Tag Archives: Daniel Shibeshi

በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፣ የመብት አራማጆች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ የበርካታ ዜጎች እስር አሁንም እንደቀጠለ ነው

የኢትዮጵያ መንግሥት የተነሳበት ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ባወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋዜጠኞችን፣ የመብት አራማጆችን፣ የማኀበራዊ ገፅ አምደኞችን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ በርካታ ዜጎችን ማሰሩን ቀጥሏል፡፡

በተለይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈፀም እንደተቋቋመ የተነገረለት ኮማንድ ፖስት ጠረጠርኳቸው ያላቸውን ዜጎች ሁሉ እያሰረ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት ጋዜጠኛ አናኒያ ሶሪ፣ ጋዜጠኛ አሊያስ ገብሩ፣ ጋዜጠኛ አብዱ ገዳ፣ የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ የነበሩት እና ከዚህ ቀደም ከአንድ ዓመት በላይ በመንግሥት ታስረው በነፃ የተሰናበቱት አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና የማኀበራዊ ሚዲያ አምደኛው ኢዩኤል ፍስሃ መታሰራቸው ታውቋል፡፡

elias-anania-and-daniel

እንደ አሜሪካ ደምፅ ሬዲዮ ዘገባ ከሆነ፤ ሰማያዊው ፓርቲ እስካሁን 23 አባላቶቹና ከ80 በላይ ደጋፊዎቹ እንደታሰሩበት አስታውቋል፡፡የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክረሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) እና የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ሕብረት በርካታ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው መታሰራቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡
መንግሥት ህዝባዊ አመፁን ለመቆጣጠርና ለማረጋጋት ብሎ በሰየመው ኮማንድ ፖስት ከሳምንት በፊት የታሰረው ጋዜጠኛ እና የዞን 9 ብሎገር በፈቃዱ ኃይሉን ጨምሮ ከ11,600 በላይ ዜጎችን ማሰሩን ቢያምንም፤ የመብት አራማጆችና የመንግሥት ተቃዋሚዎች በበኩላቸው የታሰሩ ሰላማዊ ዜጎች ቁጥር መንግሥት ካመነው ከ3 እጥፍ በላይ እንደሚልቅ ሲናገሩ ይስተዋላል፡፡

እንደ አካባቢ ምንጮች እና የመብት አራማጆች ከሆነ፤ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ያሉ የተለያዩ ወረዳዎች የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና የኃይል ርምጃ በመቃወም የአፀፋ መልስ እየሰጡ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ቀላል የማይባል የመንግሥት ወታደራዊ ኃይሎች ከፍተኛ ጥቃት እንደተሰነዘረባቸውና ከገበሬዎችም የተጎዱ እንዳሉ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

በተለይ በአማራ ክልል የፀረ አገዛዝ ጭቆና ህዝባዊ ተቃውሞ ከተጀመረበት ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ አሁንም ድረስ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና የአካል ማጉደል ድርጊት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ፤ ድርጊቱን የተቃወሙ የአካባቢው ነዋሪዎች አካባቢያቸውን እና መኖሪያ ቤታቸውን ጥለው በመሄድ ለአፀፋ መልስ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

መንግሥት ከባለፈው ዓመት ህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ዛሬም ድረስ እንዳልቆመ የሚነገርለትን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መንስኤው የመንግሥት ሹማምንት ስልጣናቸውን ለግል ጥቅማቸው በማዋል የተፈጠረ የመልካም አስተዳደር ችግር ነው በሚል ከዚህ በፊት ከነበሩት 30 ሚኒስትሮች መካከል 21 የቀድሞ ሚኒስትሮችን፣ ሁለት የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረጎችን እና በሚኒስትርነት ማዕረግ የነበሩ በርካታ አማካሪዎችን አሰናብቷል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ከዛሬ ሶስት ሳምንት በፊት፤ ለህዝባዊ ተቃውሞና ለተፈጠረው ችግር ተገቢውን ምላሽ ይሰጣሉ በሚል 21 አዳዲስ ሚኒስትሮችን በመሾም ከነባር 9 ሚኒስትሮች ጋር እንዲሰሩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲፀድቅ ማድረጋቸው ይታወሰል፡፡ ምክር ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የገዥው የኢህአዴግ ፓርቲ ተወካዮች ብቻ የተሞላ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኃላ በተወሰነ መልኩ የተረጋጋ ሁኔታ እንተፈጠረ መንግሥት ቢናገርም አሁንም በተለይ በአማራ ክልል እና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞዎች የቀጠሉ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡ ፡

ምንም እንኳ ህዝባዊ ተቃውሞ የተፈጠረው በራሱ በመንግሥት ብልሹ በሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር እንደሆነ ራሱ መንግሥት ቢያምንም፤ በፀጥታ ኃይሎች በሚወሰድ የኃይል ርምጃ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና እንግልት ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ቀጥሏል፡፡

ለመከላከያ ምስክርነት የተጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ “ሊቀርቡ ባለመቻላቸው” ምስክርነታቸው ውድቅ ተደረገ

*አብርሃ ደስታ 4 ወራት፣ የሺዋስና ዳንኤል 2 ወራት እስር ይቀራቸዋል

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ አንደኛ ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ በቀረበበት የሽብር ክስ ላይ ከግንቦት ሰባት ዋና ጸሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጋር ተጻጽፈሃል የሚል ማስረጃ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት በመግለጽ ይህን እንዲከላከሉለት አቶ አንዳርጋቸውን ለምስክርነት ቢጠራቸውም በተደጋጋሚ ቀጠሮ ሊቀርቡ ባለመቻላቸው ከፍተኛው ፍርድ ቤት ምስክሩ በተከሳሽ በኩል እንደተተው ይቆጠራል በሚል በይኗል፡፡

Zelalem Workagegnehu

ፍርድ ቤቱ ዛሬ የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም ብይኑን ሲያሰማ እንደገለጸው ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ ምስክሩን በተመለከተ በተደጋጋሚ እንዲቀርቡለት ጠይቆ እንዳልቀረቡለት በመግለጽ ‹‹ምስክሩ የማይቀርቡልኝ ከሆነ ከምስክሩ ጋር በተያያዘ የቀረበብኝ ክስ ፍሬ ነገር ከክሱ ወጥቶ ብይን ይሰጠኝ›› የሚል አቤቱታ አቅርቧል፡፡

አቃቤ ህግ በበኩሉ ተከሳሹ ምስክሩን አቅርቦ የማሰማት ግዴታ እንዳለበት በመጥቀስ ተከሳሹ የጠየቀው የፍሬ ነገር ይውጣልኝ አቤቱታ የህግ አግባብን የተከተለ ስላልሆነ ምስክሩን እንደተዋቸው ተቆጥሮ ብይን እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡

ችሎቱ በበኩሉ ለምስክሩ የተጻፈው የመጥሪያ ትዕዛዝ ደርሷቸው እንደቀሩ ማረጋገጫ ስለሌለ በተከሳሽ የቀረበው አቤቱታ ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ምስክሩ እንደተተው ቆጥሮ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ በመዝገቡ ላይ በተካተቱት አምስት ተከሳሾች ላይ የፍርድ ብይን ለመስጠት ለመጋቢት 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ከዚህ ቀጠሮ በፊት የክርክር ማቆሚያ ካላቸው ግራቀኙም በጽህፈት ቤት በኩል በጽሁፍ ማቅረብ እንደሚችሉ ፍርድ ቤቱ ገልጹዋል፡፡

Andaregachew Tsigie
በሌላ በኩል ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በዚሁ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ከተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ነጻ ናቸው በሚል የተበየነላቸው እነ አብርሃ ደስታ በዚሁ ችሎት፣ ‹‹ችሎት ደፍራችኋል›› በሚል የተላለፈባቸው ቅጣት ከመቼ ጀምሮ እንደሚታሰብ ግልጽ አድርጓል፡፡

በዚህም አመት ከአራት ወር የተፈረደበት አቶ አብርሃ ደስታ እና እያንዳንዳቸው አንድ አመት ከሁለት ወር የተፈረደባቸው አቶ የሺዋስ አሰፋ እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ በሚታሰብ እስር መቀጣታቸውን ገልጹዋል፡፡ በመሆኑም አብርሃ አራት ወራት፣ እና እነ የሺዋስ ሁለት ወራት እስር ይቀራቸዋል ማለት ነው፡፡

Abereha, Yeshiwas, Daniel
እነ አብርሃ ደስታ አቃቤ ህግ በጠየቀባቸው ይግባኝ ላይ ብይን ለማግኘት ለመጋቢት 30 ቀን 2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀጠሮ እንዳላቸው ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ

እነ ሀብታሙ አያሌው በጠቅላይ ፍርድ ቤት የቃል ክርክር አደረጉ

ኢዩኤል ፍስሃ ዳምጤ

“እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” አብርሃ ደስታ
“እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ዳንኤል ሺበሺ

Political prisoners

 

በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው በሥር ፍርድ ቤት ውሳኔ በነፃ የተሰናበቱት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋና በተመሳሳይ የክስ መዝገብ ውስጥ ከአመራሮቹ ጋር የተከሰሰው አቶ አብርሃም ሰለሞን በፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዛሬ ታህሳስ 15 ቀን 2008 ዓ.ም በመቅረብ የቃል ክርክር አድርገዋል፡፡
በችሎቱ የተሰየሙት ግራ ዳኛ መዝገቡ ለዛሬ የተቀጠረው ታህሳስ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ተከሳሾቹ የፍርድ ቤቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ዳኜ መላኩ ከሰብሳቢነታቸው እንዲነሱ ባቀረቡት የፅሁፍ አቤቱታ ላይ መልስ ለመስጠት፤ የተከሳሾቹንና የአቃቤ ሕግን የቃል ክርክር ለማድመጥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ተከሳሾቹ “ሰብሳቢው ዳኛ ይነሱልን!” ብለው ያቀረቡት ጥያቄ ፍ/ቤቱ ስላላመነበት ውድቅ መደረጉን ገልፀዋል፡፡

አቃቤ ሕግ በችሎቱ ባቀረበው የይግባኝ አቤቱታው ተከሳሾቹ ከግንቦት ሰባት አመራር አባላት ጋር በተለያየ ጊዜ መገናኘታቸውን፤ ይህንንም የሚያስረዳ ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ማቅረባቸውን ነገር ግን የስር ፍርድ ቤቱ እነዚህን ማስረጃዎች ሳይመዝን “በደፈናው ውሳኔ ስለሰጠ” ይግባኝ መጠየቃቸውንና የስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሲሰጥ ከጭብጥ መውጣቱን ገልጿል፡፡ “ፍርድ ቤቱ ከፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀፅ 23 መሰረት የቀረበውን የሰነድ ማስረጃዎች በመመልከት የስር ፍርድ ቤት ውሳኔን በመሻር ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ፍርድ ቤቱ ይወስንልን ዘንድ እንጠይቃለን” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌውና 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን በጠበቃቸው አምሃ መኮንን በኩል የመከራከሪያ ሃሳባቸውን አቅርበዋል፡፡ አቶ አምሃ መኮንን የስር ፍርድ ቤቱ ደምበኞቻቸውን በነፃ ሲያሰናብታቸው የቀረቡትን ማስረጃዎች መዝኖ መሆኑን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡ አቃቤ ሕግ በክሱ ላይ ያቀረባቸው ነገሮች እንደመረጃ እንጂ እንደማስረጃ ሊያዙ እንደማይገባ የተከሳሾቹ የቀድሞ ጠበቃ በስር ፍርድ ቤት ክርክር አድርገው የስር ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 2 ቀን 2007 ዓ.ም “በማስረጃ ሊያዙ ይገባል!›› ብሎ ብይን ማስተላለፉን አቶ አምሃ አውስተዋል፡፡

ጠበቃው ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ ማስረጃዎችም ፍርድ ቤት ሊመረምራቸው እንደሚገባ ሲያስረዱ፡- “የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ መረጃዎችን ፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነ የፍርድ ቤቱ ሚና ምን ሊሆን ነው? ፍርድ ቤቱ ከተቋሙ በኩል የሚቀርቡለትን መረጃዎች ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነም ፈራጁ ፍርድ ቤት ሳይሆን ብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ነው” በማለት አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

ደምበኛቸው አቶ ሀብታሙ አያሌውም በክሱ ላይ ‹‹ዘመነ ካሴ›› ከተባለው የግንቦት ሰባት አባል ጋር በመነጋገር አብረው ለመስራት ተስማሙ ተብሎ ቢገለፅም ይህን የሚያስረዳ ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ ደምበኛቸው ከግለሰቡ ጋር ባደረጉት የስልክ ልውውጥ አንድም ቦታ ላይ አብረው ለመስራት መስማማታቸውን እንዳልገለፁ ጠበቃው ጠቁመዋል፡፡ በክሱ ላይ የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ የሆነው አቶ ሀብታሙ አያሌው ከዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አደረጉ ተብሎ የተገለፀው ከእውነታ የራቀ መሆኑን ጠበቃው ገልፀዋል፡፡ በተጠቀሰው ጊዜ አቶ ሀብታሙ አይደለም የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሊሆኑ ቀርተው፤ የፓርቲው አባል እንዳልነበሩም አቶ አምሃ አስረድተዋል፡፡ አቶ ሀብታሙ በበኩላቸው በክሱ ላይ ተከሳሽ በዚህ የሞባይል ቁጥር ግንኙነት አድርጓል ተብሎ አለመገለፁን የስልክ ልውውጡም ምን እንደሆነ የሚያስረዳ አንዳች ነገር አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

Abreham Solomon

አቶ አምሃ ደምበኛቸው በሆነው 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን ላይ ምንም አይነት የሰነድ ማስረጃ አለመቅረቡን የግንቦት ሰባት አባል ነው ሲባልም፤ በግንቦት ሰባት መዋቅር ውስጥ እንዳለ የሚያሳይ ማስረጃ አለመቅረቡን ደምበኛው በምንም አይነት የሽብርተኝነት ተግባር ላይ እንደተሰማራ የሚገልፅ ምንም አይነት ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ አቶ አብርሃም ሰለሞን በበኩሉ ያለአንዳች ማስረጃ መታሰሩን ሲያስረዳ፡- “ከታሰርኩ በኋላ ነው ማስረጃ ሲፈለገብኝ የነበረው፤ ከታሰርኩ በኋላም ቤቴ እንኳ አልተፈተሸም፡፡ መንግስት አሰረኝ ብዬ አላምንም ያሰረኝ አንድ ግለሰብ ነው” ሲል ተደምጧል፡፡

2ኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ 3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታና 4ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ ያለጠበቃ በመቆም በግል ክርክራቸውን ያካሄዱ ሲሆን፤ ሶስቱም ተከሳሾች የአቃቤ ሕግ የይግባኝ ማመልከቻ ላይ እነሱን የሚመለከት ቅሬታ አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ሺበሺ “እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ የቃል ክርክር ለማድረግ ያዘጋጁት ወረቀትም በማረሚያ ቤቱ እንደተቀደደባቸው ለፍርድ ቤቱ አሳይተዋል፡፡ ወረቀቱ ማህተም የተደረገበት ቦታ ተቀዶ መውጣቱን በችሎቱ ለነበሩ ታዳሚያን በግልፅ ታይቷል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታም ከታሰሩ በኋላ ማስረጃ ሲፈልግባቸው እንደነበርና በብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ የሚቀርብ መረጃ በፍርድ ቤት ሳይመዘን ሙሉ ለመሉ ተቀባይነት የሚያገኝ ከሆነ ተቋሙ ከሳሽም፣ መስካሪም፣ ዳኛም ሆነ ማለት ነው፡፡ ይህ ከሆነ ዘንድ ደግሞ ፍርድ ቤት መምጣትም አያስፈልግም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ በክሱ ላይ ለኢሳት ቴሌቪዥን ቃለምልልሰ ሰጠ ተብሎ የቀረበው ክስ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ሲያስረዱ፡- “እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” በማለት ለፍ/ቤቱ የገለፁ ሲሆን፤ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በመቅረብ ሃሳባቸውን ሲገልፁ የነበሩትም የኢህአዴግን ጭቆናን ማጋለጥ መብታቸው በመሆኑ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

4ኛ ተከሳሽ አቶ የሺዋስ አሰፋ በእሳቸው ላይ የቀረበ አንድም የሰው ምስክር እንደሌለ ገልፀው፤ ማዕከላዊ በነበሩበት ወቅትም በምርመራ ላይ አንድም ቀን ስለግንቦት ሰባት ተጠይቀው እንደማያውቁ ምርመራ ላይ ሲጠየቁ የነበሩትም ስለ ሰማያዊ ፓርቲ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አቶ የሺዋስ የሰማያዊ ፓርቲ አባል በመሆናቸው ብቻ አያሌ መከራዎችን እየተጋፈጡ እንደሚገኙ ለፍ/ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ያለፉትን 6 ወራት በማንም አለመጎብኘታቸውን ለፍ/ቤቱ ገልፀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቃል ክርክሩ በፅሁፍ ተገልብጦ ከቀጣይ ቀጠሮ በፊት ከመዝገቡ ጋር ተያይዞ እንዲቀርብ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌው የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተከሳሹ ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ታህሳስ 19 ቀን 2008 ዓ.ም መልስ እንዲሰጥ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ተወካዩ በተጠቀሰው ቀን አቶ ሀብታሙን ይዞ እንዲቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል፡፡

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር መዝኖ ውሳኔ ለመስጠት ለታህሣሥ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ እነ ሀብታሙ አያሌው ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ከተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ውሳኔ ማስተላለፉ አይዘነጋም፡፡

ሰበር ዜና፤ በእስር ላይ የነበሩት የቀድሞ የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲ አመራሮች እና አንድ ሌላ ተከሳሽ በነፃ እንዲሰናበቱ ተወሰነ

የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት፤ ዛሬ ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ በፌደራሉ አቃቤ ህግ በሽብርተኝነት ከአንድ ዓመት ከአንድ ወር አካባቢ ታስረው ከነበሩት መካከል አራት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና አንድ መምህር በነፃ እንዲሰናበቱ ወሰነ፡፡

Politicians
ከተመሰረተባቸው ክስ በነፃ እንዲሰናበቱ የተወሰነላቸው የአንድነት ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋና የቤተል ትምህርት ቤት መምህርና የሀገር አቀፍ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሀገር አቀፍ አሸናፊ የነበረው መምህር አብርሃም ሰለሞን በነፃ የተሰናበቱት፣ የቀረበባቸው የሽብርተኝነት ክስ ከጥርጣሬ ባለፈ ተሳትፎአቸውን ማረጋገጥ ባለመቻሉ መሆኑን ፍርድ ቤቱ በውሳኔው አስታውቋል፡፡
በውሳኔው መሠረት አቶ ሀብታሙ የሚጠየቁበት ወይም ሌላ የሚፈለጉበት ጉዳይ ከሌለ በዛሬው ዕለት እንዲፈቱ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺና አቶ የሺዋስ አሰፋ ከዚህ ቀደም ችሎት በመድፈር የተፈረደባቸውን ቅጣት እንዳጠናቀቁ እንዲፈቱ ሲል መወሰኑ ታውቋል፡፡

አብርሃም ሰለሞን

አብርሃም ሰለሞን

በዚሁ ክስ መዝገብ በተመሳሳይ ተከሰው ከነበሩት 10ሩ መካከል ከላይ የተጠቀሱት 5ቱ እንዲፈቱ ሲወሰን፤ ቀሪዎቹ 5ቱ እንዲከላከሉ እንተበየነባቸው ተጠቁሟል፡፡
በአሁን ወቅት በርካታ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች እና የኃይማኖት ነፃነት ጠያቂዎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወቅ ሲሆን፤ ባለፈው ሶስት ጋዜጠኞች፤ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ እንዲሁም የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ሁለቱ ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን ከተመሰረተባቸው ክስ በነፃ ሲሰናበቱ፤ የተፈረደባቸውን ፍርድ ከጨረሱት መካከል ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ እና የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባ ከእስር መፈታታቸው አይዘነጋም፡፡

የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ‘ሰጡ’

“ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ህወሓት/ኢህአዴግ ነው” አብርሃ ደስታ
“የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” የሺዋስ አሰፋ

prisoners

በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገቡ የተካተቱ ተከሳሾች በተከሰሱበት ድርጊት ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ፡፡

የሰማያዊ፣ የአንድነት እና የዓረና ትግራይ ፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ 10 ተከሳሾች መጋቢት 10 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡ ሲሆን ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ በዚህ መሰረት ከአንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ጀምሮ፣ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም?” የሚል ተመሳሳይ ጥያቄ ለእያንዳንዳቸው የቀረበላቸው ሲሆን ብዙዎቹ ተከሳሾች ምላሻቸውን በቀጥታ ለመስጠት አለመፈለጋቸውን አሳይተዋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ለቀረበለት ጥያቄ፣ “በአቃቤ ህግ እና በፖሊስ ተቀነባብሮ የቀረበብኝን ክስ በተመለከተ ለክሱ እውቅና ላለመስጠት ምንም አልልም፡፡ በክሱ ላይ አስተያየት በመስጠት ለጸረ-ሽብር አዋጁ እውቅና መስጠት አልፈልግም” የሚል መልስ በመስጠቱ ፍርድ ቤቱ ክሱን ክዶ ቃል እንደሰጠ አድርጎ መዝግቦታል፡፡

2ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት እንዳልፈጸምኩ እንኳን እኔ ከሳሾቼም በደንብ ያውቃሉ፡፡ ከሳሾቼ እኔ ድርጊቱን የመፈፀም ፍላጎቱም ሀሳቡም እንደሌለኝ ያውቃሉ” ብሏል፡፡

3ኛ ተከሳሽ ዳንኤል ሺበሽ ደግሞ፣ “እኔ ስለ ሽብር የሰማሁት ከአልቃይዳው መሪ ኦሳማ ቢላደን እና መለስ ዜናዊ ነው፡፡ እኔ አሸባሪ አይደለሁም፤ ሀሳቡም ሆነ ፍላጎቱም የለኝም፡፡ ባህሌና እምነቴም አይፈቅድልኝም” ሲል ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡

4ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታ “አሸባሪ ማለት የፖለቲካም ሆነ ሌላ ዓላማውን ሰላማዊ ዜጎችን በማሸበር ለማስፈፀም የሚሰራ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ድርጅት ህወሓት/ኢህአዴግ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የዚህ አሸባሪ ድርጅት ተቃዋሚ ነኝ” ብሏል፡፡

5ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ በበኩሉ፣ “በመጀመሪያ ለመጨረሻ ጊዜ ስለሆነ የምናገረው እንዳታቋርጡኝ አደራ እላለሁ፡፡ ክሱ ቅንብር ነው፡፡ ዳኞችም ህጉ የሰጣቸው ነጻነት አይታይባቸውም፡፡ ይህ 19ኛ ወንጀል ችሎት የጦር ችሎት ነው የሚመስለኝ፡፡ ስለሆነም የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” ሲል ተናግሯል፡፡ የሺዋስ በዳኞች በተደጋጋሚ ንግግሩ እንዲቅረጥ ተደርጓል፡፡ በመጨረሻም ክሱን ክዶ ቃል ሰጥቷል በሚል ተመዝገቦለታል፡፡

6ኛ ተከሳሽ ዮናታን ወልዴ፣ “የተዘጋጀብኝን ክስ ያለፍቃዴ እንድተውን እየተገደድኩ ነው” ብሏል፡፡

7ኛ ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞን ደግሞ፣ “የተቀነባበረ ክስ ላይ ምንም ማለት አይቻልም” ብሏል፡፡

8ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማ፣ “ነፃ ሰው ነኝ፡፡”

9ኛ ተከሳሽ ባህሩ ደጉ “ባህሉንና ፈጣሪውን ከሚያከብር ማህበረሰብ ወጥቼ አሸባሪ ልሆን አልችልም” ሲል አስረድቷል፡፡

10ኛ ተከሳሽ ተስፋዬ ተፈሪ ደግሞ፣ “ድርጊቱን አልፈጸምኩም” ብሏል፡፡

በአጠቃላይ ተከሳሾች ክሱ ላይ የተጠቀሰውን ድርጊት ክደው ቃል በመስጠታቸው አቃቤ ህግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ለግንቦት 13፣ 14፣ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ለተከታታይ 3 ቀናት ምስክር እንዲሰማ ቀጠሮ መሰጠቱን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክታል፡፡

%d bloggers like this: