በከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ላይ ሰኔ 15 የተፈጸመው ግድያ ዓቃቤ ሕግንና ተጠርጣሪዎችን እያወዛገበ ነው
ታምሩ ጽጌ
‹‹ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተቋሙን የማይመጥን ውሳኔ ሰጥቷል››
ተጠርጣሪዎች
‹‹የተወሰኑ ተጠርጣሪዎች በህቡዕ ተደራጅተው ጦርነት ይመሩ ነበር››
ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ
በአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ በመከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹምና በጓደኛቸው ላይ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በተቀራራቢ ሰዓታት ውስጥ የተፈጸመው ግድያ፣ ዓቃቤ ሕግንና ከግድያው ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው የታሰሩ ተጠርጣሪዎችን ማወዛገቡ ቀጥሏል፡፡
ግድያው በተፈጸመ ማግሥት ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በቁጥጥር ሥር ውለው በተለያዩ ጊዜያት ፍርድ ቤት ሲቀርቡ፣ የተጠረጠሩት ከግድያው ጋር በተያያዘና የሽብርተኝነት ሕግን አዋጅ ቁጥር 652/2001 በመተላለፍ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው መሆኑን የሚናገሩት ቁጥራቸው ከ30 በላይ የሚሆኑት ተጠርጣሪዎች፣ ግድያውን በሚመለከት የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥት አመራሮች የተናገሩትና ያሰራቸው የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ የሚናገረው የተለያየ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ የሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ከፍተኛ አመራሮች ግድያን በማቀነባበርና በመሳተፍ ተጠርጥረው፣ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው በፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ተጠይቆባቸው ቢፈቀድም፣ ፖሊስ በተሰጠው ጊዜ ምንም ዓይነት ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ባለመቻሉ፣ ፍርድ ቤቱ ሰፊ ትንታኔ በመስጠት በዋስ እንዲለቀቁ ውሳኔ ሰጥቶ እንደነበር ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት አስረድተዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በጠበቆቻቸው አማካይነት ነሐሴ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ባቀረቡት ክርክር እንዳስረዱት፣ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ያቀረቡት የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዝርዝር ትንታኔ በመስጠት ለደንበኞቻቸው የጠበቀላቸውን ሕገ መንግሥታዊ የዋስትና መብት፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ያላግባብ ስለነፈጋቸው ነው፡፡ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ሕገ መንግሥታዊ የሆነውን የዋስትና መብት የነፈጋቸው፣ ተቋሙን በማይመጥንና የዳኝነትን ብቃት ግምት ውስጥ ሊያስገባ በሚችል ሁኔታ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼውም አንድ የፀረ ሽብር ተግባር ወንጀል ፈጽሟል ተብሎ የተጠረጠረ ዜጋ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 20 (3) ድንጋጌ መሠረት ምርመራ ሊፈቀድበት የሚችለው 28 ቀናት ሆኖ ተደንግጎ እያለ፣ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በደንበኞቻቸው ላይ የተሰጠው የምርመራ ጊዜ 42 ቀናት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼ ደግሞ የሕጉን ድንጋጌ ከመጣሱም በላይ፣ ምንም ዓይነት ማስረጃ ያልቀረበባቸው ተጠርጣሪዎችን ከሕግ አግባብ ውጪ እንዲታሰሩ ማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ዓቃቤ ሕግ፣ የፖሊስ አባል፣ የአብን አመራሮችና አባላት፣ የተቋማት ሠራተኞችና ሌሎችም ሲሆኑ፣ በመዝገብ ቁጥሮች 181966፣ 181965፣ 182124፣ 182129 እና በመዝገብ ቁጥር 182150 ተካተው በአምስት መዝገቦች ከ30 በላይ ተጠርጣሪዎች የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔን በመቃወም በሰባት ጠበቆች ተወክለው ሰፊ ክርክር አድርገዋል፡፡
የፌዴራል መንግሥትና የአማራ ክልል የመንግሥት አመራሮች በአማራ ክልል አመራሮች ላይ የተፈጸመው ግድያ ‹‹የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ነው›› እያሉ በይፋ ከዕለቱ ጀምሮ በመገናኛ ብዙኃን ጭምር ገልጸው እያለ፣ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል መጠርጠር እርስ በርሱ የሚጣረስና ሕዝብንም እምነት የሚያሳጣ መሆኑን ጠበቆቹ ገልጸዋል፡፡
ፖሊስ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሯቸዋል ቢባል እንኳን፣ በተፈቀደለት የ28 ቀናት ጊዜ ውስጥ ማን በማን ላይና ምን ዓይነት ወንጀል እንደፈጸመ በመለየት በዝርዝርና በተናጠል ለፍርድ ቤት ማቅረብ እንዳለበት በሕጉ ተደንግጎ ቢገኝም፣ 28 ቀናት ቆይቶ ፍርድ ቤት ሲቀርብ ምንም ዓይነት የምርመራ ውጤት አለማቅረቡን አስረድተዋል፡፡
የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤትም የፖሊስ ምርመራ መዝገቦችን አስቀርቦ ከመረመረ በኋላ፣ ምንም ዓይነት ለሽብር ተግባር ወንጀል የጥርጣሬ መነሻ ነገር ባለማግኘቱ፣ ተጠርጣሪዎቹ ከ2,000 ብር እስከ 5,000 ብር በሚደርስ ዋስትና ከእስር እንዲፈቱ ውሳኔ መስጠቱንም ገልጸዋል፡፡ ፖሊስ ‹‹በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ›› በማለት ላሰራቸው የአብን አባላት ያቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹ማንን ነው የምትረዱት? ማነው ያሰማራችሁ?›› የሚሉና ‹‹ጠርጥሬያችኋለሁ›› ካለበት መነሻ ሐሳብ ጋር የማይገናኝ መሆኑንም ጠበቆቹ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የአዲኃን ሥልጠና ወስዳችኋል፣ ከእነ ዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አላችሁ›› የሚሉ የግለሰቦች ወይም የተወሰነ ቡድን ፍላጎትን የሚያንፀባርቁ ጥያቄዎች እንጂ፣ ከሰኔ 15 ቀን የከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር የሚያያዝ ምንም ዓይነት ምርመራ እንዳልተካሄደባቸውም አስረድተዋል፡፡
አንዳንዶቹ በተለይ ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለና የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ባልደረባና የልደታ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያ መርማሪ ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆናቸውን ደርሰንበታልና መረጃ ያቀብላሉ›› ከሚል ምርመራ በስተቀር፣ የሽብር ወንጀል ተሳትፏቸው ምን እንደሆነ ያቀረበው የጥርጣሬ መነሻ ማስረጃ እንደሌለም ገልጸዋል፡፡
‹‹የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዋስትና የከለከላቸው አቋም ይዞ ነው፤›› የሚሉት የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች፣ ይኼንንም ሊያስብላቸው የቻለው በዋስ እንዲወጡ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት እያንዳንዳቸው የ5,000 ብር ዋስትና ማቅረብ እንዳለባቸው ውሳኔ የተሰጠላቸው፣ አቶ የወግሰው በቀለና ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ ዋስትናቸው ወደ 200,000 ብር ማሳደጉ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ዋስትና ከተፈቀደላቸው ሳምንት ቢሞላቸውም፣ አቅማቸውን ያላገናዘበ ዋስትና በመሆኑ ከእስር ሊለቀቁ እንዳልቻሉም አክለዋል፡፡ ሌላው ጠበቆቹ ያቀረቡት ክርክር ሕጉ ግልጽ ሆኖ ሳለ፣ ለምን ተለጥጦና ለተጠርጣሪ በማይጠቅም ሁኔታ እንደሚተረጎም እንዳልገባቸው ጠቁመው፣ ከሰኔ 15 ቀን የእነ ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ግድያ ጋር በተያያዘ፣ ‹‹የገዳዩ ሚስት ናት›› የተባለችና ከግድው ጋር ምንም ግንኙነት የሌላት ሴትም ታስራ እንደምትገኝ ገልጸዋል፡፡ ዳኞቹ የሚሠሩት ለህሊናቸውና ለሕግ ተገዥ ሆነው ቢሆንም፣ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአግባቡ የሰጠውን ውሳኔ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ያገደበትና ከሕጉ ውጪ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር በአጠቃላይ 42 ቀናት የፈቀደበት ሒደት፣ ከሕግ አግባብ ውጪ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ ራሱ ጠይቆ የነበረው 28 ቀናት እንደሚበቃው ገልጾ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ 42 ቀናት መፍቀዱ ለምንና በየትኛው የሕግ አግባብ እንደሆነ ግልጽ አለመሆኑንም አክለዋል፡፡ አዴፓ ‹‹እርስ በርሳችን ተጠፋፋን›› እያለ ከ30 በላይ ንፁኃን ዜጎችን ማሰር፣ ተገቢ አለመሆኑንም ገልጸዋል፡፡ መፈንቅለ መንግሥት መሆኑ የተገለጸበትን ድርጊት የሽብር ተግባር ወንጀል በማለት ዜጎችን ያላግባብ ማሰር ሆን ተብሎ ሰብዓዊ መብታቸውን ላለማክበር የተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ጠበቆችን ጭምር በነፃነት እንዳይከራከሩና እንዳይናገሩ ጫና በማድረግ፣ በክርክሩ ወቅት ያነሷቸውን መከራከሪያ ሐሳቦች እንኳን እንዳልመዘገበላቸውም አስረድተዋል፡፡ በአጠቃላይ ደንበኞቻቸው ታስረው የሚገኙበት ጉዳይ እንኳን በሽብር ተግባር ወንጀል፣ በተራ ወንጀል እንኳን ሊያስጠረጥር እንደማይችል የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በክርክራቸው አስረድተዋል፡፡
ከሰኔ 15 ቀን ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረዋል ስለተባሉትና ይግባኝ ስለጠየቁት ተጠርጣሪዎች፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀርቦ ምላሽ የሰጠው (የተከራከረው) የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል መርማሪ ሳይሆን ዓቃቤ ሕግ ነው፡፡ በዕለቱ የቀረቡት ሁለት ዓቃቢያነ ሕግ እንዳስረዱት፣ እያንዳንዳቸው ተጠርጣሪዎች ከሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በፊት ሲደራጁ ቆይተው፣ በተለያዩ አቅጣጫዎች በመንቀሳቀስ ግድያው እንዲፈጸም አድርገዋል፡፡ ይኼ ሁኔታ በተፈጸመበትና ፖሊስ ስለሁኔታው በማጣራት ላይ እያለ፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተጠርጣሪዎቹ በዋስ እንዲወጡ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ድርጊቱን ‹‹ተራ የፖለቲካ ሽኩቻ ነው›› በማለት የዳኛውን ገለልተኛነት የሚያጠራጥር መሆኑንም አክለዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ እንዳብራሩት የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የምርመራ መዝገቡን ወስዶ ለሳምንት ማቆየቱና አልመልስም በማለቱ፣ እጃቸው ላይ በነበረ ሰነድ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብለው፣ የተጠርጣሪዎቹ የዋስትና መብት እንዲታገድ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡ በተለይ አራት ተጠርጣሪዎች በኅቡዕ ጦር እየመሩ እንደነበርና መረጃ ሲለዋወጡበት የነበረን ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጠይቀው በመጠባበቅ ላይ እያሉ፣ ዋስትና መፍቀድ ተገቢ አለመሆኑንም ዓቃቢያነ ሕጉ ተናግረዋል፡፡
በግለሰብ እጅ ሊገባ የማይችል የጦር ሜዳ መነጽር መገኘቱንም ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ በወታደራዊ አመራሮች ላይ ግድያ ሲፈጸም የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲቋረጥ ግዳጅ የተሰጣቸው፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሠራተኞች መያዛቸውንም ገልጸዋል፡፡ የጦር መሣሪያ መግዛቱንና 6,000 ጥይቶች ቢኖሩትም ከጎንደር እንዴት እንደሚያሳልፈው ምክክር ሲያደረግ የነበረ ተጠርጣሪና ሌሎችም፣ በኅቡዕ ተደራጅተው በእነማን ላይ ዕርምጃ እንደሚወስዱ ሥልጠና ጭምር የወሰዱ ተጠርጣሪዎች መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ ይኼ ሁሉ ባለበት ገና በምርመራ ላይ እንደሆኑ እየገለጹ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዋስትና መፍቀዱ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰኔ 15 ከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ የሽብር ተግባር ስለመፈጸሙ ከተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ጋር እየሠሩ እያለ፣ የወንጀል ተግባሩን በመቀየር ዋስትና መስጠቱም ተገቢ አለመሆኑን ዓቃቢያነ ሕጉ ደጋግመው አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በመሀል፣ ‹‹በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ላይ ለወንጀል ጥርጣሬ መነሻ የሚሆን የምርመራ ውጤት አቅርባችሁ ነበር?›› የሚል ጥያቄ ለዓቃቢያነ ሕጉ አቅርቦላቸው፣ ማን ከማን ጋር ግንኙነት እንደነበረው በቂ መጠርጠሪያ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ቀሪ መረጃና ማስረጃ በመሰብሰብ ላይ እንደሆኑም ማስረዳታቸውን ከኢትዮ ቴሌኮም፣ ከባንክ፣ የባልደራስ ምክር ቤትን እንደ ሽፋን በመጠቀም ወንጀል መፈጸማቸውን ለማሳየት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት መረጃ መጠየቃቸውን ቢገልጹም፣ ፍርድ ቤቱ እንዳልተቀበላቸው አስረድተዋል፡፡
ከፍተኛው ፍርድ ቤት ግን ያቀረቡትን የይግባኝ አቤቱታ በሚገባ ከተመለከተ በኋላ፣ ዋስትናውን እንደሻረውም አክለዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹እናንተ (ዓቃቢያነ ሕጉ ወይም ፖሊስ) 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ጠይቃችሁ ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንዴት ከዚያ በላይ ሊፈቅድ ቻለ?›› በማለት ሲጠይቃቸው፣ ችሎቱ የበዓል ቀናትን ትቶ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር መስጠቱን ጠቁመው ስህተት ከሆነ ሊታረም እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በምርመራ ላይ ከሆናችሁ እንዴት እስካሁን አልጨረሳችሁም? አሁንስ በምን ላይ ናችሁ?›› የሚል ጥያቄ አቅርቦላቸው፣ ተጠርጣሪዎቹ ሲዘጋጁ የከረሙት ከጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም. ጀምሮ መሆኑን፣ በቤንሻንጉል ጉምዝ ዋና ከተማ በአሶሳና በአዲስ አበባ የተፈጸመውን ሁሉ ማጣራት ስላለባቸው፣ እየሠሩና የጠየቁት ለመረጃ እስከሚመጣላቸው እየጠበቁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በተሰጣቸው ድጋሚ የመከራከሪያ ዕድል እንዳስረዱት፣ ዓቃቤያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንት ቀናት በዳኛ ዕግድ መቆየቱን ለችሎቱ መግለጻቸው፣ ከአንድ ከፍተኛ የሕግ ተቋም የማይጠበቅ ምላሽ ከመሆኑም ባለፈ ግምት ውስጥ የሚከት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ የራሱን ዋና የምርመራ መዝገብ ይዞ ለፍርድ ቤት የሚያቀርበው ደግሞ ግልባጩን (ኮፒ) መሆኑን ጠቁመው፣ መዝገቡ ዳኛው ዘንድ ስምንት ቀናት መቆየቱንና ‹‹አልሰጥም አሉኝ›› የሚል ሰበብ ማቅረብ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሌላው ዓቃቢያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ አካል ያልሆነን ጉዳይ ‹‹አሶሳ ከተማ የተፈጸመን ድርጊትም እየመረመርኩ ነው›› ማለቱ የማይገናኝ ነገር ለማገናኝት መሞከር መሆኑንም አክለዋል፡፡ የጦር ሜዳ መነጽር ይዘው ተገኝተዋል በማለት ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹን ለመወንጀል ያደረገው ጥረት፣ ‹‹መነጽር አይደለም ታንክ ይዘው ቢገኙ ሽብር ነው ማለት ነው?›› በማለት ጠይቀው፣ ፍርድ ቤቱ መዝገቡን አስቀርቦ እንዲያይላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተገኘ የተባለው የጦር ሜዳ መነጽር የዩኒቨርሲቲ ማስተማሪያና ከመምህር ቤት የተገኘ መሆኑንም አክለዋል፡፡ በኅቡዕ ተደራጅተው ጦር ሲመሩ ነበር የተባሉት ደንበኞቻቸው ጫማ የሚጠርጉ ሊስትሮዎች፣ የቤት ሠራተኞችና የፖለቲካ ድርጅት አባላት መሆናቸውንም አክለዋል፡፡
ግድያው ሰኔ 15 ቀን ተፈጽሞ ደንበኞቻቸው ሰኔ 16 ቀን መያዛቸው የሚገርም እንደሆነ የገለጹት ጠበቆቹ፣ ይኼ የሚያሳየው እነሱን ለመያዝ ዝርዝር ተይዞና ቀደም ብሎ ዝግጅት መኖሩ የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሽብር ተግባር ወንጀል አያስቀጣም ሳይሆን፣ በአዋጅ ቁጥር 652/2011 አንቀጽ (19) መሠረት ሊያስጠረጥራቸው የሚችል ማስረጃ እንዳልተገኘባቸው ወይም ፖሊስ በተሰጠው የ28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ሊያቀርብ እንዳልቻለ መግለጹ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹ የጦር ሥልጠና ሲያደርጉ እንደነበር መግለጻቸው ስህተት መሆኑን ጠበቆቹ ጠቁመው፣ መንግሥት ራሱ በጀት መድቦ ሲያሠለጥናቸው የነበሩ መሆናቸውን አክለዋል፡፡ በአጠቃላይ ፖሊስ እንኳን ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ቀርቶ ቃላቸውን እንኳን እንዳልተቀበላቸውም ጠቁመዋል፡፡
ተጠርጣሪው ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለ ለሥር ፍርድ ቤቶች ከታሰረ 50 ቀናት እንደሞላው ሲያስረዳ፣ ፍርድ ቤቱ ለምን ምርመራ እንዳልጨረሰ ፖሊስን ሲጠይቀው፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆኑን ስለደረሰበት እያጣራ መሆኑን እንደገለጸም አስታውሰዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለነሐሴ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
Ethiopian Reporter
በኢትዮጵያ የለውጥ ተስፋ እና ስጋቶች
ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com
ጥንታዊ እና ቀዳሚ ከነበሩ ሀገሮች መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በተለይ በቅርቡ ከአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) በዓለ ሲመት ከተደረገበት መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. አካባቢ የተስፋ አድማሶች ጎልተው ይታዩ ነበር። ዛሬም በርካታ ፈተናዎች ተደቅነውባታል። ህዝቡም ዛሬም ቅን መሪና የዴሞክራሲ ሥርዓትን ይናፍቃል። ምንም እንኳ የተፈጥሮ ሃብትን የተቸረች ቢሆንም፤ ዛሬም ድረስ ለዜጎቿ ንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት፥ የምግብ ዋስትና አለመረጋገጥ፥ የመብራት አቅርቦት እና አገልግሎት መጓል፥ ጥራቱን የጠበቀ በቂ የትምህርት እና የጤና ሽፋን በበቂ ሁኔታ አለመዳረስ ተጠቃሽ ችግሮች ናቸው።
በሀገሪቱ ስር የሰደደ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ሌላው የዜጎች ትልቁ ፈተና ነው። በተለይ ከሀገሪቱ ኢኮኖሚ ጋር ያልተመጣጠነ የህዝብ ብዛት፥ የወጣቶች ሥራ አጥነት፥ የህግ የበላይነት አለመረጋገጥ እንዳለ ሆኖ፤ ልቅ የሆነው የሙስና ሰንሰለት ሀገሪቱ ከውጭ በዕርዳታ፥ ብድርና ንግድ ከምታገኘው ዓመታዊ የውጭ ምንዛሪ ይልቅ በተደራጀ ፖለቲካዊ መዋቅር ተደግፎ ከሀገር የሚሸሸው የዶላር መጠን እና አድሏዊነት የተፀናወተው ሥርዓት አልባው የንግድ ሥርዓት የዜጎችን ሰላምና ህይወት ሲፈታተን ቆይቷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ (ፎቶ፡ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የተወሰደ)
በርግጥ በኮሎኔል መግሥቱ ኃይለማርያም ይመራ ከነበረው የኢሕዴሪ መንግሥታዊ ሥርዓት መገርሰስ በኋላ ግንቦት 1983 ዓ.ም. በምዕራባዊያን እና አረብ ሀገራት ድጋፍ ወደ ሥልጣን የመጣው የቀድሞው የጫካ አማጺ የትግራይ ነፃ አውጭ ድርጅት (ህወሓት) ኢህአዴግ በሚል ካባ በአምሳሉ ከፈጠራቸው የፖለቲካ ድርጅት (ብአዴን/አዴፓ፥ ኦህዴድ/ኦዴፓ እና ደኢህዴግ/ደኢህዴን) ድርጅቶች ጋር ኢህአዴግ በሚል ግንባር ወደ ሥልጣን ሲመጣ ብዙ ተስፋ ተጥሎበት ነበር። ይሁን እንጂ በነበረበት ያለፉት 27 ዓመታት የማዕከላዊ መንግሥት ሥልጣን ቆይታው ለሀገሪቱም ሆነ ለዜጎችም በበርካታ ጉዳዮች እጅግ ፈተና የበዛበት የግፍ አገዛዝ ነበር። በአገዛዙም በርካታ ዜጎች በግፍ ታስረዋል፥ ተገድለዋል፥ ከሀገር ተሰደዋል። የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብት ጥሰትም ከሀገር አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ መነጋገሪያ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። በርካታ ሰነዶችና ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ የህዝቡን ብቻ ሳይሆን ብሔራዊ የሀገሪቱን ጥቅም በማሳጣትም በሀገሪቱ ታሪክ ከነበሩ አገዛዞች በተለየ በጥቁር መዝገብ እንዲሰፍር ተደርጓል።
ከሶስት ዓመታት ተከታታይ ህዝባዊ አመፅ በኋላ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ ም የሀገሪቱ 15ኛው ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን ወደ ሥልጣን የመጡት አብይ አህመድ (ዶ/ር) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፊት ቃለ መሐላ በመፈፀም ከወትሮ የኢህአዴግ አሰልቺ የቃላት ጋጋት እጅጉን የራቀና በዜጎች የተወደደላቸውን ንግግር በተሰማበት ወቅት ሀገሪቱ በብሩህ ተስፋ ተሞልታ ነበር። በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተከታታይ በወሰዷቸው መልካም ርምጃዎች፤ በተለይም የታሰሩ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞችን እና ጦማሪዎችን ጨምሮ የፖለቲካ እስረኞችን መፍታት፥ መንግሥት በዜጎች ላይ ለፈፀመው ጥፋት በይፋ ይቅርታ መጠየቅ፥ ብረት ያነሱ ተቀናቃኝ አማጺያንን ጨምሮ በውጭ ያሉ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ኃይሎች በሰላም ወደ ሀገር ገብተው ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ እንዲያካሂዱ ጥሪና ድጋፍ ማድረግ ተጠቃሽ በጎ ርምጃዎች ናቸው።
ለረጅም ጊዜ “ሞት አልባ” ጦርነት የነበረው የኢትዮጵፃ እና የኤርትራ መፋጠጥ በሰላም እንዲቋጭ ማድረጋቸው እና ብሔራዊ አንድነትና መግባባትን በአደባባይ ከማቀንቀን አልፈው ለተግባራዊነት መንቀሳቀሳቸው ከህዝቡ ባልተለመደ መልኩ በርካታ ድጋፍና አጋርነት አስገኝቶላቸዋል። እንዲሁም ለበርካታ ዓመታት ህዝቡ ያለገዥው ህወሓት/ኢህአዴግ ፍላጎት ውጭ ናቸው የተባሉና ታግተው የነበረው የሳተላይትና የመረጃ መረብ ሚዲያዎች ክፍት እንዲሆኑና ለህቡም አማራጭ ሆነው እንዲያገለግሉ መፍቀዳቸው፤ በተለይ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ እና የፕሬስ ነፃነት አቀንቃኞችና ተሟጋቾች ሳይቀር ይበል የሚያሰኙ በርካታ ውዳሴዎችን እንዲያገኙ አስችሏቸዋል።
በሀገር ውስጥ በተለያዩ ከተሞች ጉብኝትና ምክክር ከማድረጋቸው በተጨማሪ በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ጋር ያደረጉት ምክክርና መቀራረብም ያልተለመደና የተወደሰ አዲስ የለውጥ ክስተት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በህዝባዊ አመፅ ተዳክሞ የነበረውን እና የተራቆተውን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሻሻሉ እየወሰዱ ያሉት በጎ ርምጃም ከሚወደስላቸው ተግባራት መካከል አንዱ ነው። በተጨማሪም ላለፉት 27 ዓመታት በፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ለሁለት ተከፍሎ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወደ አንድነት እንዲመጡ የተደረገው ድጋፍና አስተዋፅዖ ፤ እንዲሁም በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ ሙስሊም መጅልስ ተቋም ላይ በተደረ ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት የነበረው መለያየት ወደ አንድነት እንዲመጣ መደረጉ በበጎ የሚወሱ ተግባራት ናቸው። እነኚህ በጎ ተግባራት የህዝቡን አንድነትና ህብረት ከማጠናቀር በተጨማር በሀገሪቱ ሰላም፥ ዕድገትና ብልፅግና ላይ ዜጎች ብሩህ ተስፋን እንዲሰንቁ አስችሏቸዋል።
ነገር-ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያ ሁሉ የነበረው ተስፋና ድጋፍ ግን ከአንድ ዓመታ በላይ መዝለቅ የቻለ አይመስልም። ለአንድ ዓመት ያህል የመብት ተሟጋቾችና ጋዜጠኞች ሳይታሰሩ የመቆየታቸው በጎ ተስፋ አሁን አሁን ስጋት እየታየበት ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ የለውጥ መሪውና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይወክሉታል በሚባለው ኦሮሚያ ክልልን ጨምሮ በርካታ ዜጎች የደህንነት ዋስትና ማጣት እየተለመደ መጥቷል። በአማራ ክልል፥ በደቡብ እና ቤኒሻንጉል ክልልም የተለያዩ አካባቢዎች ተመሳሳይ የፀጥታና ደህንነት ስጋቶች ይስተዋላሉ።
በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ከሚነሱ ነቀፌታዎች መካከል ይሰሩልኛል ብለው የነበረውን ህግ ወደ ጎን በመተው የራሳቸውን ሰው ከህግ አግባብ ውጭ የሾሟቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አካላት ሹመት፥ የሥራ ስምሪት እና የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣን እና ሹመት ከብቃትና አካታችነት ይልቅ ከዚህ ቀደም ይወገዝና ተቃውሞ ይቀርብበት የነበረውን የሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ እና የድርጅታቸው ህወሓት አገዛዝን ተመሳሳይ መንገድ እየተከተሉ ነው በሚል በርካታ ደጋፊዎቻቸው ሳይቀር ነቀፌታ ማቅረባቸውን ቀጥለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት በዋናነት ሶማሊና ኦሮሚያ ክልል አካባቢ ወደ አንድ ሚሊዮን ዜጎች ከመደበኛ መኖሪያቸው የተፈናቀሉ ቢሆንም፤ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የአንድ ዓመት አስተዳደር ጊዜ ውስጥ ግን ወደ ሁለት ሚሊዮን ዜጎች በኃይል ተፈናቅለዋል፥ በርካቶችም በርስ በርስ ግጭት ተገድለዋል፥ ቆስለዋል።
አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ብቻ የአዲስ አበባ ወጣቶችን ከአንዴም ሁለት ጊዜ ያለምንም ህጋዊ መሰረትና ምክንያት በጅምላ ሰብስቦ ማሰርና ማንገላታት በቀዳሚነት ይደግፏችው የነበሩ ወጣቶች አዲሱን አስተዳደር በጥርጣሬ እንዲያዩት ምክንያት ሆኗል። በተለያዩ መንግሥታዊ አስተዳድር ጉዳዮች እና አገልግሎት አሰጣጥ ላይም ሁሉንም በእኩል ከማየት ይልቅ ፖለቲካዊ ወገንተኝነትን የተላበሰ አድሏዊነት እየተንፀባረቀ ነው በሚልም የነበረውን ተስፋ በሂደት ወደ ስጋት እየተለወጠ መጥቷል። በተለይም በኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ አቅራቢያ ቡራዩ፥ ለገዳዲና ለገጣፎ ከተሞች፥ ምዕራብ ወለጋ፥ ቄለም ወለጋ፥ ሆሮ ጉድሩ ወለጋ፥ ምሥራቅ ወለጋ፥ ምዕራብ እና ምሥራቅ ጉጂ ዞን፤ በአማራ ክልል፥ ሰሜን ጎንደርና ምዕራብ ጎንደር፤ በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን፥ ጉጂ ዞን፥ ቡርጂ ጌዲዮ፥ አማሮ፥ ከፋ ዞን እና ደራሼ አካባቢን መጥቀስ ይቻላል። ይህ ዘገባ በሚጠናከርበት ጊዜም መንግሥት ባመነው መረጃ እንኳ ወደ ሶስት ሚሊዮን ዜጎች ከመደበኛ ኑሯቸውና ቀዬያቸው ተፈናቅለዋል። በርግጥ የተወሰኑት ወደ ቀድሞ መኖሪያቸው እንዲመለሱ ጥረት እየተደረ መሆኑ እንዳለ ሆኖ፤ አሁንም ድረስ ዜጎች ተረጋግተው የመኖር ተስፋቸው ላይ ስጋትን ጭሯል።
በኦሮሚያ ክልል ለሰላማዊ ትግል በሚል ስምምነት ወደ ሀገር ውስጥ ጥሪ ተደርጎለት ከኤርትራ አስመራ ወደ ሀገር የገባውና በአቶ ዳውድ ኢብሳ የሚመራው ሸኔ የሚባለውና የኦነግ ክንፍ
በአራቱም የወለጋ ዞኖች በሚገኙ የተለያዩ 19 ያህል የንግድ ባንኮች ዘረፋ መፈፀሙ ቢገለፅም በጉዳዩ ዙሪያ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ አዲስ አበባ የሚገኙት የድርጅቱ መሪም ሆኑ ሌሎች የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ዝምታን መምረጣቸው የህግ የበላይነት መላላትና የዜጎች ደህንነት ከዕለት ወደ ዕለት አደጋ ውስጥ መውደቁ ሌላኛው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ድክመት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። የሀገሪቱ ፀጥታና ደህንነት ጉዳይ ከወዲሁ ትኩረት ካልተሰጠው፥ ተጠያቂነትና የህግ የበላይነት በሁሉም ዜጎች ላይ በእኩል የማይሰራ ከሆነ ወደ አላስፈላጊ ረብሻና ሥርዓት አልበኝነት እንዳያመራ ስጋት አለ። የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ከመጠበቅ አኳያ በመንግሥት በኩል እየተወሰደ ያለው የእርምትም ይሁን የጥንቃቄ ርምጃ እጅጉን ደካማ ነው።
ሐሳብን ከመግለፅና ከፕሬስ ነፃነት ጋር በተያያዘ ያለው ተስፋ በቅርቡ በአንዳንድ ጋዜጠኞችና ጦማሪዎች ላይ ስጋቶች እንደ አዲስ ተደቅኖባቸዋል። በተለይ የካቲት 23 ቀን 2011 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አቅራቢያ ባሉ የኦሮሚያ ክልል ለገዳዲና ለገጣፎ ከተሞች በመንግሥት አስተዳድር በግልፅ ውሳኔና ርምጃ የተፈናቀሉ ዜጎችን አስመልክቶ ለዘገባ የተጓዙ የ”መረጃ ቲቪ” ዘጋቢ ጋዜጠኛ ፋሲል አረጋይ እና የፎቶ ጋዜጠኛው ሀብታሙ ኦዳ በከተማው ፖሊስ ጣቢያ ፊትለፊት የአካል ጥቃት ተፈፅሞባቸዋል። ጋዜጠኛ ፋሲልም በደረሰበት ጥቃት አዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ርዳታ ተደርጎለታል። በቅርቡም የአሃዱ ቴቪ ጣቢያ ከሰንዳፋ ከተማ ጋር በተያያዝ በተላለፍ ዘገባ ጋር በሚል ግንቦት 16 ቀን 2011ዓ.ም. ጋዜጠኛ ታምራት አበራ ከሚሰራበት አሃዱ ቴልቪዥን እና ሬዲዮ ጣቢያ በኦሮሚያ ፖሊስ ተወስዶ መታሰሩና፤ በዕለቱ የታሰረውን ጋዜጠኛ ሊጎበኘው የሄደው የኢትዮ-ኦንላየን ሚዲያ ጋዜጠኛ ጌጥዬ ያለው መታሰሩ በነፃው ፕሬስ ጫና ጅማሮ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። እንደ ምንጮች ከሆነ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ አስተዳደር እየተፈፀሙ ያሉ ብልሹና አድሏዊ አሰራሮችን የሚያጋልጡ የኢንተርኔት መረጃ አምደኛ ጋዜጠኞች፥ ጦማሪዎችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች የጦማሮቻቸው እና የግል የይለፍ ቃል በኢትዮጵያ የመረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲ (INSA) ብርበራና የይለፍ ቃል ነጠቃ እየተሞከረ እንደሆነ ይነገራል። እነኚህ ሁሉ የነበሩ የለውጥ ብሩ ተስፋዎች ላይ የስጋት ደመና ጋርደዋል።
ሌላው ከዚህ ቀደም በህወሓት/ኢህአዴግ የመንግሥት አስተዳደር ወቅት የአመራር አካልና የወጣት አደረጃጀት አባላት የነበሩና ተከታዮቻቸው በአዲሱ የአብይ አህመድ ኦዴፓ/ኢህአዴግ አመራር ላይ የተለያየ ጫና ለመፍጠር ሲጥሩ ይስተዋላል። ለአብነትም የቀድሞ የኦህዴድ/ኦዴፓ የታችኛው አንዳንድ አመራር አካላት፥ የህወሃት አመራሮች፥ የቀድሞ ብአዴን/አዴፓ እና የደኢህዴን አመራሮች በየአካባቢያቸው ከሚያደርጉት እንቅስቃሴ በተጨማሪ በማኀበራዊ ሚዲያ ሳይቀር አንዳንዶቹ ከአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር መምጣት በኋላ ከኢህአዴግ አካል የነበሩት አዳዲስ የፖለቲካ ድርጅት በመፍጠር ጭምር የሚያደርጉት እንቅስቃሴ በአንዳንድ አካባቢዎች ጥርጣሬ፥ ግጭትና ስጋት መፍጠራቸው አልቀረም። በአንፃሩ ከኦነግ ታጣቂ በስተቅር አብዛኛው ከውጭ የመጡትም ሆነ በሀገር ውስጥ ያሉ የገዥው ኢህአዴግ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርጅቶች ከአዲሱ አስተዳደር ጋር የተሻለ መከባበርና መቀራረብ ይታይባቸዋል። ይሄ ለሰላምና መረጋጋቱ ተስፋ ሰጭ ቢሆንም፤ በአንዳንድ ሚዲያ ላይ የሚታዩ የጋዜጠኝነት የሙያ ስነ ምግባር ጋር የሚቃረኑ የሚዲያ አጠቃቀም ክፍተቶች፥ ተጠያቂነትና ኃላፊነትን ተላብሶ እንዲሰራ ሊረዳ የሚችል ነፃና ገለልተኛ የጋዜጠኞች የሙያ ማኀበር አለመኖርም እንደ አንድ ስጋት የሚታይ ነው።
በተለያ በማኀበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ረገድ በርካታ የማኀበራዊ የግል ገፆች ትክክለኛ ባልሆነ ስም፥ አንዳንዱ ደግሞ በህይወት ባለም ሆነ በሌለ ስመ ጥር ግለሰቦች ስም ገፅ በመክፈት የሚሰራጩ ሐሰተኛ መረጃ ስርጭት እና የጥላቻ ንግግሮች ሌላው የለውጡ ፈተና ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በተለይ ሐሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግርን የሚያሰራጩ ግለሰቦች እየተበራከተ ከሄደ መንግሥና አስተዳደር ላይ ብቻ ሳይሆን የዜጎች ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት ላይ አሉታዊ ጫና ያሳድራል። ምናልባትም ችግሩ ተባብሱ በዜጎች መካከል ግጭት እና ቅራኔ መፍጠር ሲባባስ መንግሥት የራሱን አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲወስድ ሊጋብዝ ይችላል። ይሄ ደግሞ በሌላ በኩል በዜጎች ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት ላይ የራሱ የሆነ አሉታዊ ሚና ይኖረዋል። ስለዚህ ብሩህ ተስፋን ሰንቆ የነበረው ለውጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በመንግሥትና በአንዳንዴ ዜጎች መካከል ጥርጣሬና ስጋትን እየታየ ይገኛል።
በጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀመው የዘረኝነት ጥቃት እና ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት
ብስራት ወልደሚካኤል
በዶ/ር አብይ አህመድ እና አቶ ለማ መገርሳ የሥልጣን ዘመን በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ከደረሰባቸው ወገኖች መካከል የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የደረሰው ከፍተኛው ነው። ነገር ግን በተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀሙ ጥቃቶችና በደሎች አቶ ለማ መገርሳም ሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዶ/ር አብይ አህመድ ጠንቅንቀው ያውቃሉ። ባለፈው ክረምት የተፈፀመው በደል በኦነግ እንደሆነ ብዙ ሸፋፍኖ ለማለፍ ተሞክሮ ነበር። ግን አልነበረም። መጀመሪያ ላይ የተፈፀመው ማፈናቀልና አካላዊ ጥቃት በምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ባሉ የኦህዴድ/ኦዴፓ ከፍተኛ እና የወረዳ አመራሮች ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው የሚጠሩ ወጣቶችን በማስተባበር ጭምር እንደተሳተፉ የጥቃቱ ሰለባዎችና ድርጊቱን የተቃወሙ የጉጂ ዞን ሌሎቹ አመራሮች አጋልጠው ከኦሮሚያ ክልል ሪፖርት አድርገው ነበር። ይሄንንም የክልሉ ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ምክትላቸው ወ/ሮ ጠይባ ሐሰን ያውቃሉ። ለዚህም ነው አቶ ለማ መገርሳ ተፈናቃዮቹ ያሉበት ጉጂ ዞን በአካል ሄዶ የጎበኘውና ድርጊቱን ኮንኖ ሀዘኑን የገለፀው። ይህም ብቻ አይደለም በድርጊቱ የተሳተፉና መረጃ የተገኘባቸው ናቸው ያየተባሉት ላይ ወዲያውኑ ከሥራ ማገድ እስከ እስር ርምጃ መውሰዳቸውን ያሳወቁት። በወቅቱ የነበረውን የዘረኝነት ቅስቀሳና ማፈናቀሉን የተቃወሙ አመራሮችና የሀገር ሽማግሌዎች ቢኖሩም አደጋውን ከመቀነስ ባለፈ ማስቆም አልቻሉም ነበር። ምክንያቱም ጥቃቱ በመሳሪያ የታገዘ ስለነበር። ድርጊቱ ከዚህ ቀደም ሱማሌ ክልልና ወሰን አካባቢ በአብዲ ኢሌ እና አጋዦቹ በምስኪኑ ኦሮሞ ላይ ከተፈፀመው ጋር ተመሳሳይ ነው። ያንን አውግዘን እና ኮንነን ይሄን መሸፋፈን አይቻልም። ወንጀል የትም በማንም ላይ ይፈፀም ያው ወንጀል ነው።
ድርጊቱ የተፈፀመው በፖለቲካ መሪዎችና የፀጥታ ኃይሉ እንጂ በህዝቡ አለነበረም። ታዲያ በአብዲ ኢሌ የተፈፀመውን ኮንነን እና አውግዘን ስናብቃ ምስኪኑ የጌዲዖ ማኅበረሰብ መፈናቀልን እና የፖለቲካዊ የርሃብ ጥቃት መሸፋፈን ለምን አስፈለገ? የጌዲዖ መፈናል እና ሰብዓዊ ርዳታ ልክ ኦሮሞ በክፉ ሥራው የተጋለጠ ለማስምሰል ሌላ ጥፋት ነው። አንድም የግለሰቦችን ወንጀል ለምስኪኑ ኦሮሞ ማላከክ አሊያም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ ስም ማጥፋት አስመስሎ ማስፈራራት እና ወንጀሉን ለመሸፋፈን የመሞከር ወንጀል። ይሄ ጊዜ ያለፈበት ነው። ልክ የሶማሌ ማኅበረሰብ ኦሮሞ ከአስተዳደር ክልላቸው የኦሮሞ ማኅበረስብ እንዲፈናቀል ለእነ አብዲ ኢሌ ትዕዛዝ እና ድጋፍ እንዳላደረገ ሁሉ በምስኪን የጌዲዖ ማኅበረሰብ ከጉጂ ዞኖች መፈናቀል የኦሮሞ ማኅበረስብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ድጋፍ አድርጓል ብሎ የሚያምን የለም። የአካባቢው የኦህዴድ/ኦዴፓ ፅንፈኞችና ዘረኛ አመራሮች ግን አድርገውታል። ይሄን መካድ አይቻልም። ለዚህም በሁለት ዙር በግፍ የተፈናቀሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብን ሰቆቃ በአካል ሄዶ ማየት በቂ ነው። ይሄ ደግሞ ከህግም፥ ከሞራልም ሆነ ከሰብዓዊነት አንፃር መጋለጥና መወገዝ ያለበት ወንጀል ነው። ያውም “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት። ያኔ በህወሓት እና አብዲ ኢሌ ፖለቲካዊ ወንጀል የኦሮሞ ማኅበረሰብ ከሶማሌ ክልል በግፍ ሲፈነቀል ከሀገሩ ሊፍናቀል አይገባም ብለን በጋራ እንደተቃወምነው ሁሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብ በግፍ መፈናቀልንም ልናወግዝ ይገባል እንጂ ጉዳዩ ተጋለጠ ብሎ በርሃብና ሞት እንዲቀጡ መሸፋፈን ትክክል አይደለም። ይሄ ጭካኔ የተሞላበት ኢ- ሰብዓዊነት ነው።
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በማንነታቸው የተፈናቀሉ የጌዲዮ ማኅበረሰብ በከፊል (ፎቶ፡ የጌዲዮ ዞን ኮሚኒኬሽን ጽህፈት ቤት)
በተለይ አቶ ለማ መገርሳ ከፌደራል የደኢህዴን አመራሮች መካከል ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል እና ከደቡብ ክልል ደግሞ አቶ ሚሊዮን ማቴዎስ እንዲሁም በችግሩ ቅርበት ያለው የጌዲዖ ዞን አመራሮች የጥቃቱ ሰለባዎች የሚገኙበት ጊዜያዊ መጠለያ ቦታ ድረስ በመሄድ አረጋግጠው፤ ጉዳዩ በሽምግልና እንዲፈታ፥ የተፈፀመባቸው ጥቃትም ወደ አደባባይ እንዳይወጣ ብዙ ሞክረው ነበር። ጉዳዩን አለዝቦ “በጉጂ ኦሮሞ እና በጌዲዖ ማኀበረሰብ ተከስቶ የነበረው ግጭት በሀገር ሽማግሌዎች ርቀሰላም ተፈቷል” በሚል ለዘብ ያለ የዜና ሽፋን ሁሉ ተሰጥቶት ነበር። ያውም ከቪዲዮ ምስል ጋ ተያይዞ። እንደ ጥቃቱ ሰለባዎች ገለፃ ከሆነ ግጭቱ የተቀሰቀስውም ሆነ የተቀነባበረው በጉጂ ኦሮሞ ማኀበረሰብና ብጌዲዖ ማኀበረብ መካከል ሳይሆን በምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን በሥልጣን ላይ ባሉ አካላትና የ“ብሔር” እና ጥላቻ ቅስቀሳ ሲያደርጉ በነበሩና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች እና የማኀበራዊ ሚዲያ “አክቲቪስቶች” ነበር። በተለይ ከአካባቢው ጋር በተያያዘ በማኀበራዊ ሚዲያ ጭምር በኦሮሚኛ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥላቻ ቅስቅሰሳ ይደርግ ሁሉ እንደነበር አስታውሰዋል።
በወቅቱ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት የደረሰባቸው የዘረኝነት ጥቃት መካከል፡-
1ኛ. በርካቶች ቤቶቻቸው እየተመረጠ ተቃጥሎባችዋል።
2ኛ. የእርሻ ማሳ ላይ ያለ ቡና እና ሰብሎችን ጨምሮ ንብረቶቻቸው ተዘርፈዋል፥ መሬቶቻቸውም በአካባቢው ባለሥልጣናትና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች የተነጠቁም ይገኙበታል።
3ኛ. እናቶችን ጨምሮ ወጣት ሴቶች ተደፍረዋል።
4ኛ. በዚህ ወቅት ሊታሰብ የማይችል አሰቃቂ ግድያ ተፈፅሞባቸዋል። ከሞት የተረፉትም በዲላ እና ይርጋለም ሆስፒታሎች ሳይቀር ህክምና ርዳታ ያገኙ ነበሩ። በወቅቱም የኦሮሚያና የደቡብ ክልል ባለሥልጣናትም እንደተጎበኙ መረጃው አለ። ለውጡ እንዳይደናቀፍ በሚል ችላ ከተባለ በኋላ ዘግይቶ ጥቃቱ ግን በኦነግ ላይ ብቻ ተሳቦ ተሸፋፍኖ ታልፏል። ይሁን እንጂ የኦሮሚያ ክልልም ሆነ የደቡብ ክልል ባለሥልጣናት እውነታውን በደንብ ያውቁት ነበር። ከዚያም አቶ ለማ መገርሳ በጥቃቱን የተሳተፉ የምስራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን አመራሮችን ከሥልጣን በማንሳት እንዲታሰሩና በህግ እንዲጠየቁ ማድረጋቸውን በአደባባይ በዕርቀ ሰላሙ ወቅት ተናግረው ነበር። ጥቃቱ የደረሰባቸው ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ በተጨማሪ አጎራባች የደቡብ ክልል ጌዲዖ ዞን ወረዳዎች የነበሩ ምስኪን ገበሬዎችም ጥቃት ደርሶባቸው ተፈናቅለዋል። በተለይ አጎራባች በጌዲዖ ዞን ትምህርት ቤቶች ሁሉ በጥቃቱ ወድመዋል። ከዛም በመንግሥት ግፊት፥ በሀገር ሽማግሌዎችና አባገዳዎች ድርድር አማካኝነት ነሐሴ 30 ቀን 2010 ዓ. ም. ወደ 359 ሺህ የሚሆኑ ተፈናቃዮች ወደ ቀድሞ ቀዬያቸው እንዲመለሱ ተደርጎም ነበር።
ነገር ግን የመንግሥትን እና የሀገር ሽማግሌዎችን ጥሪ ተቀብለው ወደ ቀዬያቸው ሲመለሱ የተዘረፉና ንብረቶቻቸውን እና የተወረሱ መሬቶቻቸውን ተከልክለው ድጋሚ ሌላ ጥቃት ደርሶባቸዋል። በዚህም ወደ 175 ሺህ ያህ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት በድጋሚ እንዲፈናቀሉ ተደርጓል። የሁለተኛው መፈናቀል ላይ ከኦህዴድ/ኦዴፓ የአካባቢው አመራሮች በተጨማሪ የኦነግ ታጣቂዎችም እንደተሳተፉ የተገለፀ ሲሆን፤ ድርጊቱን አውግዘው የተቃወሙ የጉጂ የሀገር ሽማግሌዎች በጥቃት አድራሽ የአካባቢው አመራሮች፥ ወጣቶችና ታጣቂዎች ማስፈራሪያና ዛቻ እንደደረሰባቸው ለኦሮሚያ ባለሥልጣናት ጭምር አሳውቀዋል። ይሄን በደል ያጋለጡ እና ለኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ሪፖርት ያደረጉ አካላት አሁንም አሉ። ይሁን እንጂ ተፈናቃዮቹ ከኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናትም ሆነ የሚመለከተው የፌደራል መንግሥት ተገቢውን የሰብዓዊ እና የህግ ከለላ ድጋፍ ካለማግኘታቸው በተጨማሪ ፥ የተዘረፉና የተወረሱባቸው ንብረቶች እና የእርሻ ማሳዎች ሳይመለሱ ለረጅም ጊዜ በታፈነ አነስተኛ ጊዜያዊ የሸራ መጠለያ እንዲቆዩ መደረጉንም ያስታውሳሉ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ያለሰብዓዊ ድጋፍ በመጠለያ እያሉ የህግ ከለላና ድጋፍ ባለማግኘታቸው በተወስኑ ተመላሾች ላይ በፅንፈኞቹ ተደጋጋሚ የዘረኝነት ጥቃት ሲደርስባቸው በድጋሚ ከጉጂ ዞን ጊዜያዊ መጠለያዎቻቸውም ተፈናቅለው ወደ ጌዲዖ ዞን በተለይም ገደብ፥ ይርጋጭፌ እና ወናጎ ባሉ ወረዳዎች ተሰደው በአብያተ ክርስቲያናት አዳራሽ መኝታ አልባ ወለል ላይ እንዲሁም በሸራ በተወጠረ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ተፋፍገው ይገኛሉ። ከርሃቡ በተጨማሪም ለተለያየ ተላላፊ በሽታም የተጋለጡ ይገኝበታል። በድጋሚ ከተሰደዱትና በከፍተኛ ደረጃ ለርሃብ ከተጋለጡት መካክለ ከ45 ሺህ በላይ የሚሆኑት በጌዲዖ ዞን ገደብ ወረዳ ባሉ ቤተክርስቲያኖችና ትምህርት ቤቶች የተጠለሉ ቢሆንም በድጋሚ ወደ ቀዬያችሁ ካልተመለሳችሁ በሚል በፌደራል፥ በደቡብ እና ኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናት ግፊት ሰብዓዊ ድጋፍ እንዳይደረግላቸው መደረጉን መረጃዎች ይፋ ከሆኑ ሁለተኛ ሳምንቱን ይዟል። በዚህም በአማካይ በቀን ከ2 እስከ 3 ሰዎች በርሃብ እየሞቱ እነደሆነ፥ ቀሪዎቹ ለከፍተኛ ርሃብ በመጋለጣቸው አስቸኳይ የምግብ፥ የጤና እና መሰል የሰብዓዊ ድጋፍ ካላገኙ በአጭር ጊዜ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ አባላት ለሞት እንደሚጋለጡ የገደብ ወረዳ አመራሮች፥ የአካባቢው የመካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጉዳዩን አጋልጠዋል።
ከኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ጉጂ ዞን ከተፈናቀሉና የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰለባ ከሆኑ እናቶች መካከል አንዷ ናቸው።(ፎቶ፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ድርጊቱን ያጋለጡ የዲላ ዩኒቨርስቲ በጎ ፈቃደኞች እና ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ የተወሰደ)
መረጃው የደረሳቸው የዲላ እና ይርጋጨፌ ከተማ ነዋሪዎች እንዲሁም የተወሰኑ የዲላ ዩኒቨርስቲ ማኅበረሰብ አባላት ፈጥነው በመድረስ የተቻላቸውን ሰብዓዊ ድጋፍ በማድረግ ጉዳዩን ለቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስና አስቸኳይ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ከምስል ጋር ይፋ አድርገዋል። ይሁን እንጂ የደቡብ ክልል፥ የጌዲዖ ዞን፥ የኦሮሚያ ክልል እና የፌደራል ከፍተኛ አመራሮች በተለይም የሰላም ሚኒስቴር እና የፌደራል አደጋ መከላከል ዝግጁነት አመራሮች ጉዳዩን እያወቁ ለማስተባበል ሞከረው የነበረ ቢሆንም፤ በድጋሚ በቪዲዮ ማስረጃ ጭምር ከተጋለጠ በኋላ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያ ካሚልና የደቡብ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ልክ ጉዳዩን እንደማያውቅ በመምሰል ተፈናቃይ ተጎጂዎችን በአካል ጎብኝተዋል።
በተለይ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ እና የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል በከፍተኛ ርሃብ የተጋለጡ ከ45 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ያሉበትን ገደብ ወረዳ መካከል ኮቲት ቀበሌን ብቻ ጎብኝተው በመመለስ የገጎጂዎቹን ቁጥር 13 ሺህ ናቸው በሚል ዝቅ ለማድረግና አደጋውንም ለማሳነስ ሞክረዋል። ይሄ የቀዳማዊ አጽ ኃይለሥላሴ ዘመን የትግራይና ወሎ ርሃብ እንዲሁም የደርግ ዘመን የ1977ቱ ርሃብ መደበቅ ጋር ተመሳሳይ ተግባር መሆኑ ነው። የጌዲዖ ርሃብ የሚለው ርሃቡ በተፈጥሮ ድርቅ ምክንያት የተከሰተ ሳይሆን በአመራሮች እና ጽንፍ የያዙ ዘረኞች የተቀናጀ ቅጣት መሆኑ ነው። ርሃቡን ለመሰበቅ ብቻ ሳይሆን ለማስተባበልም በሶስት ቀን ውስጥ ብቻ የተለያየ ይሐሰት ማስተባበያ መረጃ ለማሰራጨት ተሞክሯል። ግን ለምን? ሰው እንዴት በወገኑ ላይ ይህን ያህል ይጨክናል? ይባስ ብሎ ራሳቸው የኦሮሞ “ጠበቃ” ያደረጉ እና ዘረኝነት በተደጋጋሚ ሲያቀነቅኑ የነበሩ አካላት የመፈናቀሉና ርሃቡ መጋለጡ ለምን አስቆጣቸው? ምናልባት የማፈናቀሉና የርሃቡ ቅጣት ላይ ተባባሪ ነበሩ ወይስ በምስኪን ህፃናትና ሞት የሚገኝ ሌላ ትርፍ ፍለጋ? ያሳዝናል።
የጌዲዖ ማኅበረሰብ “ብሔር” ተኮር ዘረኝነት ላይ መሰረት አድርጎ የተፈፀመው መፈናቀል እና የአመራሮች የተቀናጀ የርሃብ ቅጣት በዝምታ መታለፍ የለበትም። ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ ተደርጎበት ተሳታፊዎችና ጉዳዩን ለመሸፋፈን የሞከሩ የሚመለከታቸው አካላት በህግ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄ በዋናነት የምሥራቅ ጉጂ፥ ምዕራብ ጉጂ እና ጌዲዖ ዞኖች፥ የደቡብ ክልል እንዲሁም የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ካቢኔያቸው፥ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ የፌደራል፥ የኦሮሚያ እና የደቡብ ክልል አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ቋቋሚያ) አመራሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን በህግ ሊጠየቁና መልስ ሊሰጡ ይገባል። ምክንያቱን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ በስተቅር የተጠቀሱ አካላት እና አመራሮች ከዚህ ቀደም ችግሩን በአካል ድረስ ሄደው አይተዋልና። ስለዚህ ለተጎጂው የሚደረገውን የሰብዓዊ ድጋፍና ርዳታ ለማጣታልና ከኦሮሞ ህዝብ ጋራ ማያዝ ተገቢ አይደለም። ይሄ የባሰውኑ የለየለት ዘረኝነትና ጥላቻ ነው። ቢያንስ ሰብዓዊነት ተሰምቶን ለተጎጂዎች ቀና ትብብር ማድረግ ቢያቅተን እንኳ ደጋግና ቅን ሰዎች ድጋፍ ሲያደርጉ ከ”ኦሮሞ ብሔር” ስም አስታከን ለምን ተጋለጠ በሚል ግብዝነት ዓይናችን ሊቀላ አይገባም። ስለሆነም ተጎጂዎቹ የጌዴዖ ማኀበረሰብ አባላት በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰላባም ጭምር መሆናቸው ሊታወቅ ይገባል።
የጌዲዮ ማኀበረስብ የአረንጓዴ ወርቅ “ቡና” የበለፀጉ ታታሪ ገበሬና ነጋዴዎች ናቸው። በድርቅ ምክንያት በርሃብ የሚጎዱ የአካባቢውን ወገን ከመርዳት ባለፈ በርሃብ ምክንያት ለልመና እጅ የሚሰጡም አይደሉም። በዛ ላይ በዓለም ላይ ውድ የሆነውን እና የኢትዮጵያ ቡና (ኮፊ አረቢካ) ልዩ ተፈጥሯዊ ጣዕም የይርጋጨፌ ቡና ብራንድ ብቸኛ አምራችም ናቸው። ጥራት ያለው ተፈጥሯዊ ልዩ የይርጋጭፌ ቡና ወደዓለም አቀፍ ገበያ በመላክምለሀገራችን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከማስገኘት በተጨማሪ የተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃም የተካኑና የተመሰገኑ ታታሪዎች ናቸው። ዛሬ ቀን ጎድሎና በዘረኝነት የፖለቲካ ጥቃት ሰለባ ሆነው ለርሃብ ሲጋለጡ ቢያንስ በሰብዓዊነት ልናዝንላችውና ልንደርስላቸው ይገባል እንጂ ለምን ጥቃታችውና ርሃባቸው ተጋለጠ፥ ለምን ተረዱ በሚል ቡራ ከረዩ ማለት ያስገምታል። ቢያንስ እኮ የክፉ ቀን ደራሽ ባለፀጎች እንጂ በሥንፍና ደኽይተው ለርሃብ የተጋለጡ አልነበሩም። የደረሰባቸው “ብሔር” ተኮር ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት እንጂ። ይሄ በኢትዮጵያ ያልነበረ አዲስ አስቀያሚና ልዩ ታሪክ ነው። ምንም እንኳን ዴሞክራሲያዊና በህዝብ የተመረጠ መሪ ኖሮን ባያውቅም፤ በሀገራችን የነበሩ ርሃቦች በተፈጥሮ የድርቅ አደጋ ተከስተው መሪዎች ለግል ፖለቲካ ስብዕናቸው ሲሉ (አጼ ኃይለሥላሴና መንግሥቱ) ደብቀዋል እንጂ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ደርሱ ዜጎች ተፈናቅለው ፖለቲካዊ ርሃብ ጥቃት ደርሶ አያውቅም።
የተፈፀመባቸው እኮ የዘረኝነት ጥቃት ብቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣትም ጭምር ነው። በዚህ ልናፍርና ሊሰማን ይገባ ነበር። ጉዳዩ ለታሪክም መመዝገብ አለበት። ህዝብን ማፈናቀልና በርሃብ መቅጣት ወንጀል። ይሄ ወንጀል የተፈፀመው በምስኪኑ ኦሮሞ ህዝብ ድጋፍና ይሁንታ አይደለም፤ በአመራሮቹና በደጋፊዎቻቸው እንጂ። ይሄ ደግሞ በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን “የመብት” አራማጅና ወኪል አድርገው የሚቆጥሩ “አክቲቪስቶች” ሚና ቀላል አልነበረም። ለዚህም በተለይ ከ2008 ዓ. ም. ጀምሮ የአቶ ጃዋርን፥ አውስትራሊያ ሜልቦርን የሚገኘው አቶ ፀጋዬ አራርሳ፥ ኖርዌይ ኦስሎ የነበረው አቶ ግርማ ጉተማ፥ ሀገር ውስጥ ያለው አቶ አየለ ደጋጋ ፥ አሜሪካ ያለው ኢታና ሀብቴ እንዲሁም አንዳንድ በ #OMN_TV እና #ONN_OnlineTV ላይ በተለያየ ጊዜ “ብሔር” ተኮር ጥላቻ አዘል ንግግሮች እና ውይይት ላይ ሲሳተፉ የነበሩት ተጠቃሾችን ማኀበራዊ ገፅና ቪዶዮ መመልከት ይቻላል። ይሁን እንጂ እስካሁን ድረስ ግለሰቦች አሊያም የፖለቲካ ድርጅቶች በ”አሮሞ” ስምና ሰቆቃ ከመነገድ እና ራስን የህዝብ “እንደራሴ” አድርጎ ከማቅረብ ባለፈ ማንም ጥላቻና ዘረኝነት እንዲሰብክም ሆነ ዜጎችን እንዲያፈናቅል ሥልጣን አሊያም ውክል የሰጠው ኦሮሞም ሆነ ሌላ ብሔር የለም።
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን ተፈናቅለው በጌዲዮ ዞን ገደብ ወረዳ መጠለያ ካሉ የጌዲዮ ተጎጂዎች በከፊል (ፎቶ፡ የጉጂ ዞን ኮሚኒኬሽን)
በአጠቃላይ በሀገርም ሆነ በብሔር ወይም በፖለቲካ ፓርቲ ወይም ድርጅት ከአቻዎቹ ጋር ተወዳድሮና አማራጭ ሐሳብ አቅርቦ በህዝብ ተመርጦ የተወከለ ማንም የለም። ለደረሱትም ሆነ እየደረሱ ላሉ ጥፋቶች ተጠያቂዎች የበደሉ ፈፃሚዎችና ተባባሪዎቻቸው እንጂ ህዝብ አይደለም። ምክንያቱም ህዝብ እንደ ህዝብ አይበድልም፤ በህዝብ የተወከለም የለምና። የበደል ውክልናም ሆነ ውርስ የለም። ስለዚህ በየትኛውም ቦታ ከክፉዎች ጋር አትተባበር።
እውነታው ከላይ የተጠቀሰው ሆኖ ሳለ ራሳቸውን የ”ኦሮሞ” ማኅበረሰብ ተወካይ ወኪል አድርገው የሾሙና ራሳቸውን የመብት አራማጅ አድርገው የሚቆጥሩ አካላት ፤ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ፖለቲካዊ ርሃብና ጥቃቱ መጋለጥ ለምን አስቆጣቸው? የምስኪኖች ርሃብና ስቃይ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር ምን ያገናኘዋል? ርግጥ ነው። የተፈናቀሉትም ሆነ በደል የደረሰባቸው በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ ነው። በደሉ የተፈፀመባቸው ደግሞ በኦህዴድ/ኦዴፓ ፥ በዘረኝነት ጥላቻ የተገፋፉ ወጣቶች እና በኋላም በአካባቢው በነበሩ የኦነግ ታጣቂዎች ነው። እዚህ ላይ የደቡብ ክልልና፥ በተለይ ለርካሽ ጊዜያዊ ሥልጣናቸው ሲሉ በግፍ ተፈናቃይ ህዝብ ላይ በተፈፀመው ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት ላይ የደቡብ ክልልና የጌዲዖ ዞን አመራሮች እንዲሁም የተወሰኑ የፌደራል ባለሥልጣናት እጅ አለበት። በተለይም በርሃብ መቅጣትና መሸፋፈኑ ላይ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና ህግ ካለ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄን መካድ አይቻልም።
ሌላው አስቂኝ ነገር መልካም ነገር ሲሆን “እኔ ይህን አድርጌ፥ እገሌ ይህን አድርጎ” ይሉናል፥ ሲወደሱም ምስጋናው እና ውዳሴውን ለግላቸው ጠራርገው ይወስዱና ስንት ዋጋ የከፈለውን እና አስተዋፅዖ ያበረከቱትን ስም ቅርጫት ውስጥ ይጥሉታል። ያው ባለሥልጣን ወይም “አክቲቪስት” ሲበድልና ግፍ ስፈፅም ልክ ኦሮሞን አማክረውና አስፈቅደው ያደረጉ ይመስል፤ በደሉንም ውግዘቱንም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ በማስመስል ለማስፈራራት ይሞክራሉ። ወዴት ወዴት!? ይሄ ግብዝነት ብቻ ሳይሆን ድንቁርናም ነው። የቀድሞው ጭካኙ አቶ ጌታቸው አሰፋ በወንጀል ሲጠየቅ ተመሳሳይ የህወሓት ደናቁርት አቶ ጌታቸውን ከምስኪኑ የትግራይ ህዝብ ጋር አያይዘው “ የትግራይ ህዝብ ላይ የተቃጣ ጥቃት” አስመስለው ካድሬዎቻቸው ህዝቡን አስገድደውና አታለው ሰልፍ አስወጥተው ነበር። ይሄንንም ራሳቸውን ተረኛ ባለሥልጣንባለጊዜ አድርገው የሚያቀርቡልን ድኩማን የኦህዴድኦዴፓ ካድሬዎችን ጭምሮ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሲኮንኑ ነበር። በዛ እኔም እስማማለሁ። ምክንያቱም አቶ ጌታቸውም ሆነ የህወሓት አመራሮች እንደዛ አረመኔና ጨካኝ እንዲሆኑ የትግራይ ህዝብ ውክልናም ሆነ ድጋፍ አልሰጣቸውምና። ቀድሞንስ የተበደለ ካልሆነ ማን ያውቅና? ህዝቡ ሚኒገረው ልክ እንደዛርው እንደነ ጠቅላይ ሚኒስር ዶ/ር አብይና ካድሬዎቻቸው የምናቧን ኢትዮጵያ አልነበር? የህወሓት አመራሮችን በተለይም የነ መለስ ዜናዊ እና ጌታቸው አሰፋ የፈፀሙትን በደል ከትግራይ ህዝብ እንደለያችሁት ሁሉ በጉጂዎች የተፈፀመውንም በደል ከኦሮሞ ጋር አታገናኙት። በደለኛው ራሱ ይጠየቅ፥ ሥራው ያውጣው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ አቶ ለማ መገርሳም ቢሆኑ ሰዎች እንጂ መላዕክት አይደሉም። አንዳንዱም ፈጣሪ አድርጎ ሊስላቸው ሚዳዳው ሁሉ አለ። ይቅር በለን እንጂ። ትናንት ጅልጣን ላይ የነበሩም ሆነ ዛሬ በህዝብ ማዕበል ተገፍተውና ተደግፈው ወደ ሥልጣን የመጡት እነ አብይ፥ ደመቀ፥ ለማ፥ ገዱ ያው ኢህአዴግ ናቸው፤ እንደየ ድርሻቸው የተለያየ ወንጀልብደል ላይም ተሳትፎ የነበራቸው ናቸው። ይሄን እነሱም ሚክዱት አይመስለኝም። ያው ከነበረው የ27 ዓመታት ሰቆቃ ወደ ለውጥ መግባታችን ጥሩ፥ “የሚታየውን ብሩህ ለውጥ” ማጨለምና እንቅፋት መሆን ጥሩ አይደለም በሚል እንጂ እያንዳንዱ ዶሲው ከቢሮው መደርደሪያ ቢፀዳም ከያንዳንዱ የጥቃት ሰለባ ወገን እና ተባባሪዎቻቸው ህሊና ሊጠፋ አይችልምና ድጋፉንም ቢሆን በልክ እናድርገው። በየትኛውም ቦታና ጊዜ በደልን እንፀየፍ። መልካም ነገሮችን እናበረታታ። ከዛ ውጭ የሚፈፀሙ በደሎችን ደብቁልን እያሉ ከምስኪኑ ህዝብ ጋር ለማገናኘት መጋጋጥ የትም አያደርስም። የህወሓትም ሰዎችም ቢሆኑ ይህንንም ነበር ያደረጉት። ግን አልጠቀማቸውም። እና ያንን የቆሸሸ መንገድ መልሶ መድገም ጭፍኑ እና ላሞኛችሁ” ዓይነት የጅል ጨወታ ስልሆነ ጉድፍና ቆሻሻን ነገር ከ”ብሔር” ጋር ማያያዝ ተውትይቅርባችሁ። በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን ባጩ “ልሂቃን” እና “አክቲቪስቶች” በስሙ፥ በአስከሬኑ እና ሰቆቃው እየተነገደ ለነበረው ኦሮሞ ማኅበረሰብ ልክ ለፖለቲካ መቆመሪያ የያ ርካሽ ትውልድ እንዳደረገው ዛሬም የልቅሶና የበታችኘት፥ የማስፈራሪያና ዛቻ ስሜት ቅስቀሳን ፖለቲካ አይመጥነውም።
በሰው በደል የሚደሰት ኦሮሞ፥ አማራ፥ ትግሬ፥ ሶማሌ፥ ጌዲዖ፥ አፋር፥ ሲዳማ፥ አኝዋክ፥ ጋሙ፥ ሀዲያ፥ ጉራጌ፥ ስልጤ፥ ሐረሬ፥ … ወዘተረፈ የለም። ህዝብ እንደህዝብ በደል የለበትም፤በጅምላ አንዱን ወገን ከሌላው በመለየት በደልም አያደርስም። ልክ ውዳሴና ሙገሳውን ለግላችሁ እንደምታደርጉት የፈፀማችሁትን በደልና ልለበደሉ ያላችሁን ተሳትፎም ኃላፊነቱን ለወንጀለኞችና ተባባሪዎች እንተው። የተጎዱ ወገኖቻችንን ግን እንታደግ። ሰብዓዊነት ዜግነትም ሆአ ብሔር የለውም። ብሔር ሰውን አልፈጠረም፤አይፈጥርም። ሰው ነው ብሔርንም፥ ባህልንም የፈጠረው። ስለዚህ ቅድሚያ ሰው እንሁን፤ ለሰብዓዊነት ይሰማን። በዛ ላይ የኦሮሞ ማኀበረሰብ እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ማኀበረሰብ ነው። ማኅበራዊ ህይወት የሚመቸው፥ ከመንደርና ቀበሌኛ አስተሳሰብ ይልቅ ሰፋ ያለ ቦታና አድማስን የሚያስቀድም፥ ቀናዒ፥ ኃይማኖትና ሥርዓት ያለው ማኅበረሰብ ነው።
በስሙ የምትነግዱ “ሊሄቃን” እና አክቲቪስቶች” ግን በተቃራኒው ጥላቻ፥ ቀበሌኛ፥ መንደርተኛ፥ የበታችነትና ተጠቂነት ስነ ልቦና ላይ ቆሞ የቀረ ጊዜ ያለፈበት ኋላቀር አስተሳሰብ ላይ ናችሁ። በዛ ላይ ትውልዱም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ሆኖ ከአድማስ ወዲያ አስቦና ሰርቶ፤ ራሱን፥ ቤትሰቡን፥ ማኅበረሰቡን፥ ሀገሩን፥ አህጉሩን እና ዓለምን ሊረዳ የሚችልበት ጉልበቱን፥ አእምሮና ጊዜውና በጥላቻ፥ በተጠቂነት፥ መንደርተኝነትና ቀበሌኛ ስነልቦና ውስጥ አታስቀሩት። የትናንቷ ዓለም ዛሬ የለችም። የዛሬዋ ደግሞ ነገ አትኖርም። ነገ ደግሞ ከዛሬው የበለጠ ብዙ ፈታኝ ውስብስብ የውድድር ዓለም ነው የሚጠብቀን። ከትንሽ ጊዜ በኋላ አይደለም የመንደር “ብሔር” ተኮር ቀበልኛ ኋላ ቀር አስተሳሰብ ቀርቶ ኢትዮጵያ ራሷ ትንሽዬ መንደር የምትሆንበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። ያውም ዓለም በመሰረተ ልማትና በዲጅታል ትክኖሎጂ ከምናስበው ፍጥነት በላይ እየተሳሰረ ባለበት በዚህ ወቅት። እንኳን የስግብግብ መንደርተኛ ፖለቲካ ላይ እኝኝ ብለን ቀርቶ ምሥራቅ አፍሪካ እንኳ አንድ ላይ ብንቀናጅ እየመጣ ያለውን ፈታኝ የውድድር ህይወት መቋቋም አንችልም። ከመቼው ጊዜ በላይ የጠነከረ ህብረት፥ አንድነትና መከባበር ያስፈልጋል። ለአንዱ ሚያስፈልገው መልካም ነገር ሁሉ ለሌላውም ያስፈልገዋል። አንዱ ላይ የንፈፅመው በደልና ጥላቻ ሁሉ ይዋል ይደር እንጂ አፀፋዊ መልስ ይዞ መምጣቱ የማይቀር ነው። በዛ ላይ መቶ ዓመት ለማንኖርባት ጊዜያዊ ዓለም።
በርግጥ አውቃለሁ። በ”ኦሮሞ” ስም የሚነግዱ ኋላቀር እና የዘረኝነት ቅስቃሳና ፖለቲካ የሚያራምዱ በምቾት የሚኖሩበት የሌላ ሀገር ፓስፖርትና መኖሪያ ቤት አንዳንዶቹ በአሜሪካ፥ አውሮፓና አውስትራሊያ አላቸው። እንደ ሀገር ኢትዮጵያ ብትጎዳ፥ ወይም እንደ ህዝብ ኦሮሞ ቢጎዳ እነሱ ሌላ የምቾት መኖሪያሌላ ሀገር ስላላቸው ሳይነግሩህ በቦሌ ተሳፍረው ነው ሚሄዱት። ከዛ ባንተ አስከረንና ሰቆቃ ገንዘብ ይለቃቅማሉ። አለቀ። አንተ ሰላም ከሆንክና አተመቸንህ ግን ባንተ ስም ገቢ የላቸውም። ከዚህ የተለየ ግብ አላቸው ካልክ በስምህ ምለው ተገዝተው የሚነግዱትን ፍላጎታቸውና ዓላማቸውን እንዲሁም ምክንያታቸውን ጠይቅ። ከዛ ለምን የሌላ ሀገር ፓስፖርት ይዘው እንደሚኖሩ ጠይቅና፤ ከዛ እሱን ትተውካንተ ጋ ያለውን ተካፍለው እንዲኖሩ ጠይቃቸው። ያኔ ምላሽና ተግባራቸውን ተመልከት። በነጋታው ቻዎ እንኳን ሳይሉህ ደጋግ፥ ሥልጡን እና ሰብዓዊነት የሚሰማቸው ሰዎች ወደሰጧቸውና ወደፈቀዱላቸው የምቾት ሀገር ይመጣሉ። የሚያሳዝነኝ ምስኪኑ ወጣት ነው። አጣችም ደኽየችም ያለችው ያቺው ምስኪን አንዲት ኢትዮጵያ ናት። ተከባብሮ በአንድነት በሰላም ኖሮና ሰርቶ ፤ወጣቱ ተረጋግቶ እንዳይኖር በሰቆቃው የጉስቁልናው ህይወቱ ለሚነግዱ መቆመሪያ ማድረጉ ነው። ወዳጄ! ከሞት በኋላ ትንሳኤ ኃይማኖት ላይ እንጂ ምድርና ፖለቲካ ላይ የለም። ከሞትክ ሞትክ ነው፤ አበቃ። ስትሞትና ስትጎዳ ምታጎለው ራስህን እና ቤትሰብህን ሌላ ማንንም አይደለም። በሞትህ የሚጠቀመው ደግሞ፥ የሬሳ ሳጥን ሻጭ፥ የመቃብር ጉድጓድ ቆፋሪና በሞትህና ስቃይ ቆምሮ የሚከብር አረመኔን ብቻ ነው። ስለዚህ ነፃ ሆነህ፥ ሰልጥነህ፥ ጤናማ ደስተኛ ሆነህ ከሁሉም ጋር በፍቅር ኑር።
አንተ ላይ እንዲፈፀም የማትፈልገውን መጥፎ ነገር በሌሎች ላይ አታድርግ፤ ላንተ እንዲሆንል የምትመኘውን መልካም ነገር ሁሉ ያለምንም አድሎ ለሌሎችም አድርግ!! ምክንያቱም ሌላውም ሰው ልክ እንዳንተ መልካም ነገሮች የሚያስፈልጉት ሰው ነውና።