Tag Archives: Ethiopian press freedom

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ የተፈረደበትን ፅኑ እስራት ጊዜውን አጠናቆ ወጣ

የቀድሞው ፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ተፈርዶበት የነበረውን የ3 ዓመት ፅኑ እስራት አጠናቆ በጣ። ጋዜጠኛው የእስር ጊዜውን ካጠናቀቀ ሁለት ቀናት ቢያልፉትም፤ ዛሬ ጥቅምት 5 ቀን 2010 ዓ.ም. መለቀቁ ታውቋል።

journalist-temesgen-desalegn

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ    ፎቶ_ ከማኅበራዊ ገፅ
ጋዜጠኛው ከመታሰሩ በፊት በባለቤትነት እና በዋና አዘጋጅነት ከሚያስተዳድረው ፍትህ ጋዜጣ በተጨማሪ፥ በልዕልና ጋዜጣ፥ በአዲስ ታየምስ እና በፋክት መፅሔቶች ላይም በቋሚነት ይፅፍ እንደነበር ይታወቃል።

ጋዜጠኛ ተመስገን ለእስር የተዳረገውም ቀደም ሲል በፍትህ ጋዜጣ በፃፋቸው ፅሑፎች እንደነበር ቀርቦበት የነበረው የክስ ሰነድ ያስረዳል።

በኢትዮጵያ ምንም እንኳ ጋዜጠኛ ተመስገን የተፈረደበትን የእስር ጊዜ አጠናቆ ቢወጣም ፤ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬን ጨምሮ ሌሎች ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች አሁንም ድረስ በእስር ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል።

ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ የይግባኙን ጉዳይ በተመለከተ ለሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታ አቀረበ

የቀድሞው የአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በ2003ዓ.ም. ሰኔ ወር ላይ ከሌሎች 4 ሰዎች ጋር (ጋዜጠኛ ኤልያስ ክፍሌ፣ ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ፣ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሄር እና ወ/ሮ ሂሩት ክፍሌ) የፀረ ሽብርተኝነት ህጉን ተላልፈሃል ተብሎ ክስ ተመስርቶበት የነበረ ሲሆን፤በዚህም የ14 አመት የእስር ቅጣት እንደተወሰነበት የሚታወስ ነው።

Journalsit Woubeshet Taye
ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ

ቅጣቱ ከተላለፈበት በኋላ ጥፋተኛ መባሉን በመቃወም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ቢልም መዝገቡ በይቅርታ ጉዳይ እየታየ መሆኑ ተገልፆለት በወቅቱ ይግባኝ ማለት ሳይችል ቀርቷል። ከእርሱ ጋር የይቅርታ ጥያቄ ያቀረቡ የስዊድን ጋዜጠኞች እና በተመሳሳይ መዝገብ የምትገኘው ሂሩት ክፍሌ ከእስር የተለቀቁ ሲሆን፤ የጋዜጠኛ ውብሸት የይቅርታ ጉዳይ ግን እስካሁን ድረስ ተፈፃሚ አልሆነም።

በመሆኑም በቅርቡ በወንጀለኛ መቅጫ ስነስረዓት ህጉ አንቀፅ 191 ስር በተመለከተው መሰረት የይግባኝ ጊዜ ካለፈ በኋላ ይግባኝ ለማቅረብ ፈቃድ ለማግኘት የሚቀርብ ማመልከቻ በማስገባት ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኙን አቅርቦ ነበር። የወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህጉ አንቀፅ 196 (1) እና (2)፤ የተፈረደባቸው ብዙ ሰዎች ሆነው አንዱ ብቻ ይግባኝ ያቀረበ እና የተጠቀመ [ከእርሱ ጋር አብራ የተከሰሰችው ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ከጋዜጠኛ ውብሸት ጋር ተመሳሳይ የቀረበባት እነወዲሁም የስር ፍርድ ቤት 14 ዓመት ከፈረደባት በኋላ በይግባኝ ወደ 5 አመት እንደተቀነሰላት ይታወቃል።] እንደሆነ ሌሎቹም ይግባኝ እንዳሉ እንደሚቆጠር እንደሚደነግግ በመጥቀስ ነው ይግባኙን ያቀረበው። ይግባኙን የተመለከተው ይግባኝ ሰሚ ችሎት የይግባኙን አቤቱታ ሳይቀበለው ውድቅ አድርጎበታል። ጋዜጠኛ ውብሸትም ይግባኝ ሰሚ ችሎት መሰረታዊ የህግ ስህተት በመጣስ ይግባኙን እንዳልተቀበለው በመግለፅ ያቀረበው አቤቱታ ዛሬ ሰበር ሰሚ ችሎት ቀርቦ ነበር። ዳኞች ጉዳዩን መርምረው ብይኑን ሰኔ 12 ቀን 2009 ዓ ም ቀን እንደሚያደርሱ እና ውሳኔውን ከመዝገብ ቤት ከማግኘት እንደሚቻል ተናግረዋል።

ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በ2007 ዓ. ም. “የነፃነት ድምፆች” እና “ሞጋች እውነቶች” የተሰኙ መፅሐፍት ለንባብ ያበቃ ሲሆን በመጪው ሰኞ ሰኔ 12/2009 ቀን ከታሰረ 6ዓመት ይሞላዋል።

EHRP

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው አንድ ዓመት ከ6 ወር እስር ተፈረደበት

(አዲስ ሚዲያ) የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በፌደራል አቃብ ህግ በተመሰረተበት ክስ ከአንድ ዓመት ከ አምስት ወር እስር በኋላ የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አዲስ አበባ ልደታ ምድብ ችሎት ግንቦት 18 ቀን 2009 ዓ. ም. የ 1 ዓምት ከ 6 ወር የቅጣት እስር ፈርዶበታል።

Getachew Shiferaw

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

ጋዜጠኛው ከህዳር 2008 ዓ. ም. ጅምሮ የነበረውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ሲታሰር፥ ቀደም ሲል የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶበት የነበረ ቢሆንም፤ በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ ክሱን ወደ መደበኛ ወንጀል ክስ ዝቅ በማድረግ አመፅ ማነሳሳት በሚል ክስ የቅጣት ውሳኔውን ማሳለፉን አሳውቋል። ይሁን እንጂ ጋዜጠኛው ለተላለፈበት የቅጣት ውሳን ብይን የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ፍርድ ቤቱ ቢጠይቀውም ጋዜጠናው ባልሰራሁት ወንጀል የምጠይቀው የቅጣት ማቅለያ የለም በማለት የፍርድ ቤቱን ጥያቄ ውድቅ ማድረጉ ታውቋል።

ጋዜጠኛው ክስ የተመሰረተበትና የ1 ዓመት ከ6 ወር እስር ቅጣት የተጣለበት፤ በፌስ ቡክ ማኅበራው ሚዲያ በውጭ ከሚገኝ ጋዜጠኛ በተለይም መቀመጫውን ዋሸንግተን ዲሲ ካደረገው ጋዜጠኛ አበበ ገላው ጋር መልዕክት ተለዋውጠሃል፥ አመፅ ቀስቅሰሃል የሚል እንደነበር የቀረበበት ክስ አመልክቷል።

ጋዜጠኛው ህትመቱና ስርጭቱ በመንግሥት እንዲቋረጥ ከተደረገው የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ከማገልገሉ በተጨማሪ በተለያዩ መፅሔቶች፥ ጋዜጦችና ድረ-ገፆች ላይም የተለያዩ ፖለቲካዊ፥ ሰብዓዊ መብትና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደረጉ በርካታ ፅሑፎችንም ያበረክት እንደነበር ይታወቃል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰኔ 2006 ዓ ም በመንግሥት እውቅና ተነፍጎት አባላቱና አመራሩ ምንም ዓይነት የስራ እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ እግድ የተጣለብት የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ (ኢጋመ) መስራችና አስተባባሪ እንደነበር ይታወቃል።

ጋዜጠኛ ጌታቸው ከታህሳሥ 15 ቀን 2008 ዓ ም ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛል።

በተለይ መንግሥት ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ በወሰደው ርምጃ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራውን ጨምሮ፥ ሌሎች ጋዜጠኞችና 60 ሺህ ያህል ሰላማዊ ዜጎች መታሰራቸውን የሀገርው ውስጥ የሰብዓዊ መብት አራማጆችና ተሟጋቾች መረጃ አመልክቷል።

በዝዋይ ወህኒ ቤት እስር ላይ የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ አሁን የት እንዳለ አለመታወቁን ቤተሰቦቹ አስታወቁ

(አዲስ ሚዲያ) የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ እና መስራች የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ባለፈው ህዳር 2007 ዓ.ም. በመንግሥት በተመሰረተበት ክስ የ3 ዓመት ፅኑ እስር ተፈርዶበት ዝዋይ ወህኒ ቤት የነበረ ቢሆንም፤ ከፋለፈው ማክሰኞ ህዳር 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ የነበረበት ዘዋይ ወህኒ ቤትን ጨምሮ ቃሊቲ፣ የአቃቂ ቂሊንጦ እና ሸዋ ሮቢት ወህኒ ቤት ጥበቃ ሰራተኞችና ኃላፊዎች፤ ጋዜጠኛ ተመስገን የት እንዳለ ከቤተሰቦቹ ለቀረበላቸው ጥያቄ በተጠቀሱት ወህኒ ቤቶች እንደሌለ በመግለፅ በአሁን ወቅት የት እንዳለ ግን እንደማያውቁ መናገራቸውን የጋዜጠኛው ቤተሰቦች ይፋ አድርገዋል፡፡

journalist-temesgen-desalegn

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፤ ፎቶ ከማኀበራዊ ገፅ

አዛውንቱ ወላጅ እናቱን ጨምሮ ሌሎች የጋዤተኛው ቤተሰቦችና ወዳጆች ቀደም ሲል ታስሮ የነበረበትን እና በፌደራል ደረጃ የሚታወቁ ወህኒ ቤቶች በሙሉ በመሄድ ያለበትን ሁኔታ ለማረጋገጥ ሙከራ ቢያደርጉም ሊያገኙት እንዳልቻሉ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዕድሜ የገፉ አዛውንት ወላጅ እናቱ ወ/ሮ ፋንታዬ እርዳቸው በከፍተኛ ስጋትና ጭንቀት ላይ መሆናቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኛው ቀደም ሲል በእስር ላይ እያለ በደረሰበት ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ለማግኘት ጠይቆ በተደጋጋሚ መከልከሉ አይዘነጋም፡፡

የፌደራል አቃቤ ህግ ጋዜጠኛ ተመስገን በፍትህ ጋዜጣ ላይ በፃፋቸው ፅሑፎችን ዋቢ በማድረግ በመሰረተበት ክስ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 3 ዓመት ፅኑ እስራት እና የፍትህ ጋዜጣ አሳታሚ ማስተዋል ህትመትና ማስታወቂያ ድርጅትደግሞ 10 ሺህ ብር እንዲቀጣ መበየኑ ይታወሳል፡፡ጋዜጠኛ ተመስገን ከመታሰሩ በፊት መንግሥት ይፈፅማል ያላቸው የመብት ረገጣዎችና ብልሹ አሰራሮችን በግልፅ በመተቸት ይታወቃል፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ በገዥው የኢህአዴግ መንግሥት 11 ጋዜጠኞችና 1 ብሎገር ኢትዮጵያውያን እንዲሁም 3 የውጭ ዜጋ ጋዜጠኖች በአጠቃላይ 15 ጋዜጠኞችና ብሎገር በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይ በእስር ከሚገኙ ጋዜጠኞች መካከል ኢትዮጵያውያኑ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ ጌታቸው ሽፈራው፣ ፈቃዱ ምርከና፣ጌታቸው ወርቁ፣ አናኒያ ሶሪ፣ ኤልያስ ገብሩ፣ በፈቃዱ ኃይሉ፣ ከድር መሐመድ፣ ዳርሰማ ሶሪ እና የደ ብርሃን ብሎገር ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ተጠቃሾች ናቸው፡፡

እንደ ሀገር ውስጥ የሰብዓዊና የፕሬስ ነፃነት መብት ተሟጋቾች እና እንደ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መረጃ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ በአሁን ወቅት የፕሬስ ነፃናት ከሌለባቸው የዓለም ሀገራት ተርታ በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት አንዷ ስትሆን፤ በርካታ ጋዜጠኞችን በማሰር በአፍሪካ ከጎረቤት ኤርትራ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ ሀገር ነች፡፡

በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፣ የመብት አራማጆች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ የበርካታ ዜጎች እስር አሁንም እንደቀጠለ ነው

የኢትዮጵያ መንግሥት የተነሳበት ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ባወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋዜጠኞችን፣ የመብት አራማጆችን፣ የማኀበራዊ ገፅ አምደኞችን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ በርካታ ዜጎችን ማሰሩን ቀጥሏል፡፡

በተለይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈፀም እንደተቋቋመ የተነገረለት ኮማንድ ፖስት ጠረጠርኳቸው ያላቸውን ዜጎች ሁሉ እያሰረ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት ጋዜጠኛ አናኒያ ሶሪ፣ ጋዜጠኛ አሊያስ ገብሩ፣ ጋዜጠኛ አብዱ ገዳ፣ የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ የነበሩት እና ከዚህ ቀደም ከአንድ ዓመት በላይ በመንግሥት ታስረው በነፃ የተሰናበቱት አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና የማኀበራዊ ሚዲያ አምደኛው ኢዩኤል ፍስሃ መታሰራቸው ታውቋል፡፡

elias-anania-and-daniel

እንደ አሜሪካ ደምፅ ሬዲዮ ዘገባ ከሆነ፤ ሰማያዊው ፓርቲ እስካሁን 23 አባላቶቹና ከ80 በላይ ደጋፊዎቹ እንደታሰሩበት አስታውቋል፡፡የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክረሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) እና የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ሕብረት በርካታ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው መታሰራቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡
መንግሥት ህዝባዊ አመፁን ለመቆጣጠርና ለማረጋጋት ብሎ በሰየመው ኮማንድ ፖስት ከሳምንት በፊት የታሰረው ጋዜጠኛ እና የዞን 9 ብሎገር በፈቃዱ ኃይሉን ጨምሮ ከ11,600 በላይ ዜጎችን ማሰሩን ቢያምንም፤ የመብት አራማጆችና የመንግሥት ተቃዋሚዎች በበኩላቸው የታሰሩ ሰላማዊ ዜጎች ቁጥር መንግሥት ካመነው ከ3 እጥፍ በላይ እንደሚልቅ ሲናገሩ ይስተዋላል፡፡

እንደ አካባቢ ምንጮች እና የመብት አራማጆች ከሆነ፤ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ያሉ የተለያዩ ወረዳዎች የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና የኃይል ርምጃ በመቃወም የአፀፋ መልስ እየሰጡ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ቀላል የማይባል የመንግሥት ወታደራዊ ኃይሎች ከፍተኛ ጥቃት እንደተሰነዘረባቸውና ከገበሬዎችም የተጎዱ እንዳሉ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

በተለይ በአማራ ክልል የፀረ አገዛዝ ጭቆና ህዝባዊ ተቃውሞ ከተጀመረበት ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ አሁንም ድረስ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና የአካል ማጉደል ድርጊት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ፤ ድርጊቱን የተቃወሙ የአካባቢው ነዋሪዎች አካባቢያቸውን እና መኖሪያ ቤታቸውን ጥለው በመሄድ ለአፀፋ መልስ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

መንግሥት ከባለፈው ዓመት ህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ዛሬም ድረስ እንዳልቆመ የሚነገርለትን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መንስኤው የመንግሥት ሹማምንት ስልጣናቸውን ለግል ጥቅማቸው በማዋል የተፈጠረ የመልካም አስተዳደር ችግር ነው በሚል ከዚህ በፊት ከነበሩት 30 ሚኒስትሮች መካከል 21 የቀድሞ ሚኒስትሮችን፣ ሁለት የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረጎችን እና በሚኒስትርነት ማዕረግ የነበሩ በርካታ አማካሪዎችን አሰናብቷል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ከዛሬ ሶስት ሳምንት በፊት፤ ለህዝባዊ ተቃውሞና ለተፈጠረው ችግር ተገቢውን ምላሽ ይሰጣሉ በሚል 21 አዳዲስ ሚኒስትሮችን በመሾም ከነባር 9 ሚኒስትሮች ጋር እንዲሰሩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲፀድቅ ማድረጋቸው ይታወሰል፡፡ ምክር ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የገዥው የኢህአዴግ ፓርቲ ተወካዮች ብቻ የተሞላ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኃላ በተወሰነ መልኩ የተረጋጋ ሁኔታ እንተፈጠረ መንግሥት ቢናገርም አሁንም በተለይ በአማራ ክልል እና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞዎች የቀጠሉ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡ ፡

ምንም እንኳ ህዝባዊ ተቃውሞ የተፈጠረው በራሱ በመንግሥት ብልሹ በሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር እንደሆነ ራሱ መንግሥት ቢያምንም፤ በፀጥታ ኃይሎች በሚወሰድ የኃይል ርምጃ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና እንግልት ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ቀጥሏል፡፡