በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል፤ በኦሮሚያ ኢኮኖሚ ተኮር ተቃውሞ እንደሚጀመር ይፋ ተደረገ
ብስራት ወልደሚካኤል
(አዲስ ሚዲያ)የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ አድርጎ በጎንደር ፋሲል ከተማ የተጀመረው ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የተለያዩ የሰሜን እና ደቡብ ጎንደር ወረዳና ከተሞችን ጨምሮ ወደ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም እንዲሁም ወደ ሰሜን ወሎ መቄት እና ሸዋ ሮቢት መስፋፋቱን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡
በተለይ ነሐሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ጎጃም ፍኖተ ሰላም ከተማ፣ ነሐሴ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ቡሬ ወምበራ ወረዳ ቡሬ ከተማ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር በተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ተቃውሞዎች እና የመንግሥት የኃይል ርምጃዎችም የቀጠሉ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡
በጎንደር፣ ባህርዳር እና ደብረማርቆስ ከተሞች ከቤት ያለመውጣት ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች የተደረጉ ሲሆን ከነሐሴ 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ በተመሳሳይ ምልኩ በደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር ከተማ ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ እንደሚደረግ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በአማራ ክልል ባሉ ሰሞንኛ ተቃውሞች በተለይ በማክሰኝት፡በገደብዬ፡በእንፍራንዝ፣ በአብደራፊ፣ በአርማጭሆ፣ በፍኖተ ሰላም፡ቡሬ፡ ጅጋ እና ማንኩሳ በተባሉ ወረዳዎች ህዝባዊ ተቃውሞዎች የበረቱባቸው መሆኑን ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡ በነኚህ ስፍራዎች የነበሩ ተቃውሞች መካከልም የተወሰኑ በማኀበራዊ ሚዲያዎች ሲሰራጩ መዋላቸውን ለመታዘብ ተችሏል፡፡
በነበሩ የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞች ሁለት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት መገደላቸው የተጠቆሙ ሲሆን፤ በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች በነበሩ ተቃውሞች ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በኦሮሚያ ክልልም ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞች የቀጠሉ ሲሆን፤ በዚህም በምዕራብ ሐረርጌ መሰላ ወረዳ በሚገኙ ዋልተሲስ እና ጎሮ በተባሉ መንደሮች በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ አራት ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ መገደላቸው ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሀገሪቱ ያለውን የመንግሥትን ግድያ፣ እስርና እና አፋና በመቃወማቸው በአዲስ አበባ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች በተለይም እነ አቶ በቀለ ገርባ በሀገሪቱ ከነሐሴ 19-21 ቀን 2008 ዓ.ም. ብሔራዊ የሀዘን ቀን በሚል ታስቦ እንዲውል ያደረጉት ጥሪ ከወዲሁ በተለያዩ ደጋፊዎቻቸው ተግባራዊ መደረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡
የመንግሥት የኃይል ርምጅና ግፍ በመቃወም በሚደረግ ብሔራዊ የሀዘን ቀንም ፀጉር መላጨት፣ ጥቁር ልብስ መልበስ፣ ጥቁር ባንድራ(ጨርቅ) ማውለብለብ፣ ሻማ ማብራት፣ በተቃውሞ ትግሉ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቤተሰቦችን መጎብኘት እና ተሰብስቦ ህዝባዊ ውይይት በማካሄድ እንዲተገበር ጥሪ ማስተላለፋቸውን ተከትሎ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ባሉ ዜጎች ከወዲሁ ተግባራዊ መደሩ የሚያመለክቱ የተለያዩ ምስሎች በማኀበራዊ ሚዲያዎች ላይ መሰራጨታቸውን ማየት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ ካለው የፖለቲካና ማኀበራዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ከጳጉሜ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞችም እንደሚተገበሩ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች እና የመብት አራማጆች ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞው ምን ላይ እንደሚያተኩር በዝርዝር የተቀመጠ ነገር ባይኖርም፤ ወደፊት ይፋ እንደሚደረግ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡
በታቀደው መሰረት በኦሮሚያ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ መንግሥት በክፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪ እጥረትና አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ይጠበቃል፡፡ በተለይም መንግሥት ከክልሉ በከፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪና የሀገሪቱ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የሆኑት እንደ ቡና፣ የጫት፣ የአበባ፣ የቁም እንሰሳትና፣ የቆዳና ሌጦ እንዲሁም የምግብ ነክ የሆኑ የብግርና ምርቶች እንዲሁም ወርቅና የመሳሰሉ የማዕድን ሃብቶች ከክልሉ እንዳይወጡና ወደ ማዕከላዊም ሆነ የክልሉ ገበያ ንግድ ላይ የማይውሉ ከሆነ ምን አልባትም በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ፈተና በመንግሥት ላይ ሊደርስ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡
የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ በቀጣይ ወደሌሎች ክልሎች በተለይም አማራ እና ደቡብ ክልል የሚዛመት ከሆነ ደግሞ የመንግሥት 90% የገቢ ምንጭ በማድረቅ ስርዓቱን ሙሉ ለሙሉ አደጋ ላይ እንደሚጥለው ይገመታል፡፡ በተለይ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ብቻ የሀገሪቱን 54% የሆነውን ህዝብ ቁጥር እንደሚሸፍኑ እና ከ65% የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪና የገቢ ምንጭም መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ከባለፈው ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ የተቀጣጠለው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መላው ኦሮሚያ ክልልን በማዳረስ፤ ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አማራ ክልል ተዛምቷል፡፡ በሁለቱም ክልሎች ዘገባው እስከተጠናቀረበት ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞዎቹ በተለያዩ ወረዳዎችና ከተሞች ቀጥሏል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በሁለቱም ክልሎች ባሉ የተለያዩ ቦታዎች መደበኛ የመንግሥት ስራን ጨምሮ የተለያዩ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋቶች እየታዩ ነው፡፡
አስረኛ ወሩን ባስቀጠረው ህዝባዊ ተቃውሞ በሁለቱም ክልሎች ከ650 በላይ ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ ሲገደሉ፣ ከ 1,250 ያላነሱ ዜጎች ቆስለው በግምት ከ35,000 በላይ ሰዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉ እና የቆሰሉ ሰዎች በተለያየ ጊዜ ስማቸውና ምስላቸው በሰፊው በማኀበራዊ ሚዲያ እየተገለፀ ይገኛል፡፡ በሁለቱም የኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የወጣው ህዝብ አንዱ ለሌላው በተለያዩ ጊዜና ቦታ ያሳዩት የርስ በርስ አጋርነት፤ መንግሥትን ከፍተኛ ድንጋጤ ላይ እንደጣለው ባለስልጣናቱ በስራቸው ባሉ መገናኛ ብዙኃን ሲናገሩ የተደመጡ ሲሆን፤ በዚህም ስጋት እንዳደረባቸው ባለስልጣናቱና ደጋፊዎቻቸው በይፋ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎችና ከሚሰነዝሯቸው አስተያየቶች መረዳት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ፤የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ”የጋራ ልማት የተቀናጀ ማስተር ፕላን” በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ገበሬዎች የሚያፈናቅልና ለጎዳና ህይወት የሚዳርግ ነው በሚል ቀደም ሲል የነበረውን ተቃው ከዓመት በኋላ በማገርሸት በምዕራብ ሸዋ ጊንጪ ከተማ መጀመሩ ይታወቃል፡፡ በአማራ ክልል ደግሞ የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ ህዝባዊ ወኪሌ ኮሚቴ አባላት ላይ መንግሥት በሌሊት በመኖሪያቸው አካባቢ የፀጥታ ኃይሎችን በመላክ የኃይል ርምጃ መውሰዱን ተከትሎ በጎንደር ከተማ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ ስለደረሱ አጠቃላይ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶች በተመለከተ በመንግሥት ጉዳዩን ለመሸፋፈን ከመሞከር በዘለለ ትክክለኛውን ቁጥርና የጉዳት መጠለን ለመናገር አልደፈረም፡፡ ቀደም ሲል ሀገር በቀል በሆነው የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ) እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች በሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች (HRW) አማካኝነት በተወሰኑ ወረዳዎችና አካባቢዎች የተደረጉ ምርመራዎች ይፋ ከመደረጋቸው በስተቀር አጠቃላይ በደረሱ የሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጉዳቶች የተደረገ ምርመራም ሆነ ሪፖርት የለም፡፡ ይህን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ምት ኮሚሽን ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ እንዲደረግ በይፋ ጥያቄ ቢያቀርብም በስልጣን ላይ ያለው መንግሥት በበኩሉ የመንግሥታቱን ድርጅት ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ምላሽ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እንቅስቃሴን የተመለከተ መረጃ ለኤርትራ መንግስት ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በእስራት ተቀጡ
በታሪክ አዱኛ
በኢትዮጵያ ድንበር ስለሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና ኤርትራውያን ስደተኞች እንቅስቃሴ ለኤርትራ መንግስት መረጃ ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በፅኑ እስራት ተቀጡ።
ተከሳሾቹ 1ኛ ካሃሳ መስፍን፣ 2ኛ አብደላ ኢብራሂም፣ 3ኛ ልኡል መሃሪ፣ 4ኛ ፍስሃይ ተክለገብረስላሴ፣ 5ኛ ጎይቶም ይደጎ ተስፋይ፣ 6ኛ ጎበዘይ ገብረስላሴ፣ 7ኛ ገብረሚካኤል ገብረማርያም፣ 8ኛ ብርሃኔ ምረጽ ይልማ እና 9ኛ ትኩህ ንጉሴ ገብረ መድን ይባላሉ።
ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያሉ ተከሳሾች የኤርትራ ዜግነት ያላቸው ሲሆኑ ከ6ኛ እስከ 9ኛ ያሉ ተከሳሾች ደግሞ ኢትዮጵያውያን ናቸው።
ተከሳሾቹ ከጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም እስከ 2006 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ከኤርትራ መንግስት የመረጃ ሰራተኞች ጋር ሚስጥራዊ ግንኙነት በመፍጠር በኢትዮጵያ ድንበር የሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና የኤርትራ ስደተኞች እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ስለ ኢትዮጵያ ሚስጥራዊ መረጃዎችን ለኤርትራ መንግስት አቀብለዋል ይላል የአቃቤ ህግ ክስ።
በተጨማሪም 2ኛ ተከሳሽ በግንቦት ወር 2006 ዓ.ም አራት ኤፍዋን ቦምቦችን በአካባቢው ለሚገኙ ግለሰቦች ለመሸጥ ሲዘጋጅ በቁጥጥር ስር ውሏል።
በተመሳሳይ 8ኛ ተከሳሽም የመሳሪያ ጥይቶችን እና አምስት ቦምቦችን ሸሽጎ መያዙንም ክሱ ያስረዳል።
በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ የሃገሪቱን ሚስጥራዊ መረጃ በማቀበል እና ስለላ ወንጀል ክስ መስረቶባቸዋል።
ተከሳሾቹ ድርጊቱን ክደው የተከራከሩ ቢሆንም አቃቤ ህግ የብሄራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎት ኤጀንሲ የሰነድ ማስረጃና የሰው ምስክር አቅርቦ አሰምቷል።
የግራ ቀኙን ክርክር የተከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎትም ተከሳሾቹን ጥፋተኛ ብሏቸዋል።
ችሎቱ ከ7ኛ እና ከ8ኛ ተከሳሾች ውጪ ያሉትን ተከሳሾች በ3 አመት ከ4 ወር እስራት እንዲቀጡ ወስኗል።
7ኛ ተከሳሽ የደም ግፊት ህመምተኛ መሆኑን በማስረጃ በማቅረቡ አንድ ማቅለያ ተይዞለት በሶስት አመት ጽኑ እስራት ሲቀጣ፥ 8ኛ ተከሳሸ ደግሞ በአራት አመት ከስድስት ወር እስራትና በ500 ብር እንዲቀጣ ተወስኖበታል።
በተከሳሾቹ እጅ ላይ የተያዙ ቦምቦች ለመንግስት ገቢ እንዲሆኑ ፍርድ ቤቱ አዟል።
በአጠቃላይ ሁሉም ተከሳሾች ለአምስት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብታችው እንዲታገዱ ችሎቱ ወስኗል።
ምንጭ፡- ፋናቢሲ (የሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘገባ), http://www.fanabc.com/index.php/news/item/17450
በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በተለያየ የአፍሪካ ሀገራት እየታሰሩ መሆኑ ቢታወቅም፤ በርካታ ወጣቶች አሁንም በመሰደድ ላይ መሆናቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አስታወቀ
በተለያዩ የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት ቁጥራችዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን በእስር ላይ መሆናቸውንና በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ እንደሚገኙ የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ሐሙስ አስታወቀ ። ባለፉት ስድስት ወራቶች ብቻ በተለያዩ 10 የአፍሪካ ሀገራት ለዚሁ ችግር ተጋለጠዉ የነበሩ 1ሺ 657 ኢትዮጵያዉያንን ወደ ሀገር ቤት መመለስ እንደቻለም ድርጅቱ ገልጿል።
የዓለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹን ወደ ሀገር ለማመላለስ ጥረትን ቢያደርግም አሁንም ድረስ በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ መሆናቸው ስጋትን እየፈጠረ መምጣቱን አክሎ አመልክቷል።
በተያዘዉ ሳምንት በዛሚቢያ በህገ-ወጥ መንገድ ገብታችኋል ተብለዉ የተላለፋባቸዉን የእስር ቅጣት የጨረሱና ወደ ሀገር መመለስ ያልቻሉ 14 ታዳጊ ህፃናት ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የስደተኞች ተቋም ገልጿል። በማላዊ ፣ ዛሚቢያ ፣ ታንዛኒያ እና ሌሎች ሀገራት ቁጥራቸዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኞች በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን የእስር ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸዉ የሚመልሳቸዉ ባለመኖሩ ለችግር ተጋልጠዋል ። የማላዊ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከ120 የሚበልጡ ኢትዮጵያዉያን በእስር ቤት እየደረሰባቸዉ ያለን ስቃይ በመቃወም ስደተኞቹ ወደ ሀገራቸዉ እንዲመለሱ በመጠየቅ ዘመቻን መክፈታቸዉ ይታወሳል።
የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራትን በመጠቀም ስደተኛ ኢትዮጵያውያኑ ወደ ደቡብ አፍሪካ የመግባት እቅድ እንዳላቸዉ የተለያዩ አካላት ይገልፃሉ። ሰሞኑን የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ታዳጊ ህፃናት በርካታ ኢትዮጵያዉያን በተለያዩ ሀገራት በሚገኙ እስር ቤቶች በስቃይ ላይ መሆናቸዉን እንዳስታውቁ ድርጅቱ በችግሩ ዙሪያ ባወጣዉ ሪፖርት አመልክቷል።
የስደተኛ ድርጅቱ ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገር ለመመለስ እያደረገ ባለዉ ጥረት ባለፉት 6 ወራቶች ብቻ 1 ሺ 657 ስደተኞች ከ10 የፍሪካ ሀገራት ሊጓጓዙ ችለዋል። መንግስት በተለያዩ ሀገራት ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ እስካሁን ድረስ የሰጠው ምላሽ የለም ።
ምንጭ፡- ኢሳት
በጎንደር በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ሰዎች ሲገደሉ፤ በአካባቢው ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው
በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በሚገኘው ጎንደር ከተማ፤ በያዝነው ሳምንት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸው ተጠቆመ፡፡ መረጃዎች እንደሚመለክቱት ከሆኑ፤ 10 ያህል ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ በወሰደው የአፀፋ እርምጃ 9 የፌደራል ፖሊስ እና 1 የመከላከያ ሰራዊት አባል ተገድለዋል፡፡
በስፍረው የሚገኙ የዓይን እማኞች በበኩላቸው የተገደሉ ሶወች ቁጥር ከተጠቀሰው እንደሚልቅ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በግጭቱ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር በተመለከተ እስካሁን ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት በጎንደር ለሁለት ተከታተይ ቀናት የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደሌሎች አጎራባች ከተሞች መዛመቱ ተሰምቷል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውም ሐሙስ ወደ ዳባርቅ ከተማ የተዛመተ ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ወደ ሳንጃ ወረዳ እና ወደ ሌሎች አጎራባች ከተሞችና ወረዳዎች መዛመቱ እየተነገረ ነው፡፡
በተፈጠረው ግጭትም የሰው ህይወትን ጨምሮ የህወሃት እና የደጋፊው ናቸው የተባሉ ንብረቶች መውደምንም አስከትሏል፡፡
የግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ማንነትና ተያያዥ መብታቶቻችን ይከበሩልን የሚል ጥያቄን ለትግራይ ክልላዊ መስተዳደርና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲያቀርቡ የነበሩ ተወካይ ኮሚቴዎችን ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ የትግራይ ክልልና የፌደራሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የደህንነት አባላት ለማፈን እና ለማሰር በወሰዱት የኃይል እርምጃ በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተለይ ከወልቃይት የአማራ ማንነት ተወካይ ኮሚቴዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፤ ሊያግቷቸው የመጡ የፀጥታ ኃይሎችን “ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፤ ካልሆነ በሌሊት እኔ እጄን ለማንም አልሰጥም” ማለታቸውን ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት፤ ህዝቡ የመንግሥት ኃይሎችን የሌሊት እገታና ሌሎች 4 የኮሚቴ አባላትን እስርና እገታ በመቃወም ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት እንደተፈጠረ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
በጎንደር በተፈጠረው አለመረጋጋት የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ የአሜሪካና የእንግሊዝ መንግሥታት ዜጎቻቸው ወደጎንደርና አቅራቢያው ከመሄድ እንዲቆጠቡ አስጠንቅቀዋል፡፡ እስራኤል በበኩሏ በጎንደር የሚገኙ 6 ሺህ ቤተ እስራኤላውያንን እና በስፍራው የሚገኙ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ተወካዮችን ደህንነት በተመለከተ ከፍተኛ ቁጥጥር ወደሚደረግበት ስፍራ ጥበቃ እያደረገችላቸው መሆኑን የኢየሩሳሌም ፖስት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በጎንደር ግጭቱ ለጊዜው የተረጋጋ ቢመስልም፤ አሁንም በአካባቢው በመንግሥትና በህዝቡ መካከል ከፍተኛ ውጥረት መኖሩ እየተገለፀ ነው፡፡
ለውጥን እንደ ሰማይ መና
ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com
አንድ ሰው ለሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ሁሉ ዓላማ እና ግቦች አሉት። እነኚህን ግቦች የሚያስቀምጥበት እና ለማሳካት የሚፈልግበት ደግሞ አንድ ምክንያት ይኖረዋል። እዚያ ምክንያታዊነት ላይ እንዲደርስ ያስቻለው ደግሞ የቆመበት እና የሚከተለው መርሕ ነው። እነኚህ ጉዳዮች ተያያዥነት ቢኖራቸውም አንዱ ከሌላው የሚለይበት የራሳቸው የሆነ ልዩነቶች አሏቸው።
ወደ አገራችን የኢትዮጵያ ፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ስንመጣ ትኩረታቸው ግብ ላይ እንጂ ዓላማ፣ መርሕ እና ምክንያታዊነት ላይ ነው ለማለት አያስደፍርም። አስገራሚው ነገር ፖለቲካውን በቅርበት ለሚከታተል ሰው፣ አብዛኞቹ ግባቸው ሥልጣን የመቆጣጠር እና የበላይነትን መጎናፀፍ ግብ እንጂ ቆመንለታል ላሉት ዓላማ፣ መርሕ እና ምክንያት ሲሆን አይስተዋልም። ይህ ችግር ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲመጣ የሚፈለገው ዴሞክራሲያዊ ለውጥ እስካሁን እንዳይመጣ ከፊል መንስኤ ሆኗል። የዚህ ጽሑፍ ዓላማም ችግሩን በጨረፍታ መዳሰስ ነው።
ትችትን መድፈር
ምንም እንኳ ብቃታቸው፣ሚናቸውና እና ዓላማቸው የተለያየ ቢሆንም፣በአሁን ሰዐት በአገሪቱ 50 ያህል የፖለቲካ ድርጅቶች አሉ። ይህ አሐዝ ከ7 ያላነሱ በትጥቅ ትግል እንቀስቃሴ የሚያደርጉትን ሳያካትት ነው። ምንም እንኳ ጥቅል ድምዳሜ ለመስጠት ሰፊ ጥናት የሚጠይቅ ቢሆንም፣ በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ላይ ብንመረኮዝ ገዥው ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.ን ጨምሮ አብዛኞቹ የፖለቲካ ንቅናቄ እንጂ የፖለቲካ ፓርቲ ተክለቁመና ላይ አልደረሱም ወይም ለመድረስ ዕድሉን አላገኙም። ምክንቱም በኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደ ፖለቲካ ፓርቲ እንዲንቀሳቀሱ የሚያስችል ነባራዊ ሁኔታ የለም። ይህ የተደረገው በሥልጣን ላይ ባለው ገዥው ስርዓት ነው። ነገር ግን ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችም መጠነኛም ቢሆን የራሳቸው ድርሻ አላቸው።
ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ስኬታማ እንዳይሆኑ ቀዳሚውን ድርሻ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. የሚወስድ ቢሆንም፣ ተፎካካሪዎች ስለራሳቸውም ሆነ ስለድርጅቶቻቸው ድክመቶች በግልጽ ሲነጋገሩም ሆነ በአደባባይ ከደጋፊዎቻቸው ጋር ሲወያዩ አይስተዋልም። በርግጥ ያን መድረክ በቀላሉ ማግኘት አይችሉ ይሆናል። ነገር ግን ችግሩን ቦታ ሰጥተውት ሲጠቀሙና ድክመቶቻቸውን ሲያርሙ አይታይም። ከድክመቶቻቸው መካከልም ዓላማና መርህ ላይ ያለመቆም ችግር አንዱ ነው።
በተለይ ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት እውን መሆን የስርዓት ለውጥ መኖር እንዳለበት እያመኑ፣ ነገር ግን ደግሞ በሥልጣን ላይ ላለው አካል መጠንክር የሚሠሩ ጥቂት አይደሉም። በተለይ ከወረቀት ባለፈ ከጊዜው እና ከተቀናቃኛቸው ጋር ሊገዳደር የሚችል ስትራቴጂ ነድፎ ወደመሬት ያለማውረድና ፖሊሲና ፕሮግራማቸውን በተለያየ ዘዴ ወደ ሕዝቡ የማስረፅ ችግር አለ። እነዚህን የተቃዋሚውን ችግሮች ለትችት ማቅረብ የተቃውሞውን ጎራ እንደመጉዳት ስለሚቆጠር ልምዱ የለም።
ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ግን ከተቃዋሚዎች በተሻለ፣ ለይስሙላም ቢሆን አልፎ አልፎ አሁን የመልካም አስዳደር እንደሚለው እነዚህ ችግሮች አሉብኝ የማለት ልማድ አለው። እርግጥ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ችግር እንዳለ በደፈናው ቢያምንም፣ የተጠቀሱ ችግሮች ግን ለኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ቅዱስ የሆኑ የሥልጣን መሠረቱ ናቸው። ምክንያቱም የሚከተለው ርዕዮተዓለም “አብዮታዊ ዴሞክራሲ” እና የምጣኔሀብት “ልማታዊ መንግሥት” ፍልስፍና የተጠቀሱ ችግሮችን ለማረም የሚያስችሉ አይደሉም፤ ይልቁኑ ያባብሱታል እንጂ። ምናልባት በውጫዊ ጫና ምክንያት ስርዓቱ ችገሮቹን ለማረም አንዲት ርምጃ ወደፊት ቢጓዝ፤ ስርዓቱ ታሪክ ብቻ ሆኖ እንደሚቀር መሪዎቹ ጠንቅቀው ያውቁታል። ስለዚህ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.ም ቢሆን ለተሻለ ለውጥ ከልብ አምኖ ራሱን የመተቸት ወይም ትችትን የመቀበል ልማድ አለው ማለት አይቻልም። በመሆኑም በሁለቱም ጎራ ያሉት የፖለቲካ ድርጅቶች የትችትን ፋይዳ የማይቀበሉ በመሆናቸው ዴሞክራሲያዊ መርሕ አላቸው ማለት አይቻልም።
ራስን ከመገምገም አንፃር ሲታይ፤ ስርዓቱ ራሱን የሚያወዳድረው በአቅራቢያ ካሉ እንደነ ታንዛኒያ፣ኬንያ፣ ጋና ወይም ሞርሽየስ ጋር አሊያም ዘመኑን ከሚመኑ የተሸሉ ስርዓቶች ጋር ሳይሆን ሞተው ከተቀበሩ ስርዓቶች ጋር ነው፡፡ ስለሆነም 17 ዓመት የገዛውን ደርግን 25 ዓመታት ሙሉ ከራሳቸው ጋር አወዳድረው አልጠገቡም፣ ኮንነውና አኮስሰው አልጨረሱም። በዚህም ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ራሱን ብቻ አይደለም ከሙታን ጋር እያወዳደረ ያለው፣ ተፎካካሪውን እና ሕዝቡንም ጭምር እንጂ።
የራስን መለያ ምልክት ማኖር
ምንም እንኳ በበጎ ባይሆንም ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. የራሱን መለያ ምልክት (ብራንድ) አኑሯል። እዚህ ላይ የተፎካካሪ ፖለቲካ ድርጅቶችም ሆኑ አመራሮች የራሳቸውን በጎ መለያ ምልክት የማኖር ችግር ይስተዋላል። በተለይ ለስርዓት ለውጥ የሚታገሉ አመራሮችና አባላት በሕዝቡ ዘንድ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.ን ያህል የተወገዘ ተግባር ባይኖራቸውም፤ በጎ ምልክት በማኅበረሰቡ አዕምሮ ስሎ የማኖር ዘዴን እየተጠቀሙ ነው ለማለት ያስቸግራል። በርግጥ በጣም ጥቂቶች በፖለቲካው መስክ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን በጎ ምልክት ያላቸው ቢሆንም፣ ከከተማ የዘለለ ዕውቅና እና ድጋፍ እንዲኖራቸው ከዓላማቸው እና ከመርሓቸው ጋር አብሮ ሊሄድ የሚችል የራሳቸውን ምልክት የማኖር ክፍተት አለ።
የራስን በጎ መለያ ምልክት የግድ በፖለቲካ መስክ ብቻ ላይሆን ይችላል። በተለይ ማኅበራዊ ክንፍ በመመሥረት፣ በማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ያላቸው ተሳትፎ ላይም ትኩረት ቢሰጡ ለፖለቲካው እንቀስቃሴም የበለጠ ይጠቅማቸዋል፤ ሕዝቡን በቅርብ የማግኘት ዕድል ያገኛሉ። ለምሳሌ በአባላት የሚደረግ የደም ልገሳ፣ አገር በቀል የሕፃናት እና አረጋውያን እንክብካቤና መጠለያን ሄዶ መጎብኘት እና ያቅምን ያህል ድጋፍ ማድረግ፣ እንዲሁም የአካባቢና ተፈጥሮ ሀብት እንክብካቤ በግልም ሆነ በድርጅት ሥም ብሎም ሌሎች ሙያዊ የበጎ ፈቃድ ነጻ አገልግሎት መስጠት፣… የመሳሰሉት ላይ ቢሳተፉ ተደራሽነታቸውም ሆነ ተቀባይነታቸው እየጨመረ በጎ ምልክትን እያኖሩ የመሄድ ዕድላቸው ሰፊ ይሆን ነበር። በርግጥ ይህ ሥራ የሲቪክ ተቋማት እና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች አንዱ ሥራ ቢሆንም፣ ፖለቲከኞች እንደ አንድ ዜጋ ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚኖራቸው ተሳትፎ ሕዝቡጋ በቀላሉ ከመድረስ በተጨማሪ፣ ነገ የመንግሥትን ሥልጣን ቢይዙ ምን ማድረግ እንዳለባቸው የሚከተሏቸውን ፖሊሲዎችም ከሕዝብ አገር በቀል ዕውቀትና ልምድ ጋር እንዴት ማስተሳሰር እንዳለባቸው እና በቀጥታ የሕዝቡን ችግር የበለጠ ለመረዳት ትልቅ ግብኣት ሊሆናቸው ይችላል።
ራስን ችሎ መቆም
ብዙውን ጊዜ ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት አለመኖር ወይም አለመጎልበት ትልቁን ድርሻ የሚወስደው ስርዓቱ ቢሆንም፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶችም የራሳቸው ሚና እንዳላቸው ሲገልጹ አይስተዋልም። ስርዓቱ የዴሞክራሲ ተቋማት እንዳይኖሩ አድርጓል በሚል ይወቀሳል። ከዴሞክራሲ ተቋማት በተጨማሪ ዴሞክራሲያዊ ማኅበረሰብ የመገንባት ሒደት ችግር ላይ ገዥውም ሆነ ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች የማይተናነስ ድርሻ እንዳላቸው።
የአገራችን የፖለቲካ ድርጅቶች በተለይ ተቀናቃኝ አካል የሚያቀርባቸውን አማራጭ ሐሳቦችም ሆኑ ትችቶች እነርሱን ጭምር የሚጠቅም እንኳ ቢሆኑ፤ እንዲፈሩና በአሉታዊ ጎን ብቻ እንዲመለከቱ ቀፍድዶ ስለያዛቸው በሐሳብ የበላይነት የሚያምን ነጻ ማኀበረሰብ እንዳይኖር በማድረግ ረገድ ትልቅ አገራዊ ጉዳት አስከትሏል። ለዚህም ነው፤ ከጥቂት አመራሮቻቸው በስተቀር ከሌላው ማኅበረሰብ ያልተለየ አንዳንዶችም የባሰ ጎስቋላ ሕይወት እየመሩ እንኳ ከለውጥ ይልቅ የሚደግፉት ስርዓት ልዩ ጥቅም እንደሰጣቸው አድርገው የሚቆጥሩት። ይህ የመንጋ አስተሳሰብ ውጤት ነው፤ ራሳቸውን ችለው እንዳይቆሙ በማድረግ በፖለቲካው፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴያቸው የበለጠ ጥገኛ እንዲሆኑ ያደረጋቸው።
በገዢው ፓርቲ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርቶች በኩል ብዙውን ጊዜ ለእንቀስቃሴያቸው አስፈላጊ የሆነ የፋይናንስ እና የሰው ኃይል ችግር አለ። ያን ችግር ለመፍታት በአቅራቢያቸው ከማኅበረሰቡ ጋር ቀጥታ ትስስርን በመፍጠር ሌላ አማራጭ ከማየት ይልቅ፣ ፈራ ተባ እያሉ በሚያዋጡ ጥቂት አባሎቻቸው እና ዳያስፖራው ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። በርግጥ የፖለቲካ ድርጅቶች ማቋቋሚያ አዋጅ የፖለቲካ ድርጅቶች የንግድ እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ የሚያስገድድ ቢሆንም፤ ይህ ግን ለገዥው ስርዓት የሚሠራ እንዳልሆነ በየአባል ድርጅቶቹ (በአባላት ባለቤትነት ሥም) የሚያስተዳድራቸው የንግድ ኩባንያዎች ማስረጃዎች ናቸው። ተፎካካሪዎች ያን ዕድል ባያገኙ እንኳ፤ ከኢትዮጵያውያን የተለያየ ዘዴን በመጠቀም ቢያንስ በፖለቲካው መስክ ራሳቸውን ችለው ሲንቀሳቀሱ አይታይም።
የፖለቲካ ድርጅቶች በፋይናንስ ራሳቸውን ችለው አለመቆማቸው ዓላማቸውን በተወሰነ የጊዜ ገደብ ከግብ እንዳያደርሱ አንዱ እንቅፋት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከጊዜውና አገር ውስጥ ካለው ማኅበረሰብ ፍላጎትና አቅም ጋር አብረው እንዳይጓዙ የፈጠረው የፋይናንስ ችግር በሐሳብ ደረጃም የዳያስፖራው ጥገኛ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል። ይህ ማለት ግን የዳያስፖራው ድጋፍ አያስፈልግም፣ አይጠቅምም ማለት አይደለም፤ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን በፋይንናስም በሐሳብም ሙሉ ለሙሉ ጥገኛ መሆን በቀጥታ የሀገር ውስጥ እንቅስቃሴ ራሱን ችሎ እንዳይቆም ያደርጋል፡፡ ስለዚህ የደጋፊውን እና የአባላቱን ድርሻ በግልፅ ለይቶ ግንዛቤ በማስጨበጥ መንቀሳቀስ የራስ መተማመንን ይፈጥራል፡፡
መተባበር፣ መተማመን እና መከባበር
በሐሳብ አለመስማማት ወይም በፖለቲካ ርዕዮተዓለም አብሮ አለመጓዝ አንዱ ሌላውን እንደ አንድ አገር ዜጋ ሳይሆን እንደጠላት ማየት፣ ለፓርቲ ታማኝነት እያስመሰለው ይገኛል። ይህ ልምድ ገዥው ስርዓት ተቀናቃኞቹን የሥልጣን ተፎካካሪ አድርጎ ከመመልከት ይልቅ በጠላትነት የመፈረጅ አንዱ መለያ ፀባዩ ከሆነ ይኸው ሁለት ዐሥርት ዓመታት አልፈዋል። ምንም እንኳ በግፍ ባያስሩና ባያስፈርዱም ይህን ባሕል ተፎካካሪዎቹም ይጋሩታል።
በተፎካካሪዎች ዕርስበርስ ያለው መተባበር፣ መከባበርና መተማመንም አለመኖር ችግርን በጋራ አለመጋፈጥ ብቻ ሳይሆን ያላቸውንም የሰው፣የጊዜ እና የገንዘብ ሀብት በአግባቡ እንዳይጠቀሙ አድርጓቸዋል። ይህ ማለት ግን ከቆሙለት ዓላማና መርህ ውጭ የግድ “የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው” የሚለውን የተሳሳተ መንገድ መከተል ማለትም አይደለም፡፡ መተባበርንና አብሮ መስራት መፍጠር ያለበት የያዙት ዓላማና የቆሙለት መርህ እንጂ የተቀናቃኝ አካል ተቃዋሚ ስለሆነ አይደለም፡፡
የርዕዮተዓለም ልዩነት መኖር የጋራ ተቀናቃኝን ለመቋቋም ተባብሮ መሥራትን እና መከባበርን አይከለክልም። በተለያየ ርዕዮተዓለም በጋራ ሰርቶ ውጠየታማ መሆንን ዴሞክራሲ በዳበረባቸው አገሮች በተለይ እንደ ጀርመን፣ ስዊድን እና እስራኤልን ማንሳት ይቻላል።
ርስበርስ መተባበር አለመኖሩ አለመተማመኑን ፈጥሯል። ያለመተማመኑ ደግሞ አለመከባበርን አስከትሏል። በተለይ ፖለቲካው ከሐሳብ የበላይነት ይልቅ በመንጋ ቲፎዞ ማዕቀፍ ውስጥ መውደቁ ርስበርስ ከመከባበር ይልቅ በመካከላቸው መናናቅና ጥርጣሬን በማስፈን ለጋራ መብትና ጥቅም እንኳ በጋራ ባለመቆም ፖለቲካው እንዳይዘምን ጥላ አጥልቶበታል። ምክንያቱም ፖለቲካው የሚመነዘረውና የሚተረጎመው ከምክያታዊነት እና ከቆሙለት መርህ ይልቅ በስሜት ስለሆነ፤ ዛሬም ድረስ የሐሳቦችን ጠቀሜታና ጉዳት ከማየት ይልቅ ሐሳቡን የሚሰነዝረው “እሱ ማን ነው?” የሚል ኋላ ቀር የግለሰብ ተክለ ስብዕና አምልኮ ላይ የመጠመድ ዝንባሌ ይታያል፡፡ ይህ ችግር በገዥውም ሆነ በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ሊሂቃን እና ደጋፊዎች የተለመደ ተግባር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከሐሳቡ ጥራት ይልቅ የግለሰቡ ማንነት ላይ ብቻ የተንጠለጠለ፣ የጎደላቸውን ከሌሎች አጋሮቻቸው መሙላት እንደሚችሉ ባለመገንዘብ ለራስ የሚሰጥ እጅግ የገዘፈ ትልቅ ግምት፤ ሰጥቶ አለመቀበል፣ አለመተባበር፣ አለመተማመን እና አለመከባበርን አስከትሏል።
ቀድሞ መተንተን እና መተንበይ
የነበሩ ተሞክሮዎችን በማጥናትና በመረዳት የእንቅስቃሴዎች ውጤትን ቀድሞ መተንበይ እንዳለ ሁሉ፣ ሊመጣ የሚችለውንም አሉታዊና አዎንታዊ ችግርንም ከግምት ማስገባት አስቀድሞ ክፍተቶችን ለመቀነስ ይረዳል። ይህ እንቅስቃሴዎችን በዕቅድ መሠረት ማስኬድ ብቻ ሳይሆን መተንተን እና መተንበይ የተሻለ ውጤት ከማስመዝገብ በተጨማሪ ውጤታማ ሊያደርግ የሚችል የተለያየ አቅጣጫን ሊያመላክት ይችላል። ይሄ ብዙ ሲሠራበት አይታይም። ምክንያቱም ቀድሞ መተንተን እና መተንበይ የቻለ የፖለቲካ ድርጅትም ሆነ መሪ የግድ በአምስት ዓመት አንድ ጊዜ በሚደረግ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ብቻ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ አይጠብቅም፡፡
ከፊት ሊመጣ የሚችለውን ውጤትን በተመለከተ፤ እንኳን ዴሞክራሲያዊ ተቋማት በሌለበት አገር ቀርቶ፣ በሠለጠነ እና ዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ በሕግ የበላይ የተረጋገጠበት አገር የወቅቱ አስተዳደር ተፎካካሪ እንደመሆኑ መጠን በቀናነት ዕድሉን ይሰጣል ተብሎ አይታሰብም። ስለዚህ እንቅስቃሴዎችና የነበሩ ልምዶች ቀጣዩን ጊዜ ለመተንተንም ሆነ ለመተንበይ በቂ ግብኣት መሆናቸው አምኖ ያለመጠቀም ችግር አለ። በተለይ የተፎካካሪ ፖለቲካ ድርጅቶች ነገሮች ቀድመው ተንብየው ባለመዘጋጀታቸው ውጤቱ ላይ ሲደረስ የመረበሽና ያለመረጋጋት ስሜት ይታያል። ይህ ሥልጣን ላይ ያለው አካል ከሚፈጥረው ችግር በተጨማሪ በራስ ስንፍናም የሚፈጠር ነው።
ከጊዜው ጋር አብሮ መዘመን
የአባላትም ሆነ የመሪዎች ከጊዜው ጋር አብሮ መዘመን፤ የአገሪቱን የፖለቲካ እንቅስቃሴ አብሮ ያዘምነዋል። በተለይ አመራሮቻቸው ኃላፊነት እና ተጠያቂነትን ማንፀባረቅ፣ አባላቱን በመረጃ መረብ ማግናኘትና ወቅታዊ መረጃን በፍጥነት መለዋወጥ ግልጽነት ያለውን አሠራር ለመከተል ያስችላል።
ቢቻል ሁሉም አመራር ከማኅበረሰቡ ጋር በቀላሉ ሊያገናኛቸው የሚችሉ ዝሙን ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ ቢጠቀሙ ተደራሽ ከመሆናቸው በተጨማሪ ራሳቸውም አዳዲስ መረጃና ዕውቀትን የመቅሰም ዕድላቸው የሰፋ ነው። በዚህም ራሳቸውን በመረጃ አበልፅገው ጠንካራና ደካማ ጎናቸውን ከማኅበረሰቡ ቀጥተኛ ግብረመልስ ከማግኘት በተጨማሪ አዳዲስ ደጋፊና ተከታይ የማፍራት አጋጣሚም ይኖራቸዋል። በተለይ ከኮምፒዩተርና ቴሌፎን ቴክኖሎጂዎች ጋር ራስን ማስማማትና ማላመድ ራስን በዕውቀት ለማበልፀግም ይረዳል። እዚህ ላይ በገዥውም ይሁን በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች መሪዎች ከሕዝቡ ይልቅ በይበልጥ ራሳቸውን ብቻ የሚያደምጡ በመሆናቸው ራሳቸውን ለሕዝቡ ግልጽ አድርገው ሲቀርቡ አይታይም።
በቴክኖሎጂ አጠቃቀም በኩል አብዛኛው የገዠውም ሆነ የተፎካካሪ ድርጅት መሪዎች ተመሳሳይ ባሕርይ ነው ያላቸው። ሁለቱም ማኅበራዊ ሚዲያውንም ሆነ ዝሙን የመረጃ ቴክኖሎጂዎችን ሥራ ፈት ወጣቶች የሚጠቀሙበት አድርገው ይቆጥሩታል፤ በዚህም ጠቃሚ ነገሮችን እንዲያጡ አድርጓቸዋል።
በተለይ በአሁን ሰዐት የአውሮፓም ሆነ የአሜሪካ መሪዎች በተጨማሪ የጎረቤታችን ኬንያ መሪዎችን ጨምሮ የተለያዩ የአፍሪካና የእስያ ሀገራት መሪዎች ዘመን ያፈራውን ቴክኖሎጂ ራሳቸውን ከማኅበረሰቡ ጋር በቀጥታ በማገናኘት ከሚሰጣቸው ፖለቲካዊ ፋይዳ በተጨማሪ ለአገራቸው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎት የበለጠ ጥቅም ላይ እንዲያውሉ ገፋፍቷቸዋል። በኢትዮጵያ ግን ገዥው ስርዓት ቴክኖሎጂውን ራሱ በአግባቡ ተጠቅሞ ማኅበረሰቡም የበለጠ እንዲጠቀም ከመጋበዝ ይልቅ፤ አፋኝ ሕጎችን ማውጣቱና መተግባሩ ሳያንስ ቴክኖሎጂውን በሌላ ፀረ-ቴክኖሎጂ መሣሪያ ለማፈን እና ለማዘግየት ሥራ ላይ ሲያውል ይስተዋላል። በዚህም አገሪቱም ሆነች ሕዝቡ ዓለም ከደረሰበት ዘመን ጋር አብሮ እንዳይጓዝ እንቅፋት ፈጥሯል።
በዚህ መሠረት በፖለቲካው እንቅስቃሴ ላይ ተሳትፎ ያላቸው አካላት ዓላማቸው ግቡን ይመታ ዘንድ በቆሙለት መርሕ መሠረት ትችቶችን ከግብታዊ ስሜት በፀዳ መልኩ ለመስማት መድፈር፣ ራስን ችሎ መቆም፣ በጎ የሆነ የራስን ምልክት ማኖር፣ በሐሳብ የበላይነት ማመን፣ ርስ በርስ መተባበር፣ መተማመን፣ መከባበር፣ መጪውን ጊዜና ውጤት አስቀድሞ መተንተን እና መተንበይ እንዲሁም ከጊዜው ጋር አብሮ መዘመን የተሻለ ውጤት እንድናይ ያስችለናል የሚል እምነት አለኝ። አለበለዚያ የራሳችንን ጉድፍና በሽታ ደብቀን የሌላ ድክመት ላይ መንጠልጠል የአገሪቱን ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች በሰው ልጅ ጥረት ለሰው የሚመጡ መሆናቸው ቀርቶ፤ ለውጥን እንደሰማይ መና ለመጠበቅ መገደዳችን አይቀሬ ነው፡፡ ምክንያቱም በሀገሪቱ ያሉ ችግሮች መነሻቸው የፖለቲካው አለመዘመን ውጤት ስለሆነ፤ መፍትሄውም ከነበረው ተሞክሮና ልምድ በተለየ መልኩ ሁሉንም ሊያሳትፍና ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችል የፖለቲካ ለውጥ ነው፡፡