Tag Archives: Amhara regional state

በከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ላይ ሰኔ 15 የተፈጸመው ግድያ ዓቃቤ ሕግንና ተጠርጣሪዎችን እያወዛገበ ነው

ታምሩ ጽጌ
‹‹ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተቋሙን የማይመጥን ውሳኔ ሰጥቷል››

ተጠርጣሪዎች

‹‹የተወሰኑ ተጠርጣሪዎች በህቡዕ ተደራጅተው ጦርነት ይመሩ ነበር››

ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ

በአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ በመከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹምና በጓደኛቸው ላይ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በተቀራራቢ ሰዓታት ውስጥ የተፈጸመው ግድያ፣ ዓቃቤ ሕግንና ከግድያው ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው የታሰሩ ተጠርጣሪዎችን ማወዛገቡ ቀጥሏል፡፡

ግድያው በተፈጸመ ማግሥት ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በቁጥጥር ሥር ውለው በተለያዩ ጊዜያት ፍርድ ቤት ሲቀርቡ፣ የተጠረጠሩት ከግድያው ጋር በተያያዘና የሽብርተኝነት ሕግን አዋጅ ቁጥር 652/2001 በመተላለፍ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው መሆኑን የሚናገሩት ቁጥራቸው ከ30 በላይ የሚሆኑት ተጠርጣሪዎች፣ ግድያውን በሚመለከት የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥት አመራሮች የተናገሩትና ያሰራቸው የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ የሚናገረው የተለያየ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ከፍተኛ አመራሮች ግድያን በማቀነባበርና በመሳተፍ ተጠርጥረው፣ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው በፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ተጠይቆባቸው ቢፈቀድም፣ ፖሊስ በተሰጠው ጊዜ ምንም ዓይነት ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ባለመቻሉ፣ ፍርድ ቤቱ ሰፊ ትንታኔ በመስጠት በዋስ እንዲለቀቁ ውሳኔ ሰጥቶ እንደነበር ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት አስረድተዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በጠበቆቻቸው አማካይነት ነሐሴ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ባቀረቡት ክርክር እንዳስረዱት፣ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ያቀረቡት የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዝርዝር ትንታኔ በመስጠት ለደንበኞቻቸው የጠበቀላቸውን ሕገ መንግሥታዊ የዋስትና መብት፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ያላግባብ ስለነፈጋቸው ነው፡፡ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ሕገ መንግሥታዊ የሆነውን የዋስትና መብት የነፈጋቸው፣ ተቋሙን በማይመጥንና የዳኝነትን ብቃት ግምት ውስጥ ሊያስገባ በሚችል ሁኔታ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼውም አንድ የፀረ ሽብር ተግባር ወንጀል ፈጽሟል ተብሎ የተጠረጠረ ዜጋ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 20 (3) ድንጋጌ መሠረት ምርመራ ሊፈቀድበት የሚችለው 28 ቀናት ሆኖ ተደንግጎ እያለ፣ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በደንበኞቻቸው ላይ የተሰጠው የምርመራ ጊዜ 42 ቀናት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼ ደግሞ የሕጉን ድንጋጌ ከመጣሱም በላይ፣ ምንም ዓይነት ማስረጃ ያልቀረበባቸው ተጠርጣሪዎችን ከሕግ አግባብ ውጪ እንዲታሰሩ ማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ዓቃቤ ሕግ፣ የፖሊስ አባል፣ የአብን አመራሮችና አባላት፣ የተቋማት ሠራተኞችና ሌሎችም ሲሆኑ፣ በመዝገብ ቁጥሮች 181966፣ 181965፣ 182124፣ 182129 እና በመዝገብ ቁጥር 182150 ተካተው በአምስት መዝገቦች ከ30 በላይ ተጠርጣሪዎች የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔን በመቃወም በሰባት ጠበቆች ተወክለው ሰፊ ክርክር አድርገዋል፡፡

የፌዴራል መንግሥትና የአማራ ክልል የመንግሥት አመራሮች በአማራ ክልል አመራሮች ላይ የተፈጸመው ግድያ ‹‹የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ነው›› እያሉ በይፋ ከዕለቱ ጀምሮ በመገናኛ ብዙኃን ጭምር ገልጸው እያለ፣ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል መጠርጠር እርስ በርሱ የሚጣረስና ሕዝብንም እምነት የሚያሳጣ መሆኑን ጠበቆቹ ገልጸዋል፡፡

ፖሊስ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሯቸዋል ቢባል እንኳን፣ በተፈቀደለት የ28 ቀናት ጊዜ ውስጥ ማን በማን ላይና ምን ዓይነት ወንጀል እንደፈጸመ በመለየት በዝርዝርና በተናጠል ለፍርድ ቤት ማቅረብ እንዳለበት በሕጉ ተደንግጎ ቢገኝም፣ 28 ቀናት ቆይቶ ፍርድ ቤት ሲቀርብ ምንም ዓይነት የምርመራ ውጤት አለማቅረቡን አስረድተዋል፡፡

የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤትም የፖሊስ ምርመራ መዝገቦችን አስቀርቦ ከመረመረ በኋላ፣ ምንም ዓይነት ለሽብር ተግባር ወንጀል የጥርጣሬ መነሻ ነገር ባለማግኘቱ፣ ተጠርጣሪዎቹ ከ2,000 ብር እስከ 5,000 ብር በሚደርስ ዋስትና ከእስር እንዲፈቱ ውሳኔ መስጠቱንም ገልጸዋል፡፡ ፖሊስ ‹‹በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ›› በማለት ላሰራቸው የአብን አባላት ያቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹ማንን ነው የምትረዱት? ማነው ያሰማራችሁ?›› የሚሉና ‹‹ጠርጥሬያችኋለሁ›› ካለበት መነሻ ሐሳብ ጋር የማይገናኝ መሆኑንም ጠበቆቹ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የአዲኃን ሥልጠና ወስዳችኋል፣ ከእነ ዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አላችሁ›› የሚሉ የግለሰቦች ወይም የተወሰነ ቡድን ፍላጎትን የሚያንፀባርቁ ጥያቄዎች እንጂ፣ ከሰኔ 15 ቀን የከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር የሚያያዝ ምንም ዓይነት ምርመራ እንዳልተካሄደባቸውም አስረድተዋል፡፡

አንዳንዶቹ በተለይ ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለና የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ባልደረባና የልደታ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያ መርማሪ ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆናቸውን ደርሰንበታልና መረጃ ያቀብላሉ›› ከሚል ምርመራ በስተቀር፣ የሽብር ወንጀል ተሳትፏቸው ምን እንደሆነ ያቀረበው የጥርጣሬ መነሻ ማስረጃ እንደሌለም ገልጸዋል፡፡

‹‹የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዋስትና የከለከላቸው አቋም ይዞ ነው፤›› የሚሉት የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች፣ ይኼንንም ሊያስብላቸው የቻለው በዋስ እንዲወጡ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት እያንዳንዳቸው የ5,000 ብር ዋስትና ማቅረብ እንዳለባቸው ውሳኔ የተሰጠላቸው፣ አቶ የወግሰው በቀለና ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ ዋስትናቸው ወደ 200,000 ብር ማሳደጉ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ዋስትና ከተፈቀደላቸው ሳምንት ቢሞላቸውም፣ አቅማቸውን ያላገናዘበ ዋስትና በመሆኑ ከእስር ሊለቀቁ እንዳልቻሉም አክለዋል፡፡ ሌላው ጠበቆቹ ያቀረቡት ክርክር ሕጉ ግልጽ ሆኖ ሳለ፣ ለምን ተለጥጦና ለተጠርጣሪ በማይጠቅም ሁኔታ እንደሚተረጎም እንዳልገባቸው ጠቁመው፣ ከሰኔ 15 ቀን የእነ ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ግድያ ጋር በተያያዘ፣ ‹‹የገዳዩ ሚስት ናት›› የተባለችና ከግድው ጋር ምንም ግንኙነት የሌላት ሴትም ታስራ እንደምትገኝ ገልጸዋል፡፡ ዳኞቹ የሚሠሩት ለህሊናቸውና ለሕግ ተገዥ ሆነው ቢሆንም፣ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአግባቡ የሰጠውን ውሳኔ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ያገደበትና ከሕጉ ውጪ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር በአጠቃላይ 42 ቀናት የፈቀደበት ሒደት፣ ከሕግ አግባብ ውጪ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ ራሱ ጠይቆ የነበረው 28 ቀናት እንደሚበቃው ገልጾ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ 42 ቀናት መፍቀዱ ለምንና በየትኛው የሕግ አግባብ እንደሆነ ግልጽ አለመሆኑንም አክለዋል፡፡ አዴፓ ‹‹እርስ በርሳችን ተጠፋፋን›› እያለ ከ30 በላይ ንፁኃን ዜጎችን ማሰር፣ ተገቢ አለመሆኑንም ገልጸዋል፡፡ መፈንቅለ መንግሥት መሆኑ የተገለጸበትን ድርጊት የሽብር ተግባር ወንጀል በማለት ዜጎችን ያላግባብ ማሰር ሆን ተብሎ ሰብዓዊ መብታቸውን ላለማክበር የተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ጠበቆችን ጭምር በነፃነት እንዳይከራከሩና እንዳይናገሩ ጫና በማድረግ፣ በክርክሩ ወቅት ያነሷቸውን መከራከሪያ ሐሳቦች እንኳን እንዳልመዘገበላቸውም አስረድተዋል፡፡ በአጠቃላይ ደንበኞቻቸው ታስረው የሚገኙበት ጉዳይ እንኳን በሽብር ተግባር ወንጀል፣ በተራ ወንጀል እንኳን ሊያስጠረጥር እንደማይችል የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በክርክራቸው አስረድተዋል፡፡

ከሰኔ 15 ቀን ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረዋል ስለተባሉትና ይግባኝ ስለጠየቁት ተጠርጣሪዎች፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀርቦ ምላሽ የሰጠው (የተከራከረው) የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል መርማሪ ሳይሆን ዓቃቤ ሕግ ነው፡፡ በዕለቱ የቀረቡት ሁለት ዓቃቢያነ ሕግ እንዳስረዱት፣ እያንዳንዳቸው ተጠርጣሪዎች ከሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በፊት ሲደራጁ ቆይተው፣ በተለያዩ አቅጣጫዎች በመንቀሳቀስ ግድያው እንዲፈጸም አድርገዋል፡፡ ይኼ ሁኔታ በተፈጸመበትና ፖሊስ ስለሁኔታው በማጣራት ላይ እያለ፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተጠርጣሪዎቹ በዋስ እንዲወጡ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ ድርጊቱን ‹‹ተራ የፖለቲካ ሽኩቻ ነው›› በማለት የዳኛውን ገለልተኛነት የሚያጠራጥር መሆኑንም አክለዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ እንዳብራሩት የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የምርመራ መዝገቡን ወስዶ ለሳምንት ማቆየቱና አልመልስም በማለቱ፣ እጃቸው ላይ በነበረ ሰነድ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብለው፣ የተጠርጣሪዎቹ የዋስትና መብት እንዲታገድ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡ በተለይ አራት ተጠርጣሪዎች በኅቡዕ ጦር እየመሩ እንደነበርና መረጃ ሲለዋወጡበት የነበረን ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጠይቀው በመጠባበቅ ላይ እያሉ፣ ዋስትና መፍቀድ ተገቢ አለመሆኑንም ዓቃቢያነ ሕጉ ተናግረዋል፡፡

በግለሰብ እጅ ሊገባ የማይችል የጦር ሜዳ መነጽር መገኘቱንም ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ በወታደራዊ አመራሮች ላይ ግድያ ሲፈጸም የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲቋረጥ ግዳጅ የተሰጣቸው፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሠራተኞች መያዛቸውንም ገልጸዋል፡፡ የጦር መሣሪያ መግዛቱንና 6,000 ጥይቶች ቢኖሩትም ከጎንደር እንዴት እንደሚያሳልፈው ምክክር ሲያደረግ የነበረ ተጠርጣሪና ሌሎችም፣ በኅቡዕ ተደራጅተው በእነማን ላይ ዕርምጃ እንደሚወስዱ ሥልጠና ጭምር የወሰዱ ተጠርጣሪዎች መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ ይኼ ሁሉ ባለበት ገና በምርመራ ላይ እንደሆኑ እየገለጹ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዋስትና መፍቀዱ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰኔ 15 ከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ የሽብር ተግባር ስለመፈጸሙ ከተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ጋር እየሠሩ እያለ፣ የወንጀል ተግባሩን በመቀየር ዋስትና መስጠቱም ተገቢ አለመሆኑን ዓቃቢያነ ሕጉ ደጋግመው አስረድተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ በመሀል፣ ‹‹በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ላይ ለወንጀል ጥርጣሬ መነሻ የሚሆን የምርመራ ውጤት አቅርባችሁ ነበር?›› የሚል ጥያቄ ለዓቃቢያነ ሕጉ አቅርቦላቸው፣ ማን ከማን ጋር ግንኙነት እንደነበረው በቂ መጠርጠሪያ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ቀሪ መረጃና ማስረጃ በመሰብሰብ ላይ እንደሆኑም ማስረዳታቸውን ከኢትዮ ቴሌኮም፣ ከባንክ፣ የባልደራስ ምክር ቤትን እንደ ሽፋን በመጠቀም ወንጀል መፈጸማቸውን ለማሳየት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት መረጃ መጠየቃቸውን ቢገልጹም፣ ፍርድ ቤቱ እንዳልተቀበላቸው አስረድተዋል፡፡

ከፍተኛው ፍርድ ቤት ግን ያቀረቡትን የይግባኝ አቤቱታ በሚገባ ከተመለከተ በኋላ፣ ዋስትናውን እንደሻረውም አክለዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹እናንተ (ዓቃቢያነ ሕጉ ወይም ፖሊስ) 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ጠይቃችሁ ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንዴት ከዚያ በላይ ሊፈቅድ ቻለ?›› በማለት ሲጠይቃቸው፣ ችሎቱ የበዓል ቀናትን ትቶ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር መስጠቱን ጠቁመው ስህተት ከሆነ ሊታረም እንደሚችል ተናግረዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በምርመራ ላይ ከሆናችሁ እንዴት እስካሁን አልጨረሳችሁም? አሁንስ በምን ላይ ናችሁ?›› የሚል ጥያቄ አቅርቦላቸው፣ ተጠርጣሪዎቹ ሲዘጋጁ የከረሙት ከጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም. ጀምሮ መሆኑን፣ በቤንሻንጉል ጉምዝ ዋና ከተማ በአሶሳና በአዲስ አበባ የተፈጸመውን ሁሉ ማጣራት ስላለባቸው፣ እየሠሩና የጠየቁት ለመረጃ እስከሚመጣላቸው እየጠበቁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በተሰጣቸው ድጋሚ የመከራከሪያ ዕድል እንዳስረዱት፣ ዓቃቤያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንት ቀናት በዳኛ ዕግድ መቆየቱን ለችሎቱ መግለጻቸው፣ ከአንድ ከፍተኛ የሕግ ተቋም የማይጠበቅ ምላሽ ከመሆኑም ባለፈ ግምት ውስጥ የሚከት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ የራሱን ዋና የምርመራ መዝገብ ይዞ ለፍርድ ቤት የሚያቀርበው ደግሞ ግልባጩን (ኮፒ) መሆኑን ጠቁመው፣ መዝገቡ ዳኛው ዘንድ ስምንት ቀናት መቆየቱንና ‹‹አልሰጥም አሉኝ›› የሚል ሰበብ ማቅረብ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሌላው ዓቃቢያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ አካል ያልሆነን ጉዳይ ‹‹አሶሳ ከተማ የተፈጸመን ድርጊትም እየመረመርኩ ነው›› ማለቱ የማይገናኝ ነገር ለማገናኝት መሞከር መሆኑንም አክለዋል፡፡ የጦር ሜዳ መነጽር ይዘው ተገኝተዋል በማለት ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹን ለመወንጀል ያደረገው ጥረት፣ ‹‹መነጽር አይደለም ታንክ ይዘው ቢገኙ ሽብር ነው ማለት ነው?›› በማለት ጠይቀው፣ ፍርድ ቤቱ መዝገቡን አስቀርቦ እንዲያይላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተገኘ የተባለው የጦር ሜዳ መነጽር የዩኒቨርሲቲ ማስተማሪያና ከመምህር ቤት የተገኘ መሆኑንም አክለዋል፡፡ በኅቡዕ ተደራጅተው ጦር ሲመሩ ነበር የተባሉት ደንበኞቻቸው ጫማ የሚጠርጉ ሊስትሮዎች፣ የቤት ሠራተኞችና የፖለቲካ ድርጅት አባላት መሆናቸውንም አክለዋል፡፡

ግድያው ሰኔ 15 ቀን ተፈጽሞ ደንበኞቻቸው ሰኔ 16 ቀን መያዛቸው የሚገርም እንደሆነ የገለጹት ጠበቆቹ፣ ይኼ የሚያሳየው እነሱን ለመያዝ ዝርዝር ተይዞና ቀደም ብሎ ዝግጅት መኖሩ የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሽብር ተግባር ወንጀል አያስቀጣም ሳይሆን፣ በአዋጅ ቁጥር 652/2011 አንቀጽ (19) መሠረት ሊያስጠረጥራቸው የሚችል ማስረጃ እንዳልተገኘባቸው ወይም ፖሊስ በተሰጠው የ28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ሊያቀርብ እንዳልቻለ መግለጹ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹ የጦር ሥልጠና ሲያደርጉ እንደነበር መግለጻቸው ስህተት መሆኑን ጠበቆቹ ጠቁመው፣ መንግሥት ራሱ በጀት መድቦ ሲያሠለጥናቸው የነበሩ መሆናቸውን አክለዋል፡፡ በአጠቃላይ ፖሊስ እንኳን ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ቀርቶ ቃላቸውን እንኳን እንዳልተቀበላቸውም ጠቁመዋል፡፡

ተጠርጣሪው ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለ ለሥር ፍርድ ቤቶች ከታሰረ 50 ቀናት እንደሞላው ሲያስረዳ፣ ፍርድ ቤቱ ለምን ምርመራ እንዳልጨረሰ ፖሊስን ሲጠይቀው፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆኑን ስለደረሰበት እያጣራ መሆኑን እንደገለጸም አስታውሰዋል፡፡

የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለነሐሴ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Ethiopian Reporter

ኢትዮጵያ- የአማራ ህዝብ የመብት ጥያቄና ( #AmharaProtests) በመንግስት የተወሰደው የኃይል እርምጃ

በአማራ የተቃውሞ ድምጽ በሚያሰሙ ዜጎች ላይ የሚደርሰው የመብት ጥሰት ግድያ፣ የእስርና ደብዛ መጥፋት መጠኑ ይለያይ እንጂ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ በተለይም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ አሁንም ድረስ በጎንደር፣ በባህር ዳርና በምዕራብ ጎጃም ዞኖች ዜጎችን በገፍ የማሰሩ እርምጃ ቀጥሏል፡፡

nigist-yirga-gonder-on-public-protest

ወጣት ንግስት ይርጋ  በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ

በተቃውሞ ሰልፎች የተሳተፉ ወጣቶችን በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች በገፍ ማሰሩ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው ከተሞች ከፍተኛ ነው ፡፡ ለምሳሌ በጎንደር ከተማ በሚገኙ 1ኛ፣ 2ኛ፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ እና 6ኛ ፖሊስ ጣቢያዎች በጠባብ ክፍሎች ውስጥ በአንድ ጣቢያ በአማካይ እስከ 140 ሰዎች እንደሚታሰሩ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

ጎንደር ከተማ ውስጥ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ለሁለት ሳምንታት ታስሮ የነበረ ወጣት ደረጀ ጌቱ (ስሙ የተቀየረ) እንደሚናገረው በጣቢያው ውስጥ አብረውት ታስረው የነበሩት አብዛኞቹ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ መሳተፋችሁ በፎቶ ተረጋግጧል በሚል ለእስር ተዳርገው የነበሩ ናቸው፡፡

በተመሳሳይ በባህር ዳር ከተማ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እንዲሁ በከተማዋ ተደርጎ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት በተሳተፉ ወጣቶች በገፍ እየታሰሩ ነው፡፡ እነዚህ ወጣቶች አንዳንዶቹ በአጭር ጊዜ ሲታሰሩ እና ሲፈቱ ሌሎች ደግሞ በተደጋጋሚ መታርና መፈተታ እንደሚገጥማቸው ማየት ተችሏል፡፡
በእነዚህ ፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩትን ማን እንደታሰረና፣ የት እንደታሰረ ቤተሰብና ዘመድ የማወቅ እድል ቢኖረውም ሌሎች የት እንደታሰሩ ሳይታወቅ ለቀናት፣ ለሳምንታትና ለወራትም የሚከርሙ መኖራቸውም ታውቋል፡፡ እነዚህ የእስር ስፍራዎች በይፋ የማይታወቁና በተቃውሞ እንቅስቃሴው እጃቸው በሰፊው አለበት በሚል መንግስት የጠረጠራቸውን “የሚመረምርባቸው” ናቸው፡፡

ከእነዚህ ድብቅ የእስር ቦታዎች መካከል ለምሳሌ ባህር ዳር አባይ ማዶ ከብአዴን ጽ/ቤት ጀርባ የሚገኝ ቀድሞ የመሳሪያ መጋዘን የነበረ ስፍራ ይገኝበታል፡፡ በዚህ ቦታ የሚታጎሩ ወጣቶችን ቤተሰቦቻቸው ለመጠየቅም ሆነ በዚያ ስፍራ ስለመኖር አለመኖራቸው ለማወቅ እንደማይችሉ ታስረው የተፈቱና፣ ታስረው እንደነበርም እንዳይናገሩ ማስፈራሪያ ደርሷቸው የወጡ ይመሰክራሉ፡፡ አበበ አስረስ (ስሙ የተቀየረ) በዚህ ድብቅ የእስር ቦታ ለ17 ቀናት ሲሰቃይ ቆይቶ መለቀቁን ይናገራል፡፡

‹‹ቦታው የሆነ መጋዘን ነገር ነው፤ ሰፊ አዳራሽ ነው፡፡ በዚህ አዳራሽ ውስጥ በጣም ብዙ ሰዎች አብረውኝ ታስረው ነበር፡፡ የእስራችን ምክንያት ብለው የነገሩን ባህር ዳር ነሐሴ 01/2008 ዓ.ም በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰልፉን አደራጅታችኋል የሚል ነው፡፡ በእስራችን ጊዜ ቤተሰቦቻችን አንድም ቀን አላገኙንም፡፡ በኋላ ብዙዎችን ወደ ብርሸለቆ ሲወስዷቸው እኔን ድጋሜ ሰልፍ ላይ ካገኘንህ እንገድልሃለን ብለው ዝተውብኝ የሆነ ወረቀት ላይ አስፈርመው ለቀውኛል፡፡ ማታ ላይ ነው በመኪና ከሌሎች ሦስት ልጆች ጋር ጥለውኝ የሄዱት›› ሲል ያስታውሳል አበበ፡፡

አበበ አስረስ ከድብቅ እስር ቤቱ መፈታቱን ተከትሎ ዘመድ ለመጠየቅ በሚል ከአካባቢው ዞር ለማለት አስቦ የቤተሰቦቹን ምክር ተቀብሎ ወደ አዲስ አበባ ዘመድ ጋር ሳምንታትን አሳልፏል፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ጊዜ ነበር እስር ላይ ሆኜ ያሳለፍኩት›› የሚለው አበበ፣ ከሳምንታት የአዲስ አበባ ቆይታ በኋላ የገና በዓልን ከቤተሰቦቹ ጋር ለማሳለፍ ወደ ባህር ዳር በተመለሰበት ወቅት፣ ‹‹የት ጠፍተህ ከርመህ እንደመጣህ እናውቃለን!›› በሚል በድጋሜ ለእስር እንደተዳረገ ታውቋል፡፡

በድብቅ እስር ቤቶችም ሆነ በፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩ ሰዎች የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጸም ለማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን፣ በተለይ ድብደባ በብዙዎቹ ላይ በምርመራ ወቅት የሚፈጸም የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፡፡ በባህር ዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ የሚታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በምርመራ ወቅት ጥፍርን እስከመንቀል የሚደርስ ኢ-ሰብዓዊ የሆነ ድርጊት ይፈጸምባቸዋል፡፡

ብዙዎች በፖሊስ ጣቢያ ለሳምንታት እንዲቆዩ ከተደረገ በኋላ ወደ ብርሸለቆ የወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም ለ‹ተሃድሶ ስልጠኛ› ተግዘዋል፡፡ በማሰልጠኛ ተቋሙ በሚኖራቸው ቆይታም ቢሆን ተመሳሳይ፣ አንዳንዴም የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል፡፡ (በተሃድሶ ማሰልጠኛ ስፍራዎች ስለሚፈጸም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት በቅርቡ ለማሳያነት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት መመልከት ይቻላል፡፡)
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት በዋናነት ቀድሞውንም በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ በሚታገሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ ያነጣጠረ የእስር እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ‹የጸረ-ሽብር ግብረ-ኃይል› በሽብር ጠርጥሬያቸዋለሁ በሚል 2008 ዓ.ም ሐምሌ ወር መግቢያ ላይ በጎንደር በነበሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጠያቂ የህዝብ ተወካይ (ኮሚቴ) አባላትን ለማሰር በተደረገ እንቅስቃሴ በሁዋላ በአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ህዝባዊ ተቃውሞዎች በተደጋጋሚ መከሰታቸው ይታወሳል፡፡ የህዝባዊ ተቃውሞዎቹም መነሻ ከመስፋፋታቸው በፊት ጎንደር ላይ ብዙ ነዋሪዎች የተሳተፉበት ትልቅ እና ሰላማዊ ሰልፍም ተካሄዷል፡፡

ከጎንደር በማስከተል በሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም የተከናወነው የባህር ዳር ሰልፍ ግን በተለየ መልኩ በአሳዝኝ ሁኔታ የተጠናቀቀ ነበር፡፡ ሰልፉ ሲጀምር ሰላማዊ የነበር ቢሆንም ዘግይቶ የመንግስት ታጣቂዎች በወሰዱት እርምጃ በአንድ ቀን ብቻ ከ50 በላይ የሚገመቱ ንጹሃን መገደላቸው የሚታወስ ነው፡፡

እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት አማራ ክልል ከሚገኙት በአጠቃላይ 11 ዞኖች በስድስቱ ዞኖች የጎላ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ተደርጎባቸዋል፡፡ እነዚህም ሰሜን ጎንደር፣ ደቡብ ጎንደር፣ ባህር ዳር ልዩ ዞን፣ አዊ ዞን፣ ምዕራብ ጎጃም እና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች ናቸው፡፡ በስድስቱ ዞኖች የሚገኙ አብዛኞቹ የዞንና የወረዳ ከተሞች (አንዳንድ ቦታዎች ላይ ገጠር ቀበሌዎችንም ጨምሮ) መንግስትን የሚቃወሙ ሰላማዊ ሰልፎችንና የቤት ውስጥ አድማዎችን አስተናግደዋል፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማና የቱሪስት መናሃሪያዋ ጎንደር ላይ የተጀመረው እንቅስቃሴ፣ ደባርቅ፣ ደብረታቦር፣ መተማ፣ አምባ ጊዮርጊስ፣ ወረታ፣ ስማዳ፣ ጋይንት፣ ባህር ዳር፣ ፍኖተ ሰላም፣ ቡሬ፣ እንጅባራ፣ ዳንግላ፣ ቻግኒ፣ ቲሊሊ፣ ብርሸለቆ፣ ቋሪት፣ ደምበጫ፣ አማኑኤል፣ ደብረ ማርቆስና ሌሎች በርካታ ከተሞችን አዳርሷል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት አድማሱን እያሰፋ የሄደውን የተቃውሞ እንቅስቃሴ ለመግታት የኃይል እርምጃ መውሰዱን በተግባር ከማሳየቱም በላይ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የመንግስት ጦር ተቃውሞውን ለመግታት ‹ማንኛውንም እርምጃ እንዲወስድ› ማዘዛቸው የሚታወስ ነው፡፡ በዚህም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል፡፡ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች እንደ ብርሸለቆ የመሰሉ የጦር ማሰልጠኛዎች ውስጥ ሳይቀር በተለያዩ ቦታዎች ታስረዋል፤ በርካቶች ደግሞ የደረሱበት አልታወቀም፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ባለፉት ወራት በተደረጉት የአማራ ህዝብ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ወቅት ለጊዜው ያሰባሰበው መረጃም ብዙ ዜጎች በመንግስት ኃይሎች እንደተገደሉ ያሳያል፡፡ ከዚህ በታች ያለው ዝርዝር ለጊዜው ተለይተው የታወቁ የሟቾችን ስምና አድራሻ አካትቶ ለማሳያነት የቀረበ ነው፡፡

የተገደሉ ሰዎች ስም አድራሻ
1. ይሻል ከበደ ……………………………ጎንደር
2. ሲሳይ ታከለ ……………………………ጎንደር
3. አበበ ገረመው…………………………ባህር ዳር
4. ተፈሪ ባዬ ………………………………ባህር ዳር
5. እድሜዓለም ዘውዱ ……………………ባህር ዳር
6. አደራጀው ደሳለኝ …………………… ባህር ዳር (ዩኒቨርሲቲ)
7. ይበልጣል…………………………………ደብረ ታቦር
8. ግዛቸው ከተማ …………………………ጎንደር
9. አዳነ አየነው ………………………………ጎንደር
10. ማንደፍሮ አስረስ………………………ባህር ዳር
11. ቁምላቸው ቃሉ …………………………ባህር ዳር
12. አወቀ ጥበቡ ……………………………ፍኖተ ሰላም
13. ሲሳይ ከበደ ……………………………ጎንደር
14. ሰጠኝ …………………………………ጎንደር (የወልቃይት ተወላጅ)
15. እቴነሽ ሽፈራው ……………………ም/ጎጃም፣ ጂጋ
16. እንዳለው መኮነን …………………ጎንድር፣ ጋይንት
17. እሸቴ ……………………………… ባህር ዳር (ቀበሌ 16)
18. ሰለሞን አስቻለ ………………………ባህር ዳር
19. ሙሉቀን ተፈራ ………………………ባህር ዳር
20. አደራጀው ኃይሉ ………………………ባህር ዳር
21. አስማማው በየነ ……………………… ባህር ዳር
22. ታዘበው ጫኔ …………………………ባህር ዳር
23. አስራት ካሳሁን …………………………ባህር ዳር
24. የሺዋስ ወርቁ ……………………………ባህር ዳር
25. ብርሃን አቡሃይ ………………………… ባህር ዳር
26. ሽመልስ ታየ ………………………………ባህር ዳር
27. አዛናው ማሙ …………………………… ባህር ዳር
28. ሲሳይ አማረ ………………………………ባህር ዳር
29. ሞላልኝ አታላይ ………………………… ባህር ዳር
30. መሳፍንት ………………………………………ጎንደር፣ እስቴ
31. እንግዳው ዘሩ ………………………………… ባህር ዳር
32. ዝናው ተሰማ ………………………………… ባህር ዳር
33. ሞገስ ሞላ ………………………………………ባህር ዳር
34. ሞላልኝ ታደሰ …………………………………ባህር ዳር
35. ይታያል ካሴ ………………………………………ባህር ዳር
36. እሸቴ ብርቁ …………………………………… ባህር ዳር
37. ሞገስ………………………………………………ባህር ዳር
38. ገረመው አበባው ………………………………ባህር ዳር
39. ማህሌት…….…………………………………… ባህር ዳር
40. ተስፋየ ብርሃኑ …………………………………ባህር ዳር
41. ፈንታሁን………………………………………… ባህር ዳር
42. ሰጠኝ ካሴ ……………………………………… ባህር ዳር
43. ባበይ ግርማ ………………………………………ባህር ዳር
44. አለበል ዓይናለም ……………………………… ደብረ ማርቆስ
45. አብዮት ዘሪሁን …………………………………ባህር ዳር
46. አበጀ ተዘራ ………………………………………ወረታ
47. ደሞዜ ዘለቀ ……………………………………ወረታ
48. አለበል ሀይማኖት ………………………………ባህር ዳር
49. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
50. ዓይናዲስ ለዓለም ……………………………… ደብረወርቅ
51. ሽመልስ ወንድሙ ……………………………… ቡሬ
52. ታደሰ ዘመኑ ………………………………………አዴት
53. ሀብታሙ ታምራት ……………………………ባህር ዳር
54. ይበልጣል እውነቱ …………………………ባህር ዳር፣ ጭስ አባይ
55. ይህነው ሽመልስ ………………………………ደብረታቦር
56. በለጠ ካሴ ………………………………………ደብረታቦር
57. አዳነ እንየው ……………………………………ጎንደር፣ ቀበሌ 16
58. አለማየሁ ይበልጣል ……………………………ዳንግላ
59. ያየህ በላቸው …………………………………… ዳንግላ
60. በረከት አለማየሁ …………………………………ዳንግላ
61. ተመስገን ……………………………………………ዳንግላ
62. ቅዱስ ሀብታሙ ………………………………… ባህር ዳር
63. ፍስሃ ጥላሁን ………………………………………ባህር ዳር
64. ሰለሞን ጥበቡ …………………………………… ቻግኒ
65. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
66. ዘሪሁን ገደብዬ …………………………………ጎንደር
67. ሲሳይ ባብል ………………………………………ጎንደር
68. ባየሁ ጎንደር ………………………………………ጎንደር
69. በለጡ መሃመድ …………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
70. እንጀራ ባዬ ………………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
71. ወንድም ……………………………………………ጎንደር
72. ግርማቸው ከተማ ………………………… ላይ አርማጭሆ
73. ሊሻን ከበደ ………………………………………አይባ
74. መሌ አይምባ …………………………………… አይባ
75. አዛነው ደሴ ………………………………………አርማጭሆ
76. አራገው መለስ ……………………………………አርማጭሆ
77. ሰጠኝ አድማሱ ……………………………………ደልጊ
78. ታረቀኝ ተሾመ ……………………………………ደልጊ
79. ሄኖክ አታሎ ………………………………………ደልጊ
80. ደሴ ደረሰ …………………………………………ሻውራ
81. ግርማቸው ሞገስ …………………………………ሻውራ
82. ወርቁ ጠቁሳ ………………………………………ሻውራ
83. ማማዬ አንጋው …………………………………ዳንሻ
84. ፈንታ አህመድ ……………………………………ዳንሻ
85. ክንፌ ቸኮል ………………………………………በአከር
86. ሲሳይ ታከለ ……………………………………… አርማጭሆ
87. ማዕረግ ብርሃን …………………………………ደብረታቦር
88. መምህር ተስፋየ ብርሃን ……………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
89. ይበልጣል ደሴ ………………………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
90. አራጋው መለሰ …………………………… አርማጭሆ
91. አዳነ አያሌው ………………………… አርማጭሆ
92. አያናው ደሴ ………………………… አርማጭሆ
93. ትርፌ አጣናው ……………………… አርማጭሆ
94. መምህር ብርሃኑ አየለ …………… ሰሜን ሸዋ፣ ማጀቴ
95. አብራራው አለማየሁ ………………ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
96. ተመስገን ሲሳይ …………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
97. ጋሻው ሲራጅ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
98. ፈንታ ሞገስ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
99. ታደለ ያየህ ……………………………ምዕራብ ጎጃም፣ ቡሬ

(*ማስታወሻ፡- መንግስት ህዝባዊ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው አካባቢዎች የኢንተርኔትና የስልክ ግንኙነቶችን በሙሉና በከፊል መዝጋቱ በእነዚህ አካባቢዎች ስለተከሰቱ ጉዳዮች መረጃ የማግኘት ስራውን አዳጋች በማድረጉ ይህ ዝርዝር ሁሉንም የመብት ጥሰት የደረሰባቸው ዜጎችን ያሳያል ተብሎ አይጠበቅም፡፡)

*ሌላው ከአማራ ህዝባዊ ተቃውሞ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው
1. ንግስት ይርጋ………የመብት ተሟጋች፣ አድራሻ ሳንጃ ሰሜን ጎንደር…. ቃሊቲ እስር ቤት ታስራ ትገኛለች
2. አለምነው ዋሴ የመኢአድ አባል አድራሻ ጎንደር ቂሊንጦ በእስር ላይ ያለ
3. ቴዎድሮስ ተላይ……….አድራሻ ጎንደር
4. አወቀ አባተ……………….የመኢአድ አባል
5. በላይነህ አለምነህ…የሰማያዊ ፓርቲ አባል፣ አድራሻ ባህር ዳር
6. ያሬድ ግርማ…………………. የመኢአድ አባል
7. አታላይ ዛፌ…የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ኮሚቴ አባል

*ክስ ሳይመሰረትባቸው በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት
7. ማሩ ዳኛው
8. ቢሆን
9. መልካሙ ታደለ
10. ሲሳይ ታፈረ
11. ወርቁ ጥላሁን
12. ድንቁ
13. ስማቸው ማዘንጊያ
14. እያዩ መጣ
15. ድርሳን ብርሃኔ
16. አንዳርጌ አባይ
17. ዮናስ ሰለሞን
18. መሃመድ ኑርየ
19. መምህር መሃመድ አሊ
20. መንግስቴ ብርሃኔ
21. ጌታነህ ደምሴ
22. ታደለ እንዳልፈራ
23. መምህር ለወየሁ ጌቱ
24. እሸቴ ደረሰ
25. ጌጤ ላሽተው
26. ሰይዒድ እንድሪስ
27. አህመድ በዛብህ
28. ጀማል ኡመር
29. አብደላ መሃመድ
30. አዲሱ ጌታነህ
31. ዘሪሁን እሸቱ
32. ጀማል ይመር
33. አበበ ጥላሁን
34. ተሻገር ወልደሚካኤል
35. እያሱ ሁሴን
36. በላቸው አወቀ
37. ዘውዱ ነጋ
38. ወልደመስቀል ማማየ
*የህዝቡን የመብት ጥያቄ (ህዝባዊ ተቃውሞ) ደግፋችኋል በሚል ከታሰሩት መካከል፡-
39. ገድፍ ጌታነህ……ሰሜን ጎንደር በለሳ ወረዳ
40. ሊቀሊቃውንት እዝራ (ቤተ-ክርስቲያንን ሽፋን አድርገው የህዝቡን ተቃውሞ ይደግፋሉ በሚል የታሰሩ)
41. ቀለመወርቅ ዓለሙ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የጎንደር ሀገረ ስብከት ጳጳስ ኃላፊ)
42. ሂሪያኮስ አበበ…..ጎንደር ከተማ
43. ዶክተር ጋሹ ክንዱ
(ዶክተር ጋሹ ክንዱ የቡሬ ዳሞት ሆስፒታል ሜዲካል ዳሬክተር ናቸው፡፡ ታህሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም ለገና በዓል ወደ ቤተሰቦቻቸው ባመሩበት ጊዜ ባህር ዳር ከተማ ለእስር ተዳርገው ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲዛወሩ ተደርገው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡

ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (ኢሰመፕ) የተዘጋጀ

በአማራ ክልል በአገዛዙ ወታደሮችና በነፃነት አርበኞች መካከል ውጊያ እየተካሄደ ሲሆን፤ ከሁለቱም ወገን ጉዳት መድረሱ ተገለፀ

(አዲስ ሚዲያ)በአማራ ክልል በተለይም በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የገዥው ስርዓት በደል እና ጭቆናን የተቃወሙ የአማራ ተጋድሎ አርበኞች እና የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ድርጅት የነፃነት ኃይሎች ከመንግሥት ወታደሮች ውጊያ ማካሄዳቸው ተገለጠ፡፡ በተለይ ካለፈው ሐሙስ ህዳር 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በዋናነት በሰሜን ጎንደር ምዕራብ እና ላይ አራማጭሆ፣ ሳንጃ፣ ደንብያ፣ ጃን አሞራ፣ ዳባት፣ ደባርቅ እና ወገራ ወረዳዎች፤ እንዲሁም በወልቃይት አካባቢ ቃፍታ ሑመራ እና ጠገዴ ተከታታይ ውጊያ መደረጉን እና አሁንም በተጠቀሱ አካባቢዎች ውጊያዎቹ የቀጠሉ መሆናቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

kefagn-amhara-resistance

የአማራ ተጋድሎ መብት አራማጆችም በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የተጋድሎው አርበኞች ከአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ጋር ውጊያ መግጠማቸውን እና ከ70 ያላነሱ የአገዛዙ መንግሥት ወታደሮች ሲገደሉ ከአማራ ተጋድሎ በኩል 2 ያህል አርበኞች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ አገዛዙን ስርዓት ለመጣል በይፋ ሁለገብ ትግል እያደረገ የሚገኘውና በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው የአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህና ለነፃነት ንቅናቄ በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ወረዳዎች አውደ ውጊያዎች በአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ላይም ተደጋጋሚ ጥቃት በመክፈት ድል መቀዳጀቱን በመግለፅ ከንቅናቄው ወገን በወቅቱ አዛዥ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን (ገብርዬ) ጨምሮ የተወሰኑ ታጋዮቹ እንደተሰዉ ይፋ አድርጓል፡፡ በነበረው ውጊያም ንቅናቄው በርካታ የአገዛዙ ወታደሮችን መግደሉን፣ ማቁሰሉን እና መማረኩንም ይፋ አድርጓል፡፡

ገዥው መንግሥት በበኩሉ በሰሜን ጎንደር ዞን እና በምዕራብ ትግራይ ዞን የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ኃይሎች ጋ ውጊያ መኖሩን እና በወቅቱ የንቅናቄው መሪ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን ገድሎ 70 ያህል የንቅናቄው ወታደሮችን መማረኩን በስሩ በሚቆጣጠረው የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ ከአገዛዙ በኩል ስለደረሰ ጉዳት የጠቀሰው ነገር የለም፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች በበኩላቸው አገዛዙ ተጨማሪ በርካታ ወታደሮችን ከነ ሙሉ ትጥቃቸው ወደ ስፍራው ማንቀሳቀሱን እንደተመለከቱ ይናገራሉ፡፡ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በርካታ የአገዛዙ ወታደራዊ ተሸከርካሪዎች ጎንደር ከተማን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የዞን እና የወረዳ ከተሞች እንደሚታዩ ተጠቁሟል፡፡

tplf-soldiers-logistic

አገዛዙ ተግባራዊ ያደረገውን የ6 ወር አስቸኳይ አዋጅ ተከትሎ ከአማራ ክልል ብቻ ከ 19 ሺህ ያላነሱ ሰላማዊ ዜጎችን በተለያዩ የክልሉና የፌደራል እስር ቤቶች በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ መታሰራቸውን የአማራ ተጋድሎ የመብት አራማጆች እና የአካባቢው የፖሊስ መረጃ ምንጮች የጠቆሙ ሲሆን፤ የተጠቀሰው አሀዝ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት በነበሩ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ወቅት የታሰሩትን ቁጥር ሳይጨምር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአገዛዙ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የአንድ ወር የወሰደውን ርምጃን ይፋ ባደረገበት ወቅት በአጠቃላይ 11,706 ያህል ዜጎች መታሰራቸውን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

እንደ መረጃ ምንጮች ጥቆማ ከሆነ፤ በአማራ ክልል ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት ጠገዴ ሁመራ የአማራ ማንነት የመብት ጥያቄ መነሻ አድርጎ በነበረው ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ ተከትሎ በአገዛዙ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው፣ መታሰራቸውና ለከፋ ስቃይ መዳረጋቸው ያስቆጣቸው የአማራ ማኀበረሰብ አባላት መካከል በርካታ ሰዎች ራሳቸውን ” ከፋኝ” በሚል በየአካባቢው የጎበዝ አለቃ በሚመራ የአማራ ተጋድሎ ራሳቸውን አደራጅተው በአገዛዙ ላይ የአፀፋ እርምጃ መውሰድ እንደጀመሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በጎንደር በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ሰዎች ሲገደሉ፤ በአካባቢው ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው

በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በሚገኘው ጎንደር ከተማ፤ በያዝነው ሳምንት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸው ተጠቆመ፡፡ መረጃዎች እንደሚመለክቱት ከሆኑ፤ 10 ያህል ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ በወሰደው የአፀፋ እርምጃ 9 የፌደራል ፖሊስ እና 1 የመከላከያ ሰራዊት አባል ተገድለዋል፡፡

በስፍረው የሚገኙ የዓይን እማኞች በበኩላቸው የተገደሉ ሶወች ቁጥር ከተጠቀሰው እንደሚልቅ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በግጭቱ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር በተመለከተ እስካሁን ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡

Gonder Protest

ባለፈው ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት በጎንደር ለሁለት ተከታተይ ቀናት የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደሌሎች አጎራባች ከተሞች መዛመቱ ተሰምቷል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውም ሐሙስ ወደ ዳባርቅ ከተማ የተዛመተ ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ወደ ሳንጃ ወረዳ እና ወደ ሌሎች አጎራባች ከተሞችና ወረዳዎች መዛመቱ እየተነገረ ነው፡፡

car buring in Gondar

በተፈጠረው ግጭትም የሰው ህይወትን ጨምሮ የህወሃት እና የደጋፊው ናቸው የተባሉ ንብረቶች መውደምንም አስከትሏል፡፡
የግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ማንነትና ተያያዥ መብታቶቻችን ይከበሩልን የሚል ጥያቄን ለትግራይ ክልላዊ መስተዳደርና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲያቀርቡ የነበሩ ተወካይ ኮሚቴዎችን ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ የትግራይ ክልልና የፌደራሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የደህንነት አባላት ለማፈን እና ለማሰር በወሰዱት የኃይል እርምጃ በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑ ይታወቃል፡፡

በተለይ ከወልቃይት የአማራ ማንነት ተወካይ ኮሚቴዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፤ ሊያግቷቸው የመጡ የፀጥታ ኃይሎችን “ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፤ ካልሆነ በሌሊት እኔ እጄን ለማንም አልሰጥም” ማለታቸውን ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት፤ ህዝቡ የመንግሥት ኃይሎችን የሌሊት እገታና ሌሎች 4 የኮሚቴ አባላትን እስርና እገታ በመቃወም ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት እንደተፈጠረ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡

በጎንደር በተፈጠረው አለመረጋጋት የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ የአሜሪካና የእንግሊዝ መንግሥታት ዜጎቻቸው ወደጎንደርና አቅራቢያው ከመሄድ እንዲቆጠቡ አስጠንቅቀዋል፡፡ እስራኤል በበኩሏ በጎንደር የሚገኙ 6 ሺህ ቤተ እስራኤላውያንን እና በስፍራው የሚገኙ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ተወካዮችን ደህንነት በተመለከተ ከፍተኛ ቁጥጥር ወደሚደረግበት ስፍራ ጥበቃ እያደረገችላቸው መሆኑን የኢየሩሳሌም ፖስት ዘገባ አመልክቷል፡፡

በጎንደር ግጭቱ ለጊዜው የተረጋጋ ቢመስልም፤ አሁንም በአካባቢው በመንግሥትና በህዝቡ መካከል ከፍተኛ ውጥረት መኖሩ እየተገለፀ ነው፡፡

የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ…

ከዚህ ቀደም በቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት የነበሩና ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የትግራይ ክልል ስር ያሉት የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ “እኛ አማራ ነን፣ ያለፈቃዳችን ተገደን ነው ወደ ትግራይ የተካለልነው፣ የአማራ ማንነት ጥያቄያችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አማራ እንጠቃለል” የሚል ጥያቄን ቢያነሱም፤ ከመንግሥት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ አባላት ተገደው ያለፈቃዳቸው ወደ ትግራይ እንድንጠቃለል ተደርገናል ከሚለው ጥያቄ በተጨማሪ አማራ በመሆናችን ብቻ በትግራይ ክልል አስተዳደር ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብና፤እየተፈፀመብንም ይገኛል በማለት የቀደመው የአማራ ማንነታችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አስተዳደር አማራ ክልል ለመጠቃለል አንዱ ምክንያታቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ይስተዋላል፡፡

Wolkite Tegedie

እንደ ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴዎች አገላለፅ፤የነበረው የወልቃይት ጠገዴ አስተዳደር ወሰን ክልልም በሰሜን ተከዜ ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ ኤርትራ፣ በምስራቅ የቀድሞው ትግራይ ጠቅላይ ግዛት ፣ በምዕራብ ሱዳን በደቡብ የቀድሞው ቤጌምድር (የአሁኑ ጎንደር) አስተዳደር አካል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አካባቢውም በአሁን ወቅት በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በሚል አስተዳደር ስር በ3 ወረዳዎች የተዋቀሩት ቃፍታ ሁመራ፣ ወልቃይት እና ጠገዴ ወረዳዎች በቀድሞ ቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት ወልቃይት ጠገዴ አውራጃ አስተዳደር እንደነበርም ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ቀደምት የአስተዳደር ሰነዶችን እና የአማራ ማንነትን ያረጋግጣሉ የሚሏቸው መረጃዎችን አያይዘው በሕገ-መንግሥቱ መሰረት ጥያቄ ቢያቀርቡም ከሚመለከተው አካል እስካሁንም ምላሽ አለማግኘታቸውን ገልፀዋል፡፡

በተለይ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ ተወካዮች የአማራ ማንነት ጥያቄ ይዘው ላለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ ጥያቄ ያቀርቡ እንደነበር እንደሚያውቁ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲአዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አስታውሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ይህን ያስታወሱት ባለፈው ከኦሮሚያ እና በሌሎች ሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ በተያያዘ መድረክ በዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ላይ ነበር፡፡
የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላቱም በተለያየ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ከሆነ፤ አማራ ሆነው ሳለ ሳይወዱ በግድ ወደ ትግራይ መጠቃለላቸውን፣ ልጆቻቸውም ከአፍ መፍቻ አማርኛ ውጭ ተገደው በትግርኛ እንዲማሩ መደረጉን፣ የአካባቢው ህዝብ ከአማርኛ በተጨማሪ አረብኛ እና ትግርኛም ባላቸው የድንበር ግንኙነት አማካኝነት መናገር ቢችሉም፤ ባህላቸውን እና ማንነታቸውን የሚገልፁበት ቋንቋ አማርኛ መሆኑን እና የማንነት ስነ ልቦናቸውም አማራ እንደሆነ፤ ይህንንም ላለፉት 25 ዓመታት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማት ጥያቄ ሲያነሱ ግድያ፣ እስራት፣ ድብደባ፣ ማስፈራራትና ስደት እንደደረሰባቸው፣ ከጥያቄው ጋር በተያያዘ የትግራይ ክልል መስተዳደር ግድያን ጨምሮ የተለያዩ በደሎችንም ይፈፅም እንደነበርና አሁንም እየፈፀመ እንደሆነ ሲያነሱ ይደመጣል፡፡

የአማራ ማንነት ፈቃዳችን ሳይጠየቅ ተገደን እንድንጠቃለል ተደርገናል ለሚሉት የትግራይ ክልል መስተደዳደርና በፌደራሉ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄን የሚያቀርቡ ተወካዮች በአዲስ አበባም ለተወሰኑ ቀናት በፖሊስና ደህንነት አባላት ታግተው መለቀቃቸው የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን ጨምሮ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን የተዘገበ ሲሆን፤ በተለይ የትግራይ ክልል አስተዳደርና እና የክልሉ ምዕራባዊ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎች አሁንም ከፍተኛ ማስፈራሪያ እና ዛቻ እየፈፀሙ መሆኑን የኮሚቴው አባላት ገልፀዋል፡፡ አዲሱን የአስተዳደር ክልል መዋቅር የመሰረተው ኢህአዴግ መንግሥት እና የትግራይ ክልል መስተዳደር ቀድሞ የነበረውን የአማራ ስነ ህዝብ ስብጥር፣ ባህል እና ማንነትን ለማጥፋትና መቀየር ላለፉት 25 ዓመታት ሙሉ ሲሰሩ ተቃውሞ ብናቀርብም ሰሚም አላገኘንም፣ እንደወንጀለኛም ተቆጥረናል ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ከዛ በተጨማሪ የእኛ የአማራ ማንነት እንደሌለ ተቆጥሮና ተክዶ ልጆቻችን በአማር እንዳይማሩና እንዳይናገሩ፣ በአማራ ማንነታቸው እንዲያፍሩና የነበረውን የአማራ ማንነት ባህል እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ በግድም የትግርኛ ቋንቋ እንዲነገሩ፣ የትግራይ ማንነት ባህልን ብቻም እንዲያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ይህም ህገ-መንግሥቱን እንደሚፃረር ብናነገርም የከፉ በደሎች ተፈፅመውብናል ይላሉ፡፡

በተለይ አካባቢውን በተመለከተ በአጼ ኃይለስላሴ ዘመን የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩትና የአጼ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል መንገሻ ስዩም ወልቃይት ጠገዴ በሳቸው ዘመንም ሆነ ከዛ በፊት ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ አስተዳደር ስር እንዳልነበር እንደሚያውቁ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ገልፀው ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሃላፊ በኩላቸው ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ እንደሆነ እና ከዛ ጋ ተያይዞ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ የህዝቡ እንዳልሆነ ከመግለፃቸው በተጨማሪ የአማራ ማንነት ጥያቄ የሚያነሱ ተወካዮች የሚቃወም ሰልፍም በአካባቢው ተደርጎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአማራ ማንነት ጥያቄን ለሚያነሱ ማኀበረሰብ አባላትና ተወካዮች ጥያቄያቸው መፍትሄ አሊያም ህዝባዊ ውሳኔ ያገኝ ዘንድ ባሉበት ወልቃይት ጠገዴ ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፍ ቢጠይቁም በትግራይ ክልልም ሆነ በክልሉ ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሊፈቀድ ባለመቻሉ የማኀበረሰቡ ተወካዮች ህዝባዊ ስብሰባዎቻቸውን በአጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች ለማድረግ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡

በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለ ኦሮሚያው ተቃውሞ እና ስለ ጎንደር የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ቢገልፁም፤ ስለ ወልቃይ ጠገዴ አማራ ማንነት ጥቄን ግን ሳያነሱት ከማለፋቸው በተጨማሪ በጥቅሉ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንነት ጋር በተያያዘ ያልተመለሰ ጥያቄ የለም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ አዲስ ሚዲያ ባለው መረጃ መሰረት የብሔረሰብ ማንነት እና የራስ አስተዳደር ጋ በተያያዘ በትግራይ ወልቃይት ጠገዴን እና በኣማራ ክልል ምላሽ አግኝቷል ከተባለው የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጥያቄ በተጨማሪ በኦሮሚያ፣ በደቡብ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ከክልሎቹ እስከ አዲስ አበባው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ እስካሁንም ምላሽ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡