አሰግድ መነሻ ሐሳብ አቅራቢነት ኢትዮጵያ ያመከነቻቸውን የለውጥ ዕድሎች አስመልክቶ ገለጻና ውይይት ተደርጓል፡፡

የመጀመርያ ዕለት ውሎ በእነዚህ አጠቃላይ ሐሳቦችና ጉዳዮች ሲወያዩና ውይይቱን ሲያዳምጡ የነበሩ ተሳታፊዎች፣ በሁለተኛው ቀን ግን አሁን አገሪቱ ካለችበት የፖለቲካ ሁኔታ አንፃር አንገብጋቢ የሆኑ ጉዳዮች የተዳሰሱበት የሦስት ፖለቲከኞችን ውይይት በተመስጦ አዳምጠዋል፡፡ ከማዳመጥ ባለፈም የምሣ ሰዓትን እስከ መግፋት የደረሰ ጥያቄና መልስ፣ ውይይትና ሙግት አካሂደዋል፡፡

በሁለተኛው ቀን የከፍተኛ ፖለቲከኞችና ምሁራን ውይይት በለውጡ ወቅታዊ ቁመና፣ ፈተናዎቹና ዕድሎቹ ዙሪያ ያላቸውን አተያይ እንዲያቀርቡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) እና የዝሕባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ ጌታቸው ረዳ፣ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ታዋቂውን ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌውን በመድረኩ ሰይሟል፡፡

እነዚህ ሦስት ፖለቲከኞች ከሚወክሉት የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም አንፃር፣ ለውጡን አስመልክቶ ሊለዋወጡ የሚችሉት ሐሳብ ከመጀመርያው ቀልብን የሳበ ነበር፡፡

ባለፈው አንድ ዓመት ተኩል በአገሪቱ እየተካሄደ ባለው ለውጥ ምንነት ዙሪያ ሦስቱም ሐሳብ ሰንዛሪዎች የተለያየ አረዳድ እንዳላቸው የገለጹ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ግን ሒደቱ በጀመረበት ፍጥነት ካለመጓዙም በላይ ሊቀለበስ እንደሚችል ሥጋታቸውን አጋርተዋል፡፡ ሆኖም ሦስቱም ተናጋሪዎች አሠራሮችን ዳግም ለማየት ከተሞከረ ሒደቱን ከመቀልበስ አደጋ መታደግም እንደሚቻል አውስተዋል፡፡

ለውጡን ለመተርጎም በመሞከር ንግግራቸውን የጀመሩት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ለውጥ የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ላይ በሒደቱ ተዋናይ የሆኑት ቡድኖች ወጥ ትርጓሜ እንደሌላቸው አውስተዋል፡፡ ለዚህም በምዕራባውያን ስለለውጡ የሚሰጠው ትርጓሜና በኢትዮጵያውያን ፖለቲከኞች ዘንድ የሚሰጠው ትርጓሜ ለየቅል መሆኑን በማውሳት ነው፡፡

‹‹የፖለቲካ ምኅዳሩን ማስፋት በሚሉ በጣም አጓጊ ቃላት የሚታጀብ ቢሆንም፣ በዋነኛነት የምዕራባውያን የለውጥ ጽንሰ ሐሳብ ተቋማትን ወደ ግል ይዞታ ብቻ ሳይሆን ወደ ምዕራባውያን የግል ይዞታ ከማዞር አንፃር ብቻ ነው የሚያዩት፤›› በማለት፣ የምዕራባውያንን አረዳድ ገልጸዋል፡፡

በተመሳሳይ ደግሞ፣ ‹‹በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ኃይሎች የራሳቸው ውስንነት ቢኖራቸውም ለውጥ ሲሉ የፖለቲካ ምኅዳር መስፋትን፣ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት መጠናከርን፣ በግለሰብና በቡድን ነፃነትና መብቶች መካከል ያለውን ሚዛን መጠበቅ፣ አገራዊ ማንነትና ብሔራዊ ማንነትን ማመጣጠን የሚሉ በርካታ ነገሮችን ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፤›› በማለት፣ በአገራዊውና በውጭው ኃይሎች መካከል ያለውን የጉዳዩን አረዳድ አስረድተዋል፡፡

ከዚህ አንፃር እነዚህ ውስንነት ያሉበትን ጽንሰ ሐሳብ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደተፈታና ስምምነት እንደተደረሰበት አድርጎ ማቅረቡ በራሱ ችግር አለበት በማለት፣ በጉዳዩ ላይ የጠራ አቋም መያዝ አስፈላጊነት ላይ ተናግረዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ አቶ ጌታቸው የለውጡ ባለቤትነት ጥያቄ ያስከተላቸው ውዥንብሮች በራሱ የለውጡ ተግዳሮት እንደሆነ በመግለጽ፣ በዋነኛነት ግን ለውጡ የኢሕአዴግ ነው በማለት በተለያዩ መድረኮች በተደጋጋሚ የሚገልጹትን አቋማቸውን በዚህ መድረክም አራምደውታል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘም፣ ‹‹አመራሩ በጋራ አንድ ላይ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ ሲያበቃ በተወሰኑ የአመራር አካላት ግን ለውጡ የእኔ ነው ወደሚል ሁኔታ ተሂዷል፡፡ ስለዚህ ለውጡ የማን ነው የሚለው ጥያቄ ችግር ያለበት ነው፡፡ እዚህ መግለጽ ካለብን ለውጡ የሕዝብ ጥያቄ ያመጣው፣ ግን ደግሞ ኢሕአዴግ በሕዝብ ግፊትም ቢሆን ተገዶ ይህን ካላደረግኩ በስተቀር አገር ይፈርሳል ብሎ አምኖ የተቀበለው ነው፤›› ተብሎ መወሰድ እንዳለበት ሞግተዋል፡፡

ለውጡ የሕዝቡ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው የለውጡ ችግሮች ያሏቸውን ሐሳቦችም አያይዘው አቅርበዋል፡፡ ከነዚህ ችግሮች መካከል ለውጡ ኢሕአዴግን እንደ ፓርቲ ማግለሉ፣ የአመራሩ እውነታን መሸሽ፣ በየሥፍራው የታጠቁ ኃይሎች መበራከት፣ እንዲሁም ድሮም ጠንካራ ያልነበሩት ተቋማት ከለውጡ ወዲህ ይበልጥ መልፈስፈሳቸውን እንደ ችግር በመጥቀስ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሳም፣ ‹‹አሁን ባለንበት ሁኔታ ለውጡ ፈተና ውስጥ የገባ ነው የሚል እምነት አለኝ፤›› ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ ለውጥ መደረግ አለበት ብሎ ያምናል፡፡ ከአሁን በፊት የሠራቸው ጥፋቶች መቀጠል አለባቸው የሚል ጤነኛ አዕምሮ ያለው ሰው የለም፡፡ ነገር ግን መልካም ነገሮችን አስቀጥሎ ለአገር ህልውና ቀጣይነት በሚያግዝ መንገድ ለውጥ መደረግ አለበት ብሎ መሥራት አንድ ነገር ነው፡፡ ኢሕአዴግን ወደ ጎን አድርገህ በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ስምና ዝና ላይ የተመሠረተ ለውጥ ለማድረግ መንቀሳቀስ፣ አማራጭ የፖለቲካ አስተሳሰብ ባስቀመጥክበትና በቅጡ የተተረጎመ ጽንሰ ሐሳብ እየመራህ ባለህበት ሁኔታ አሁን በምናየው ደረጃ ለውጡን ማስቀጠል ሳይሆን፣ አገር ትርምስ ውስጥ የሚከት ነገር ውስጥ ነው የሚከተን፤›› ብለዋል፡፡

እነዚህን ሥጋቶች ለማስወገድና ቅቡልነት ያለው መንግሥት እንዲመሠረት ደግሞ የመጪው ዓመት ምርጫ መካሄድ አለበት በማለት አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይ የአገሪቱ ዕጣ ፈንታ ላይ ለመወሰን፣ ‹‹የኢትዮጵያን ሕዝብ አምነን ቢቻል በወቅቱ ካልሆነ እንዲያውም አስቸኳይ (Snap) ምርጫ ማድረግ አለብን፤›› ሲሉ ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡

ብዙ የማያግባቡ የታሪክ ሰበዞች እንዳሉ በመጥቀስ ንግግራቸውን የጀመሩት አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው ደግሞ፣ ‹‹ምንም እንኳን የማያግባቡን በርካታ የታሪክ ክስተቶች ቢኖሩም ቢያንስ ግን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ያለማወቃችን፣ ራሳችን በመረጥነው መንግሥት ተዳድረን አለማወቃችንና የመሳሰሉት ነገሮች የሚያግባቡን የታሪክ ሰበዞቻችን ይመስሉኛል፤›› በማለት፣ አሁንም አገሪቱ ውስጥ የተፈጠረውን ሁኔታ ከታሪካዊ ዳራው ጋር እያያያዙ አብራርተዋል፡፡

ባለፉት 27 ዓመታት ግፍ ያልተፈጸመበት የአገሪቱ ክልል የለም ያሉት አቶ በቀለ፣ የግፉ ደረጃ ግን ከሥፍራ ሥፍራ እንደሚለያይ በመጥቀስ በተለይ ባለፉት ሦስትና አራት ዓመታት ከመሬት ጋር በተያያዘ ጥያቄና አመፅ በመላው ኦሮሚያ በመቀስቀሱ፣ እንዲሁም ይህንና መሰል ጥያቄዎች በአማራ ወጣቶች ዘንድ መፈጠራቸውና በገዥው ፓርቲ ውስጥም ለውጥ ያስፈልጋል የሚሉ አመራሮች መፈጠራቸው፣ አሁን ላለው አጠቃላይ አገራዊ ለውጥ አስተዋጽኦ ማድረጉን አትተዋል፡፡

በገዥው ፓርቲ ውስጥ የተፈጠረው የአሠላለፍ ለውጥ በርካታ ትሩፋቶች ማስከተሉን በዝርዝር ገልጸው፣ የእስረኞች መፈታትን፣ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት ቃል መገባቱን፣ የሰብዓዊ መብት ረገጣ መቆሙን ማወጅ፣ የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች ወደ አገር ቤት እንዲገቡ መደረጉን እንደ ምሳሌ ጠቃቅሰዋል፡፡

ይህን ጊዜ የጫጉላ ሽርሽር ጊዜ በማለት በመጥቀስ በተለይ ከውጭ አገር የገቡ ፓርቲዎች ያራመዷቸው አንዳንድ አቋሞች መፈጠር ሲጀምሩ፣ የለውጥ እንቅስቃሴው እየተቀዛቀዘ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት አገሪቱ አሁን ቅርቃር ውስጥ መግባቷን እንደሚያሳይ ገልጸዋል፡፡

‹‹አገሪቱ አሁን በሁለት ጽንፎች መካከል ተወጥራ የምትገኝ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት ያልተሞከረውን ሁሉን ነገር አጥፍተንና አውድመን እንደ አዲስ ከመጀመር አባዜ ወጥተናል ብለን ተስፋ ባደረግንበት ወቅት፣ አሁን ደግሞ ወደዚያ ሊመልሱን የሚችሉ አዝማሚያዎች እየታዩ ነው፡፡ አንደኛው የሌላውን ሐሳብ ለመቀበል ፈጽሞ ያለ መፈለግና የእኔ ብቻ ነው ትክክል የማለት፣ ቁጭ ብሎ ለመደራደርና ለመነጋገር ያለ መፈለግ አዝማሚያዎች እጅግ በጣም እየገነገኑ መጥተዋል፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

እነዚህ ሁኔታዎችም ለውጡን እየመሩ ላሉ ኃይሎች ከባድ ችግር መፍጠራቸውን በመጥቀስ፣ ‹‹ለውጡ ማዝገም ብቻ ሳይሆን ወደ ኋላ እየተንሸራተተ ያለበት ሁኔታ ነው የሚታየኝ፤›› ብለዋል፡፡

ለውጡ ወደ ኋላ ስለመጓዙ ያቀረቡት መከራከሪያና ምክንያት ደግሞ ከዚህ ቀደም የተቃውሞ ምንጭ የነበረው የመሬት ዘረፋ ተስፋፍቶ እየተከናወነ መሆኑ፣ የሕዝብ መፈናቀል፣ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰዎችን ማሰር መቀጠሉን፣ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መታፈን መጀመራቸው፣ የመሰብሰብና የመደራጀት መብቶች መገደብ የሚሉትን ነው፡፡ ‹‹ስለዚህ ወደ ቀደመው ሥርዓት እየተመለስን መሆናችን በግልጽ እየታየ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

‹‹ስለሆነም ያሉንን ተቋማት ወደ ማደራጀት እንጂ አዲስ ተቋም ለመገንባት መሯሯጥ የለብንም፤›› ብለው፣ እነዚህን የመሳሰሉ ሥራዎች ምርጫውን በጊዜው በማካሄድ የሚመረጠው መንግሥት በሒደት ሊሠራው ይችላል የሚል እምነት እንዳላቸው አብራርተዋል፡፡

በአገሪቱ ባለፈው አንድ ዓመት ተኩል የተከሰተውን ለውጥ በተመለከተ ያለፉት 27 ዓመታት የአገሪቱ የፖለቲካ ትግል መዘንጋት እንደሌለበት በመግለጽ ሐሳባቸውን መስጠት የጀመሩ አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፣ ‹‹የማስታወስ ችግር ስላለብን ነው እንጂ ለውጡ ላለፉት ሰባት ዓመታት የተደረገ ትግል ውጤት ነው፤›› ካሉ በኋላ፣ ‹‹አንዱና ትልቁ የለውጡ ጉድለት ውለታ ቢስ መሆኑ ነው፤›› በማለት ገልጸውታል፡፡

ከዚህ ባለፈ ግን በዋነኛነት በአገሪቱ የተከሰተው ለውጥ የአገሪቱን መሠረታዊ የፖለቲካ ቅራኔ መፍታት አለበት የሚል አቋም እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ የአገሪቱ መሠረታዊ የፖለቲካ ቅራኔ የሚመነጨው ከሕገ መንግሥቱ እንደሆነ ገልጸው፣ ሕገ መንግሥቱ አገሪቱን ያፈራርሳታል በሚል፣ የለም ሕገ መንግሥቱ በፓርቲ ማዕከላዊነት ተጠለፈ እንጂ የብሔር ብሔረሰቦችን ጥያቄ የሚመልስ ነው በሚል እንደሆነም አስረድተዋል፡፡

‹‹እነዚህ ጥያቄዎች እስካለፈው አንድ ዓመት ተኩል ድረስ መሠረታዊ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ አንድ ለውጥ መመዘን ያለበት እነዚህን መሠረታዊ ቅራኔዎች ለማስታረቅ በሚሄደው ርቀት ነው፤›› በማለት፣ ለውጡን በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ መመልከት ተገቢ መሆኑንና መመዘን ያለበትም በዚህ መሥፈርት እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

ከዚህ ባለፈ ግን በአገሪቱ ካለፉት አንድ ዓመት ተኩል ጀምሮ እየተተገበረ ያለውን ለውጥ ጠንካራ ጎኖች አውስተዋል፡፡ ከነዚህም መካከል በአንፃራዊነትም ቢሆን ትግሉ የሰላማዊ ትግል ውጤት መሆኑ፣ በመጣበት ወቅት ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኝቱ፣ ገዥው ፓርቲ እስከ መጨረሻው ድረስ ከመጋፈጥ ይልቅ ሽንፈቱን መቀበሉና ይቅርታ መጠየቁ፣ እንዲሁም የለውጡ መሪዎች ሆነው ብቅ ያሉት ወጣቶች መሆናቸው የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል፡፡

ነገር ግን እነዚህን ጠንካራ ጎኖች ወይም ትሩፋቶች የያዘው ይህ ለውጥ፣ አሁን ግን የመቀልበስ አደጋ ተጋርጦበታል በማለት እሳቸውም እንደ ቀዳሚ ተናጋሪዎች ሥጋታቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹ምንም እንኳን ይህ ለውጥ የረፈደበት ቢሆንም የመሸበት አይመስለኝም፡፡ ስለሆነም አዲስ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ መግባት አለብን፤›› ሲሉ፣ አዲሱ የለውጥ እንቅስቃሴ ደግሞ ሁሉንም አሳታፊ ያደረገ ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀት ሊጀመር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

የለውጥ ሒደቱን የሚመራ ፍኖተ ካርታ ማዘጋጀት ድርሻ ደግሞ የሁሉም የኢትዮጵያ ኃይሎች እንደሆነ በመጥቀስ፣ ‹‹ይህን ለማድረግ ግን ቀጣዩ ምርጫ መራዘም አለበት፤›› በማለት ሞግተዋል፡፡

‹‹ይህን ሳናደርግ ወደ ምርጫ ብንገባ ምናልባት በኢትዮጵያ ታሪክ ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ ያደረገችው ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ ያደረገችው ምርጫ እንዳይሆን እሠጋለሁ፤›› በማለት ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡

ባለፉት አንድ ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ የተካሄደውን ለውጥ አስመልክቶ በአገሪቱ የፖለቲካ ልሂቃን ዘንድ ጽንሰ ሐሳቡን ከመረዳት ጀምሮ እስከ ውጤቱ ድረስ፣ የተለያዩና ጽንፍ የያዙ አተያዮች የተስተናገዱበት ይህ መድረክ የተለያዩ ጥያቄዎችን በማስተናገድ ተጠናቋል::

Ethiopian Reporter

Leave a comment