Tag Archives: Bekele Gerba

ፍርድ ቤት በባለስልጣናቱ ምስክርነት ጉዳይ ብይን መስጠት አልቻለም

ጌታቸው ሺፈራው

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት በጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ምስክርነት ጉዳይ ላይ ዛሬ ብይን እሰጣለሁ ባለው መሰረት ብይን መስጠት አልቻለም።

ታህሳስ 17 ቀን 2010 ዓ.ም. አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በጊዜ ጥበት ምክንያት ፍርድ ቤት ቀርበው መመስከር እንደማይችሉ በጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈት ቤት በኩል ለፍርድ ቤቱ በደብዳቤ ተገልፆአል። በዚሁ ቀን አቶ ለማ መገርሳን ጨምሮ በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ተከሳሾች መከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት መቅረብ ባለመቻላቸው ፍርድ ቤቱ በቀጠሮው መጨረሻ፣ ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ብይን እሰጣለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም ብይን ሳይሰጥ ቀርቷል። ታህሳስ 17 ቀን 2010 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ተከሳሾች አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ታስረው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ለችሎት ያመለከቱ ሲሆን ለኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ትዕዛዝ ስላልደረሳቸው በቀሪዎቹ ሁለት ቀናት ይቀርባሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር።

ትናንት ታህሳስ 18 ቀን 2010 ዓ.ም. በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ተከሳሾች ጠበቃ አብዱልጀባር ሁሴን በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱትን የኦሮምያ ባለስልጣናት በአካል አግኝተው ባነጋገሯቸው መሰረት ባለስልጣናቱ ለዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው ሊመሰክሩ እንደሚችሉ ለፍርድ ቤቱ አስረድተው ነበር። ይሁንና ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት በስብሰባ ምክንያት ቀርበው መመስከር እንዳልቻሉና ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ፍርድ ቤት ቀርበው እንዲመሰክሩ ከኦህዴድ ማህከላዊ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት በተፃፈ ደብዳቤ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል።

ሆኖም ፍርድ ቤቱ በቀጠሮው የመጨረሻ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ታስረው እንዲቀርቡ የተነሳው አቤቱታ ላይ ብይን ይሰጣል ተብሎ ሲጠበቅ በዚህ ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል። ከአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተጨማሪ በስብሰባ ምክንያት ለዛሬ ቀርበው መመስከር ባለመቻላቸው ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው በደብዳቤ የጠየቁት የእነ ለማ መገርሳ አቀራረብ ጉዳይ ላይም ታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ብይን እሰጣለሁ ብሏል።

የተከሳሾቹ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን ባለስልጣናቱ ተለዋጭ ቀጠሮ በጠየቁበት ሁኔታ በእነሱ ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ መያዙ ግልፅ እንዳልሆነ ተናግረዋል። ታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. በባለስልጣናቱ የመከላከያ ምስክርነት አቀራረብ ላይ ብይን ለመስጠት ብቻ የተያዘ ቀጠሮ ሲሆን ለተከሳሾቹ ከየካቲት 5 እስከ የካቲት 9 ተከታታይ ቀጠሮ ተይዟል።

የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ

በጌታቸው ሺፈራው

የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ
“ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” አቃቤ ህግ
የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝ አቃቤ ህጉ “ፊልድ ወጥቷል” በሚል ሰበብ ሳይሰማ ቀርቷል

Bekele Gerba

ፎቶ፦ አቶ በቀለ ገርባ

ተከሰውበት ከነበረው የ”ሽብር ክስ” በብይን ወደ መደበኛ ወንጀል ህግ ተቀይሮላቸው ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የዋስትና ጥያቄ አቅርበው ውድቅ የተደረገባቸው የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የዋስትና ይግባኝ ክርክር ዛሬ ጥቅምት 9/2010 በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተሰምቷል።

የአቶ በቀለ ገርባ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን በአቶ በቀለ የተጠቀሰው አንቀፅ በመርህ ደረጃ ዋስትና እንደማያስከለክል፣ የእስር ፍርድ ቤቱም አቶ በቀለ በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ስለነበር በእነዚህ አካላት በኩል ወደ ውጭ ይወጣሉ እንዲሁም የዋስ መብት ተፈቅዶላቸው ቢፈቱ ግዴታቸውን አክብረው ላይቀርቡ ይችላሉ በሚል አቃቤ ህግ ባቀረባቸው ነጥቦች የዋስትና መብታቸውን መከልከሉ ትክክል እንዳልሆነ በመግለፅ ክርክራቸውን በዝርዝር አቅርበዋል።

አቶ አምሃ አቃቤ ህግ ለዋስትና መከልከያነት ያቀረበው መቃወሚያ እና የእስር ፍርድ ቤቱም ዋስትና የከለከለበት ጉዳይ የሽብር ክሱ በብይን ሲወድቅ የወደቀ መሆኑንም አስረድተዋል። በውጭ ከሚገኙ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ነበር የተባለውም በብይን በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ማድረግ ወንጀል አይደለም ተብሎ እንደተበየነ አስረድተዋል። በመሆኑም ወንጀል ያልሆነ ነገር መሰረታዊ የዜጎች መብት የሆነውን የዋስትና መብት ሊያስከለክል አይገባም ሲሉ ክርክራቸውን አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ካቀረበው ነጥብ ውጭ የዋስትና መከልከያ ነጥብ ሳያገኝ የዋስትና መብት የከለከለ ከመሆኑም ባሻገር አቶ በቀለ ዋስትና የተከለከሉበት ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ በመጥቀስ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ጠይቀዋል።

አቃቤ ህግ በበኩሉ አቶ በቀለ የሽብር ክሱ ውድቅ ሳይደረግ ዋስትና ተከልክለው ስለነበር የእስር ፍርድ ቤቱ ለሁለተኛ ጊዜ የዋስትና መብት ሊያይ አይገባውም ብሎ ለልደታ ፍርድ ቤት አቅርቦት የነበረውን መቃወሚያ በማስታወስ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ክርክሩን እንዲያግደው ጠይቋል። ” ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” ሲልም ተቃውሞ አቅርቧል። ይሁንና ፍርድ ቤቱ ክርክሩን እንዲቀጥል ከወሰነ በሚል ከአሁን ቀደም ለእስር ፍርድ ቤት ያቀረባቸውን የዋስትና መቃወሚያዎች ደግሞ አቅርቧል። አቶ በቀለ ይከላከሉ የተባሉበት ወንጀል ከባድና እስከ 10 አመት የሚያስቀጣ ነው በሚል የእስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲፀና ጠይቋል።

አቶ አምሃ በበኩላቸው እነሱ በጠየቁት ይግባኝ አቃቤ ህግ ” ክርክሩ መደረግ የለበትም!” ብሎ ተቃውሞ ማቅረብ እንደማይችል፣ እስከ 10 አመት ያስፈርዳል የሚባለው በተጠቀሰው ወንጀል ከፍተኛ ጉዳት ሲደርስ መሆኑን፣ አቶ በቀለ ይከላከሉ ተባለ እንጅ ጥፋተኛ እንዳልተባሉ በመግለፅ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ለአቃቤ ህግ መቃወሚያ በሰጡት መልስ አስረድተዋል። የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክርክሩን መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለጥቅምት 20/ 2010 ዓም ቀጠሮ ሰጥቷል።

በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት የነበረው እና 6 አመት ከ6 ወር የተፈረደበት የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝም ዛሬ ጥቅምት 9/2010 ቀጠሮ ተይዞለት የነበር ቢሆንም ለአቶ በቀለ ገርባ ክርክር መልስ የሰጠው አቃቤ ህግ “ለዮናታን ጉዳይ መልስ የሚሰጠው አቃቤ ህግ ፊልድ ወጥቷል። ፍርድ ቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን” የሚል ጥያቄ አቅርቧል። የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ጠበቃ “መልስ መስጠት ያለበት ተቋም እንጅ ግለሰብ አይደለም” ሲሉ በአቃቤ ህግ በኩል የቀረበውን ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ አስረድተዋል። ፍርድ ቤቱም እንዲህ አይነት አሳማኝ ያልሆነ ምክንያት መቅረብ እንደሌለበት ገልፆ ለጥቅምት 24/2010 ቀጠሮ ሰጥቷል።

በእነጉርሜሳ አያኖ መዝገብ 5ት ቀሪ የአቃቤ የህግ ምስክሮችን ለመስማት ተጨማሪ ቀን ተሰጠ

አቃቤ ህግ ታህሳስ 27 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀሪ ምስክሮች ቀርበው እንደሆነ ሲጠየቅ፤ አምስት ምስክሮች እንደሚቀሩት እና ተገቢውን ጥረት ቢያደርግም ሊቀርቡ እንዳልቻሉ በመግለፅ የበለጠ ጉዳዩን እንዲያስረዱለት ከፓሊስ የቀረቡትን ረዳት ኢንስፔክተር ቴድሮስ አዳነ ጠይቋል።

Bekele Gerba

አቶ በቀለ ገርባ

ረዳት ኢንስፔክተሩ የተሰጣቸው ጊዜ አጭር በመሆኑ በተሰጠው ቀጠሮ ሁሉንም ማቅረብ አለመቻላቸውን፤ ምስክሮቹ አካባቢያቸውን አበመልቀቃቸው በአዲሱ አድራሻቸው እያፈላለጓቸው በመሆኑ፤ ራቅ ያለ ቦታ ያሉ ምስክር በመኖራቸው ከፍተኛ የጊዜ እጥረት ስለገጠማቸው በመሆኑ ጊዜ እንዲጨመርለት ጠይቋል። በመቀጠልም አቃቤ ህግ ከቀሩት 5ት ምስክሮች ውስጥ አንዱ ጉጂ ዞን የሚገኝ፣ አንዱ ፀበል ላይ እንደነበረ እና ማስረጃ እስኪያመጣ ጊዜ ስላጠረ፣ አንደኛው አድራሻ ቀይሮ ሌላ ቦታ በመሄዱ በተሰጠው ጊዜ ቀርበው መመስከር እንዳልቻሉ ተናግሮ የተቀሩት ሁለቱ ግን የአዲስ አበባ ነዋሪ መሆናቸውን መመስከር ስላልፈለጉ አድራሻቸውን እየቀያየሩ እንዳስቸገሯቸው ተናግሯል። እስካሁን ይመሰክራሉ ከተባሉ 42 ምስክሮች ውስጥ 37ቱን እንዳሰማ የተናገረው አቃቤ ህግ የተከሰሱበትን የክስ ክብደት እንዲሁም ከፍተኛ ጉዳት ያስከተለ ተግባር መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ቀሪ ምስክሮችን አቅርበው እንዲያሰሙ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

የተከሳሽ ጠበቆች የተሰሙት ምስክሮች በችሎቱ ግፊት እንጂ አቃቤ ህግ ዳተኛ እንደነበረ፤ ምስክሮቹን ማቅረብ ስላልፈለገ እንጂ በቂ ጊዜ ተሰጥቶት እንደነበረ፤ የፍትህ ሂደት የሚለካው በሂደቱም ጭምር መሆኑን፤ ከባለፈው ቀጠሮ ጀምሮ በሰበብ አስባቡ ምስክሮችን ለማምጣት በሚል ቀጠሮ መሰጠቱን ተቃውመው እንደነበረ እና የዛሬው ቀጠሮም የመጨረሻው በሚል የተያዘ እንደሆነ ገልፀው ተጨማሪ ቀጠሮ መሰጠት እንደሌለበት ተናግረዋል።

“እንደሚታወቀው ከታሰርን ሁለት ወራችን አይደለም። አንድ አመት አልፎናል። እነሱ ቤታቸው እያደሩ እኛን እያሾፉብን ነው። በአንድ ቀን ብዙ ሺዎችን እያሰረ ያለ መንግስት፤ እንዴት ነው 5ት ምስክሮችን ማቅረብ ያልቻሉት? ” በማለት የኦፌኮ ም/ፕሬዝዳንት አቶ በቀለ ተጨማሪ ቀጠሮ መኖር የለበትም ሲሉ ተከራክረዋል። አቶ ደጀኔ ጣፋም ተቃውሟቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል። “አቃቤ ህግ ሲናገር 2ቱ አዲስ አበባ ናቸው ብሏል። ለምን አልቀረቡም እስካሁን? ክሳችን መጀመሪያም የፓለቲካ ክስ ነው አሁንም የፓለቲካ ድምዳሜ ነው የምንሰማው። እንዲሁ እንደከሰሳችሁን እንዲሁ ፍረዱብን። ወይስ ፍትህ አለ ለማስባል ነው? የኛን እና የናንተን ጊዜ ለምን ይፈጃሉ? ጉጂ እኮ ወርቅ የሚዘረፍበት ነው። እንዴት ከዛ አንድ ሰው ማምጣት ይከብዳቸዋል? አቃቤ ህግ ሌላ ጫና ከሌለባቸው በህጉ አግባብ ይስሩ። ፍርድ ቤት በየጊዜው እያሳሰሰባቸው ነው ምስክር ይዘው ሚቀርቡት። ያልቀረቡ ምስክሮችን በተመለከተ ከቀበሌ ደብዳቤ ይዘው ቀርበዋል ወይ? አልቀረቡም! የፍርድ ቤት ትእዛዝ እየተከበረ አይደለም። እናንተም የካድሬ አይነት ሳይሆን የባለሙያነት አሰራር ስሩልን።” በማለት ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱን እንደሚቃወሙ ተናግረዋል።

“አቃቤ ህግ ዛሬ አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን ብሏል በወቅቱ ቀጠሮ ሲሰጥ ለምን አጭር ጊዜ ነው የተሰጠን አይበቃንም አላለም? ከቀበሌ ይቅረብ የተባለው ማስረጃ አልቀረበም። የችሎቱ ብይን መከበር አለበት። ማእከላዊ ሲያሰቃዩን የነበሩ ፓሊሶች ናቸው ዛሬ ቀርበው ያልተገባ ተጨማሪ ቀጠሮ እየጠየቁ ያሉት።” ሲል የተጨማሪ ቀጠሮውን ጉዳይ ተቃውሞ አሰተያየታቸውን የሰጡት አቶ አዲሱ ቡላላ ናቸው።

ዳኞች ከተማከሩ በኋላ አቃቤ ህግ ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ፤ ተከሳሾችን ደግሞ የፓለቲካ እስረኛ ብሎ ነገር እንደሌለ፣ ያሉበትን ሁኔታ እንደሚረዷቸው፣ እንዲያውም ማነፃፀር ባይገባም ከሌላው መዝገብ ሲተያይ በፍጥነት እየሄደ መሆኑን፣ እነሱም [ተከሳሾች] መከላከያ ምስክር በሚያሰሙበት ጊዜ ምስክሮችን ለመስማት ጊዜ እንደሚሰጡ በመግለፅ ፓሊስ በ15 ቀን ውስጥ ከየትም ፈልጎ ምስክሮቹን እንዲያመጣ፤ የማይገኙ ከሆነም ይኖሩበት ከነበረው ቀበሌ ደብዳቤ እንዲቀርብ ትእዛዝ ሰጥተዋል። አቃቤህግ የተሰጠው ጊዜ አጭር እንደሆነ በመግለፅ ትንሽ ረዘም ያለ ቀጠሮ እንዲሰጠው ቢጠይቅም ዳኞች ጥያቄውን ሳይቀበሉት፤ ፓሊስ የተቻለውን ሁሉ ጥረት በማድረግ በቀጠሮው ቀን እንዲያቀርብ አዘዋል።

የተከሳሽ ጠበቃ የሆኑት አቶ መልካሙ የሚሰጠው ቀጠሮ የመጨረሻ እንዲሆን በሚል ላቀረቡት ሃሳብ፤ የመጨረሻ ቀጠሮ የሚባል እንደሌላ አሳማኝ ምክንያት ከተገኘ ሌላ ቀጠሮ ሊሰጥ እንደሚችል፤ አሳማኝ ምክንያት ካልተገኘ የመጨረሻ ባይባልም የምስክር የመስማት ሂደት ሊቋረጥ እንደሚችል በመጥቀስ ቀጣዩ ቀጠሮ የመጨረሻ መባል የለበትም ሲሉ ዳኞች መልስ ሰጥተዋል።

ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 15 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀጠሮ ተይዟል።

ምንጭ፦EHRP

እነ በቀለ ገርባ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች አልተሰሙም፤ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ አላቀረበም

‹‹እሰነጥቅሃለሁ ተብያለሁ›› አቶ በቀለ ገርባ

bekele-gerba-et-al

በኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል ውስጥ የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የቀረበባቸው የኦፌኮ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ከሦስት ወራት በኋላ እንደገና ወደ ችሎት ሲመለሱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ በመያዝ የነበር ቢሆንም፣ በእስር የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ ባለማቅረቡ ምክንያት ምስክሮቹ ሳይሰሙ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም በዋለው ችሎት ላይ እንደተመለከተው በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከተካተቱት ተጠርጣሪዎች (22 ሰዎች) መካከል 5ቱን ማረሚያ ቤቱ አላቀረባቸውም፡፡ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም ለፍርድ ቤቱ በጻፈው ደብዳቤ እንደገለጸው ‹4ቱ ተጠርጣሪዎች በቂሊንጦ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ አደጋ ተከትሎ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው ስላልተመለሱ› ማቅረብ አልቻለም፡፡ ማረሚያ ቤቱ ሸዋሮቢት እንደሚገኙ ያመለከታቸው ተጠርጣሪዎች ገላና ነጋሪ፣ ገመቹ ሻንቆ፣ ደረጀ መርጋ እና ቶምሳ አብዲሳ ናቸው፡፡

ሆኖም ግን ማረሚያ ቤቱ በስም ጠቅሶ ሸዋሮቢት ስለሆኑ ማቅረብ አለመቻሉን ከጠቀሰው ሌላ አንድ ተጠርጣሪ ችሎት አለመገኘቱን በማጣራት ፍርድ ቤቱ ተጠርጣሪውን ለምን እንዳላቀረበ የማርሚያ ቤቱን ተወካይ ጠይቋል፡፡ ሆኖም የዕለቱ ጉዳይ አስፈጻሚ ምክትል ሰርጀንት ዘውዱ ወልደማርያም ተጠርጣሪው በእርግጥ የት እንደሚገኝ እንደማያውቁ ተናግረዋል፡፡ ይህ የት እንዳለ ያልታወቀው ተጠርጣሪ ጭምሳ አብዲሳ ይባላል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ ተጠርጣሪዎች ብቻ ሳይሆኑ ጠበቆችም ተሟልተው አለመቅረባቸው ታውቋል፡፡ የብዙዎቹ ተጠርጣሪዎች ጠበቃ የሆኑት አቶ ወንድሙ ኢብሳ አልቀረቡም፡፡ ተከሳሾችም ጠበቃቸው ከቀጠሮ በፊት ደንበኞቻቸውን ለማነጋገር ወደቂሊንጦ ሄደው ማግኘት እንደማይችሉ ተነገሯቸው መመለሳቸውን ከማወቃቸው ውጭ በዛሬው ችሎት ለምን እንዳልቀረቡ እንደማያውቁ ለችሎቱ ተናግረዋል፡፡ በችሎት የቀረቡት ሌሎች ጠበቆችም ቢሆን ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ደንበኞቻቸውን በነጻነት ስለጉዳያቸው ለማነጋገር እንዳይችሉ እንቅፋት እየፈጠረባቸው መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ችሎቱ ዛሬ የተሰየመው የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት መሆኑን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ከአጠቃላይ 42 ምስክሮቹ መካከል አምስቱ መቅረባቸውን በመግለጽ ምስክሮቹ ቀርበው እንዲሰሙለት ጠይቋል፡፡ ሆኖም ግን ተከሳሾቹ ሁሉም ተሟልተው ባልተገኙበት ሁኔታ ምስክር ሊሰማ እንደማይገባ ጠቅሰው ተቃውመዋል፡፡ ተከሳሾቹ በክሱ ላይ በጋራ የቀረበባቸው ፍሬ ነገር ስላለ በተናጠል ምስክሮች ቢደመጡ መብታችንን ይነካል በሚል በጠበቆቻቸው አማካኝነት አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል አቶ በቀለ ገርባ አሁን ጉዳያቸውን እየየ የሚገኘው ችሎት በክስ መቃወሚያቸው ላይ ጉዳያቸው በፌደራል ፍርድ ቤት ሳይሆን በኦሮሚያ ክልል ፍርድ ቤቶች ሊታይ ይገባል በሚል ያነሱትን ህገ-መንግስታዊ የመብት ጥያቄ በጣሰ መልኩ ሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም መቃወሚያቸውን ውድቅ ማድረጉን በማስታወስ፣ በፍርድ ቤቱ ገለልተኝነት ላይ ጥያቄ ስላላቸው ችሎት ቀርበው ክርክር ለማድረግ እንደማይፈልጉ ቀደም ብለውም ገልተጸው እንደነበር ጠቅሰው በዛሬው ችሎት ላይም ፖሊስ በጉልበት እየደበደበ እንዳቀረባቸው አስረድተዋል፡፡

አቶ በቀለ ሌሎችንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዱት ከዚህም በኋላ ችሎት የሚቀርቡ ከሆነ ተገደው እየቀረቡ እንዳሉ ችሎቱ እንዲያውቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውድቅ ያደረገባቸውንና በክስ መቃወሚያ የጠቀሱትን ይህንኑ የህገ-መንግስት ጉዳይ ከጠበቆቻቸው ጋር ተመካክረው ወደ ፌደሬሽን ምርድ ቤት የመውሰድ ሀሳብ እንዳላቸውም ጠቅሰዋል፡፡

ፖሊስ በጉልበት መኪና ውስጥ ካስገባን በኋላ ‹‹እሰነጥቅሃለሁ›› የሚል ዛቻ እንደደረሰባቸው፣ ይህን የተናገረውን ፖሊስ ችሎት ፊት ጠቁመው በማሳየት ጭምር ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ግን ይህን ዛቻ ያደረሰውን ፖሊስ ችሎቱ አንድም ጥያቄ ሳያቀርብለት አልፎታል፡፡

በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ በዛሬው ውሎ ያልቀረቡ ተከሳሾችን ማረሚያ ቤት እንዲያቀርብ፣ 7ኛ ተከሳሽ ጭምሳ አብዲሳን ማረሚያ ቤት ለምን እንዳላቀረባቸው ምክንያት እንዲያስረዳ እንዲሁም የኦሮምኛና ስዋህሊ ቋንቋዎች አስተርጓሚዎች እንዲመደቡ ትዕዛዝ በመስጠት ተከሳሾቹ ተሟልተው ሲቀርቡ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለህዳር 6 ፍርድ 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤት ማንኛውም ተከሳሽ በቀጠሮው ዕለት የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ አክብሮ መገኘት እንዳለበትም ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ የኦሮምኛ ቋንቋ አስተርጓሚ ችሎቱ ባለማቅረቡ ከተከሳሾች መካከል አቶ በቀለ ገርባ በአጋዥነት ሲያስተረጉሙ ውለዋል፡፡ የዛሬውን ችሎት ከተከሳሽ ቤተሰቦች በተጨማሪ የዲፕሎማቲክ ኮሚኒቲ ተወካዮችና ጋዜጠኞች ተከታትለውታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

እነ በቀለ ገርባ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ገለፁ

”ፍርድ ቤቱ ገለልተኛ ነው ብዬ ስለማላምን ቃሌን አልሰጥም” አቶ በቀለ ገርባ

Bekele Gerba

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የቀረበባቸው የኦፌኮ አመራሮችና አባላት በቀረበባቸው ክስ ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ጉዳያቸውን ለሚያየው ችሎት ገልጸዋል፡፡
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 5 ቀን 2008 ዓ.ም መዝገቡን የቀጠረው የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ሲሆን፣ ችሎቱ ተከሳሾችን አንድ በአንድ በስማቸው እየጠራ የቀረበባቸውን የወንጀል ድርጊት ስለመፈጸም አለመፈጸማቸው የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡት ጠይቋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ አቶ ጉርሜሳ አያኖ የቀረበባቸውን ክስ የወንጀል ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም ተብለው ሲጠየቁ፣ ‹‹ይሄ ክስ ለእኔ ግልጽ አይደለም፡፡ በመቃወሚያ ላይ ይህን ገልጫለሁ፡፡ እኔ በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ የሚታገል ፓርቲ አባል ሆኜ ስታገል የኦነግ አባል ሆነሃል ተብዬ መከሰስ የለብኝም፡፡ ይህ የምታገልለትን ህዝብ እንደመወንጀል ይቆጠራል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ አሸባሪ ከተባለ እኔም አሸባሪ ነኝ፡፡ ይህ በደል ነው፡፡ ስለዚህ እኔ እዚህ ቆሜ ቃሌን መስጠት አያስፈልገኝም›› በማለት ተናግረዋል፡፡

2ኛ ተከሳሽ አቶ ደጀኔ ጣፋ በበኩላቸው ‹‹እኔ የምታገልለት ህዝብ በመንግስት ጦር እያለቀ ባለበት ሰዓት እኔ እዚህ ቆሜ ቃሌን መስጠት አልፈልግም፡፡ ይህ ፍርድ ቤትም ህገ-መንግስቱን የጣሰ ውሳኔ ስላሳለፈብኝ ለዚህ ፍርድ ቤት ቃሌን መስጠት ታሪካዊ ስህተት ነው የሚሆነው፡፡ ድጋሜ እዚህ ፍርድ ቤት መቅረብም አልፈልግም›› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ አዲሱ ቡላላም በተመሳሳይ ቃላቸውን ለመስጠት እንደማይፈልጉ ተናግረዋል፡፡ ‹‹የደረሰን በክስ መልክ የቀረበ ድረሰት ግልጽ አይደለም፡፡ በባህላችን ውሻ እንኳ ዝም ተብሎ አይነካም፡፡ ከተነካም ባለቤቱን መናቅ ነው የሚሆነው፡፡ እኔ ለኦሮሞ ህዝብ በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ እታገላለሁ፡፡ የተሰጠኝ ድርሰት ግን የኦነግ አባል ሆነሃል የሚል ነው፡፡ እኔ የኦፌኮ አባል እንጂ የኦነግ አባል አይደለሁም፡፡ ስለዚህ በፍርድ ቤቱ ወንጀሉን ፈጽመሃል አልፈጸምህም ተብዬ ስጠየቅ ያሳፍረኛል፡፡ ከዚህ በኋላ አስገዳጅ ሁኔታ ካልተፈጠረ በቀር እዚህ ችሎት መቅረብ አልፈልግም፡፡ ውሳኔያችሁን ልትልኩልኝ ትችላላችሁ›› በማለት ለችሎቱ ተናግረዋል፡፡

የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ታደለ ተገኝ ተከሳሾቹ በአጭሩ ድርጊቱን ስለመፈጸም አለመፈጸማቸው ብቻ መልስ እንዲሰጡ፣ ሌላ ረጂም ንግግር ማድረግ ተገቢ እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ማሳሰቢያ ሲሰጡ ተደምጠዋል፡፡
ከማሳሰቢያው በኋላ፣ 4ኛ ተከሳሽ የሆኑት የኦፌኮ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ በቀለ ገርባ ደግሞ፣ ‹‹በክስ መቃወሚያችን ወንጀሉ ተፈጸመ በተባለበት ቦታ እንዳኝ ብለን ጠይቀን ይህ ችሎት ውድቅ አድርጎታል፡፡ ጥያቄያችን ህገ-መንግስታዊ ነበር፡፡ ግን አልተቀበላችሁትም፡፡ ስለዚህ ይህ ፍርድ ቤቱ ገለልተኛ ነው ብዬ ስለማላስብ ቃሌን ለመስጠት አልፈልግም፡፡ ካሁን በፊትም የሀሰት ማስረጃ ቀርቦብኝ ስምንት አመት ፈርዶብኛል፡፡ የዚህንም ውሳኔ ባለሁበት ልትልኩልኝ ትችላላችሁ›› ብለዋል፡፡

ከ5ኛ ተከሳሽ ጀምሮ እንዲሁ በተመሳሳይ ቃላቸውን እንዲሰጡ እየተጠየቁ በአብዛኛው ተመሳሳይ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ከተከሳሾች መካከል 10ኛ እና 12ኛ ተከሳሾች ብቻ ‹‹ድርጊቱን አልፈጸምንም›› የሚል ቀጥተኛ የክህደት ቃላቸውን ሲሰጡ 13ኛ ተከሳሽ በበኩሉ የዝምታ ምላሽን ሰጥቷል፡፡ 7ኛ ተከሳሽ ‹‹ክሱ ንቀትና ጥላቻ የታጨቀበት ስለሆነ መልስ አልሰጥም›› ሲል ቀሪዎቹ ክሱ ግልጽ አይደለም፣ ፍርድ ቤቱም ገለልተኛ ነው ብለን አናምንም በሚል የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ለችሎቱ ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር 11ኛ እና 19ኛ ተከሳሾችን ‹‹በስራ ጫና ምክንያት ቆጥረን አረጋግጠን ማቅረብ አልቻልንም›› የሚል መልስ በሰጠበት ምክንያት ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡ ይህን በተመለከተ ጠበቃቸው በሰጡት አስተያየት ደበኞቻቸው ላይ የደህንት ስጋት ተጋርጦባቸው ሊሆን እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸው ፍርድ ቤቱ ይህንኑ ስጋታቸውን እንዲመዘግብላቸው አሳስበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ አስተዳደሩ በነገው ዕለት እንዲያቀርባቸው በማዘዝ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመቀበል ቀጠሮ ይዟል፡፡

ፍርድ ቤቱ ዛሬ የቀረቡት ተከሳሾች ቃላቸውን ለመስጠት ፍቃደኛ አለመሆናቸውን ከመዘገበ በኋላ ‹‹ወንጀሉን አልፈጸምንም›› እንዳሉ ተቆጥሮ ክደው እንደተከራከሩ በመመዝገብ ያለ አቃቤ ህግ አሳሳቢነት የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በሚል ከህዳር 02-16 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ የሰው ምስክሮች በርካታ በመሆናቸው ተከታታይ የቀጠሮ ቀናትን መስጠቱን ገልጹዋል፡፡
በዛሬው የችሎት ውሎ ተከሳሾቹ ዳኞች ወደ ችሎት ሲገቡም ሆነ ችሎቱ ጉዳያቸውን ሲያይ በችሎቱ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ ለመግለጽ ከመቀመጫቸው ሳይነሱ ቀርተዋል፡፡
ምንጭ፡-EHRP

%d bloggers like this: