Tag Archives: Oromo Protest Ethiopia

በእነጉርሜሳ አያኖ መዝገብ 5ት ቀሪ የአቃቤ የህግ ምስክሮችን ለመስማት ተጨማሪ ቀን ተሰጠ

አቃቤ ህግ ታህሳስ 27 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀሪ ምስክሮች ቀርበው እንደሆነ ሲጠየቅ፤ አምስት ምስክሮች እንደሚቀሩት እና ተገቢውን ጥረት ቢያደርግም ሊቀርቡ እንዳልቻሉ በመግለፅ የበለጠ ጉዳዩን እንዲያስረዱለት ከፓሊስ የቀረቡትን ረዳት ኢንስፔክተር ቴድሮስ አዳነ ጠይቋል።

Bekele Gerba

አቶ በቀለ ገርባ

ረዳት ኢንስፔክተሩ የተሰጣቸው ጊዜ አጭር በመሆኑ በተሰጠው ቀጠሮ ሁሉንም ማቅረብ አለመቻላቸውን፤ ምስክሮቹ አካባቢያቸውን አበመልቀቃቸው በአዲሱ አድራሻቸው እያፈላለጓቸው በመሆኑ፤ ራቅ ያለ ቦታ ያሉ ምስክር በመኖራቸው ከፍተኛ የጊዜ እጥረት ስለገጠማቸው በመሆኑ ጊዜ እንዲጨመርለት ጠይቋል። በመቀጠልም አቃቤ ህግ ከቀሩት 5ት ምስክሮች ውስጥ አንዱ ጉጂ ዞን የሚገኝ፣ አንዱ ፀበል ላይ እንደነበረ እና ማስረጃ እስኪያመጣ ጊዜ ስላጠረ፣ አንደኛው አድራሻ ቀይሮ ሌላ ቦታ በመሄዱ በተሰጠው ጊዜ ቀርበው መመስከር እንዳልቻሉ ተናግሮ የተቀሩት ሁለቱ ግን የአዲስ አበባ ነዋሪ መሆናቸውን መመስከር ስላልፈለጉ አድራሻቸውን እየቀያየሩ እንዳስቸገሯቸው ተናግሯል። እስካሁን ይመሰክራሉ ከተባሉ 42 ምስክሮች ውስጥ 37ቱን እንዳሰማ የተናገረው አቃቤ ህግ የተከሰሱበትን የክስ ክብደት እንዲሁም ከፍተኛ ጉዳት ያስከተለ ተግባር መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ቀሪ ምስክሮችን አቅርበው እንዲያሰሙ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

የተከሳሽ ጠበቆች የተሰሙት ምስክሮች በችሎቱ ግፊት እንጂ አቃቤ ህግ ዳተኛ እንደነበረ፤ ምስክሮቹን ማቅረብ ስላልፈለገ እንጂ በቂ ጊዜ ተሰጥቶት እንደነበረ፤ የፍትህ ሂደት የሚለካው በሂደቱም ጭምር መሆኑን፤ ከባለፈው ቀጠሮ ጀምሮ በሰበብ አስባቡ ምስክሮችን ለማምጣት በሚል ቀጠሮ መሰጠቱን ተቃውመው እንደነበረ እና የዛሬው ቀጠሮም የመጨረሻው በሚል የተያዘ እንደሆነ ገልፀው ተጨማሪ ቀጠሮ መሰጠት እንደሌለበት ተናግረዋል።

“እንደሚታወቀው ከታሰርን ሁለት ወራችን አይደለም። አንድ አመት አልፎናል። እነሱ ቤታቸው እያደሩ እኛን እያሾፉብን ነው። በአንድ ቀን ብዙ ሺዎችን እያሰረ ያለ መንግስት፤ እንዴት ነው 5ት ምስክሮችን ማቅረብ ያልቻሉት? ” በማለት የኦፌኮ ም/ፕሬዝዳንት አቶ በቀለ ተጨማሪ ቀጠሮ መኖር የለበትም ሲሉ ተከራክረዋል። አቶ ደጀኔ ጣፋም ተቃውሟቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል። “አቃቤ ህግ ሲናገር 2ቱ አዲስ አበባ ናቸው ብሏል። ለምን አልቀረቡም እስካሁን? ክሳችን መጀመሪያም የፓለቲካ ክስ ነው አሁንም የፓለቲካ ድምዳሜ ነው የምንሰማው። እንዲሁ እንደከሰሳችሁን እንዲሁ ፍረዱብን። ወይስ ፍትህ አለ ለማስባል ነው? የኛን እና የናንተን ጊዜ ለምን ይፈጃሉ? ጉጂ እኮ ወርቅ የሚዘረፍበት ነው። እንዴት ከዛ አንድ ሰው ማምጣት ይከብዳቸዋል? አቃቤ ህግ ሌላ ጫና ከሌለባቸው በህጉ አግባብ ይስሩ። ፍርድ ቤት በየጊዜው እያሳሰሰባቸው ነው ምስክር ይዘው ሚቀርቡት። ያልቀረቡ ምስክሮችን በተመለከተ ከቀበሌ ደብዳቤ ይዘው ቀርበዋል ወይ? አልቀረቡም! የፍርድ ቤት ትእዛዝ እየተከበረ አይደለም። እናንተም የካድሬ አይነት ሳይሆን የባለሙያነት አሰራር ስሩልን።” በማለት ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱን እንደሚቃወሙ ተናግረዋል።

“አቃቤ ህግ ዛሬ አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን ብሏል በወቅቱ ቀጠሮ ሲሰጥ ለምን አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን አይበቃንም አላለም? ከቀበሌ ይቅረብ የተባለው ማስረጃ አልቀረበም። የችሎቱ ብይን መከበር አለበት። ማእከላዊ ሲያሰቃዩን የነበሩ ፓሊሶች ናቸው ዛሬ ቀርበው ያልተገባ ተጨማሪ ቀጠሮ እየጠየቁ ያሉት።” ሲል የተጨማሪ ቀጠሮውን ጉዳይ ተቃውሞ አሰተያየታቸውን የሰጡት አቶ አዲሱ ቡላላ ናቸው።

ዳኞች ከተማከሩ በኋላ አቃቤ ህግ ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ፤ ተከሳሾችን ደግሞ የፓለቲካ እስረኛ ብሎ ነገር እንደሌለ፣ ያሉበትን ሁኔታ እንደሚረዷቸው፣ እንዲያውም ማነፃፀር ባይገባም ከሌላው መዝገብ ሲተያይ በፍጥነት እየሄደ መሆኑን፣ እነሱም [ተከሳሾች] መከላከያ ምስክር በሚያሰሙበት ጊዜ ምስክሮችን ለመስማት ጊዜ እንደሚሰጡ በመግለፅ ፓሊስ በ15 ቀን ውስጥ ከየትም ፈልጎ ምስክሮቹን እንዲያመጣ፤ የማይገኙ ከሆነም ይኖሩበት ከነበረው ቀበሌ ደብዳቤ እንዲቀርብ ትእዛዝ ሰጥተዋል። አቃቤህግ የተሰጠው ጊዜ አጭር እንደሆነ በመግለፅ ትንሽ ረዘም ያለ ቀጠሮ እንዲሰጠው ቢጠይቅም ዳኞች ጥያቄውን ሳይቀበሉት፤ ፓሊስ የተቻለውን ሁሉ ጥረት በማድረግ በቀጠሮው ቀን እንዲያቀርብ አዘዋል።

የተከሳሽ ጠበቃ የሆኑት አቶ መልካሙ የሚሰጠው ቀጠሮ የመጨረሻ እንዲሆን በሚል ላቀረቡት ሃሳብ፤ የመጨረሻ ቀጠሮ የሚባል እንደሌላ አሳማኝ ምክንያት ከተገኘ ሌላ ቀጠሮ ሊሰጥ እንደሚችል፤ አሳማኝ ምክንያት ካልተገኘ የመጨረሻ ባይባልም የምስክር የመስማት ሂደት ሊቋረጥ እንደሚችል በመጥቀስ ቀጣዩ ቀጠሮ የመጨረሻ መባል የለበትም ሲሉ ዳኞች መልስ ሰጥተዋል።

ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 15 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀጠሮ ተይዟል።

ምንጭ፦EHRP

የኢትዮጵያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ብቻ 11,700 በላይ ዜጎችን ማሰሩን አስታወቀ

(አዲስ ሚዲያ)ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራ እና በደቡብ ክልል ኮንሶ የነበረውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በተፈጠረው ህዝባዊ ቁጣ ለማረጋጋት በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ በሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ን ተከትሎ 11,607 ዜጎች መታሰራቸውን ገዥው መንግሥት አስታውቋል፡፡

ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ የመብት አራማጆች፣ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ገበሬዎች፣ ሴቶች እንዲሁም በርካታ ወጣቶች እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዕድሜ የገፉ አዛውንትም የታሰሩ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ውስጥ ብቻ መታሰራቸው ይፋ የተደረገው የታሳሪዎች ቁጥር ከዚህ ቀደም በህዝባዊ ተቃውሞው ወቅት በ10 ሺህዎች የሚገመቱ የታሰሩትን እንደማያካትት ተጠቁሟል፡፡

ገዥው መንግሥት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ህዝባዊ ተቃውሞውን ለማረጋጋት ቢሞክርም፤ አሁንም በተለይ በአማራ ክልል ሰሜን እና ደቡብ ጎንደር እንዲሁም ምዕራብ ጎጃም ተቃውሞ እና የመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጅ በተለይም ግድያ እና የአካል ማጉደል ርምጃዎች መቀጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በኦሮሚያም ክልል በተለይም ምዕራብ እና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና አርሲ አካባቢ ተቃውሞች እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡

በተለይ አዋጁን ተከትሎ የፀጥታ ኃይሎች በወንጀል የጠረጠሩት ሰው ላይ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣን መስጠቱ ቢታወቅም፤ ከተጠቀሰው የ11706 እስረኞች በስተቀር ስለተፈፀመው እርምጃና ስለተጎጂዎች የተሰጠ ዝርዝር ማብራሪያም ሆነ መረጃ የለም፡፡

እነ በቀለ ገርባ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች አልተሰሙም፤ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ አላቀረበም

‹‹እሰነጥቅሃለሁ ተብያለሁ›› አቶ በቀለ ገርባ

bekele-gerba-et-al

በኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል ውስጥ የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የቀረበባቸው የኦፌኮ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ከሦስት ወራት በኋላ እንደገና ወደ ችሎት ሲመለሱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ በመያዝ የነበር ቢሆንም፣ በእስር የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ ባለማቅረቡ ምክንያት ምስክሮቹ ሳይሰሙ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም በዋለው ችሎት ላይ እንደተመለከተው በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከተካተቱት ተጠርጣሪዎች (22 ሰዎች) መካከል 5ቱን ማረሚያ ቤቱ አላቀረባቸውም፡፡ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም ለፍርድ ቤቱ በጻፈው ደብዳቤ እንደገለጸው ‹4ቱ ተጠርጣሪዎች በቂሊንጦ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ አደጋ ተከትሎ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው ስላልተመለሱ› ማቅረብ አልቻለም፡፡ ማረሚያ ቤቱ ሸዋሮቢት እንደሚገኙ ያመለከታቸው ተጠርጣሪዎች ገላና ነጋሪ፣ ገመቹ ሻንቆ፣ ደረጀ መርጋ እና ቶምሳ አብዲሳ ናቸው፡፡

ሆኖም ግን ማረሚያ ቤቱ በስም ጠቅሶ ሸዋሮቢት ስለሆኑ ማቅረብ አለመቻሉን ከጠቀሰው ሌላ አንድ ተጠርጣሪ ችሎት አለመገኘቱን በማጣራት ፍርድ ቤቱ ተጠርጣሪውን ለምን እንዳላቀረበ የማርሚያ ቤቱን ተወካይ ጠይቋል፡፡ ሆኖም የዕለቱ ጉዳይ አስፈጻሚ ምክትል ሰርጀንት ዘውዱ ወልደማርያም ተጠርጣሪው በእርግጥ የት እንደሚገኝ እንደማያውቁ ተናግረዋል፡፡ ይህ የት እንዳለ ያልታወቀው ተጠርጣሪ ጭምሳ አብዲሳ ይባላል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ ተጠርጣሪዎች ብቻ ሳይሆኑ ጠበቆችም ተሟልተው አለመቅረባቸው ታውቋል፡፡ የብዙዎቹ ተጠርጣሪዎች ጠበቃ የሆኑት አቶ ወንድሙ ኢብሳ አልቀረቡም፡፡ ተከሳሾችም ጠበቃቸው ከቀጠሮ በፊት ደንበኞቻቸውን ለማነጋገር ወደቂሊንጦ ሄደው ማግኘት እንደማይችሉ ተነገሯቸው መመለሳቸውን ከማወቃቸው ውጭ በዛሬው ችሎት ለምን እንዳልቀረቡ እንደማያውቁ ለችሎቱ ተናግረዋል፡፡ በችሎት የቀረቡት ሌሎች ጠበቆችም ቢሆን ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ደንበኞቻቸውን በነጻነት ስለጉዳያቸው ለማነጋገር እንዳይችሉ እንቅፋት እየፈጠረባቸው መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ችሎቱ ዛሬ የተሰየመው የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት መሆኑን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ከአጠቃላይ 42 ምስክሮቹ መካከል አምስቱ መቅረባቸውን በመግለጽ ምስክሮቹ ቀርበው እንዲሰሙለት ጠይቋል፡፡ ሆኖም ግን ተከሳሾቹ ሁሉም ተሟልተው ባልተገኙበት ሁኔታ ምስክር ሊሰማ እንደማይገባ ጠቅሰው ተቃውመዋል፡፡ ተከሳሾቹ በክሱ ላይ በጋራ የቀረበባቸው ፍሬ ነገር ስላለ በተናጠል ምስክሮች ቢደመጡ መብታችንን ይነካል በሚል በጠበቆቻቸው አማካኝነት አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል አቶ በቀለ ገርባ አሁን ጉዳያቸውን እየየ የሚገኘው ችሎት በክስ መቃወሚያቸው ላይ ጉዳያቸው በፌደራል ፍርድ ቤት ሳይሆን በኦሮሚያ ክልል ፍርድ ቤቶች ሊታይ ይገባል በሚል ያነሱትን ህገ-መንግስታዊ የመብት ጥያቄ በጣሰ መልኩ ሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም መቃወሚያቸውን ውድቅ ማድረጉን በማስታወስ፣ በፍርድ ቤቱ ገለልተኝነት ላይ ጥያቄ ስላላቸው ችሎት ቀርበው ክርክር ለማድረግ እንደማይፈልጉ ቀደም ብለውም ገልተጸው እንደነበር ጠቅሰው በዛሬው ችሎት ላይም ፖሊስ በጉልበት እየደበደበ እንዳቀረባቸው አስረድተዋል፡፡

አቶ በቀለ ሌሎችንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዱት ከዚህም በኋላ ችሎት የሚቀርቡ ከሆነ ተገደው እየቀረቡ እንዳሉ ችሎቱ እንዲያውቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውድቅ ያደረገባቸውንና በክስ መቃወሚያ የጠቀሱትን ይህንኑ የህገ-መንግስት ጉዳይ ከጠበቆቻቸው ጋር ተመካክረው ወደ ፌደሬሽን ምርድ ቤት የመውሰድ ሀሳብ እንዳላቸውም ጠቅሰዋል፡፡

ፖሊስ በጉልበት መኪና ውስጥ ካስገባን በኋላ ‹‹እሰነጥቅሃለሁ›› የሚል ዛቻ እንደደረሰባቸው፣ ይህን የተናገረውን ፖሊስ ችሎት ፊት ጠቁመው በማሳየት ጭምር ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ግን ይህን ዛቻ ያደረሰውን ፖሊስ ችሎቱ አንድም ጥያቄ ሳያቀርብለት አልፎታል፡፡

በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ በዛሬው ውሎ ያልቀረቡ ተከሳሾችን ማረሚያ ቤት እንዲያቀርብ፣ 7ኛ ተከሳሽ ጭምሳ አብዲሳን ማረሚያ ቤት ለምን እንዳላቀረባቸው ምክንያት እንዲያስረዳ እንዲሁም የኦሮምኛና ስዋህሊ ቋንቋዎች አስተርጓሚዎች እንዲመደቡ ትዕዛዝ በመስጠት ተከሳሾቹ ተሟልተው ሲቀርቡ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለህዳር 6 ፍርድ 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤት ማንኛውም ተከሳሽ በቀጠሮው ዕለት የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ አክብሮ መገኘት እንዳለበትም ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ የኦሮምኛ ቋንቋ አስተርጓሚ ችሎቱ ባለማቅረቡ ከተከሳሾች መካከል አቶ በቀለ ገርባ በአጋዥነት ሲያስተረጉሙ ውለዋል፡፡ የዛሬውን ችሎት ከተከሳሽ ቤተሰቦች በተጨማሪ የዲፕሎማቲክ ኮሚኒቲ ተወካዮችና ጋዜጠኞች ተከታትለውታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ የሰላማዊ ዜጎች እስር ቢኖርም፤ በአንዳንድ ቦታዎች አሁንም ተቃውሞች እንደቀጠሉ ናቸው

(አዲስ ሚዲያ) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓም ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በጅምላ እየታሰሩ ነው፡፡ በተለይ በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እስሩ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ሳምንት ከአዲስ አበባ በደቡብ ምዕራብ በቅርብ ርቀት የምትገኘው ሰበታ ከተማ ብቻ ከ አንድ ሺህ በላይ ተጠርጣሪ ናቸው ያላቸውን ነዋሪዎችን ማሰሩን ራሱ መንግሥት ያስታወቀ ሲሆን፤ በሌሎችም የኦሮሚያ እና አማራ ክልል ከተሞችና ወረዳዎችም በተመሳሳይ መልኩ እስሩ መቀጠሉን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

በአማራ ክልል ሰሜን እና ጎንደር ዞን መንግሥት የነዋሪዎቹን ትጥቅ ለማስፈታት ወደ ወረዳዎች እና ገጠር ቀበሌዎች የፀጥታ ኃይሉን ቢያሰማራም ከህዝቡ የአፀፋ ርምጃ በመወሰዱ በርካታ ወታደሮችና ሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ተገድለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ህዝባዊ ተቃውሞው ከተጀመረበት ቀን አንስቶ የመንግሥት የፀረ አገዛዝና ጭቆና ተቃውሞ እንደቀጠለ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

በአፋር ክልልም እንዲሁ የሰላማዊ ዜጎች እስሩ የቀጠለ ሲሆን፤ ባለፈው ሳምንት ጥቅምት 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በአፋርኛ በማዜም የምትታወቀው ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌን ጨምሮ አስር ሰላማዊ ዜጎች በአሳይታ ከተማ መታሰራቸው ታውቋል፡፡

ethiopian-singer-mefera-mohmmed

ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌ

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ትግበራ ላይ መንግሥት እንደ ኢሳት፣ ኦ.ኤም.ኤን. የመሳሰሉ መገናኛ ብዙኃን መከታተልና መረጃ መለዋወ ላይ መመሪያው እገዳ ጥሏል፡፡ በተጨማሪ ያልተፈቀደ ሰልፍና የአደባባይ ስብሰባ፣ ለህዝብ አገልግሎት አለመስጠት፣ በትምህርትና በስፖርት ማዘውተሪያ አድማ ማድረግ በክልከላው ተካተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ትግበራባለመቀበል በድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ከቤት ያለመውጣት አድማ ማድረጋቸውን ቀጥለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመውጣቱ አስቀድሞ በኢትዮጵያ የመንግሥትን በደልና ብልሹ አሰራር ለመቃወምና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ  ቀድሞም ቢሆን ለዓመታት ፈፅሞ የተከለከሉ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለአንድ ዓመት ያህል ያለማቋረጥ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የቀጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማርገብ በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ የሆነ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማውጣት ኢንተርኔትን በተለይም ማኀበራዊ ሚዲያ፣ በውጭ ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ተዘጋጅተው ለህዝቡ አማራጭ የመረጃ ምንጭ በመሆን እያገለገሉ ያሉ እንደ ኢሳት፣ ኦ ኤም ኤን ያሉ መገናኛ ብዙኃን እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ሚዲያ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዳይሰራጩ ከማፈን በተጨማሪ ህዝቡም መረጃ መለዋወጥና መስማትም እንደሌለበት በአዋጁ መከልከሉ ይታወሳል፡፡

አዋጁን ተከትሎ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተለይ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ ክልል ኮንሶ ፣ ጋሞ ጎዳ ዞን፣ በአፋርና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል (ኦጋዴን) የተለያዩ ከተሞችና ወረዳዎች በመዘዋወር ድንገት ቤት ለቤት ፍተሻ በማድረግ የተለያዩ የወርቅ ጌጣጌጦችን፣ ገንዘብ፣ ተንቀሳቃሽ ስልክ ከመወስድ በተጨማሪ ጠርጥረንሃል ያሉትን ሰው ያለምንም ፍርድ ቤት ማዘዣ እየደበደቡ በመውሰድ ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሚያስሯቸው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ምክንያት ከወትሮ በተለየ መልኩ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢ ነዋሪው በፍርሃት ድባብ ውስጥ እንደሚገኙ በመጠቆም በማኀበራዊና ንግድ እንቅስቃሴዎች ላይም አለመረጋጋቶች እንደሚስተዋሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

መንግሥትበአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መሰረት አፈና እና ቁጥጥሩን አጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ዋነኞቹ የህዝባዊ ተቃውሞ አስተባባሪዎች መካከል የአማራ ተጋድሎና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች ከመንግሥት ርምጃ ጋር ተመጣጣኝ ሊሆን የሚችል አዳዲስ የትግል ስልቶችንም በቅርቡ ሊጀምሩ እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡ በተለይ በውጭ የሚኖሩ የመንግሥትን አገዛዝ የሚቃወሙ ኢትዮጵያውያን በስልጣን ላይ ካለው ገዥው ስርዓት ለውጥ በኋላ በኢትዮጵያ ሊመሰረት ስለሚገባው ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ትግበራ በቪዥን ኢትዮጵያ እና በኦሮሞ ማኀበረሰብዓለም አቀፍ የህግ ባለሙያዎች ማኀበር አስተባባሪነት ከወዲሁ በሰሜን አሜሪካ ዋሸንግተን ዲሲ  እበእንግሊዝ ለንደን ምክክር መጀመራቸው ታውቋል፡፡

የኦሮሞ ቻርተር ጉዳይ ወዴት ያደርሰናል?

semahegn-gashu

ሰማሀኝ ጋሹ (ዶ/ር)

የኦሮሞ ቻርተርና ወታደራዊ ክንፍ መቋቋምን በተመለከተ የሚመክር በአትላንታ የሚካሄድ ስብሰባ ዜና እና ሰነድ ይፋ ከተደረገ በሗላ በተለያዩ ወገኖች ዘንድ ጥርጣሬና ጥያቄ አስነስቷል። ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ አቶ ጃዋርንና ፕ/ር ህዝቄልን የኦሮሞ ቻርተርን በተመለከተ ውይይትም አካሂዷል። በውይይቱ ወቅት የመገንጠል ጥያቄዉን በተመለከተ ጥሩ ማብራርያ የተሰጠ ቢሆንም አሁንም በርካታ መልስ የሚሹ ጉዳዮች አሉ። በተለይ አትላንታ ይካሄዳል ተብሎ የታሰበዉን ስብሰባ በተመለከተ የወጣዉ መግለጫ በብዙዎች ዘንድ ያልተጠበቀ ነገር ነዉ። በጎንደር በተካሄዳዉ የተቃዉሞ ሰልፍ ወቅት ህዝቡ ‘ የኦሮሞ ደም የኛ ደም ነዉ’ ፥ ‘ በቀለ ገርባ መሪያችን ነዉ’ በማለት ለኦሮሞ ህዝብ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ ያለዉን አጋርነት ከገለፀ በሗላ በህዝቦች መካከል የነበረዉንና በህወሓት ለዘመናት የሚዘወረዉን የከፈፍልህ ግዛ (divide and conquer) ፖለቲካ በማዳከም ከፍተኛ የትግል አንድነት ያመጣ መሆኑ ይታወቃል። ህዝቡ ይህንን የተፈጠረዉን አንድነት የሚያጠናክር የፖለቲካ ሀይሎች የጋራ መድርክ ሲጠብቅ የተናጥል ስብሰባ መጠራቱ በብዙዎች ዘንድ ጥርጣሬ መጫሩ የሚጠበቅ ነዉ። ከዚህ አኳያ የተፈጠረዉን የህዝብ አንድነት ሊያጠናክር የሚችል ስራ ላይ ማተኮር ሲገባ የተናጠል የስብሰባ ጥሪ መጠራቱ በጋራ ትግሉ ላይ የራሱን ተፅእኖ ማሳደሩ የማይቀር ነዉ።

ከዚህ የከፋዉ ደግሞ የቀረበዉ ሰነድ ስለ ህዝቡ የጋራ ትግልና የደረሰበትን ደረጃ ጨርሶ አያነሳም። ሰነዱ ወደፊት የኦሮሞ ህዝብ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርአት ዉስጥ የሚኖረዉን ሚና በተመለከተም ምንም አይነት ፍንጭ ያልሰጠ ሲሆን የኦሮሞን ህዝብ በደሴትነት ተነጥሎ የተቀመጠ ያስመስለዋል። እንደዉም ሰነዱ የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት አድርጎ ያቀርበዋል። የቅኝ ግዛት ትንታኔዉን (colonial thesis) በርካታ የኦሮሞ ምሁራንና ፖለቲከኞች እንደማይደግፉት እየታወቀ ሁሉንም የኦሮሞ መሪዎች ላማሰባሰብ ያለመ ሰነድ ለምን ያአንድ ወገን አቋም ብቻ ለማንፀባርቅ እንደፈለገ ግልፅ አይደለም። የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት ጥያቅ እንዳልሆነ የሚያምኑትን የኦሮሞ ፖለትከኞችና ምሁራን የሚያገል ያሰመስለዋል። የኦሮሞን ህዝብ ቅኝ እንደተገዛ አድርጎ ማቅረቡ የኦሮሞ ህዝብ ከሌላዉ ህዝብ ጋር ያለዉን የባህልና የታሪክ ትስስርና የኦሮሞ ህዝብ ለኢትዮጵያ አንድነትና ህልዉና ያበረከተዉን አስተዋፅኦ የሚያሳንስ ነዉ። ከዚህም በተጨማሪ ይህን አይነቱ ትንታኔ አንዱን ማህበረሰብ ጨቋኝ ሌላዉን ተጨቋኝ በማድረግ የሚቀርበዉን የታሪክ ትንታኔ ህያዉ ሆኖ እንዲቆይ የሚፈልግ ያስመስለዋል። ይህም እስካሁን የሄድንበትን የጋራ አለመተማመን (mutual suspicion) በማስቀጠል ልንፈጥረዉ ለምናስበዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት እንቅፋት ይሆናል።

በተለይ በኢትዮጵያን አንድነትና በግለሰብ መብት ላይ የተመሰረተ የፖለቲካ ስርአት እንዲቋቋም የሚፈልጉ ዜጎችን የቀድሞዉ ስርአት ናፋቅዎችና ምኒልካዉያን እየተባለ መስደብ የተለመደ ነዉ። ያሁኑን ተዉልድ የፖለቲካ አስተሳሰብ መተቸት ካስፈለገ በራሱ በትዉልዱ አስተሳሰብ ላይ ተመስርቶ መተቸት ሲገባ ከቀደሙት ስርአቶች ጋር በማያያዝ አንገት ለማስደፋት የሚደረገዉ እንቅስቃሴ ያደባባይ ሚስጥር ነዉ። የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ከወራት በፊት ያደረገዉን የሬድዮ ዉይይት አስመልክቶ የቀድሞዉ ስርአት ናፋቂ የሚል ስድብና ዛቻ የኦሮሞ አክቲቪስቶች ነን ከሚሉ ወገኖች አስተናግዷል። ለዚህም ነዉ የአማራ ወጣቶች ሁሉም የብሄር ድርጅቶች አማራን በጠላትነት የሚፈርጁ በመሆኑ ተደራጅተን እራሳችንን እንከላከል እያሉ ያሉት። ምንም እንኳን ያለፈዉን ታሪካችንን በተመለከተ ብሄራዊ መግባባት ላይ መድረስ አስቸጋሪ ሊሆን ቢችልም እንዲህ አይነት የታሪክ ትንታኔዎችን ለፖለቲካ ፍጆታ ባለመጠቀም የተሻለ የፖለቲካ ድባብ ለመፍጠር ጥረት እንዳልተደረገ ግን ከቀረበዉ ሰነድ መረዳት ይቻላል።

ከዚህም በጠጨማሪ የቀረበዉ ሰነድ ባለፉት አስርተ አመታት የብሄረሰቦችን እኩልነት ለማምጣት የተሄደበትን መንገድ፥ ዉጤቱንና ችግሮቹን ሳያነሳ የኦሮሞ ህዝብ ከዛሬ አርባ አመት በፊት በነበረበት ሁኔታ እንዳለ አድርጎ ያቀርበዋል። ከሁሉም ብሄረሰቦች የተወጣጡ ወጣቶች በተማሪዎች እንቅስቅሴ ወቅት ያነሱት የመሬት ላራሹና የራስን እድል በራስ የመወሰን ጥያቄ በደቡብ ኢትዮጵያ የነበረዉን የጭሰኝነት ስርአት ያስወገደ ሲሆን ይህም ለኦሮሞ ህዝብ ታላቅ ለዉጥ አምጥቷል። ደርግም ሆነ ወያኔ ስታሊናዊ በሆነ መንገድ ችግሮቹን ለመፍታት የሄዱበት መንገድ ዉጤቱ አመርቂ ባይሆንም ሙከራዎች ግን ተደርገዋል። ይህ ሁሉ የፖለቲካ ለዉጦች በተካሄዱበት ሀገር አሁንም ቅኝ እንደተገዛን ነን የሚል እድምታ ያለዉ አቀራረብ በጣም ጨለምተኛና ካላፈዉ ስህተቶች ተምሮ የቀረዉን የእኩልነት ጥያቅ ለማሳካት በሚያስችል መልኩ አለመቀረፁ በኢትዮጵያ ያለዉን አስቸጋሪ የፖለቲካ ሁኔታ ለመፍታት ያለዉን ቁርጠኝነት ዉሱን ያስመስለዋል።

የኦሮሞ መሪዎች ስብሰባ ያስፈለገበትን ምክንያት አቶ ጃዋር ሲያስረዳ ወደፊት ለሚደረገዉ የሽግግር ወቅት እያንዳንዱ ማህበረሰብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ መምጣት ስላለበት የኦሮሞን ቻርተር ለማዘጋጀት በማስፈለጉ ነዉ ይላል። ለዚህም የደቡብ አፍሪካዉን ብሄራዊ ኮንግረስና የህንዱ ጃዋራላል ኔህሩ በትግል ወቅት እንዲህ አይነት ቻርተር አዘጋጀተዉ ነበር ሲል ያስረዳል አቶ ጃዋር። እያናንዳንዱ ማህብረስብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ ይምጣ ከተባለ ሁሉም ብሄረሰቦች አንዳንድ ቻርተር በማዘጋጀት ሲመጡ ቢያንስ ከ 80 ያላነሱ ቻርተሮች ተዝጋጅተዉ ሊቀርቡ ነዉ ማለት ነዉ( ያዉም እያንዳንዱ ማህበረሰብ በአንድ ድርጅት ይወከላል ብለን ካሰብን ነዉ።) እንዲህ ያለ ሁኔታን እንዲኖር መፈለግ አላማዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ወይስ የባቢሎንን ግንብ ለመገንባት ነዉ? ሁሉም ብሄር የራሱን መብት እንዲከበር በሚል በሚያደርገዉ ፍላጎት ሁሉንም የሚያረካ መፍትሄ ማግኘት የሚክብድ ከመሆኑም በተጨማሪ የፈለገዉን ያላገኘዉ ወገን ‘የራሴን እድል በራሴ’ እወስናለሁ ወደሚል ሌላ ዙር ግጭት ይገባል። በተለይ ወታደራዊ ክንፍ ያለዉ የብሄር ድርጅት የሚበረታታ ከሆነ በጉልበት የፈለገዉን ለማድረግ ማንገራገሩ የማይቀር ነዉ። ወያኔም በ1983 ዓም ባደረገዉ የሽግግር መንግስት ምስረታ ወቅት በብሄር የተደራጁትን ብቻ ተቀብሎ ህብረ ብሄር የሆኑትን ግን አልቀበልም ነበር ያለዉ። ለዚህም የተማመነዉ የነበረዉን ጉልበት ነዉ። ኦነግንም ከሽግግሩ መንግስት እንዲወጣ ያደረገዉ ይሄዉ የወያኔ እብሪተኝነት ነዉ። አሁንም በብሄር ተደራጅታችሁ የራሳችሁን ቻርተር አዘጋጅታችሁ ኑ ማለት ተመሳሳይ አካሄድ ያለዉ ነዉ። በርካታ ማህበረሰቦችም በተለያየ ምክንያት ተደራጅተዉ ቻርተር አዘጋጅተዉ ላይቀርቡ ይችላሉ። በዚህ ጊዜ የነዚህ ማህበረሰቦች እድል ቻርተር አዘጋጅተዉ በመጡት ሊወሰን ነዉ ማለት ነዉ? ይህስ አካሄድ ወያኔ በ1983 ካደረገዉ በምን ይለያል? ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የፖለቲካ ሃይሎች እኛ ባልነዉ ካለተስማማችሁ ዞር በሉ ቢሉ ዋስትናዉ ምንድን ነዉ? አልሸሽም ዞር አሉ እንደሚባለዉ ተመልሶ ወደ ግጭት አያስገባንም ወይ?

አቶ ጃዋር ያቀረባቸዉ የደቡብ አፍሪካ፤ ህንድና ቱኒዝያ ምሳሌዎች አሁን ከተጠራዉ የኦሮሞ የነፃነት (freedom) ቻርተር ጉዳይ በጣም የተለዩ ናቸዉ። በነዚህ ሃገሮች የቀረቡት የነፃነት (freedom) ቻርተሮች ሆነ ድርድሮች ሃገራዊና የሁሉንም ማህበረሰብ ፍላጎት የሚያንፅባርቁ እንጂ የአንድ ብሄርን ብቻ የሚመለከቱ አልነበሩም። እንዲሁም በህንድ የተካሄደዉ የፀረ ቅኝ ግዛት ትግልና በደቡብ አፍሪካ የተካሄደዉ የፀረ አፓርታይድ ትግል አሁን ኢትዮጵያ ዉስጥ ካለዉ የፖለቲካ ሁኔታ ጋር ያላቸው ዝምድናና እና ልዩነት በግልፅ አልቀረበም ። የምናቀርባቸዉ ምሳሌዎች ተገቢ ትርጉማቸዉን የያዙ ቢሆኑ የምናቀርበዉን ሃሳብ ተአማኒነት ያጠናክረዋል። አቶ ጃዋር ስለ ቱኒዝያ የተናገረዉም እኛ እየሄድንበት ካለው ጋር የሚገናኝ አይደለም። ከሌሎች አብዮት ከተካሄደባቸዉ የአረብ ሃገራት በተለየ የተሻለ የፖለቲካ ሽግግር በቱንዝያ የተፈጠረዉ እንደ ሊቢያና ሶርያ በሃይማኖትና በጎሳ ለመከፋፈል ባለመፍቀዳቸዉ ነዉ። ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የብሄር ድርጅቶችን የምናበረታታ ከሆነ ግን ለጊዜዉ በአንድ ጠላት ላይ ሲያተኩሩ ልዩነት የሌላቸዉ የሚመስሉ የፖለቲካ ህይሎች ያ ጠላት ከስፈራዉ ሲነሳ እርስ በርሳቸዉ መበላላታቸዉ የማይቀር ነዉ። ሊብያ ዉስጥ በተካሄደዉ አብዮት ወቅት ሁሉም ጎሳዎች ጋዳፊን ለመጣል ሰምና ወርቅ ሆነዉ ከሰሩ በሗላ አሁን ሁሉም በየፊናዉ ወታደራዊ ቀጠና አቋቁሞ እየተጋጨ ሲሆን ማዕከላዊ መንግስት በስምምነት ለመመስረት አልቻሉም።

በእዉነት የኢትዮጵያን የፖለቲካ ችግሮች ለመፍታት ቅንነቱና ቁርጠኝነቱ ካለ እንደ ኑክልየር ሳይንስ ዉስብስብ ስላልሆነ 80 ቻርተር ማዘጋጀት አያስፈልገዉም። የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሰረታዊ ችግሮች እንዴት ብሄራዊ አንድነትንና የብሄር መብትን፥ የግለሰብና የቡድን መብትን አጣጥመን እንቀጥል፥ እንዴት ብሄራዊ መግባባትን እንፍጠር፥ ዴሞክራሴያዊ ባህልና ተቋማት እንዴት እንገንባና ማህበራዊና ኤኮኖምያዊ ፍትህ እንዴት እናረጋግጥ የሚሉት ናቸዉ። እነዚህን የፖለቲካ ጥያቄዎች ለመመለስ ዋናዉ መነሻ የተናጥል አካሄድን በተቻለ መጠን በማስቀረት ሁሉም የፖለቲካ ሃይሎች በጋራ የሚመክሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነዉ። ነገር ግን አሁንም የሽግግር ሂደቱን በበላይነት ለመቆጣጠር የሚካሄደዉ ፉክክር ስር የሰደደዉን የፖለቲካ ሃይሎች አለመተማመን እንዲቀጥል የሚያደርገዉ ከመሆኑም በተጨማሪ የግጭትንና የእኔ አውቅልሃለሁን የቆየ የፖለቲካ ባህል ለመለወጥ የሚኖረዉን እድል ያደበዝዘዋል።

%d bloggers like this: