Tag Archives: Addis Ababa

የሰኔ 15 ቀን ጥቃት ሰለባ አመራሮች የቀብር ስነ ሥርዓት ተፈፀም

(ዳጉሚዲያ) ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በባህርዳር እና አዲስ አበባ በተፈፀሙ ጥቃቶች ሰለባ የሆኑ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች መካከል የአማራ ክልል ፕሬዘዳንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ የክልሉ አደረጃጀት ዘርፍ አማካሪ አቶ እዘዝ ዋሴ እንዲሁም በአዲሴ አበባ የመከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታማዡር ሹም የነበሩት ጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ከአንድ ዓመት በፊት በጡረታ የተሰናበቱት ሜጀር ጀነራል ገዛዒ አበራ በዕለቱ ተገድለዋል። በዕለቱ በአማራ ክልል በደረሰው ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው የነበሩት የክልሉ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የነበሩት አቶ ምግባሩ ከበደ የህክምና ዕርዳታ ቢደረግላቸውም ሰኔ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ በጥቃቱ መንግሥት ጠርጥሬያቸዋለሁ ያላቸው የክልሉ የሰላምና ደህንነት ጉዳይ ኃላፊ የሆኑት ብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ በፌደራል ፖሊስና መከላከያ በተወሰደባቸው ወታደራዊ ጥቃት ሰኔ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. መገደላቸውን መንግሥት አስታውቋል።

Amhara regiona victim leaders
ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ ብጀነራል አሳምነው ጽጌ፥ አቶ ምግባሩ ከበደ እና አቶ እዘዝ ዋሴ (ፎቶ፡ ከማኀበራዊ ሚዲያ)

ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት በአዲስ አበባ በጄነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜጀር ጀነራል ገዛዒ አበራ ግድያ ግድያ ተጠርጣሪው የጀነራል ሰዓረ መኮንን የግል ጠባቂ የአስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ ነው ሲል ይፋ አድርጓል። ይሁን እንጂ ተፈፀሙ ለተባሉ ጥቃቶች መንግሥት “መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ነው” በሚል ለዓለም ይፋ ቢያደርግም የጥቃት አድራሾችን፥ ጥቃቱን እና ምክንያቱን በተመለከተ ርስ በርሱ የተጣረሰ የአንድ ወገን መረጃ ብቻ በመሆኑ ይህ እስከተጠናቀረበት ድረስ ሁኔታውን በተመለከተ ከጥቃቱ ተርፈናል ከሚል አራት የአማራ ክልል አመራሮች በስተቀር ከተጠርጣሪዎችም ሆነ ከገለልተኛ አካል የተሰጠ ምላሽም ሆነ ማረጋገጫ የለም። ጥቃቱን ተከትሎ ከከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ግድያ በተጨማሪ ቁጥራቸው ያልተገለፀ ሌሎችም በርካታ ዜጎች መገደላቸውንም የአማራ ክልል የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰማኽኝ አስረስ ለሮይተርስ ገልፀዋል።

በጥቃቱ ህይወታቸው ያለፈ አመራሮች ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ አቶ ምግባሩ ከበደ እና አቶ እዘዝ ዋሴ ሰኔ 19 ቀን 2011 ዓ ም በባህርዳር ከተማ አባይ ማዶ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የቀብር ሥነ ሥርዓታቸው የተፈፀመ ሲሆን፤ የብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ በትውልድ ከተማቸው በላሊበላ አብያተ ቤተክርሥቲያናት በቤተ ጊዮርጊስ የቀብር ስፍራ ተፈፅሟል። በተመሳሳይም ጥር 20 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀን የጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜጀር ጀነራ ገዛዒ አበራ የቀብር ሥነሥርዓት በመቀሌ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል።
General Seare and M.General Gezae
ጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜ/ጀነራል ገዛዒ አበራ (ፎቶ፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ)

የአመራሮችን ግድያ እና የቀብር ሥነ ሥርዓት ቢያሳውቅም፤ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ የወታደራዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ በርካታ ዜጎች ቢኖሩም መንግሥት እስካሁን ቁጥራቸውንም ሆነ ማንነታቸውን አልገለፀም። መንግሥት ቀደም ሲል ጥቃቱን “መፈንቅለ መንግሥት ነው፥ የአዲስ አበባው ከባህርዳሩ ጥቃት ጋር የተያያዘ ነው” በሚል በጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ ኃላፊዎች እና በፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነሩ የተገለፀ ቢሆንም፤ ዛሬ ሰኔ 21 ቀን 2011 ዓ ም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ ቢልለኔ በበኩላቸው “የአዲስ አበባው ከባህር ዳሩ ጥቃት ጋር ስለመያያዙ ገና ይጣራል።” ሲሉ ገልፀዋል። በተለይ የባህርዳሩን እና የአዲስ አበባውን የባላሥልጣናት ግድያ በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ቃል አቀባይ ኃላፊዎች እና ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነሩ የሰጡት መግለጫዎች ርስ-በርስ የሚጣረሱ በመሆናቸው፤ መንግሥት እየሰጠ ያለው መረጃ ተዓማኒነት ላይ በርካቶች ጥርጣሬ እንዳላቸው እየገለፁ ይገኛሉ።

በሌላ በኩል ፤ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በበኩሉ በመተከል ዞን ሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ ም ከ 30 በላይ ሰላማዊ ዜጎች ባልታወቁ ታጣቂዎች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።

መንግሥት ባህርዳሩን እና የአዲስ አበባውን ጥቃት ተከትሎ በርካታ ዜጎችን እያሰረ ሲሆን፤ ከነዚህ መካከል የአማራ ክልል የፀጥታ ዘርፍ አመራሮች፥ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አመራሮች እና አባላት፥ በጋዜጠኛ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ የሚመራው የአዲስ አበባ ባላደራ ምክር ቤት (ባልደራስ) አመራር አባላት፥ ጋዜጠኞች እና የፀጥታ ዘርፍ አባላት እና ሰኣላማዊ ጄጎች በጅምላ መታሰራቸው ታውቋል። እስካሁን ባለው መረጃ ከ300 በላይ ዜጎች በጅምላ እንደታሰሩ መረጃዎች ቢጠቁሙም፤ ሌሎች ምንጮች ደግሞ የእስካሁኑ የጅምላ እስር በሺህዎች የሚቆጠር እንደሚሆን ይገምታሉ። ይህንንም ተከትሎ በርካታ ሰዎች በማኀበራዊ ሚዲያ ላይ መንግሥት የአማራ ማኅበረሰብ ልሂቃን ላይ ያነጣጠረ የጅምላ እስር እየተፈፀመ ነው ሲሉ የኮነኑት ሲሆን መንግሥትም በግፍ በጅምላ ያሰራቸውን ዜጎች እንዲፈታ፥ ያለውን እውነታም ለህዝብ ግልፅ እንዲያደርግ ተጠይቋል።

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው አንድ ዓመት ከ6 ወር እስር ተፈረደበት

(አዲስ ሚዲያ) የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በፌደራል አቃብ ህግ በተመሰረተበት ክስ ከአንድ ዓመት ከ አምስት ወር እስር በኋላ የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አዲስ አበባ ልደታ ምድብ ችሎት ግንቦት 18 ቀን 2009 ዓ. ም. የ 1 ዓምት ከ 6 ወር የቅጣት እስር ፈርዶበታል።

Getachew Shiferaw

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

ጋዜጠኛው ከህዳር 2008 ዓ. ም. ጅምሮ የነበረውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ሲታሰር፥ ቀደም ሲል የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶበት የነበረ ቢሆንም፤ በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ ክሱን ወደ መደበኛ ወንጀል ክስ ዝቅ በማድረግ አመፅ ማነሳሳት በሚል ክስ የቅጣት ውሳኔውን ማሳለፉን አሳውቋል። ይሁን እንጂ ጋዜጠኛው ለተላለፈበት የቅጣት ውሳን ብይን የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ፍርድ ቤቱ ቢጠይቀውም ጋዜጠናው ባልሰራሁት ወንጀል የምጠይቀው የቅጣት ማቅለያ የለም በማለት የፍርድ ቤቱን ጥያቄ ውድቅ ማድረጉ ታውቋል።

ጋዜጠኛው ክስ የተመሰረተበትና የ1 ዓመት ከ6 ወር እስር ቅጣት የተጣለበት፤ በፌስ ቡክ ማኅበራው ሚዲያ በውጭ ከሚገኝ ጋዜጠኛ በተለይም መቀመጫውን ዋሸንግተን ዲሲ ካደረገው ጋዜጠኛ አበበ ገላው ጋር መልዕክት ተለዋውጠሃል፥ አመፅ ቀስቅሰሃል የሚል እንደነበር የቀረበበት ክስ አመልክቷል።

ጋዜጠኛው ህትመቱና ስርጭቱ በመንግሥት እንዲቋረጥ ከተደረገው የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ከማገልገሉ በተጨማሪ በተለያዩ መፅሔቶች፥ ጋዜጦችና ድረ-ገፆች ላይም የተለያዩ ፖለቲካዊ፥ ሰብዓዊ መብትና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደረጉ በርካታ ፅሑፎችንም ያበረክት እንደነበር ይታወቃል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰኔ 2006 ዓ ም በመንግሥት እውቅና ተነፍጎት አባላቱና አመራሩ ምንም ዓይነት የስራ እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ እግድ የተጣለብት የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ (ኢጋመ) መስራችና አስተባባሪ እንደነበር ይታወቃል።

ጋዜጠኛ ጌታቸው ከታህሳሥ 15 ቀን 2008 ዓ ም ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛል።

በተለይ መንግሥት ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ በወሰደው ርምጃ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራውን ጨምሮ፥ ሌሎች ጋዜጠኞችና 60 ሺህ ያህል ሰላማዊ ዜጎች መታሰራቸውን የሀገርው ውስጥ የሰብዓዊ መብት አራማጆችና ተሟጋቾች መረጃ አመልክቷል።

የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረውና የመብት አራማጅ ዮናታን ተስፋዬ 6 ዓመት ከ6 ወር እስራት ተፈረደበት

(አዲስ ሚዲያ) የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፥ የ2007 ዓ. ም. በአዲስ አበባ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩና የመብት አራማጅ ወጣት ዮናታን ተስፋዬ ግንቦት 17 ቀን 2009 ዓ ም በዋለው ችሎት 6 ዓመት ከ6 ወር እስር ተፈርዶበታል።

yonatan-tesfaye

ዮናታን ተስፋዬ

ወጣት ዮናታን ከህዳር 2008 ዓ. ም. ጀምሮ የተነሳውን ህዝባዊ አመፅ ተከትሎ ከታሰሩት በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና የመብት ተሟጋቾች መካከል አንዱ ነው።

ወጣት ዮናታን ተስፋዬ ደም ልገሳን ጭምሮ በተለያዩ ግብረ ሰናይ ተግባራት ላይም ይሳተፍ የነበረ ቢሆንም፥ ከታህሳሥ 17 ቀን 2008 ዓ ም ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛል።

የፌደራል አቃቤ ህግ ክስ የመሰረተበት በፌስ ቡክ ማኅበራዊ ገፅ መንግሥት በዜጎች ላይ እየወሰደ የነበረውን ርምጃ የሚቃወሙና የሚተቹ ፅሑፎችን ፅፏል በሚል እንደሆነ የተመሰረተበት የክስ ሰነድ ያመለክታል።

በመጨረሻም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአዲስ አበባ ልደታ ምድብ ችሎት ግንቦት 17 ቀን 2009 ዓ ም በዋለው ችሎት በፌስ ቡክ ማኅበራዊ ገፅ የፃፋቸውን ፅሑፎች ብቻ እንደመረጃና ማስረጃ በመጠቀም 6 ዓመት ከ6 ወር እስራት ፈርዶበታል።

የዳዊት ፈተና

Befekadu Hailu

በፈቃዱ ሃይሉ

አዋሽ ሰባት በነበረኝ “የተሀድሶ” ቆይታዬ ተዋውቄያቸው ከወደድኳቸው ሰዎች መካከል ሁለት ዳዊት በሚል ሥም የሚጠሩ ወጣቶች ነበሩበት። አሁን የማጫውታችሁ ግን ስለ ዲያቆኑ ዳዊት ነው። ዲያቆን ዳዊት ተወልዶ ያደገው ትግራይ ውስጥ ነው። የሚያገለግለው ሥላሴ ካቴድራል ነው። የፖለቲካ ተሳትፏቸው እምብዛም እንደሆኑትና በአዲስ አበባ እንደሚኖሩት አብዛኛዎቹ የትግራይ ተወላጆች የሚያውቀውም፣ የሚያምነውም፣ የሚወደውም ኢሕአዴግን ብቻ ነበር።

“ነበር” ያልኩት ያለምክንያት አይደለም። እንዳጋጣሚ ሆኖ፣ ዲያቆን ዳዊት የተመደበው ኢያስጴድ እና እኔ የነበርንበት (20 ምናምን ሰው የነበረበት) የውይይት ቡድን ውስጥ ነበር። ቡድናችን በፍርሐት ታዝቦ የሚያልፈው ነገር አልነበረውም። በውጤቱ ደግሞ የውይይቱ አባላት በሙሉ የተሰላ ምላጭ ሆነዋል ማለት ይቻላል። ታዲያ ዲያቆን ዳዊት አንድ ቀን ግምገማ ላይ “ከዚህ በፊት የነበራችሁ ዕውቀት ምን ይመስላል? አሁንስ ምን ተማራችሁ?” የሚል ጥያቄ ሲነሳ፣ “እኔ እዚህ ከመምጣቴ በፊት ኢሕአዴግን ብቻ ነበር የማውቀው፤ ቅዱስም ይመስለኝ ነበር። አሁን ግን ብዙ ነገር ሰምቻለሁ። ብዙ በደል እንደሚፈፅም አውቄያለሁ። ሰነዶቹን የሚያዘጋጁት ሰዎች ዕውቀትም እዚህ ከሚታደሱት ሰዎች ዕውቀት ያነሰ መሆኑን ተምሬያለሁ” ብሎ እርፍ አለ።

ዳዊት በጣም ጥሩ ሰው እንደሆነ ከቀረቤታው ያስታውቃል። ኢሕአዴግንም ሲመለከተው የኖረው በየዋህነት ይመስላል። “እንዴት ታሰርክ?” ብዬ ስጠይቀው፣ “እኔ ራሴ ላይ ቀለም አብዮት ታውጆብኛል” አለኝ። አከአዲስ አበባ የተጋዙት ብዙዎቹ የሆነ ፀበኛዬ ቂም በቀል መወጫ ሆኜ ነው የመጣሁት ብለው ያምናሉ – በጥቆማ። ዲያቆን ዳዊትም የሚያምነው እንዲያው ነው። ምናልባት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባለ ፉክክር መጥቶ ይሆናል ብዬ ገምቼ፣ “እንዴት ነው ቤተክርስቲያኖቹ የአማራ እና የትግሬ ተብለው ተከፋፍለዋል የሚባለው እውነት ነው?” ብዬ ጠየቅኩት። “ከፖለቲካው አይብስም ብለህ ነው?” አለኝ።
ዲያቆን ዳዊት እኔና ኢያስጴድን ትግራይ ወስዶ ሊያስጎበኘን ቃል ገብቷል። ምክንያቱ ደግሞ ‘የአንድ ብሔር የበላይነት’ የሚል ነገር ስንናገር በመስማቱ ነው። ጉዳዩ ግን በተሐድሶው ወቅት ተፈርቶ በደንብ ያልተወራ ጉዳይ ነው።

ኮማንደር አበበ፣ ራሳቸው የትግራይ ተወላጅ የሆኑ፣ ከስድስቱ ለመጨረሻዎቹ ሦስት የሥልጠና ሰነዶች የኃይል (አማርኛ ተናጋሪዎች ሁሉ የተሰበሰብንበት) መድረክ መሪ (መዝጊያ ንግግር አድራጊ) ነበሩ። አንድ ቀን፣ በግምገማ ወቅት ተጠይቀው መልስ ያላገኙ ጉዳዮችን ሰብስበው መጡ። ከጉዳዮቹ አንዱ “በኢትዮጵያ የአንድ ብሔር የበላይነት አለ” የሚለው ነበር። ኮማንደሩ “መልስ ለመስጠት ጥያቄው ቢብራራልኝ፣ የቱ ብሔር ነው በየቱ ላይ የበላይ የሆነው?” አሉና ጠየቁ። ዝምታ።

ፈራ ተባ እያልኩ እጄን አውጥቼ “የሚባለው የትግራይ የበላይነት እንደሆነ፣ ነገር ግን አባባሉ የትግራይ ገበሬ የኦሮሞን ወይም የአማራን ገበሬ ይጨቁናል፣ ወይም የበላዩ ይሆናል ማለት ሳይሆን፣ የልሒቃኑ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ አመራር እና በማበብ ላይ ያሉ ቢዝነሶች ላይ ያለውን የበላይነት እንደሚመለከት” አስረዳሁ። ከዚያ በኋላም ብዙ አስተያየቶች ተከተሉ። ለምሳሌ አንድ የገረመኝ አስተያየት ሰጪ (በሙያው መምህር የሆነ ወጣት) በእናቱ ትግሬ መሆኑን ገልጦ፣ “ምናልባት የሚፈቱኝ ከሆነ ብዬ የተያዝኩ ዕለት ጣቢያ ብሔር ስጠየቅ ‘ትግሬ’ ልል ነበር፤ አፍሬ ተውኩት” ብሎ አማረረ። በመቀጠልም፣ “እንዲያውም፣ እዚህ ከመጣነው ውስጥ በናቱም ባባቱም ትግሬ የሆነ ሰው የመጣ አይመስለኝም፤ ያውም አምስት የምንሞላ አይመስለኝም” አለ። ነገር ግን ይህ አካሔድ የትግራይን ተወላጅ ሁሉ እየጠቀመ አለመሆኑን ሲያስረዳ “እናቴ የጋራ ኩሽናችንን ተጠቅማ በሌሊት እንጀራ ስትጋግር በመቀደሟ የተናደደችው ጎረቤታችን ‘ምን ይደረግ እሷ የዘመኑ ሰው ናት’ ስትል ሰምቼ በጣም ነበር ያዘንኩት” በማለት አስረዳ።

ኮማንደር አበበ “እውነቱን ልንገራችሁ” አሉን፣ “ለዚህ ሁሉ ‘ሁከትና ብጥብጥ’ መንስኤ የሆነው ይሄ አስተሳሰብ ነው። ጠላቶቻችን ለዓመታት በኢሳት እና ኦኤምኤን እንዲሁም በፌስቡክ ሲያራግቡት የነበረው የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ውጤት ነው ይሄ” አሉ። “የትግራይ ሕዝብ፣ እንዲያውም ሕወሓት ለራሱ ትልቅ ቆርሶ ወሰደ እንዳይባል በይሉኝታ እየተበደለ ያለ ሕዝብ ነው” በቁጭት ስሜት ሊያስረዱን ሞከሩ። “በርግጥ፣” አሉ “የትግራይ ተወላጅ ሆነው ሙሰኞች አሉ፣ ሌቦች አሉ፤ ነገር ግን የኦሮሞ ተወላጅ ሌቦችም አሉ፣ የአማራ ተወላጅ ሌቦችም አሉ። በጥቂት ሰዎች ሥም የአንድ ብሔር ሕዝብ መወቀስ የለበትም”።
በማግስቱ ዲያቆን ዳዊት ከኮማንደሩ የተሻለ የነገሩን ውስብስበነት አስረዳኝ። ዳዊት “እኔ በጦርነቱ ጊዜ አባቴን አጥቻለሁ፤ አሁን ደግሞ የትግራይ ተወላጅ ስለሆንኩ ብቻ በሕወሓት ጥፋት አብሬ እወቀሳለሁ። ያገኘሁት ጥቅም ምንድን ነው?” ነበር ያለኝ።

ዲያቆን ዳዊት ግቢው ውስጥ ከብዙዎቻችን የተሻለ የመንቀሳቀስ ነጻነት ነበረው። ማታም ግቢው ውስጥ አምሽቶ እንደሚገባ የክፍሉ ልጆች ነግረውኛል። ይህንን ነጻነት ጠይቆ አላመጣውም። የአነጋገር ዘዬው ላይ የትግርኛ ቅላፄ መኖሩ ያጎናፀፈው ዕድል ነው። በጊቢው ውስጥ ካሉ ጥበቃዎች ውስጥ በጣም ቁጡ የሚባሉት የትግራይ ተወላጆች መሆናቸው አነጋጋሪ ነበር። እነሱ ዲያቆን ዳዊት ላይ ቁጣቸው ይበርዳል። እኛ ክፍል ከነበረው ሌላኛው ዳዊት ጋር ስናወራ “የነሱ ክፋት የግላቸው እንጂ የወጡበት ማኅበረሰብ በውክልና የሰጣቸው ስላልሆነ የነርሱን ለነርሱ እንተወዋለን” እንባባል ነበር። ለምሳሌ ኃይሌ የሚባለው የኛ ክፍል ኃላፊ የአዲስ አበባዎቹ ‘ሠልጣኞች’ ከሔድን በኋላ መምታት በኮማንድ ፖስቱ ልዑካን ቡድን በመከልከሉ የተቆጨ ይመስላል። የውይይት ተሐድሶው የሚለውጠን ስላልመሰለው ማታ ማታ እየመጣ ይቆጣንና ይመክረን ነበር። አንዴ እንዲያውም፣ ዘላችሁ ዘላችሁ ያው የምታርፉት መሬት ነው ለማለት የእንግሊዝኛ ተረት ተርቶ በሳቅ ገድሎናል፤ “ራቢት ጃምፒያ ጃምፒያ ቱ ኧርዝ” ነበር ያለን ቃል በቃል። የእነ ኢያስጴድ ክፍል ኃላፊ ደግሞ አብርሃም ነበር። ኃይሌም አብርሃምም በጣም ከሌሎቹ ጠባቂዎች ሁሉ በጥላቻ እና በክፋት ነበር የሚያዩን።

አንድ ቀን ማታ ሜዳ ላይ ተኮልኩለን ቲቪ ስናይ ጥቂቶች ወንበር እያመጡ ሲቀመጡ እኔም ወንበር አምጥቼ ተቀመጥኩ። ሌሎቹ ምንም አይሉም፤ አብርሃም ግን “ወንበሩን መልሱ” እያለ መጥቶ አንዴ ዠለጠኝ። በጣም ተናድጄ ቻልኩት። ስመለስ ዲያቆን ዳዊት እና ሌላ አንድ ተመሳሳይ ሰው ከወንበራቸው አልተነሱም። የባሰ ተናደድኩ እና የማይገባ ቃል ተናገርኩ። ዲያቆን ዳዊት “ወንበሩን ካልለቀቅኩልህ” አለኝ፤ እምቢ አልኩት። በማግስቱ መጥቶ ሲያናግረኝ፣ በቋንቋ ላይ ተመሥርቶ አብርሃም እንደበደለኝ ነገርኩት። “የምርቃታችን” ዕለት አብርሃም ጠራኝና ይቅርታ ጠየቀኝ። ነገሩን ያደረገው “በሆነ ብስጭት” ተነሳስቶ እንደሆነና “ቂም ይዤ እንዳልሔድ” ጠየቀኝ። ይቅርታ መጠ‘የቅ ደስ ይላል። ቂም ይዤበት ነበር ለማለት ግን ይከብዳል። ነገር ግን ክፉው አብርሃም ይቅርታን ኬት አመጣው ብዬ ዳዊትን ጠየቅኩት። “አናግሬው ነበር” አለኝ። “የሠራው ሥራ ጥፋት እንደሆነ ይቅርታ መጠየቅ እንዳለበት አሳምኜዋለሁ” አለኝ። አሪፍ ነው።

ዳዊት ወደትግራይ ሊወስደኝ ቃል የገባው የሕዝቡን ድህነት እና ሰው ወዳድነት ሊያሳየኝ ፈልጎ ነው። እኔም ይሄንን አልክድም። ምናልባት እሱ ያልገባው፣ እሱ በአነጋገር ዘዬው ብቻ ያገኘውን ተቃራኒው ለኔ መሰሎቹ እየተሰጠን እንደሆነ ነው። እሱ እንደልቡ ጊቢው ውስጥ መንቀሳቀስ ሲፈቀድለት የኔብጤዎቹ ለምነንም ማግኘት አልቻልንም ነበር። እሱም እዚያ የነበረው በግፍ ነው። ይሁን እንጂ ሌሎቻችንም በተመሳሳይ ሁኔታ ከመያዛችን አንፃር እሱ ቢያንስ ግቢው ውስጥ ሲኖር በፍርሐት ተሸማቆ አልነበረም። ይሄን ችሮታ (entitlement) ዲያቆን ዳዊት ከነበፍቃዱ ተነጥቆ ይሰጠኝ አላለም፤ ነገር ግን ለሱ ችግር ስላልነበር አልታየውም። በተጨማሪም ይሄን መሰል አድሎ የትግራይ ሕዝብ ባርኮ አላፀደቀውም። ነገር ግን ተመልካች ይሄን ያመዛዝናል? የማመዛዘን ግዴታስ አለበት?

ሕወሓት/ኢሕአዴግ እታደሳለሁ ካለ መጀመሪያ ይህን ዓመሉን ይሻር እና በአዲስ የተሻለ አመል ይተካው። መልካም አስተዳደር ለማግኘት የአነጋገር ዘዬ የሚያደርገው ያልተጻፈ አዎንታዊም አሉታዊ አስተዋፅዖ ይቀረፍ።

በአዲስ አበባ የኮሌራ በሽታ አስጊ ደረጃ ላይ መድረሱን የተባበሩት መንግሥታት የውስጥ መልዕክት ልውውጦች አጋላጡ

(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የአካባቢ ንፁህና ጉድለት ችግር ምክንያት ከተከሰተው አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) የከተማዋ ነዋሪዎችን ጤና ማናጋት ከጀመረ ሶስተኛ ሳምንቱን አስቆጥሯል፡፡ በንፁህ የውሃ አቅርቦት እና በአካባቢ ንፁህና ጉድለት ምክንያት የሚከሰተው የኮሌራ በሽታ በከተማው መዛመት፤ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሰራተኞችን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎችን ለከፋ በሽታ መዳረጉ ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በከተማዋ ለሚገኙ ለሌሎች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰራተኞች ባሰራጨው የውስጥ መልዕክት መሰረት፤ ሰራተኞቹ የኮሌራ ክትባት እንዲወስዱ አሳስቧል፡፡ በተለይ ኮሌራ በተበከለ ምግብና ውሃ አማካኝነት የሚዛመትና በንፁህና ጉድለት የሚከሰት በሽታ ሲሆን፤ ወዲያውኑ ተገቢውን ህክምና በጤና ተቋማት ማድረግ ካልተቻለ፤ በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የሰውነትን ፋሳሽ በመሳጣት ለሞት እንደሚዳርግ ይታወቃል፡፡

Addis-Ababa-Water-and-Sewerage-Authority

በሽታውን በተመለከተ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሀገር ቤት በመንግሥት ቁጥጥር ስር ለሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ፤ አተት የተከሰተው የወንዝ ውሃ በሚጠቀሙ ዜጎች ላይ እንደሆነ እና ለዚህም በወንዝ ዳር አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች የመፀዳጃ እና ፍሳሽ ማስወገጃዎቻቸውን ከወንዝ በማገናኘታቸው እንደሆነ በቃል አቀባዩ አህመድ ኢማኖ በኩል አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር የንፁህ የመጠጥ ውሃ ተገቢው ቁጥጥርና ክትትል ባለመደረጉ እና በከተማዋ በተከማቸው ቆሻሻ አማካኝነት እንደሆነ የከተማዋ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ምንጮች ማረጋገጣቸው ተነግሯል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የከተማው የንፁህ መጠጥ ውሃ ጥራት ባልተጠበቀበት ሁኔታ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የከተማው ነዋሪ በመጪው 2009 ዓ.ም. ከዚህ ቀደም ከሚከፍለው የቧንቧ ውሃ ተጨማሪ ክፍያ ማሻሻያ ሊጣልበት እንደሆነም ሪፖርተር ጋዜጣ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የአዲስ አበባ ደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃነት በ1 ቢሊዮን ወጪ በሰንዳፍ ተገንብቷል ቢባልም፤ ሰራ የተባለው ግንባታ ወጪ ከግንባተው ጋር አብሮ ሊድ እንዳይመችል የተጠቆመ ሲሆን፤ ይልቁንም በአካባቢው ያሉ የሰንዳፋ ነዋሪዎች ከአካባቢ ብክለት በሚመጡ በሽታዎች እንዲጋለጥ በማድረጉ፤ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በከፍተኛ ወጪ ተሰራ በሚባለው ሰንዳፋ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ እንዳይደፋ ተቃውሞና እገዳ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአዲስ አበባ አስተዳደር ለደረቅ ቆሻሻ መጣያ ባለመኖሩ መፍትሄ ባለማበጀቱ ከዚህም በኋላ አዲስ አበባን ለውሃና አየር ወለድ በሽታ ሊያጋልጥ እንደሚችል ተሰግቷል፡፡ የከተማው መስተዳደር ከሰንዳፋ ነዋሪዎች ጋር ቀደም ሲል ያለምንም ድርድርና ምክክር አለመገንባቱ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የጥራት ችግር ያለበት በመሆኑ ነዋሪውን ለበሽታ በማጋለጡና ተቃውሞ በመቅረቡ አስተዳደሩ ሌላ መፍትሄ እስኪያዘጋጅ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በየመንደሩ ባለበት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ ይህም ከወቅቱ የክረምት ዝናብ ጋር ተዳምሮ በቀላሉ ወደተለያዩ የከተማው ወንዞችና ጉዳት ወደደረሰባቸው የንፁሃ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች በመቀየጥ፤ አሁን ከተከሰተው የኮሌራ በሽታ በተጨማሪ ለተለያየ ውሃ ወደለድ በሽታ ሊያደርግ እንደሚችል የአስተዳደሩ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ባለሙያዎች ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡

እንደ ከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ ገለፃ ከሆነ፤ በከተማ እየሰሩ ባሉ መሰረተ ልማት እና የተለያዩ የግል ግንባታዎች ምክንያት በርካታ የንፁህ የመጠጥ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች ከጥቅም ውጭ ሆነው ከከተማ ፍሳሽ ማስወገጃ ጋር በመገናኘታቸው እንደሆነ እና ችግሩንም በአጭር ጊዜ ለማስተካከል አስቸጋሪ እንደሆነ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ አስታውቀዋል፡፡ ስለሆነም፤ ችግሩ እስኪቀረፍ የከተማው ነዋሪ አቅሙ የፈቀደ ከከተማው የባንቧ ውሃ ከመጠቀም ተቆጥቦ ሌሎች አማራጮችን አሊያም ውሃን በደንብ አፍልቶ በማቀዝቀዝ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡ በተጨማሪም፤ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ምልክት የታየባቸው ሰዎች በአስችኳይ በአቅራቢያቸው ወዳለ የህክምና ጣቢያ እንዲሄዱና ተገቢውን የህክምና ክትትል እንዲያደርጉ መክረዋል፡፡

በተከሰው የኮሌራ ወረርሽን በሽታ በርካታ ህፃናትና እናቶች ሰለባ ሆነው በከተማዋ ባሉ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ተኝተው ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በበሽታው ታመው የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ከሚገኙ የከተማው ነዋሪዎች በስተቀር ህይወታቸው ያለፈ ስለመኖሩ እስካሁን የተገረጋገጠ መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ መንግሥት በስታውን እና መንስዔውን ከመገናኛ ብዙኃን ለመደበቅ ቢሞክርም፤ ዓለም ተቋማት የሚሰሩትን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎች የችግሩ ሰለባ በመሆናቸው በየ ህክምና ተቋሙ የሚሰጡ ውጤቶች ላይ ኮሌራ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ እንዳይወጣ ያደረገው ጥረት በህክምና ባለሙያዎች ሊጋለጥ ችሏል፡፡ መንግሥት ችግሩን ለመሸፋፈን ከመሞከርና ከማስተባበል ባለፈ እየወሰደ ስላለው የማስተካከያ ርምጃ በግልፅ ያለው ነገር የለም፡፡

%d bloggers like this: