Tag Archives: Yonatan Tesfaye

የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝ ክርክር ተሰማ

ጌታቸው ሺፈራው

በማነሳሳት የ”ሽብር” ክስ ተመስርቶበት 6 አመት ከ6 ወር የተፈረደበት አቶ ዮናታን ተስፋዬ የይግባኝ ክርክር ዛሬ ጥቅምት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተሰምቷል። አቶ ዮናታን ተስፋዬ የተፈረደበት ፌስ ቡክ ላይ በፃፈው ፅሁፍ ሲሆን ጠበቃው አቶ ሽብሩ በለጠ አቶ ዮናታን ተስፋዬ የተከሰሰውና የተፈረደበት ሀሳቡን በነፃነት በመግለፁ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ አብራርተዋል። ከዚህም ባሻገር አቶ ዮናታን የተከሰሰበትና የተፈረደበት አንቀፅ በህትመት ለወጣ ፅሁፍ የተደነገገ እንጅ በማህበራዊ ሚዲያ ለወጣ (ላልታተመ ፅሁፍ) እንዳልሆነ በመግለፅ አቶ ዮናታን በፀረ ሽብር አዋጁ አንቀፅ 6 ሊከሰስ እና ሊቀጣ አይገባም ነበር ብለው ተከራክረዋል።

ጠበቃው አቶ ዮናታን ህገ መንግስታዊ መብቱን ተጠቅሞ ሀሳቡን በነፃነት ገለፀ እንጅ ሽብርተኝነትን የማበረታት ተግባር አለመፈፀሙን፣ ሆኖም የስር ፍርድ ቤቱ የሰጠው ውሳኔ ህግና ማስረጃን መሰረት ያላደረገ፣ ስህተትና ያልተገባ ነው ብለዋል። በመሆኑም ጠቅላይ ፍርድ ቤት የስር ፍርድ ቤቱ የሰጠው የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ በመሻር ይግባኝ ባይን እንዲያሰናብት ጠይቀዋል። ይህ ከታለፈ እንኳን እስካሁን የታሰረው ጊዜ በቂ ተብሎ ከእስር እንዲለቀቅ አመልክተዋል። ፍርድ ቤቱ አቶ ዮናታን በበቂ እንዲለቀቅ የቀረበውን ጥያቄ ካለፈውም ፣ ለስር ፍርድ ቤቱ 6 በመረጃ የተረጋገጡ ማቅለያዎች ቀርበው ፣ በእነዚህ ማቅለያዎች መሰረት ስድስት እርከን ዝቅ ብሎ መወሰን ሲገባ ሶስት እርከን ብቻ በመቀነስ ውሳኔ ስለተሰጠ ማቅለያዎቹ ተይዘው የቅጣት ውሳኔው ተሻሽሎ እንዲወሰን የይግባኝ ክርክር አቅርበዋል።

በሌላ በኩል አቃቤ ህግ አቶ መኩርያ አለሙ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በፅሁፉ በኦነግ አላማ ሲያነሳሳ እንደነበር እና የተፈረደበትም በዝቅተኛ ደረጃ በመሆኑ ፍርዱን ሊቀንስለት አይገባም ብሎ ተከራክሯል። አቶ ዮናታን በበኩሉ አቃቤ ህግ ከኦነግ ጋር ግንኙነት አለው ብሎ ክስ ማቅረቡንና በዚህም እንደተፈረደበት በማስታወስ፣ ሆኖም በቀረበው ክስ ላይ ከኦነግ ጋር አለው ስለተባለው ግንኙነት ማስረጃ እንዳልቀረበ፣ ፍርዱም ትክክል እንዳልሆነ ተከራክሯል።

አቶ ዮናታን ተስፋዬ የተከሰሰውና የተፈረደበት ከ”ማስተር ፕላን” ጋር በተያያዘ ኦሮሚያ ክልል ተቀስቅሶ በነበረው የህዝብ ንቅናቄ ሰበብ ሲሆን አቶ ኃይለማይያም ደሳለኝ በመንግስት ሚዲያዎች ቀርበው ኦሮሚያ ውስጥ የተፈጠረው ችግር የመልካም አስተዳደር ችግር እንጅ የሽብር ባህሪ የለውም ብለው መግለጫ ሰጥተው እንደነበር ጠበቃ ሽብሩ በለጠ አስታውሰዋል። የግራ ቀኙን ክርክር መርምሮ ለመበየን ለህዳር 18 ቀን 2010 ዓ.ም. ተቀጥሯል።

የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ

በጌታቸው ሺፈራው

የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ
“ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” አቃቤ ህግ
የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝ አቃቤ ህጉ “ፊልድ ወጥቷል” በሚል ሰበብ ሳይሰማ ቀርቷል

Bekele Gerba

ፎቶ፦ አቶ በቀለ ገርባ

ተከሰውበት ከነበረው የ”ሽብር ክስ” በብይን ወደ መደበኛ ወንጀል ህግ ተቀይሮላቸው ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የዋስትና ጥያቄ አቅርበው ውድቅ የተደረገባቸው የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የዋስትና ይግባኝ ክርክር ዛሬ ጥቅምት 9/2010 በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተሰምቷል።

የአቶ በቀለ ገርባ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን በአቶ በቀለ የተጠቀሰው አንቀፅ በመርህ ደረጃ ዋስትና እንደማያስከለክል፣ የእስር ፍርድ ቤቱም አቶ በቀለ በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ስለነበር በእነዚህ አካላት በኩል ወደ ውጭ ይወጣሉ እንዲሁም የዋስ መብት ተፈቅዶላቸው ቢፈቱ ግዴታቸውን አክብረው ላይቀርቡ ይችላሉ በሚል አቃቤ ህግ ባቀረባቸው ነጥቦች የዋስትና መብታቸውን መከልከሉ ትክክል እንዳልሆነ በመግለፅ ክርክራቸውን በዝርዝር አቅርበዋል።

አቶ አምሃ አቃቤ ህግ ለዋስትና መከልከያነት ያቀረበው መቃወሚያ እና የእስር ፍርድ ቤቱም ዋስትና የከለከለበት ጉዳይ የሽብር ክሱ በብይን ሲወድቅ የወደቀ መሆኑንም አስረድተዋል። በውጭ ከሚገኙ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ነበር የተባለውም በብይን በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ማድረግ ወንጀል አይደለም ተብሎ እንደተበየነ አስረድተዋል። በመሆኑም ወንጀል ያልሆነ ነገር መሰረታዊ የዜጎች መብት የሆነውን የዋስትና መብት ሊያስከለክል አይገባም ሲሉ ክርክራቸውን አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ካቀረበው ነጥብ ውጭ የዋስትና መከልከያ ነጥብ ሳያገኝ የዋስትና መብት የከለከለ ከመሆኑም ባሻገር አቶ በቀለ ዋስትና የተከለከሉበት ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ በመጥቀስ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ጠይቀዋል።

አቃቤ ህግ በበኩሉ አቶ በቀለ የሽብር ክሱ ውድቅ ሳይደረግ ዋስትና ተከልክለው ስለነበር የእስር ፍርድ ቤቱ ለሁለተኛ ጊዜ የዋስትና መብት ሊያይ አይገባውም ብሎ ለልደታ ፍርድ ቤት አቅርቦት የነበረውን መቃወሚያ በማስታወስ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ክርክሩን እንዲያግደው ጠይቋል። ” ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” ሲልም ተቃውሞ አቅርቧል። ይሁንና ፍርድ ቤቱ ክርክሩን እንዲቀጥል ከወሰነ በሚል ከአሁን ቀደም ለእስር ፍርድ ቤት ያቀረባቸውን የዋስትና መቃወሚያዎች ደግሞ አቅርቧል። አቶ በቀለ ይከላከሉ የተባሉበት ወንጀል ከባድና እስከ 10 አመት የሚያስቀጣ ነው በሚል የእስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲፀና ጠይቋል።

አቶ አምሃ በበኩላቸው እነሱ በጠየቁት ይግባኝ አቃቤ ህግ ” ክርክሩ መደረግ የለበትም!” ብሎ ተቃውሞ ማቅረብ እንደማይችል፣ እስከ 10 አመት ያስፈርዳል የሚባለው በተጠቀሰው ወንጀል ከፍተኛ ጉዳት ሲደርስ መሆኑን፣ አቶ በቀለ ይከላከሉ ተባለ እንጅ ጥፋተኛ እንዳልተባሉ በመግለፅ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ለአቃቤ ህግ መቃወሚያ በሰጡት መልስ አስረድተዋል። የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክርክሩን መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለጥቅምት 20/ 2010 ዓም ቀጠሮ ሰጥቷል።

በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት የነበረው እና 6 አመት ከ6 ወር የተፈረደበት የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝም ዛሬ ጥቅምት 9/2010 ቀጠሮ ተይዞለት የነበር ቢሆንም ለአቶ በቀለ ገርባ ክርክር መልስ የሰጠው አቃቤ ህግ “ለዮናታን ጉዳይ መልስ የሚሰጠው አቃቤ ህግ ፊልድ ወጥቷል። ፍርድ ቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን” የሚል ጥያቄ አቅርቧል። የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ጠበቃ “መልስ መስጠት ያለበት ተቋም እንጅ ግለሰብ አይደለም” ሲሉ በአቃቤ ህግ በኩል የቀረበውን ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ አስረድተዋል። ፍርድ ቤቱም እንዲህ አይነት አሳማኝ ያልሆነ ምክንያት መቅረብ እንደሌለበት ገልፆ ለጥቅምት 24/2010 ቀጠሮ ሰጥቷል።

የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረውና የመብት አራማጅ ዮናታን ተስፋዬ 6 ዓመት ከ6 ወር እስራት ተፈረደበት

(አዲስ ሚዲያ) የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፥ የ2007 ዓ. ም. በአዲስ አበባ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩና የመብት አራማጅ ወጣት ዮናታን ተስፋዬ ግንቦት 17 ቀን 2009 ዓ ም በዋለው ችሎት 6 ዓመት ከ6 ወር እስር ተፈርዶበታል።

yonatan-tesfaye

ዮናታን ተስፋዬ

ወጣት ዮናታን ከህዳር 2008 ዓ. ም. ጀምሮ የተነሳውን ህዝባዊ አመፅ ተከትሎ ከታሰሩት በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና የመብት ተሟጋቾች መካከል አንዱ ነው።

ወጣት ዮናታን ተስፋዬ ደም ልገሳን ጭምሮ በተለያዩ ግብረ ሰናይ ተግባራት ላይም ይሳተፍ የነበረ ቢሆንም፥ ከታህሳሥ 17 ቀን 2008 ዓ ም ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛል።

የፌደራል አቃቤ ህግ ክስ የመሰረተበት በፌስ ቡክ ማኅበራዊ ገፅ መንግሥት በዜጎች ላይ እየወሰደ የነበረውን ርምጃ የሚቃወሙና የሚተቹ ፅሑፎችን ፅፏል በሚል እንደሆነ የተመሰረተበት የክስ ሰነድ ያመለክታል።

በመጨረሻም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአዲስ አበባ ልደታ ምድብ ችሎት ግንቦት 17 ቀን 2009 ዓ ም በዋለው ችሎት በፌስ ቡክ ማኅበራዊ ገፅ የፃፋቸውን ፅሑፎች ብቻ እንደመረጃና ማስረጃ በመጠቀም 6 ዓመት ከ6 ወር እስራት ፈርዶበታል።

Ethiopia court found former senior opposition figure Yonatan Tesfaye guilty of terrorism charges

Mahlet Fasil

The Federal High court fourth criminal bench has passed a guilty verdict against Yonatan Tesfaye, former opposition Blue Party public relations head.

yonatan-tesfaye

Yonatan Tesfaye

Yonatan was first arrested in December 2015, barely a month after the first wave of a year-long #Oromoprotests erupted. He was held incommunicado during the pre-trial weeks and was subsequently charged in May 2016 under Ethiopia’s infamous anti-terrorism proclamation (ATP).

Yonatan has been defending the charges against him since then. The charges of ‘encouragement of terrorism’, stipulated under article six of the ATP, were largely drawn from his Facebook activism during the protests. According to article six of the ATP, “Whosoever publishes or causes the publication of a statement that is likely to be understood by some or all of the members of the public to whom it is published as a direct or indirect encouragement or other inducements to them to the commission or preparation or instigation of an act of terrorism…” is subject to terrorism charges.

He had presented several defense witnesses, including prominent opposition party leaders from the Oromo Federalist Congress (OFC), Bekele Gerba and Dr. Merera Gudina, who are in jail at the time of their testimony fighting charges of terrorism and multiple criminal charges respectively, and journalist Eskendir Nega, who is serving 18 years in prison for terrorism-related charges.

In addition, Yonatan’s close friend Ephrem Tayachew, his father Tesfaye Regassa, and his sister Gedamnesh Tesfaye as well as academicians from the Addis Abeba University (AAU), including the outspoken philosopher Dr. Dagnachew Assefa and Dr. Yaqob Hailemariam have all appeared in court to testify in defense of Yonatan’s innocence.

However, on May 16, 2017 the court in its verdict overruled all defense testimonials by upholding prosecutors’ accusations. Yonatan’s sentencing is adjourned to May 25, 2017.
Yonatan could face from ten to 20 years rigorous prison term in a federal prison; however, the court ruled that he can appeal for a minimum sentence.

***According to new information Addis Standard received, after the sentencing is handed over, Yonatan’s defense team, led by his lawyer Shibiru Belete, is planning to object to the verdict and appeal for the charges to be reduced to criminal charges.

Source: Addisstandard

በዮናታን ተስፋዬ ላይ መከላከያ ምስክሮች መሰማት ጀመሩ

ቀደም ባሉ ቀናት በዋለው ችሎት በጊዜ እጥረት ምክንያት መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ባለመቻሉ ታህሳስ 26 ቀን 209 ዓ. ም. ተቀጥሮ ነበር። ዮናታን ተስፋዬ እንዲከላከሉለት ከዘረዘራቸው የሰው ምስክሮች ከአንዱ (ዶ/ር መረራ ጉዲና) በስተቀር የተቀሩት መከላከያ ምስክሮች መቅረባቸውን የዮናታን ጠበቃ የሆኑት አቶ ሽብሩ በለጠ ለችሎት አሳውቀዋል፡፡ መከላከያ ምስክሮች መሰማት ከመጀመራቸው በፊት አቶ ዮናታን የራሱን የምስክርነት ቃል አቅርቧል፡፡

yonatan-tesfaye

ዮናታን ተስፋዬ

“በፌስቡክ አካውንቴ እፅፍ የነበረው ሃሳቤን ለመካፈል ፈቃደኛ ለሆኑት ጓደኞቼ ብቻ ነው፡፡ ህዝብ ቀስቅሷል የሚባለው ነገር የማይመስል ነገር ነው፡፡ እድሉን አግኘቼ እንኳን ለህዝብ ደርሶ ቢሆን የሽብርን ድርጊት የሚያበረታታ አይደለም የፃፍኩት ነገር፡፡ በሃገሪቷ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ የሚገልፁ እና የሚዳስሱ ናቸው፡፡ እንዚህን ሃሳቦች ከጓደኞቼ ጋር መወያየቴ ሃሳቤን በነፃነት የመግለፅ መብቴን መጠቀሜ ነው፡፡ “ህግ መጨቆኛ መሳሪያ ሲሆን፡ አመፅ የህሊና ህግ ይሆናል፡፡” የሚለው ሃሳብ የተፈጥሮ እና አለም ዓቀፋዊ ህግ ነው፡፡ ማንም ሊቀይረው አይችልም፡፡ የፍልስፍና መርህም ነው፡፡ ምናልባትም ያን የተናገርኩ ጊዜ የሚሰማ አካል ቢኖር ኖሮ ይሄ ሁላ ችግር ባልደረሰም ነበር፡፡ በህዳር 2008 ዓ.ም. አካባቢ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን የሚገኘው ጭልሞ ጫካ ለባለሃብት ከተሸጠ በኋላ ህብረተሰቡ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ አድርገዋል፡፡ ምናልባትም ጥያቄያቸው በትክክለኛው አግባብ ቢያዝ ተቃውሞው አይስፋፋም ነበር፡፡ እኔም የሚደርሰው ጉዳት እንዲቀንስ የበኩሌን አስተዋፅኦ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ መንግስት የህብረተሰቡን ደህንነት መጠበቅ ሲኖርበት በተቃራኒው የመንግስት አካል ህብረተሰቡ ላይ ጉዳት ሲያደርስ በተለያየ መንገድ ህዝቡ ራሱን እንዲከላከል የተለያየ ሃሳብ አቅርቤአለሁ፡፡ የአንድ ሰው ህይወት ዋጋ አለው፡፡ እኔ ከመታሰሬ ቀደም ብሎ 62 የዩቨርስቲ ተማሪዎች ተገድለው ነበር፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ነገ ይህችን ዓለም ሊቀይሩ ይችሉ የነበሩ ናቸው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያምን ጨምሮ የተለያዩ የመንግስት አካላት ችግሩ የተከሰተው በመልካም አስተዳደር እጦት መሆኑን አምነው ይቅርታም የጠየቁበት ጉዳይ ነው። አንድ ሚሊዮን ብር ከሚያወጣ ንብረት ይልቅ የአንድ ሰው ህይወት ዋጋ አለው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሹፌር 20 ተሳፋሪ ይዞ ፍሬን እምቢ ቢለው መኪናውን አጠገቡ የሚገኝ ግንድ ወይም ግንብ አጋጭቶ ቢያቆመው፡ ሹፌሩ መኪናው ላይ በደረሰው አደጋ ሊቀጣ አይገባውም፡፡ በአደባባይ ሰዎች ሲሞቱና ሲገደሉ እነርሱን ዲፌንድ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ ይህንንም ሃሳቤን የመግለፅ መብቴን ተጠቅሜ የተለያየ ሃሳብ አቅርቤያለሁ፡፡ ይሄ ጥፋት የሚባል ከሆነ እቀበለዋለሁ፤ ለኔ ክብሬ ነው፡፡ ፍርዱን ከታሪክ እና ከእግዚአብሄር አገኘዋለሁ፡፡” ይህን የምስክርነት ቃሉን ዮናታን ካቀረበ በኋላ የሙያ ምስክርነታቸውን የሚሰጡትን ሶስት ምስክሮች ጠበቃው ዘርዝረዋል፡፡

የህግ ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ያእቆብ ኃይለማርያም እና የፍልስፍና መምህሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ የሙያ ምስክርነታቸውን የሚሰጡ ሲሆን ዮናታን የፃፈው ፅሁፍ ሃሳብን ከመግለፅ ነፃነት አንፃር እና ኢትዮጵያ ከፈረመቻቸው ህጎች አንፃር ገደቡን ያለፈ አለመሆኑን እንደሚያስረዱ፤ እንዲሁም ሶስተኛው የሙያ ምስክር ጦማሪ እና የመብት አራማጅ በፍቃዱ ሃይሉ ደግሞ በፌስቡክ በግለሰብ አካውንት የሚለጠፉ ፖስቶች ከመደበኛ ሚዲያ እና ከዜና ድህረገፆች የሚለይበትን እንደሚያስረዳ ጠበቃው አቶ ሽብሩ በጭብጥነት አስመዝግበዋል፡፡ አቃቤ ህግ በሶስቱም የሙያ ምስክሮች ላይ ተቃውሞ እንዳለው ከተናገረ በኋላ ህግን መተርጎም ያለበት ፍርድ ቤት እንደሆነ ከዚህም ካለፈ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማየት እንዳለበት ጠቅሶ ምስክሮች የፍርድ ቤቱን ሚና መውሰድ ስለሌለባቸው የመጀመሪያዎቹ ሁለት ምስክሮች [ዶ/ር ያእቆብ እና ዶ/ር ዳኛቸው] መሰማት የለባቸውም በማለት እንዳይሰሙ ሲል ጠይቋል፡፡ በፍቃዱ የሚመሰክርበትን ጭብጥም በተመለከተ ከክሱ ጋር የማይገናኝ ስለሆነ መመስከር የለበትም ብሎ ለችሎቱ ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡

ጠበቃ አቶ ሽብሩም “አቃቤ ህግ ዮናታንን ወንጀል ሰርቷል ብሎ ምስክር ሲያሰማ የዳኞችን ሚና ወሰደ አልተባለም፡፡ የደንበኛዬ የመከላከል መብት በሰበብ አስባብ ሊጣስ አይገባም፡፡” ብለው ከተናገሩ በኋላ ዶ/ር ያዕቆብ እና ዶ/ር ዳኛቸው ከልምዳቸው እና ከትምህርት ዝግጅታቸው አንፃር የዮናታን ፅሁፍ ከገደብ አለማለፉን በተረዱት መጠን እንደሚያስረዱ፤ በፍቃዱ የሚመሰክረውም ዮናታን የተከሰሰበት የሽብርተኝነት ህግ አንቀፅ 6 በህትመት ደረጃ ስለሚፃፉ ሽብርተኝነትን የሚያበረታቱ ፅሁፎች ስለሚል ልዩነቱን እንዲያስረዳ ነው በማለት ምስክሮቹ የሚመሰክሩበትን ጭብጥ አግባብነት አስረድተዋል፡፡ ዳኞችም የግራ ቀኙን ሃሳብ ከሰሙ በኋላ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ቃሉ ተመዝኖ መጨረሻ ላይ የሚታወቅ በመሆኑ ምስክሮች እንዲሰሙ ወስነዋል፡፡

በመጀመሪያ ለመመስከር የቀረቡት ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም ናቸው፡፡ የህግ ምሩቅ መሆናቸውን፣ የህግ አማካሪ እና በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ መምህር መሆናቸውን ገልጸው በሩዋንዳ የዘር ማጥፋት ወንጀል አጣሪ ቡድን አባል ሆነው እንደሰሩ እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህግ አማካሪ ሆነው እንደሰሩ ገልፀዋል፡፡ ስለሽብር ወንጀል ምንነት እና ከዮናታን ፅሁፍ ጋር አያይዘው እንዲመልሱ ተጠይቀው፤ “የሽብር ወንጀል አስከፊ ነው፤ ከጦር ወንጀል እና ከዘር ማጥፋት ጋር የሚሰለፍ ነው፡፡ የሽብር ወንጀል ዓለም አቀፍ ወንጀል ነው፡፡ አንድን ሽብር ፈጣሪ የትኛውም ሃገር ቢሄድ የሚጠየቅ ነው የሚሆነው፡፡ በኬኒያ እና ሌሎች የአለማችን ክፍሎች በርካታ ህዝቦች ያለቁበትን ሁኔታዎች በአለም አቀፍ ሁኔታም የሽብር ድርጊት የሚባሉ ናቸው፡፡” ካሉ በኋላ የዮናታንን በፌስቡ ከጓደኞቹ ጋር ለመወያየት የፃፋቸው ሃሳቦች ከጠቀሷቸው አለም አቀፍ የሽብር ድርጊቶች ጋር አንድ ማድረግ የሽብርተኝነት ድርጊትን ማቃለል እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የፀረ ሽብር ህጉ ህገመንግስቱን እና ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ የተቀበለቻቸውን ህጎች እንደሚጥስም ተናግረዋል፡፡

ቀጥሎ ለመመስከር የቀረቡት ዶ/ር ዳኛቸው ናቸው፡፡ የህግ ፍልስፍና ትምህርት የተማሩ መሆናቸውን እና መምህር መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ እአአ ከ 1948 ዓ. ም. ጀምሮ የተካሄዱ አራት አለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን በመጥቀስ እነዚህ ድንጋጌዎች ማእከል ያደረጉት የመናገር መብትን መሆኑን እንዲሁም ንግግር በይዘቱ እንደማይፈተሽ እና ማንም ዜጋ ሃሳብ የማዋቀር መብት እንዳለው ድንጋጌዎቹ በግልፅ ያሰፈሩት ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰዋል -ዶ/ር ዳኛቸው፡፡ እነዚህን ህጎች ኢትዮጵያ ከመቀበል ባለፈ ከመጀመሪያው ጀምሮ በማርቀቁ ሂደት ተሳታፊም እንደነበረች ገልፀዋል። ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት መኖር ለመንግስት ቅቡልነትን እንደሚያመጣ ዲሞክራሲም የሚለካው በዚህ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ፅሁፉን አይቼዋለሁ፡፡ እምነቱን አሳይቷል፡፡ የራስክን አይዲዎሎጂ ፃፍክ ነው የሚለው ክሱ፡፡ እኔ እዚህ ሃገር ከመጣሁ ስምንት አመት ሆኖኛል፡፡ ስምንት አመት ሙሉ የራሴን አይዲዮሎጂ መንግስትን እየተቃወምኩ ስፅፍ ነበር፡፡ አልታሰርኩም፡፡ እሱም መታሰር አልነበረበትም፡፡ ልጁ [ዮናታን] የፃፈው ስህተት ሊሆን ይችላል፡፡ እኔ አስተማሪው ብሆን ፅሁፎቹን አይቼ ሲ እና ዲ ልሰጠው እችላለው፡፡ ያ ማለት ግን ወንጀል ሰርቷል ማለት አይደለም፡፡ መንግስት ጥሩ ነው የማለት መብት እንዳለ ሁሉ መንግስት ጥሩ አይደለም የማለት መብትም መኖር አለበት፡፡ ንግግር እና ፅሁፍን በመፍቀድ ከሚመጣው ችግር ንግግር እና ፅሁፍን በመገደብ የሚመጣው ችግር ይበልጣል፡፡” ካሉ በኋላ አቃቤ ህግ ፍርድ ቤት የመመስከር ፍቃድ አሎት ወይ ብሎ ሲጠይቃቸው፡ የትምህርት ዝግጅታቸውን፣ የስራ ልምዳቸውን እና ከዚህ ቀደምም በፍርድ ቤት መስክረው እንደሚያውቁ ገልፀው፤ ፍርድ ቤት ለመመስከር ፍቃድ የት እንደሚሰጥ አላውቅም፤ የሚሰጥ አካል አለ? የት ነው የማገኘው? በማለት በችሎት የነበረውን ሁሉ ፈገግ አሰኝተዋል፡፡

በሶስተኛ ደረጃ የሙያ ምስክርነቱን የሰጠው ጦማሪ እና አክቲቪስት በፍቃዱ ኃይሉ ነው፡፡ አቶ በፍቃዱ በማኔጅመንት ኢንፎርሜሽን ሲስተም የመጀመሪያ ዲግሪ እንዳለው፤ በመደበኛ (ህትመት እና ራዲዮ)፣ በማህበራዊ ሚዲያ እና የዜና ድህረገፆች ያለውን ልምድ ተናግሯል፡፡ማህበራዊ ሚዲያን ለመጠቀም እያንዳንዱ ሰው አካውንት ሊኖረው እንደሚገባ፤ የሚፅፉትንም ለማየት ጓደኞች ሊኖሩ እንደሚገቡ፤ መደበኛ ሚዲያ በዋነኝነት ለሽያጭ የሚቀርብ እና ከማህበራዊ ሚዲያ የበለጠ ተደራሾች እንደሚኖሩት፤ የዜና ድረገፅን ለመጠቀም ኢንርኔት አጠቃቀም ከማወቅ በዘለለ የግል አካውንት መፍጠር እንደማያስፈልግ ተናግሯል፡፡ ስለ ግለሰብ ፌስቡክ አካውንት፣ የፌስቡክ ፔጅ እና ፋን ፔጅ ልዩነቶች አስረድቷል፡፡ ዮናታን ስለፃፈው ፅሁፍ ተጠይቆ፤ ፅሁፎቹን እንደሚያውቃቸው፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራር እንደመሆኑ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ መወያየት እና መፃፍ እንደሚወድ ተናግሯል፡፡ በወቅቱ በነበረው ተቃውሞ በመንግስት የተገደሉ ወጣቶችን በመቃወም ሲፅፍ እንደነበር፤ እንዲያውም የወጣቶችን ደህንነት አደጋ ላይ ለመጣል እና ለማሸበር ሳይሆን በተቃራኒው የወጣቶችን ደህንነት ለማስጠበቅ ሲታገል እንደነበረ ተናግሯል አቶ በፍቃዱ፡፡

መንግስት ወጣቶችን ይገድላል ወይ ተብሎ ለአቶ በፍቃዱ ከዳኞች ለቀረበለት ጥያቄ፤ የመንግስት ፀጥታ አካላት ወጣቶችን መግደላቸው ዩንቨርሳል ትሩዝ እንደሆነ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ባወጣው ሪፓርት እንኳን 173 ሰዎች በፀጥታ አካላት መገደላቸው የተገለፀ መሆኑን ገልፇል። ይህን የሙያ ምስክርነት ለመስጠት ፈቃድ እንዳለው አቃቤ ህግ ጠይቆት፤ በአዲስ አበባ መስተዳደር በሚተላለፍ የራዲዮ ፕሮግራም ፕሮዳክሽን ማኔጀር ሆኖ እንሰራ፤ የውይይት የመፅሄት ዋና አዘጋጅ ሆኖ እንደሰራ፤ የሚፅፋቸው ፅሁፎች በአዘጋጅነት ይሰራበት የነበረውን የውይይት ጋዜጣን ጨምሮ የተለያዩ የህትመት ሚዲያዎች ላይ ይታተሙ እንደነበረ፣ ዞን ዘጠኝ የተባለ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚጦምር ቡድን አባል እንደሆነ እና በቅርቡም አዲስ ስታንዳርድ የሚባል የመፅሄት ድረገፅ ላይ ፅሁፍ እንደታተመለት በመግለፅ ልምዱን በአጭሩ አብራርቷል፡፡ ይህም ልምዱ በጉዳዩ ላይ ለመመስከር ብቁ እንደሚያደርገው ተናግሮ፤ “ምስክርነት ለመስጠት ፈቃድ የሚሰጥ አካል የለም” ብሏል።

በመቀጠል የምስክርነት ቃላቸውን የሚሰጡት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ አመራር የሆኑት አቶ ሙላቱ ገመቹ እና አቶ በቀለ ገርባ መሆናቸውን የተከሳሽ ጠበቃ አቶ ሽብሩ ተናግረው፤ በህዳር 2008 ዓ. ም. በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ አካባቢዎች የጀመረበትን ምክንያት እና የነበረውን ሁኔታ እንደሚያስረዱለት በጭብጥነት አሲዟል።

አቃቤህግ አሁንም በምስክሮቹ ላይ ተቃውሞ እንዳለው ለፍርድ ቤት አሳውቋል። ምስክሮቹ በህግ ጉዳይ ላይ መመስከር እንደማይችሉ እና ተገቢነት የሌለው መሆኑን በመናገር ምስክሮቹ እንዳይመሰክሩ ጠይቋል። የተከሳሽ ጠበቃ በበኩላቸው ይህን ጉዳይ በተመለከተ የምስክር መስማት ሂደቱ ሲጀምር ተመሳሳይ ጥያቄ አቃቤ ህግ አንስቶ ውሳኔ ተሰጥቶት ያለፈ ጉዳይ መሆኑን በተጨማሪም ምስክሮቹ የፓለቲካ ፓርቲ አመራር እንደመሆናቸው መጠን የሞያውቁትን የሰሙትን እና ያዩትን የሚመሰክሩ መሆናቸውን ገልፀው ምስክሮቹ የሚመሰክሩበትን ጭብጥ አግባብነት አስረድቷል። ዳኞች የግራቀኙን ክርክር አድምጠው የምስክሮቹን የሚመሰክሩበት ጭብጥ ይዘት በኋላ ላይ የሚመዘን በመሆኑ፤ ተከሳሽ እራሱን የመከላከል መብቱን ከመጠበቅ አንፃር ምስክሮቹ ቢሰሙ እንደሚሻል ጠቁመው የምስክሮቹ የመሰማት ሂደት እንዲቀጥል አዘዋል።

በቅድሚያ ለመመስከር የቀረቡት አቶ ሙላቱ ገመቹ ናቸው። አቶ ሙላቱ በ2008 ዓ. ም. ስለተነሳው ኦሮሚያ ስለተነሳው ተቃውሞ መንስኤ ስለሆነው ነገር ሲናገሩ፤ ከ2007 ዓ. ም. ምርጫ በኋላ ተቃውሞ እየበረከተ መምጣቱ፣ በኦፌኮ በኩል ሰላማዊ በሆነ መንገድ የተነሱትን ጥያቄዎች ለመመለስ ጥረት ሲደረግ እንደነበረ፣ ህዳር ወር ላይ 2008 ዓ. ም. በጊንጪ ከተማ የከተማው አስተዳደር 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የነበረውን ለመኖሪያ ቤት መስሪያ ወሰዱ መባሉን ተከትሎ ተማሪዎች ተቃውሞ እንደጀመሩ፤ ተማሪዎቹም ትምህርት ቤቱን ማስመለስ መቻላቸውን፤ የከተማው ስታዲየምም በተመሳሳይ መልኩ ተወስዶ ሲከፋፈሉት ተቃውሞ ተነስቶ እንደነበረ፤ የጭልሞ ጫካ ለባለሃብቶች መሸጥ ህዝብ ላይ ቅሬታ እንደፈጠረ እና ተቃውሞ እንደተነሳ፤ በዚህም ሳቢያ ከጊንጪ አካባቢ ብቻ 70 የኦፌኮ አባላት እንደታሰሩባቸው ገልፀዋል። ይሄ በእንዲህ እንዳለም የተቀናጀ ማስተር ፕላን የተባለው ፕላን ይተግበር መባሉ ብዙ ተቃውሞ ማስነሳቱን ገልፀዋል አቶ ሙላቱ።

ዳኞች ቀጣዩ ምስክር [አቶ በቀለ ገርባ] ጭብጡ ተመሳሳይ ስለሆነ አዲስ ነገር የሚመሰክሩት ከሌላ ባይሰሙ የሚል አስተያየት አቅርበው ነበር፤ ሆኖም ጠበቃ ሽብሩ ቀድመው ከመሰከሩት ምስክር [አቶ ሙላቱ ገመቹ] የተለየ ሚመሰክሩት እንዳለ በመናገራቸው ዳኞችም ባልተመሰከረበት የጭብጥ ሃሳብ ላይ ብቻ እንዲመሰክሩ አዘዋል።

በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ ማስተር ፕላኑን ተቃውመው እና ጭልሞ ጫካ ለግለሰቦች በመሰጠቱ ምክንያት እንጂ ዮናታን በፃፈው ፅሁፍ እንዳልሆነ አቶ በቀለ ገልፀዋል። በተጨማሪም ፅሁፎቹ ህዝቡ ያነሳው ተቃውሞ በሰላማዊ መንገድ እንዲመለስ ለማድረግ እንደሆነ ተናግረዋል።

የመከላከያ የምስክርነት ቃላቸውን ለመስጠት ቀርበው የነበሩት አባቱ ቀሲስ ተስፋዬ ረጋሳ፣ ጓደኛው አቶ ኤፍሬም፣ እህቱ ገዳምነሽ እንዲሁም ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በእለቱ ችሎት ለመስማት ጊዜ ስላለቀ በቀጣይ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ተነግሯቸዋል። በዛሬው ቀን ያልቀረቡት ምስክር ዶ/ር መረራ ጉዲና ያሉበትን ቦታ ጠበቃ ሽብሩ ከገለፁ በኋላ ዳኞች መጥሪያ እንዲደርሳቸው እና ፓሊስ በቀጣይ ቀጠሮ ቀን እንዲያቀርባቸው ትእዛዝ ሰጥተዋል።

ቀሪ መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 18 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀጠሮ ተይዟል።
ምንጭ፦ EHRP

%d bloggers like this: