ኢትዮጵያ- የአማራ ህዝብ የመብት ጥያቄና ( #AmharaProtests) በመንግስት የተወሰደው የኃይል እርምጃ
በአማራ የተቃውሞ ድምጽ በሚያሰሙ ዜጎች ላይ የሚደርሰው የመብት ጥሰት ግድያ፣ የእስርና ደብዛ መጥፋት መጠኑ ይለያይ እንጂ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ በተለይም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ አሁንም ድረስ በጎንደር፣ በባህር ዳርና በምዕራብ ጎጃም ዞኖች ዜጎችን በገፍ የማሰሩ እርምጃ ቀጥሏል፡፡
ወጣት ንግስት ይርጋ በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ
በተቃውሞ ሰልፎች የተሳተፉ ወጣቶችን በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች በገፍ ማሰሩ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው ከተሞች ከፍተኛ ነው ፡፡ ለምሳሌ በጎንደር ከተማ በሚገኙ 1ኛ፣ 2ኛ፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ እና 6ኛ ፖሊስ ጣቢያዎች በጠባብ ክፍሎች ውስጥ በአንድ ጣቢያ በአማካይ እስከ 140 ሰዎች እንደሚታሰሩ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
ጎንደር ከተማ ውስጥ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ለሁለት ሳምንታት ታስሮ የነበረ ወጣት ደረጀ ጌቱ (ስሙ የተቀየረ) እንደሚናገረው በጣቢያው ውስጥ አብረውት ታስረው የነበሩት አብዛኞቹ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ መሳተፋችሁ በፎቶ ተረጋግጧል በሚል ለእስር ተዳርገው የነበሩ ናቸው፡፡
በተመሳሳይ በባህር ዳር ከተማ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እንዲሁ በከተማዋ ተደርጎ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት በተሳተፉ ወጣቶች በገፍ እየታሰሩ ነው፡፡ እነዚህ ወጣቶች አንዳንዶቹ በአጭር ጊዜ ሲታሰሩ እና ሲፈቱ ሌሎች ደግሞ በተደጋጋሚ መታርና መፈተታ እንደሚገጥማቸው ማየት ተችሏል፡፡
በእነዚህ ፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩትን ማን እንደታሰረና፣ የት እንደታሰረ ቤተሰብና ዘመድ የማወቅ እድል ቢኖረውም ሌሎች የት እንደታሰሩ ሳይታወቅ ለቀናት፣ ለሳምንታትና ለወራትም የሚከርሙ መኖራቸውም ታውቋል፡፡ እነዚህ የእስር ስፍራዎች በይፋ የማይታወቁና በተቃውሞ እንቅስቃሴው እጃቸው በሰፊው አለበት በሚል መንግስት የጠረጠራቸውን “የሚመረምርባቸው” ናቸው፡፡
ከእነዚህ ድብቅ የእስር ቦታዎች መካከል ለምሳሌ ባህር ዳር አባይ ማዶ ከብአዴን ጽ/ቤት ጀርባ የሚገኝ ቀድሞ የመሳሪያ መጋዘን የነበረ ስፍራ ይገኝበታል፡፡ በዚህ ቦታ የሚታጎሩ ወጣቶችን ቤተሰቦቻቸው ለመጠየቅም ሆነ በዚያ ስፍራ ስለመኖር አለመኖራቸው ለማወቅ እንደማይችሉ ታስረው የተፈቱና፣ ታስረው እንደነበርም እንዳይናገሩ ማስፈራሪያ ደርሷቸው የወጡ ይመሰክራሉ፡፡ አበበ አስረስ (ስሙ የተቀየረ) በዚህ ድብቅ የእስር ቦታ ለ17 ቀናት ሲሰቃይ ቆይቶ መለቀቁን ይናገራል፡፡
‹‹ቦታው የሆነ መጋዘን ነገር ነው፤ ሰፊ አዳራሽ ነው፡፡ በዚህ አዳራሽ ውስጥ በጣም ብዙ ሰዎች አብረውኝ ታስረው ነበር፡፡ የእስራችን ምክንያት ብለው የነገሩን ባህር ዳር ነሐሴ 01/2008 ዓ.ም በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰልፉን አደራጅታችኋል የሚል ነው፡፡ በእስራችን ጊዜ ቤተሰቦቻችን አንድም ቀን አላገኙንም፡፡ በኋላ ብዙዎችን ወደ ብርሸለቆ ሲወስዷቸው እኔን ድጋሜ ሰልፍ ላይ ካገኘንህ እንገድልሃለን ብለው ዝተውብኝ የሆነ ወረቀት ላይ አስፈርመው ለቀውኛል፡፡ ማታ ላይ ነው በመኪና ከሌሎች ሦስት ልጆች ጋር ጥለውኝ የሄዱት›› ሲል ያስታውሳል አበበ፡፡
አበበ አስረስ ከድብቅ እስር ቤቱ መፈታቱን ተከትሎ ዘመድ ለመጠየቅ በሚል ከአካባቢው ዞር ለማለት አስቦ የቤተሰቦቹን ምክር ተቀብሎ ወደ አዲስ አበባ ዘመድ ጋር ሳምንታትን አሳልፏል፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ጊዜ ነበር እስር ላይ ሆኜ ያሳለፍኩት›› የሚለው አበበ፣ ከሳምንታት የአዲስ አበባ ቆይታ በኋላ የገና በዓልን ከቤተሰቦቹ ጋር ለማሳለፍ ወደ ባህር ዳር በተመለሰበት ወቅት፣ ‹‹የት ጠፍተህ ከርመህ እንደመጣህ እናውቃለን!›› በሚል በድጋሜ ለእስር እንደተዳረገ ታውቋል፡፡
በድብቅ እስር ቤቶችም ሆነ በፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩ ሰዎች የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጸም ለማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን፣ በተለይ ድብደባ በብዙዎቹ ላይ በምርመራ ወቅት የሚፈጸም የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፡፡ በባህር ዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ የሚታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በምርመራ ወቅት ጥፍርን እስከመንቀል የሚደርስ ኢ-ሰብዓዊ የሆነ ድርጊት ይፈጸምባቸዋል፡፡
ብዙዎች በፖሊስ ጣቢያ ለሳምንታት እንዲቆዩ ከተደረገ በኋላ ወደ ብርሸለቆ የወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም ለ‹ተሃድሶ ስልጠኛ› ተግዘዋል፡፡ በማሰልጠኛ ተቋሙ በሚኖራቸው ቆይታም ቢሆን ተመሳሳይ፣ አንዳንዴም የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል፡፡ (በተሃድሶ ማሰልጠኛ ስፍራዎች ስለሚፈጸም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት በቅርቡ ለማሳያነት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት መመልከት ይቻላል፡፡)
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት በዋናነት ቀድሞውንም በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ በሚታገሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ ያነጣጠረ የእስር እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ‹የጸረ-ሽብር ግብረ-ኃይል› በሽብር ጠርጥሬያቸዋለሁ በሚል 2008 ዓ.ም ሐምሌ ወር መግቢያ ላይ በጎንደር በነበሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጠያቂ የህዝብ ተወካይ (ኮሚቴ) አባላትን ለማሰር በተደረገ እንቅስቃሴ በሁዋላ በአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ህዝባዊ ተቃውሞዎች በተደጋጋሚ መከሰታቸው ይታወሳል፡፡ የህዝባዊ ተቃውሞዎቹም መነሻ ከመስፋፋታቸው በፊት ጎንደር ላይ ብዙ ነዋሪዎች የተሳተፉበት ትልቅ እና ሰላማዊ ሰልፍም ተካሄዷል፡፡
ከጎንደር በማስከተል በሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም የተከናወነው የባህር ዳር ሰልፍ ግን በተለየ መልኩ በአሳዝኝ ሁኔታ የተጠናቀቀ ነበር፡፡ ሰልፉ ሲጀምር ሰላማዊ የነበር ቢሆንም ዘግይቶ የመንግስት ታጣቂዎች በወሰዱት እርምጃ በአንድ ቀን ብቻ ከ50 በላይ የሚገመቱ ንጹሃን መገደላቸው የሚታወስ ነው፡፡
እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት አማራ ክልል ከሚገኙት በአጠቃላይ 11 ዞኖች በስድስቱ ዞኖች የጎላ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ተደርጎባቸዋል፡፡ እነዚህም ሰሜን ጎንደር፣ ደቡብ ጎንደር፣ ባህር ዳር ልዩ ዞን፣ አዊ ዞን፣ ምዕራብ ጎጃም እና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች ናቸው፡፡ በስድስቱ ዞኖች የሚገኙ አብዛኞቹ የዞንና የወረዳ ከተሞች (አንዳንድ ቦታዎች ላይ ገጠር ቀበሌዎችንም ጨምሮ) መንግስትን የሚቃወሙ ሰላማዊ ሰልፎችንና የቤት ውስጥ አድማዎችን አስተናግደዋል፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማና የቱሪስት መናሃሪያዋ ጎንደር ላይ የተጀመረው እንቅስቃሴ፣ ደባርቅ፣ ደብረታቦር፣ መተማ፣ አምባ ጊዮርጊስ፣ ወረታ፣ ስማዳ፣ ጋይንት፣ ባህር ዳር፣ ፍኖተ ሰላም፣ ቡሬ፣ እንጅባራ፣ ዳንግላ፣ ቻግኒ፣ ቲሊሊ፣ ብርሸለቆ፣ ቋሪት፣ ደምበጫ፣ አማኑኤል፣ ደብረ ማርቆስና ሌሎች በርካታ ከተሞችን አዳርሷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት አድማሱን እያሰፋ የሄደውን የተቃውሞ እንቅስቃሴ ለመግታት የኃይል እርምጃ መውሰዱን በተግባር ከማሳየቱም በላይ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የመንግስት ጦር ተቃውሞውን ለመግታት ‹ማንኛውንም እርምጃ እንዲወስድ› ማዘዛቸው የሚታወስ ነው፡፡ በዚህም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል፡፡ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች እንደ ብርሸለቆ የመሰሉ የጦር ማሰልጠኛዎች ውስጥ ሳይቀር በተለያዩ ቦታዎች ታስረዋል፤ በርካቶች ደግሞ የደረሱበት አልታወቀም፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ባለፉት ወራት በተደረጉት የአማራ ህዝብ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ወቅት ለጊዜው ያሰባሰበው መረጃም ብዙ ዜጎች በመንግስት ኃይሎች እንደተገደሉ ያሳያል፡፡ ከዚህ በታች ያለው ዝርዝር ለጊዜው ተለይተው የታወቁ የሟቾችን ስምና አድራሻ አካትቶ ለማሳያነት የቀረበ ነው፡፡
የተገደሉ ሰዎች ስም አድራሻ
1. ይሻል ከበደ ……………………………ጎንደር
2. ሲሳይ ታከለ ……………………………ጎንደር
3. አበበ ገረመው…………………………ባህር ዳር
4. ተፈሪ ባዬ ………………………………ባህር ዳር
5. እድሜዓለም ዘውዱ ……………………ባህር ዳር
6. አደራጀው ደሳለኝ …………………… ባህር ዳር (ዩኒቨርሲቲ)
7. ይበልጣል…………………………………ደብረ ታቦር
8. ግዛቸው ከተማ …………………………ጎንደር
9. አዳነ አየነው ………………………………ጎንደር
10. ማንደፍሮ አስረስ………………………ባህር ዳር
11. ቁምላቸው ቃሉ …………………………ባህር ዳር
12. አወቀ ጥበቡ ……………………………ፍኖተ ሰላም
13. ሲሳይ ከበደ ……………………………ጎንደር
14. ሰጠኝ …………………………………ጎንደር (የወልቃይት ተወላጅ)
15. እቴነሽ ሽፈራው ……………………ም/ጎጃም፣ ጂጋ
16. እንዳለው መኮነን …………………ጎንድር፣ ጋይንት
17. እሸቴ ……………………………… ባህር ዳር (ቀበሌ 16)
18. ሰለሞን አስቻለ ………………………ባህር ዳር
19. ሙሉቀን ተፈራ ………………………ባህር ዳር
20. አደራጀው ኃይሉ ………………………ባህር ዳር
21. አስማማው በየነ ……………………… ባህር ዳር
22. ታዘበው ጫኔ …………………………ባህር ዳር
23. አስራት ካሳሁን …………………………ባህር ዳር
24. የሺዋስ ወርቁ ……………………………ባህር ዳር
25. ብርሃን አቡሃይ ………………………… ባህር ዳር
26. ሽመልስ ታየ ………………………………ባህር ዳር
27. አዛናው ማሙ …………………………… ባህር ዳር
28. ሲሳይ አማረ ………………………………ባህር ዳር
29. ሞላልኝ አታላይ ………………………… ባህር ዳር
30. መሳፍንት ………………………………………ጎንደር፣ እስቴ
31. እንግዳው ዘሩ ………………………………… ባህር ዳር
32. ዝናው ተሰማ ………………………………… ባህር ዳር
33. ሞገስ ሞላ ………………………………………ባህር ዳር
34. ሞላልኝ ታደሰ …………………………………ባህር ዳር
35. ይታያል ካሴ ………………………………………ባህር ዳር
36. እሸቴ ብርቁ …………………………………… ባህር ዳር
37. ሞገስ………………………………………………ባህር ዳር
38. ገረመው አበባው ………………………………ባህር ዳር
39. ማህሌት…….…………………………………… ባህር ዳር
40. ተስፋየ ብርሃኑ …………………………………ባህር ዳር
41. ፈንታሁን………………………………………… ባህር ዳር
42. ሰጠኝ ካሴ ……………………………………… ባህር ዳር
43. ባበይ ግርማ ………………………………………ባህር ዳር
44. አለበል ዓይናለም ……………………………… ደብረ ማርቆስ
45. አብዮት ዘሪሁን …………………………………ባህር ዳር
46. አበጀ ተዘራ ………………………………………ወረታ
47. ደሞዜ ዘለቀ ……………………………………ወረታ
48. አለበል ሀይማኖት ………………………………ባህር ዳር
49. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
50. ዓይናዲስ ለዓለም ……………………………… ደብረወርቅ
51. ሽመልስ ወንድሙ ……………………………… ቡሬ
52. ታደሰ ዘመኑ ………………………………………አዴት
53. ሀብታሙ ታምራት ……………………………ባህር ዳር
54. ይበልጣል እውነቱ …………………………ባህር ዳር፣ ጭስ አባይ
55. ይህነው ሽመልስ ………………………………ደብረታቦር
56. በለጠ ካሴ ………………………………………ደብረታቦር
57. አዳነ እንየው ……………………………………ጎንደር፣ ቀበሌ 16
58. አለማየሁ ይበልጣል ……………………………ዳንግላ
59. ያየህ በላቸው …………………………………… ዳንግላ
60. በረከት አለማየሁ …………………………………ዳንግላ
61. ተመስገን ……………………………………………ዳንግላ
62. ቅዱስ ሀብታሙ ………………………………… ባህር ዳር
63. ፍስሃ ጥላሁን ………………………………………ባህር ዳር
64. ሰለሞን ጥበቡ …………………………………… ቻግኒ
65. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
66. ዘሪሁን ገደብዬ …………………………………ጎንደር
67. ሲሳይ ባብል ………………………………………ጎንደር
68. ባየሁ ጎንደር ………………………………………ጎንደር
69. በለጡ መሃመድ …………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
70. እንጀራ ባዬ ………………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
71. ወንድም ……………………………………………ጎንደር
72. ግርማቸው ከተማ ………………………… ላይ አርማጭሆ
73. ሊሻን ከበደ ………………………………………አይባ
74. መሌ አይምባ …………………………………… አይባ
75. አዛነው ደሴ ………………………………………አርማጭሆ
76. አራገው መለስ ……………………………………አርማጭሆ
77. ሰጠኝ አድማሱ ……………………………………ደልጊ
78. ታረቀኝ ተሾመ ……………………………………ደልጊ
79. ሄኖክ አታሎ ………………………………………ደልጊ
80. ደሴ ደረሰ …………………………………………ሻውራ
81. ግርማቸው ሞገስ …………………………………ሻውራ
82. ወርቁ ጠቁሳ ………………………………………ሻውራ
83. ማማዬ አንጋው …………………………………ዳንሻ
84. ፈንታ አህመድ ……………………………………ዳንሻ
85. ክንፌ ቸኮል ………………………………………በአከር
86. ሲሳይ ታከለ ……………………………………… አርማጭሆ
87. ማዕረግ ብርሃን …………………………………ደብረታቦር
88. መምህር ተስፋየ ብርሃን ……………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
89. ይበልጣል ደሴ ………………………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
90. አራጋው መለሰ …………………………… አርማጭሆ
91. አዳነ አያሌው ………………………… አርማጭሆ
92. አያናው ደሴ ………………………… አርማጭሆ
93. ትርፌ አጣናው ……………………… አርማጭሆ
94. መምህር ብርሃኑ አየለ …………… ሰሜን ሸዋ፣ ማጀቴ
95. አብራራው አለማየሁ ………………ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
96. ተመስገን ሲሳይ …………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
97. ጋሻው ሲራጅ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
98. ፈንታ ሞገስ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
99. ታደለ ያየህ ……………………………ምዕራብ ጎጃም፣ ቡሬ
(*ማስታወሻ፡- መንግስት ህዝባዊ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው አካባቢዎች የኢንተርኔትና የስልክ ግንኙነቶችን በሙሉና በከፊል መዝጋቱ በእነዚህ አካባቢዎች ስለተከሰቱ ጉዳዮች መረጃ የማግኘት ስራውን አዳጋች በማድረጉ ይህ ዝርዝር ሁሉንም የመብት ጥሰት የደረሰባቸው ዜጎችን ያሳያል ተብሎ አይጠበቅም፡፡)
*ሌላው ከአማራ ህዝባዊ ተቃውሞ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው
1. ንግስት ይርጋ………የመብት ተሟጋች፣ አድራሻ ሳንጃ ሰሜን ጎንደር…. ቃሊቲ እስር ቤት ታስራ ትገኛለች
2. አለምነው ዋሴ የመኢአድ አባል አድራሻ ጎንደር ቂሊንጦ በእስር ላይ ያለ
3. ቴዎድሮስ ተላይ……….አድራሻ ጎንደር
4. አወቀ አባተ……………….የመኢአድ አባል
5. በላይነህ አለምነህ…የሰማያዊ ፓርቲ አባል፣ አድራሻ ባህር ዳር
6. ያሬድ ግርማ…………………. የመኢአድ አባል
7. አታላይ ዛፌ…የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ኮሚቴ አባል
*ክስ ሳይመሰረትባቸው በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት
7. ማሩ ዳኛው
8. ቢሆን
9. መልካሙ ታደለ
10. ሲሳይ ታፈረ
11. ወርቁ ጥላሁን
12. ድንቁ
13. ስማቸው ማዘንጊያ
14. እያዩ መጣ
15. ድርሳን ብርሃኔ
16. አንዳርጌ አባይ
17. ዮናስ ሰለሞን
18. መሃመድ ኑርየ
19. መምህር መሃመድ አሊ
20. መንግስቴ ብርሃኔ
21. ጌታነህ ደምሴ
22. ታደለ እንዳልፈራ
23. መምህር ለወየሁ ጌቱ
24. እሸቴ ደረሰ
25. ጌጤ ላሽተው
26. ሰይዒድ እንድሪስ
27. አህመድ በዛብህ
28. ጀማል ኡመር
29. አብደላ መሃመድ
30. አዲሱ ጌታነህ
31. ዘሪሁን እሸቱ
32. ጀማል ይመር
33. አበበ ጥላሁን
34. ተሻገር ወልደሚካኤል
35. እያሱ ሁሴን
36. በላቸው አወቀ
37. ዘውዱ ነጋ
38. ወልደመስቀል ማማየ
*የህዝቡን የመብት ጥያቄ (ህዝባዊ ተቃውሞ) ደግፋችኋል በሚል ከታሰሩት መካከል፡-
39. ገድፍ ጌታነህ……ሰሜን ጎንደር በለሳ ወረዳ
40. ሊቀሊቃውንት እዝራ (ቤተ-ክርስቲያንን ሽፋን አድርገው የህዝቡን ተቃውሞ ይደግፋሉ በሚል የታሰሩ)
41. ቀለመወርቅ ዓለሙ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የጎንደር ሀገረ ስብከት ጳጳስ ኃላፊ)
42. ሂሪያኮስ አበበ…..ጎንደር ከተማ
43. ዶክተር ጋሹ ክንዱ
(ዶክተር ጋሹ ክንዱ የቡሬ ዳሞት ሆስፒታል ሜዲካል ዳሬክተር ናቸው፡፡ ታህሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም ለገና በዓል ወደ ቤተሰቦቻቸው ባመሩበት ጊዜ ባህር ዳር ከተማ ለእስር ተዳርገው ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲዛወሩ ተደርገው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡
ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (ኢሰመፕ) የተዘጋጀ
የመብት አራማጅ ንግስት ይርጋ የሽብር ክስ ተመሰረተባት
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ጎንድር ውስጥ ለእስር ተዳርጋ ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተዛውራ ከአራት ወራት በላይ ያሳለፈችው አክቲቪስት ንግስት ይርጋና ሌሎች አምስት ሰዎች የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡
ንግስት ይርጋ
የፌደራል አቃቤ ህግ ታህሳስ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. በጻፈውና ለተከሳሾች ጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲደርሳቸው በተደረገው የክስ ቻርጅ ላይ እንደተመለከተው ንግስት ይርጋ ‹‹ከአርበኞች ግንቦት ሰባት የሽብር ድርጅት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ በሰሜን ጎንደርና በሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች አመጽ በማስነሳት፣ አመጹን በበላይነት በመምራትና በማስቀጠል…›› የሽብር ወንጀል ድርጊት ተሳታፊ በመሆን ክስ ቀርቦባታል፡፡
ንግስት ይርጋ 1ኛ ተከሳሽ በተደረገችበት የክስ ዝርዝር ላይ እንደተመለከተው፣ ተከሳሾች በ2001 ዓ.ም የወጣውን የጸረ ሽብር አዋጅ አንቀጽ 3/4/6ን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡
የመብት አራማጅ ንግስት ይርጋ ነሐሴ ወር ላይ በጎንደር ከተማ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ‹‹የአማራ ህዝብ አሸባሪ አይደለም›› የሚል ጽሁፍ የሰፈረበት ቲሸርት ለብሳ በሰልፉ ላይ መታየቷ ይታወሳል፡፡
ክሱ የቀረበለት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበውን ክስ በንባብ ለማሰማት ለጥር 10 ቀን 2009 ዓ.ም ቀጠሮ ይዟል፡፡
ምንጭ፦ EHRP
በማንነት ፖለቲካው ምስቀልቅል የአማራ ብሔረተኛነት ተጽዕኖና ተግዳሮቶቹ
የሱፍ ያሲን
yussuf.yassin @gmail.com
የሱፍ ያሲን
1. አማራ ከሰኔ (1983) ኮንፊረንስ እስከ ጥቅምት (2009) ስብሰባ
አማራ ወያኔ ኢሕዴአግ በጠራው የአዲስ አበባ 1983ቱ (1991) የሰኔ ኮንፊረንስ አልተወከለም ነበር። በቅርቡ በዋሽንግተኑ የጥቅምት 2009 (2016) በኢትዮጵያ ሃገራዊ ንቅናቄ (ኢሃን) ስብሰባ ላይም አልተወከለም ተባለ። በሁለቱም ስብሰባዎች አማራ ተገቢ ውክልና አላገኘም ነው አንዱ ቅሬታው። በመጀመሪያው ኮንፊረንስ ውክልና የተነፈገው በብሔረሰቡ ስላልተደራጀ ነው የሚል ምክንያት ነበር በኮንፈረንሱ አዘጋጆች የተሰጠው። ላሁኑ “አለመወከል” የተሰጠው ምክንያትም የአማራ ብሔረተኞችን አላረካም እንዲያውም አስቆጣ እንጂ። እንዲያውም የሚወክለው ሰው ጠፍቶ አማራ ባንድ ሰው ተወክሎ ነበር መባሉን በቅርቡ በሲያትል የተሰበሰቡት የአማራ ድርጅቶች ወኪሎች እንደ ስድብ ነው የቆጠርነው ነበር ያሉት። የመጀመሪያው ወይም የ 1983 ቱ “አለመወከል” አማራን አዲሱ መንግሥት እነሱን የሚመለከትበትን መነጽር አመላካችና የመከራ ደወል ጅማሮ ነበር ማለት ይቻላል። ምናልባት ፕሮፌሰር አሥራት ወልደየስ አማራ በራሱ መደራጀት እንዳለበት የተገነዘቡበት የመጀመሪያው አጋጣሚ ነው ማለት ይቻል ይሆናል። ለሁለተኛ ግን አማራ ከ25 ዓመት በኋላ በራሱ እንዲደራጅ ተጨማሪ አንደርዳሪ ግፊት አሳርፎ አልፏል። በተጨማሪም ምናልባት ሰሞኑን በማሕበራዊ ሜዲያ ለሚንመለከተው እንካ ስላንቲያና መፈራረጅ ቀጥተኛ ምክንያት ሆኗል ማለትም ያስኬዳል።
በሁለቱ ስብሰባዎች መሃል ግን በድልድዩ ሥር ብዙ ውሃ ፈሷል (so much water has passed under the bridge) ፈረንጆች እንደሚሉት። በሁለቱ ስብሰባዎችና መካከሎች የአማራ ማንነት በርካታ ውጣ ውረዶችን አስተናግዷል። በርካታ እንግልቶች በማህበረሰቡ ላይ ደርሰዋል። የአማራ የማንነት ትግሉ በርካታ አባጣና ጎርባጣ መንገዶችን ተጉዟል።
የአማራን በአማራነት አደረጃጀት እና ብሔረተኛነት ከፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ እስከ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ አመራር በርካታ የእድገት እርከኖች ተረማምዷል። ኢህዴንን ወደ ብአዴን ከቀዳማዊ መአሕድ እሰከ ዳግማዊ መአሕድ ከበደኖ ፍጅት እስከ ከጉራፈርዳና የቤን ሻንጉል መፈናቀሎች እንዳሉ ሆነው፡፡ በመሃሉ የእስታቲስትክስ ዋና መሥሪያ ቤት የአማራ ሕዝብ ቁጥር የመቀነሱ ዘገባ (ሪፖርት) በዚያ መሃል የተከሰተ ነበር። ሴቶች እንዳይወልዱ ከማምከን እስከ ጄኖሳይድ የሚደርሱ ሰቅጣጭ ወንጀሎች ድረስ ይሄዳሉ ክሶቹ። ወደ ኋሊት ተኬዶ እስከ ስመጥፉው የሕወሓት 1968ቱ ማኒፈስቶ ድረሰ መመለስ ይቻላል ይሆናል። እንዲያውም ትንሽ የኋሊት እንድርድሮሹን እስከ የ1969ኙ የዋለልኝ መኮነን “የብሔረሰቦች ጉዳይ” አርቲክል ድረስም መሄድም ይቻል ይሆናል። እነዚህ ሁለት ሰነዶች አማራን እንደ ጠላት የፈረጁና ለተከተለው ጥፋት ያመቻቹ ዋቢ መጣቀሻዎች ተብለው የሚገመቱት ናቸውና፣ በነገዱ ብሔረተኞች። የወልቃይት-ጠገዴ አማራ ማንነት ኮሚቴ አባላት በቁጥጥር ሥር መዋልን ተከትሎ የተቀጣጠለው የጎንደርና የጎጃም ገበሬና የከተማ ሕዝብ መነሳሳት ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ ኹነት ነው በተለይም ከኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ወደ ትግራይ መወሰድ በኋላ መፈክሩ አማራ ተደራጅ ሳይሆን ተነስ፣ ተባበር፣ መክት ነው! እንደ ወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ የአማራ ማንነት ተጋድሎና ብሔረተኛነትን ያጦዘው ጉዳይ አልነበረም ቢባል ምንም ማጋነን የለበትም። ዛሬ አማራ በነገዱ ይደራጅ ወይስ?… የሚለው ጥያቄ የአማራ ተወላጆችንም ሆነ ቀሪውን ኢትዮጵያዊ አያሳስብም። መነጋገሪያ ርእስም አይደለም፣ ብዙዎቹ ዘንድ። ምክንያቱም አማራ ካንድ ድርጅት በላይ ተደራጅቶ ይገኛል። አዲስ የተቆጡ አማራ ወጣቶች (Angry Amhara Young Men) አመራር የተቆናጠጡበት ከግማሽ ደርዘን ያላነሱ የአማራ ድርጅቶች ተመስርተዋልና። ከፊሎቹም ሰሞኑን በአሜሪካ እየተዋሃዱ ይገኛሉ።
በ1983ቱ አለመወከልና በ 2009 “አለመወከል” ቅሬታ መሃል በአማራ አደረጃጀት መሠረታዊ ለውጥ ተካሄዶበታል። በቅርጽም በይዘትም። በአቅጣጫውም፣ ገላጭ ባሕርያቶቹም። አማራ አለ ወይም የለም የሚለው ክርክርም ሆነ በማንነቱ ይደራጅ ወይስ አይደራጅ እሰጥ አገባም ካበቃ ሰንበትበት ብሏል። አማራ በምን መልኩ ተደራጅቶ ነው ከአጥቂዎች ራሱን መጀመሪያ መከላከል ብሎም በስሙ የተደራጁትን እንዴት ተግባራቸውን አቀናጅተውና አስተባብረው እንዲያውም ተዋህደው ነገዱን በወያኔ ከተደገሰለት ጥፋት የማዳኑን ተግባር የቅድሚያ ቅድሚያቸው አድርገው መንቀሳቀሱን የሚያያዙት? የወቅቱ ጥያቄ አማራ አለ? የለም? የሚልም ወይም ይደራጅ? አይደራጅ? ሳይሆን የተቀጣጠለው የአማራ ተቃውሞና ተጋድሎ አቅጣጫው ወዴት ነው? በሃገሪቷ የነጻነት ትግል ላይም ምን ዓይነት ተፅዕኖ ያሳርፋል። አልፎ ተርፎ በኢትዮጵያ የወደፊት እጣ ፋንታ ላይ ምን ዓይነት እንደምታ ይኖረዋል? እየሆነ መምጣቱ ግልጽ ነው።
የእነዚያ እድገቶችና ክሶች ትክክለኛነትንም ማጣራትም ሆነ መመርመር ከዚች አጭር መጣጥፍ ማቀፍና አቅም ውጭ ነው። የአማራ ብሔረተኛነት እንቅስቃሴን ውልደት፣ እድገትና ውጣ ውረዶቹን ቃኝተን እንቅስቃሴው በአሁኑ ወቅት ያለበትን ደረጃ በዚህ መጣጣፍ በሰፊው ለመተንተን መሞከር አስቸጋሪ ይሆናል፣ እዚህ የአማራ “ብሔረተኛነት” የደረሰበትን እድገት ደረጃ ተመልክቶ፣ በሃገሪቷ ለውጥ ብሎም በሕልውናዋ ላይ የሚያሳርፈውን ተጽእኖ፣ ጫናና የሚጫወተውን ሚና መቃኘቱ አስፈላጊ ነው። በተለይም በምንገኝበት ባሁኑ በአተረማማሹ የማንነት ፖለቲካ ምስቅልቅል ውስጥ ሆነን።
የአማራ “ብሔረተኛነት” እና የተደቀኑበት ተግዳሮቶች
በአሰባሳቢ ማንነት መጽሓፌ የኦሮሞ ብሔረተኛነት ራሱን በቻለ ምዕራፍ (የኦሮሞ ብሔረተኛነት፣ የማንነት ፖለቲካና ተፈታታኝ ተግዳሮቶቹ) እንዲፍታታ የተመረጠበት ምክንያት ብዙ አያመራምርም። የኦሮሞ ብሔርተኞች ጥያቄ ኢትዮጵያ አንደ አገር የመቀጠል ወይም የመበታተን ወሳኝ ሚና አለው ከሚለው እሳቤ በመነሳት ነው። በተባለው ምዕራፍ እንደተደረገው አዲሱን የአማራ ማንነት ታጋድሎና ብሔረተኛነት ከኦሮሞ ማንነት ተጋድሎና ብሔረተኛነት ጋር ማነጻጸሩ ማስኬዱ አጠያያቂ ነው። በምዕራፉ የተፍታቱት የኦሮሞ ብሔረተኛነት እድገት፣ አነሳስ፣ የወል የሰቆቃ ታሪክ፣ የኦሮሙማ አይድዮሎጂ ቀረጻና የታጋረጠበት ተግዳሮቶቹ ከሥር መሠረቱ ይለያሉ። ዛሬ በኢትዮጵያ ከሚታዩት የብሔረሰብ (ነገድ) ብሔረተኛነት ጋርም ቢሆን ማወዳደሩም ሆነ ማነጻጸሩ አግባብነቱም አጠያያቂ ነው። እንዲያውም በሌሎች ሃገራት ከተመለከትናቸው ከየትኛው ሃገር ብሔረተኛ እንቅስቃሴ የሚመሳሰልበት ገላጭ ባሕሪያት በቀላሉ ማግኘት አይታሰብም። ማንኛውም የሃገሪቷ አስተዳደር ያልተማከለ (Decentralize) የማድረጉ ጥረት በጥርጣሬ ዓይን በመመልከቱ ረገድ የአማራ ብሔረተኛነት ከቀድሞ ዩጎስላቪያው የሰርብ ሕዝብ ብሔረተኛነት ጋር የሚጋራው ገጽታ አለው። ሰርቦች ከቀድሞ ዩጎስላቪያ ሕዝብ 40% በመሆናቸው በጀርመንኛው ሊተረቸር ስታቲስ-ቮልክ (Staatsvolk) ወይም የሃገሬው ዋልታ ሕዝብ ይሰኙ ነበር። እርግጥ የቁጥር አብላጫ የሆነው ኦሮሞ ሳይሆን የኢትዮጵያ የሀገር-መንግሥት መሠረተ-ሕዝብ አማራ ነው ሊባል የሚቻል ይመስለኛል።
አማራው በዋናነት የተጋረጠበት ተግዳሮት ከኢትዮጵያዊነትና ከኢትዮጵያ ማንነት ጋር ያለው ቁርኝት ነው። የአማራ ብሔረተኛነት ከኦሮሞም ሆነ ከሌላ ሃገር ብሔረተኝነቶች ጋር የማይመሳሰልበት ገላጭ ባሕሪያትን ደግሞ መመልከት ተገቢ ነው። ከዚያ በፊት ራሱ የአማራ “ብሔረተኛነት” የብሔረተኛነት ፍቺ፣ ትርጉምና መመዘኛዎች ያሟላል ወይ መባሉ ሊያስፈልግ ነው። ለምን ቢባል? የአማራ ማንነት ትግልና ተጋድሎ ከራስ መንግሥት ወይም የራስ ትድድር መመሥረት ጋር የተቆራኘ ስሜት፣ እንቅስቃሴና ኢድዮሎጂ ባለቤት አለመሆኑን በእሳቤ ከወሰድን። አንዱና ዋነኛው የብሔርተኝነት መገለጫ የአንድ ማኀበረ ፖለቲካዊ ስብስብ በአንድ የራሱ መንግሥት ሥር ወይም የራሱ ራስ-ገዝ አሃድ ወይም ፌደራላዊ አሃድ መጠቃለል ከስሜት አልፎ ወደ ፖለቲካዊ አይድዮሎጂ የተቀየረ ፍላጎትና ምኞት መላበሱ ሂደት ነው። በኦሮሞ ብሔረተኞች ዘንድ የተመለከትነው “ኦሮሙማ” ዓይነቱ ርዮተ ዓለም መሰል አማራነት የሚሰኝ አይድዮሎጂ መመልከት እስካሁን አልቻልንም። ከኢትዮጵያዊነት በስተቀር የምትል ሓረግ መጨመር ሊያስፈልግ ነው።
አሁን ባለበት ሰዓት አማራ አለ ወይስ የለም ሙግት አብቅቶ፣ አማራ ይደራጅ ወይስ አይደራጅም ሙግትም እልባት አግኝቶ፣ ብዙዎቹ አማሮች የመደራጀቱን አስፈላጊነት ከተዋሃዷቸው በኋላም ቢሆን የአማራን ስሜት፣ እንቃስቃሴ እንደ ብሔረተኛ እንቅስቅሴ ራሱን የሚመለከትበት መነጸር ከሌላው ይለያል። የሞረሹ አቶ ተክለ የሻው አንድ የአሮሞ ነጻነት ግንበር ተወካይ Welcome to the club ባለው ጊዜ እኛ የተደራጀነው እናንተ ለተራጃችሁበት ዓላማ አይደለም ብዬ መለስኩለት ነበር ያለው ። ሁሉም አማራ በማንነት ወገንተኛነቱ የተደራጀው የደረሰበትን ጥቃት ለመመከት ነው የምትለዋን ልዩነት ሊያሰምርበትና አጽንኦት ለመስጠት ይሻል።
የአማራ ማንነትና ለማንነቱ ያቀጣጠለው ተጋድሎ ጥንካሬው እሱ ነው። ተግዳሮቱም እሱ ነው። ከአንድነት ኃይሎች ጋር የፈጠረው አለመግባባት ምንጩ ይኸው አስቸጋሪ ትስስር ነው ቢባል ምንም ማጋነን የለበትም። አብዛኛው የአማራ ኤሊት በኢትዮጵያዊነቱ እስከ ተደራጀ ድረስ እኔ አማራ በማንነቱ ቢደራጅ ግድ የለኝም ማለቱ ለእነዚህ በአማራ ድርጅት ለታቀፉ ወጣት አደራጆች ተግባር ቀላል አይሆንም። አልሆነምም።
ብሔርተኝነት አንድ ስብስብ የራሴ ናቸው የሚላቸውን አባላት በአንድ መንግሥት አሃድ ወይም (ትድድር) ሥር ለማጠቃለል ያለው ምኞት ተግባራዊ የሚያደርግበት ስሜት፣ እንቅስቃሴና አይድዮሎጂ ነው ብለን ከተቀበለን ዘንዳ ከመንግሥት ማዕቀፍ ውጭ ሊታሰብ የሚችል ብሔርተኛነት እምብዛም አያጋጥምም።
የራስ ስብስብ ጠቅልል መንግሥት እንደ መዳረሻ ግብ ያላደረገ እንቃስቃሴን እንደ አንድ ብሔረተኛ እንቅስቃሴ መመልከቱ ያስኬድ እንደ ሆነ ራሱን የቻለ የቲዮሪ ጉዳይ ነው። አንድ ጉዳይ ግን ግልጽ ነው። በአማራው ወገንተኛነት ላይ የተመሰረተ ስሜትና እንቅስቃሴ ብንመለከትም ቅሉ የራሱን መንግሥት የማቋቋም ትልምና ዓላማ አንግቦ የተነሳ የአማራ ኃይል በቦታው የለም። የአማራ ብሔረተኛ እንቅስቃሴ የራሱን መንግሥት የመመሥረት ዓላማ የለውም። አንዳንዶች የአማራ የራሱን መንግሥት ምስረታ እንደ አንድ አማራጭ ዕቅድ “Plan B” አድርገው ይዘዋል የሚሉ ወገኖች መኖራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ። አማራ ከኢትዮጵያዊ ማንነትና ብሔረተኛነት ጋር ያለው ቁርኝት አሁንም በቦታው እንዳለ ነው። ይህ ነው የአማራ ትግልንም ሆነ ብሔረተኛነት ከቀሪዎቹ ኢትዮጵያውያን ጋር ያለውን የትግል አጋርነት ውስብሰብ ያደረገው። ወደ ቲዮሪ ብዙ ሳንዘፈቅ በመሬት ላይ ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ በግምት ብንወስድ እንኳን። እርግጥ ወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ የማንነት እውቂያ ጥያቄ ቢሆንም ቅሉ ያንድ በሌላ ክልል የተከለለ መሬቴ ወደ ራሴ ክልል እንደ ገና ተመልሶ ይካለልልኝ ባሕርዩና ገጽታው ነው ጎልቶ የሚታየው። ድንበራችን ተከዜ ነው የምትለው መፈክርም ድንበር አካላይ ይዘት አላት። ስለዚህ የእኛ መሬት ቁራጭ አካል የነበረው መሬት ይመለሰልን ነው ጥያቄው። ፈረንጆች irredentist የሚሉት መሬት አስመላሽ እንቅስቃሴ ነው። One who advocates the recovery of territory culturally or historically related to one’s nation but now subject to a foreign state ይላል irredentis ፍቺው። እሱም ቢሆን ለሰፊ የፖለቲካ ዓላማ መቀስቀሻ መሣሪያነቱ ነው የሚጎላው። ማንኛውም ሃገሪቷን ያላማከለ የአስተዳደር አወቀቃቀር የመጠርጠር ዝንባሌው ከቀድሞ ዩግስላቪያ ከሰርብ ብሔረተኛነት ጋርም ያመሳስሏል። ልክ ሰርቦች እንደሞከሩት ግዛታዊ አይደፈርነትና ሙሉነት (territorial integrity) አማራው በወልቃይት-ጠገዴ ወደ አማራ ክልል ተመልሶ እንደገና ይካለልልኝ የሚል ጥያቄ መልክ ተላብሷል።
ከላይ እንደተመለከትነው በአሮሞ ብሔረተኞች “Welcome to the Club” እንኳን ደህና መጡ! አቀባባልም ሆነ ስለ አማራ ብሔረተኛነት ዲሞክራሲያዊነት የተቸራቸውም ውዳሴም ሆነ የምስክር ወረቀት በጸጋ የተቀበሉ አይመስሉም። አንዱ የአማራ ብሔረተኛ ድርጅት እንዲያውም “አማራ የሚደራጀው እንደ ኦነግና ወያኔ ዘረኛ ለመሆን አይደለም። አማራ የሚደራጀው የተጋረጠበትን አደጋ ተቋቁሞ በሰፊው ያባቶቹ አገር የአገሩ ባለቤት ሆኖ ለመኖር የሚያስችለውን አቅም ለመፍጠር ነው። አማራ የሚደራጀው ለዚህ ቅዱስ ተግባር ነው!” ይላል። ይህ ዓይነቱ የራስን አደረጃጀት ልዩ መሆን ለይቶ ማመስገን ሥር የሰደደውን አለመተማመን የበለጠ ያጎላ እንደሆነ ነው እንጂ እምነትንና የትግል አጋርነትን አያጸናም መቼም። ብሔረተኛነትን ላይ “ቅድስና” መደረቡ ደግሞ ተጨማሪ ጥያቄን ይጭራል። “ቅዱስ” ብሔረተኛነት ካለ የግድ ተቃራኒው ሊኖር ነው መባሉ አይቀሬ ነው። ”ያልተቀደሰ ብሔረተኛነት” ማለቴ ነው። የአማራ ብሔረተኛነት መደረሻው ግቡ ኢትዮጵያዊነት ነው ይሉናል። ሌላው ብሔረሰብ ብሔረተኛነትስ መዳረሻ ግቡ ምን ሊባል ነው? የአማራ ብሔረተኛነት ዲሞራሲያዊ እየሆነ ነው እየተባለም ነው። እሱም በራሱ አጠያያቂ ነው። ልክ “ቅዱስ” ብሔረተኛነት ብርቅ እንደሆነ “ዲሞክራሲያዊ” ብሔረተኛነት እምብዛም አያጋጥምም። አልፎ ተርፎ ብሔረተኛነት ራሱ ዲሞራሲያዊ ሊሆን ይችላልን? መባሉንም ያስከትላል። “አማራነት ማንነታችን ኢትዮጵያዊነት ዜግነታችን ነው” የሚለው መፈክር ለሁሉም 80 በላይ ለሆኑት የሃገሪቷ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እኩል የሚመለከት መፈክር መሆን አለበት ወይም ይገባዋል። አማራ ብቻ አይደለም በነገድ ማንነቱ ወገንተኛ የሚሆነው። መቼም ሁሉም በዜግነቱ “ኢትዮጵያዊ” ነኝ ባይ ነው። ምክንያቱ ዜግነት ግለሰብ ዜጋው ከሃገረ መንግሥቱ (State) ጋር ያለው ቁርኝት ነው እስከተባለ ድረስ።
የአማራነትና ኢትዮጵያዊነት ቁርኝት የአማራ “ብሔረተኛነትን” ወሰብሰብ አድርጎታል። አሁንም ከኢትዮጵያዊነት ጋር ያለው ቁርኝት የማይቆራረጠው ኢትዮጵያዊነት ዋልታና ማገር፣ ማግና ድር፣ ደምና ስጋ ስለሆነ ነው። እንደማይነጣጠሉ ለመግለጽ። “…. አማራና ኢትዮጵያዊነትን እለያያለሁ ማለት በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ዓይነት አብ፣ ወልድ መንፈስ ቅዱስን እንለይ እንደ ማለት ነው“ ይላሉ አቶ ተክሌ የሻው። ዶር ተክሉ አባተ ደግሞ ሁለቱን መለያየት መመኮሩ ” ጸጉር ለመሰንጠቅ” መሞከር ያህል ነው ብለው ያምናሉ። የአማራ ማንነት ትግል ተግዳሮት የደቀነው ይህ ኢትዮጵያዊነቱና ማንነቱን መለያየት አለመቻሉ ነው። ጉዳዩ እንደ የኢትጵያዊነት ባለ አደራና የበላይ ጥበቃ ብቻ ሳይሆን ከሌላው ኢትዮጵያዊ ይበልጥ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ መመጻደቅ ተደርጎ በሌሎች ኢትዮጵያውያን መታየቱ ነው። ይህ ደግሞ በሌላው ኢትዮጵያዊ አማሮችን ኢትዮጵያዊነትን የራሳችሁ ብቻ አደረጋችሁት ተብሎ የሚሰማው ቅሬታ አለመተማመኑና በጥርጣሬ ዓይን የመተያየቱ ምንጭ ነው። ይህ ደግሞ አማራ በነገዱ ከተደራጀ በኋላም የሚከተለው መከራ ነው። እርግማን መባሉ ያስኬድ ይሆን? እነዚህ አባባሎች አማራ ኢትዮጵያዊነትን ከሌላው ጋር “ለመጋራት” ፈቃዳኝነት እንደሌለው ያስመስልበታል። ምንም እንኳን አማራ የሚደራጀው በራሱ ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመመከት ነው መባሉ ትክክል ብቻ ሳይሆን ሁሉም ዛሬ የሚቀበለው ጉዳይ ቢሆንም ቅሉ ከሌሎች ብሔረሰብ ልሂቃን ጋር የነበረው አለመጣጣም አሁንም እንዳለ ነው። አማራ በኢትዮጵያዊነት ሽፋን ለተቀዳጀው የበላይነት ማስከበርያና ማዝለቂያ ነው እያሉ በውስጠ ታዋቂነት ጣታቸውን የሚቀስሩት ወደ አማራው ብሔረሰብ ነበር። አሁንም ይህንን አካሄድ ይህንኑ አለመተማመን ያጠናክር እንደሆነ ነው እንጂ አያለዝበውም። ዞሮ ዞሮ ከመጀመሪያው ክስና ጣት መቀሳሰር ጋር ይገናኝና ወደ መነሻ ነጥቡ ጋር ይመለሳል። የዚህ ሁሉ ጥቃት ዒላማ ያስደረገኝ ያው ከኢትዮጵያዊነት ጋር ያለኝ ቁርኝት ነው ከተባለው ጋር ግጥም ይላል። ለሌላው ይህ ኢትዮጵያዊነትን የእኔ የብቻዬ ንብረት ነው፣ የበላይ አደራ ጠባቂውም እኔው ነኝ ዓይነት መመጻደቅ ተደርጎ ይታያል።
ትልቁ የአማራ ብሔረተኛነት ተግዳሮት ከኢትዮጵያዊ ብሔረተኛነትና ማንነት ጋር የነበረውና ያለው እትብትና ትስስር መበጠስ ወይም አለመበጠስ ሁለት ልብነት ነው ቢባል ምንም ማጋነን የለበትም። አጠቃላይ ጥንካሬው እንደ የተጠበቀ ሆኖ ለውድቀት ሊዳርግ የሚችል ተጋላጭ ስስ ብልትና የአቺለስ ተረከዝ (Achilles’ heel) መሆኑ ነው። ጥንካሬውም እሱ ነው፣ ስስ ብልቱም እሱ ነው ማለት የሚቻል የመስለኛል። የሁለቱ ዲያሌክቲካዊ (ተቃርኗዊ ዝምድና?) ትስስር የዳይሌማው ወይም የመንታ ልብነት ምንጭ ነው። አማራው ከኢትዮጵያዊነት ጋር ያለው ያልተበጠሰ ቁርኝትና ትስስር ጋር መቆራረጡ ወይም መፋታቱ (disengage) አይታሰብም፡፡ ዛሬ ሁሉን እያተረማመሰ የሚገኘው የማንነት ፖለቲካ የአማራ ተወላጆችን ይበልጡኑ ድብልቅልቃቸውን ያወጣል፣ የማንነታቸውን ትግልም ይበልጡኑ ያወሳስበዋል። አወሳስቦት፣ እያናቆረን ነው። የአማራ ኤሊቶችን ብቻ ሳይሆን ውሎ-ገብ ዜጎችንም ጭምር በተመሰቃቀለው የማንነት ፖለቲካ ይበልጥ እያተተረማመሱ ናቸው።
ከ1983 ወዲህ ከላይ እንደተመለከትነው አማራ ልክ እንደ ሌላው በነገዱ እንዲደራጅ የተፈለገበት ምክንያት ነበር። ከኢሕአፓ የተገነጠለው የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕዲን) ወደ ብሔረ አማራ ዲሞራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) እንዲለወጠ የተደረገበት ምክንያት አንድ ነው። ማንንም እሰከ ምርጫ 97 ድረስ በማንነት ወገንተኛነት ካልሆነ በስተቀር በሃገራዊ ማንነቱ ወይም በሕብረ ብሔራዊነትና በኢትዮጵያዊነት ዙሪያ እንዳይደራጅ የተፈለገበትም ምክንያትም ያው ነው። በግለሰብ ካርድ መታወቂያ ላይም የጎሳ (የዘር?) ማንነት እንዲመዘገብ የተፈለገበት የፖሊሲ መመሪያም ያው ነው። ሁሉም በዘሩ ወይም በነገዱ እንጂ አደረጃጀቱ የሕብረብሔር ቅርጽም ሆነ ይዘት እንዲኖረው አልተፈለገም። ባጭሩ መመሪያው በሥልጣን ያለው ፖለቲካዊ ኃይል ንድፍና እቅድ ሆኖ በመተግበር ላይ ስለሆነም ነው።
ይህ ሁሉ ድብልቅልቅ የወያኔ ተንኮልና ሴራ ውጤት ብቻ ነው ማለት የሚያስኬድ አይመስለኝም። በአማራ ማንነት ትግልና ብሔረተኛነት ተግዳሮት የደቀነው ይህ ኢትዮጵያዊነቱና ማንነቱን የመለየቱ ችግር ብቻም አይደለም። ይህ በተራው ካንድነት ኃይሎች ጋርም በተቃራኒነት እንዲቆም አድርጎታል። ይህ ዛሬ በግልጽ እየወጣ ነው። ከኢትዮጵያዊነት ጋር ባይቆራረጥም ቅሉ ካንድነት ሃይሉ ጋር እየተራራቀ መጥቷል። ይህን በተራው በርካታ ያለመተማመኑን ንብብሮሽን እያገዘፈ ይገኛል። ይህ ሁሉ ተደምሮ እያራራቃቸው እንደሆነ ነው እንጂ የተቀራረቡና የትግል አንድነታቸው እየጸና አይደለም። ድሮ ያንድነት ኃይል የአማራ ማንነት ማሽሞንሞኛ አባባል ነው ወይ ብዬ እኔ ራሴ የጠየቅኩበትን ጊዜ አስታውሳለሁ። ዛሬ በመሬት ላይ የምንመለከተውን እውነታ እንደ ገና እንድፈትሽ እያስገደደኝ ነው። “አማራውን ከሌሎች ብሄር ብሄረሰቦች ልሂቃን እና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር ማጋጨት የታክቲክም የስትራቴጂም ጥቅም የለውም” (ፈቃደ ሸዋቀና) ቢባልም አማራ በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከእነዚህ ጋር እየተጋጨ ነው።
በምርጫውና ፊያስኮው ሳቢያና በማግሥቱ በቅንጅት ድርጅቶችና መሪዎቻቸው መካከል የተከሰቱ አይነቱ አለመግባባቶቹና የክስ ጣት መቀሳሰሩ እንደ ገና አገርሽቶበታል። ፍርስራሻቸው የወጣ የቀድሞ ትብብሮችና ሕብረት ተሞክሮዎች ትምህርት የተቀሰመባቸው አይመስልም።
ለጥርጣሬው ምክንያቶችን መፈተሽ ተገቢ ነው። ሞረሽ ወገኔ የአማራ አርበኞች ግንቦት ሰባት ድርጅትን በማሰመልከት “የድርጅቱን እንቅስቃሴ ከጅምሩ እስካሁን ድረስ በሚገባ ተከታትለናል። በቅርቡ በአንድ የአማራ ድርጅት የወጣውና በክትትላችን ያገኘነው ውጤት አርበኞች ግንቦት ሰባት በራሱ ማንነት ላይ ያልቆመ፣ ማንነቱን ከሌሎች ጋር በሚፈጥረው ጥምረት፣ ውሕደት፣ ቅንጅት ወዘተ ለማሳደግ የሚጥር፣ ተፈጠረ የሚባለው ጥምረት የት እንደ ደረሰ ሳይታወቅና የመጀመሪያው ጥምረት ፊርማ ሳይደርቅ፣ ሌሎች ጥምረቶች የሚፈሉበት መሆኑን ታዝበናል። ከሁሉም በላይ የሚገርመው ጥምረት የሚመሠረተው አማራውን በዐውራ ጠላትነት ከፈረጁ ብሔርተኛ ድርጅቶች ጋር መሆኑ እርሱም በተዘዋዋሪ መንገድ የአማራው ጠላት መሆኑን እያሳየ መጥቷል” ይላል። ከዚህ አንጻር ጉዳዩ እየከረረ መጥቶ ወደ መፈራረጁ ደረጃ ተደርሷል ማለት ነው። ቀላል ክስ አይደለም።
ባንጻሩ በአርበኞች ግንቦት 7 አመራር እናንተ የአንድነት ኃይሎች የእኛዎች ናቸሁ (የት ትሄዱብናላችሁ) ብለን በቅድሚያ ካንድነት ጎራ ያፈነገጡትን ወደ አንድነት በረት እንመልስ ብለን ነው ከእነሱ መደራደሩን ያስቀደምነው መባሉ እንደ ሽንገላ ቢወሰድ አይገርምም። በተግባር የታየውም ይህው ነው። የት ትሄዱብናላችሁ የተባሉት የአንድነት ኃይሎች በእጅ የሉም ዛሬ። አሁን እነሱን ፍለጋ ሊኬድ ነው። “የእንትና ብሄር አልተወከለም አትበሉን ይህ ፓርላማ አይደለም” መባሉም እንዲሁ አለመተማመኑን ያጸና እንደሆነ እንጂ አያቀራርብም። የአማራ ብሔረተኞች ከአርበኞች ግንቦት 7 ጋር ያላቸው ቅራኔ ይህ ብቻ አይደለም። የወልቃይት-ጠገዴ ማንነት እውቂያ ጉዳይ፣ በሰሜን (ጎንደርና ጎጃም) የተቀጣጠለው የመሣሪያ ተጋድሎ ባለቤትነትና በስሙ አለመጥራት በግንባር ቀደም የሚጠቀሱ ናቸው። ጣት መቀሳሰሩን አቁመን፣ የኋላ ታሪኮችም በቅጡ ፈትሸን ለዚህ ችግር መፍትሔ በአስቸኳይ መፈለግ አለበት።
3 ማጠቃለያ
ከላይ የተመለለከትናቸው ተግዳሮቶቹ ከኢትዮጵያዊነት ጋር ተያያዥነት ያላቸው ናቸው። በአማራ ብሔረተኛነት ላይ ሌሎች ተጨማሪ ግን ቀላል የማይባሉ ተግዳሮቶች ተጋርጦበታል። የወያኔ የቆየ ሤራ፣ ቂምና እቅድ ማለቴ ብቻም አይደለም። የአማራ ብሔረተኛ እንቅስቃሴ በክልሉ በውስጡ ባቀፋቸው እንደ አማራ የሚቆጥራቸው አገው፣ ቅማናት፣ ወይጦ፣ አርጎባ ፣ሺንሻ ያላቸው ተሳትፎ፣ በድርጅቶች መሃል ያለው ሽኩቻ፣ የአመራሮቹ ልምድ ማነስ፣ ወዘተ እንደ ተግዳሮት በግምት አልተወሰዱም። በጸረ አማራነት ከመደቧቸው ድርጅቶች ጋር ያላቸው ትስስር ይወዛገባሉ። ባንድነት ኃይሉ መሃል ያለ አለ መተማመን፣ የብሔረሰቦቹ ኤሊቶች ብቻ ሳይሆን በአንድነት ኃይሎች መካከል መካሰስ፣ መሸነጋገል ዛሬም እንዳለ ነው።
የሁሉት ታላላቅ ነገዶች (አማራ ብሔረተኞች ኦሮምኛ የተሰኘውን ጎሳ ቃል ላለመጠቀም የሚወስዱትን ቃል እንጠቅምና) ማቀራረብ የሚችል መግባባት ፈጣሪ ድርጀት ወይም መሪ ማስፈለጉ የማይታበል ሃቅ ነው። ምክንያቱም ዶር መረራ ጉዲና ብዙ ጊዜ የሚያነሷቸው የሦስቱ ብሔረሰቦች ኤሊቶች ወደ መሃል የማገናኘቱ ከባድ ኃላፊነትና አደራ እስካሁን ሊወጣ የቻለ ግለሰብም ሆነ ፖለቲካዊ ኃይል አይታይም። ደጉ ዜና ወያኔና አንዳንድ የኦሮሞ ድርጅቶች ወደ ኢትዮጵያዊነት የማምራት አዠማሚያ እያሳዩ ነው። ባንጻሩ የአማራ ወጣቶች በብዛት ወደ ነገድ አደረጃጀት እየነጎዱ ነው። ምናልባት በመሃል በመንገድ ከተገናኙ መልካም ነው። የተራራቁ ጫፎችን መሃል ላይ እንዲገናኙ ማድረግ ካልተቻለ ግን ተደጋግሞ የሚወሳው የወያኔ ኢሕዴአግ የሥልጣን ዕድሜ ማራዘሙ አይቀሬ ነው የሃገሪቷ እጣ ፋንታ ጉዳይ ይበልጥ ሊያሳስብ ነው ማለት ነው።
ወያኔ ኢሕዴአግ አደርጋለሁ የሚለው “ጥልቅ ተሃድሶ” ፣ የሕገ መንግሥት ማሻሻል፣ ከተቃዋሚዎች ጋር መነጋገር ፣ የሃይማኖት ድርጅቶች የእርቅ ሰላም የማውረዱ ሚና ወዘተ ሁሉ በመሃል የማገናኘቱ በጎ እርምጃዎች ተደርገው ሊታዩ ይገባል።
የ “ቆም ብለን እናስብ!” እና “ሰከን በል” ጥሪዎች ከሁሉም አቅጣጫ ቢዥጎደጎዱም በመጯጯህ ጫጫታ እየተዋጡ ናቸው። ቆም ብሎ ማሰብ አልተቻለም። ሁላችን ቆም ብለን እናስብ! በመጨረሻ ሁሉ ሰክኖ የትግል ስልቶቹና ሥሌቶቹን መርምሮ እኩልነትን ተቀብሎ፣ በመሃል ተገናኝተው፣ መሸነጋገል፣ጥርጣሬና ፍራቻ አስወግደው ባንዲት አገር በኢትዮጵያዊነት አስተሳሳሪ አቃፊ-ደጋፊ ሃገራዊ ሽርክና ለመጀመር ያለንን ቁርጠኝነት አንዱ ማሳያው ቆም ብሎ መነጋገርና መግባባት ነው፡፡
በበርካታ እርስ በርስ ጦርነቶች በበጣጠቋቸው ሃገራት እንደሚንመለከተው ማንም በማንም ላይ በጦር ሜዳ በላይነትም ሆነ የማያዳግም ድል ቢቀናው እንኳን የማታ የማታ ማሳረጊያው በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ ላይ የተደረሰ ተኩስ አቁምና የሰላም ስምምነት ነው። በዚያ ላይ አንዱ ወገን በተፋላሚው ላይ የተወሰነ ነጥቦች በደም ካስመዘገበ በኋላ መሆኑንም አሁንም አልሳትኩም። እርግጥ ይህ ሁኔታ በኃይል ሚዛን መለወጡ ነው አንዱ ተፋላሚ በፊት አሻፈረኝ የሚለውን እውነታ በመቀበል የአቋም መንፏቀቅ አስፈላጊነትና አስገዳጅነት የሚመነጨውም ከእዚህ ነው። ይህንንም አልሳትኩም።
አማራን ከጥቃት ለመከላከል ብቻ ሳይሆን “አማራው የራሱን ሕልውና አስከብሮ ከዚያም የኢትዮጵያዊነቱን ግዴታ ከሌሎች ጎሣዎች ጋር በእኩልነት እንዲወጣ ማድረግ የመላው አማራ ህዝብ ድርጅት ተልዕኮ ነው” ነበር ፕሮፌሰር አሥራት በባህርዳሩ መአሕድ መስራች ጉባኤ ላይ ያሉት። ደግማዊ መአሕድም ሆነ ሌሎች የአማራ ድርጅቶች ከዚህ የተለየ ተልዕኮ ይኖራቸዋል ብዬ አልገምትም። የሰሞኑ ተከታታይ የአማራ አቀፍና ሃገር አቀፍ ኃይሎች፣ የኢትዮጵያ አንድነት ኃይሎች ምክክር ጉባኤ ዓይነቶቹ ምናልባት ለዚህ መተማመን እርሾ መፍጠር ቀዳሚ ሥራ ሊይዝ ይገባል። “ካልደፈረሰ፣ አይጠራም” በሚለው ብሂል ድፍርስርሱን ባወጣ ማግሥት ለመልካም እድል አጋጣሚ ሊፈጠር ነው ከተባለም ሁሉ ሰከን ብሎ በምር መነጋገር ይጀመር! የሰሞኖቹ የዋሽንግተን ጉባኤዎችና ስብስባዎች መልካም አጋጣሚዎች ናቸው። ሌሎች መወያያ መድረኮችም ውይይቶችን ያስተናግዱ። ሰሞኑን ኢሳት በእንወያይ ፕሮግራሙ በአማራ ወጣቶች መካከል እንዳስተናገደው ማለቴ ነው ፡፡የሺ ማይል ጉዞ ባንድ እርምጃ ነው የሚጀመረው የሚሉት ቻይናውያን ናቸውን? እኛም ረዥሙን መንገድ በቀላሉ እርምጃዎች እንያያዘው!!
የኢትዮጵያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ብቻ 11,700 በላይ ዜጎችን ማሰሩን አስታወቀ
(አዲስ ሚዲያ)ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራ እና በደቡብ ክልል ኮንሶ የነበረውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በተፈጠረው ህዝባዊ ቁጣ ለማረጋጋት በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ በሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ን ተከትሎ 11,607 ዜጎች መታሰራቸውን ገዥው መንግሥት አስታውቋል፡፡
ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ የመብት አራማጆች፣ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ገበሬዎች፣ ሴቶች እንዲሁም በርካታ ወጣቶች እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዕድሜ የገፉ አዛውንትም የታሰሩ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ውስጥ ብቻ መታሰራቸው ይፋ የተደረገው የታሳሪዎች ቁጥር ከዚህ ቀደም በህዝባዊ ተቃውሞው ወቅት በ10 ሺህዎች የሚገመቱ የታሰሩትን እንደማያካትት ተጠቁሟል፡፡
ገዥው መንግሥት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ህዝባዊ ተቃውሞውን ለማረጋጋት ቢሞክርም፤ አሁንም በተለይ በአማራ ክልል ሰሜን እና ደቡብ ጎንደር እንዲሁም ምዕራብ ጎጃም ተቃውሞ እና የመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጅ በተለይም ግድያ እና የአካል ማጉደል ርምጃዎች መቀጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በኦሮሚያም ክልል በተለይም ምዕራብ እና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና አርሲ አካባቢ ተቃውሞች እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡
በተለይ አዋጁን ተከትሎ የፀጥታ ኃይሎች በወንጀል የጠረጠሩት ሰው ላይ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣን መስጠቱ ቢታወቅም፤ ከተጠቀሰው የ11706 እስረኞች በስተቀር ስለተፈፀመው እርምጃና ስለተጎጂዎች የተሰጠ ዝርዝር ማብራሪያም ሆነ መረጃ የለም፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ የሰላማዊ ዜጎች እስር ቢኖርም፤ በአንዳንድ ቦታዎች አሁንም ተቃውሞች እንደቀጠሉ ናቸው
(አዲስ ሚዲያ) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓም ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በጅምላ እየታሰሩ ነው፡፡ በተለይ በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እስሩ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ሳምንት ከአዲስ አበባ በደቡብ ምዕራብ በቅርብ ርቀት የምትገኘው ሰበታ ከተማ ብቻ ከ አንድ ሺህ በላይ ተጠርጣሪ ናቸው ያላቸውን ነዋሪዎችን ማሰሩን ራሱ መንግሥት ያስታወቀ ሲሆን፤ በሌሎችም የኦሮሚያ እና አማራ ክልል ከተሞችና ወረዳዎችም በተመሳሳይ መልኩ እስሩ መቀጠሉን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በአማራ ክልል ሰሜን እና ጎንደር ዞን መንግሥት የነዋሪዎቹን ትጥቅ ለማስፈታት ወደ ወረዳዎች እና ገጠር ቀበሌዎች የፀጥታ ኃይሉን ቢያሰማራም ከህዝቡ የአፀፋ ርምጃ በመወሰዱ በርካታ ወታደሮችና ሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ተገድለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ህዝባዊ ተቃውሞው ከተጀመረበት ቀን አንስቶ የመንግሥት የፀረ አገዛዝና ጭቆና ተቃውሞ እንደቀጠለ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
በአፋር ክልልም እንዲሁ የሰላማዊ ዜጎች እስሩ የቀጠለ ሲሆን፤ ባለፈው ሳምንት ጥቅምት 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በአፋርኛ በማዜም የምትታወቀው ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌን ጨምሮ አስር ሰላማዊ ዜጎች በአሳይታ ከተማ መታሰራቸው ታውቋል፡፡
ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌ
በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ትግበራ ላይ መንግሥት እንደ ኢሳት፣ ኦ.ኤም.ኤን. የመሳሰሉ መገናኛ ብዙኃን መከታተልና መረጃ መለዋወ ላይ መመሪያው እገዳ ጥሏል፡፡ በተጨማሪ ያልተፈቀደ ሰልፍና የአደባባይ ስብሰባ፣ ለህዝብ አገልግሎት አለመስጠት፣ በትምህርትና በስፖርት ማዘውተሪያ አድማ ማድረግ በክልከላው ተካተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ትግበራባለመቀበል በድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ከቤት ያለመውጣት አድማ ማድረጋቸውን ቀጥለዋል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመውጣቱ አስቀድሞ በኢትዮጵያ የመንግሥትን በደልና ብልሹ አሰራር ለመቃወምና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቀድሞም ቢሆን ለዓመታት ፈፅሞ የተከለከሉ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለአንድ ዓመት ያህል ያለማቋረጥ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የቀጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማርገብ በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ የሆነ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማውጣት ኢንተርኔትን በተለይም ማኀበራዊ ሚዲያ፣ በውጭ ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ተዘጋጅተው ለህዝቡ አማራጭ የመረጃ ምንጭ በመሆን እያገለገሉ ያሉ እንደ ኢሳት፣ ኦ ኤም ኤን ያሉ መገናኛ ብዙኃን እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ሚዲያ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዳይሰራጩ ከማፈን በተጨማሪ ህዝቡም መረጃ መለዋወጥና መስማትም እንደሌለበት በአዋጁ መከልከሉ ይታወሳል፡፡
አዋጁን ተከትሎ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተለይ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ ክልል ኮንሶ ፣ ጋሞ ጎዳ ዞን፣ በአፋርና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል (ኦጋዴን) የተለያዩ ከተሞችና ወረዳዎች በመዘዋወር ድንገት ቤት ለቤት ፍተሻ በማድረግ የተለያዩ የወርቅ ጌጣጌጦችን፣ ገንዘብ፣ ተንቀሳቃሽ ስልክ ከመወስድ በተጨማሪ ጠርጥረንሃል ያሉትን ሰው ያለምንም ፍርድ ቤት ማዘዣ እየደበደቡ በመውሰድ ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሚያስሯቸው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ምክንያት ከወትሮ በተለየ መልኩ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢ ነዋሪው በፍርሃት ድባብ ውስጥ እንደሚገኙ በመጠቆም በማኀበራዊና ንግድ እንቅስቃሴዎች ላይም አለመረጋጋቶች እንደሚስተዋሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
መንግሥትበአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መሰረት አፈና እና ቁጥጥሩን አጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ዋነኞቹ የህዝባዊ ተቃውሞ አስተባባሪዎች መካከል የአማራ ተጋድሎና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች ከመንግሥት ርምጃ ጋር ተመጣጣኝ ሊሆን የሚችል አዳዲስ የትግል ስልቶችንም በቅርቡ ሊጀምሩ እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡ በተለይ በውጭ የሚኖሩ የመንግሥትን አገዛዝ የሚቃወሙ ኢትዮጵያውያን በስልጣን ላይ ካለው ገዥው ስርዓት ለውጥ በኋላ በኢትዮጵያ ሊመሰረት ስለሚገባው ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ትግበራ በቪዥን ኢትዮጵያ እና በኦሮሞ ማኀበረሰብዓለም አቀፍ የህግ ባለሙያዎች ማኀበር አስተባባሪነት ከወዲሁ በሰሜን አሜሪካ ዋሸንግተን ዲሲ እበእንግሊዝ ለንደን ምክክር መጀመራቸው ታውቋል፡፡