Tag Archives: National Electoral Board of Ethiopia

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ተከላከሉ ተባሉ

*ተከሳሾች 200 የሰው መከላከያ ምስክሮች አሉን ብለዋል

የኢትዮ-ኤርትራ ድንበርን አቋርጠው ኤርትራ የሚገኘውን የአርበኞች ግንቦት ሰባት ወታደራዊ ክንፍ ሊቀላቀሉ ከአዲስ አበባ ተነስተው ሲጓዙ ማይካድራ የሚባል የድንበር ከተማ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ጠቅሶ የፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የመሰረተባቸው እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ እንዲከላከሉ ብይን ተሰጥቷል፡፡

ዛሬ የካቲት 4 ቀን 2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ተከሳሾቹ አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ወ/ሪት እየሩሳሌም ተስፋው፣ አቶ ፍቅረማርያም አስማማው እና አቶ ደሴ ካህሳይ አቃቤ ህግ ያቀረበባቸውን ክስ በሰነድና በአንድ የሰው ምስክር ማስረጃዎች አስረድቷል በሚል ተከሳሾች መከላከል ይገባቸዋል ሲል ፍርድ ቤቱ ወስኗል፡፡

Birhanu Tekleyared, et.al

ተከሳሾች 14ኛ ወንጀል ችሎት እንዲቀየርላቸው አቤቱታ አቅርበው እንደነበር በማስታወስ ይህ ጉዳይ እልባት ሳያገኝ ችሎቱ ብይኑን እንዳያሰማ ቢጠይቁም፣ ችሎቱ ‹‹አቤቱታው ቶሎ ብይን እንዲሰጣችሁ የሚጠይቅ ነው፣ በመሆኑም ብይኑ ተሰርቷል›› ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡ በዚህም ተከሳሾች ብይኑ አይሰማብን የሚለውን ጥያቄ ባለመቀበል ችሎቱ ብይኑን በንባብ አሰምቷል፡፡

እነ ብርሃኑ ተከላከሉ መባላቸውን ተከትሎ መከላከያ ማስረጃዎች ያቀርቡ ከሆነ በሚል ፍርድ ቤቱ ጠይቆ፣ ተከሳሾች 200 የሰው ምስክሮችና የሰነድ ማስረጃዎች በጋራ እንደሚያቀርቡ አስታውቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም መከላከያ ማስረጃዎችን ለማድመጥ ለመጋቢት 21 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ተከሳሾች እያዘጋጁት የነበሩት የተከሳሽነት ቃል ጽሁፍ በማረሚያ ቤት ፖሊሶች እንደተወሰደባቸው ለፍርድ ቤቱ በመግለጽ ከዚህም በኋላ ተመሳሳይ ለችሎት የሚቀርቡ ማስረጃዎችን ማዘጋጀት እንዲችሉ ለማረሚያ ቤት ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡

በተመሳሳይ ችሎት የቀረቡት እነ መቶ አለቃ ጌታቸው መኮንን እና እነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጠኝ 14ኛ ወንጀል ችሎት እንዲቀየርላቸው አቤቱታቸውን በጽሁፍ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም የቀረበውን አቤቱታ መርምሮ ብይን ለማሰማት ለየካቲት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

አቶ ማሙሸት አማረ ለውሳኔ ተቀጠሩ

“ምስክርነቱ የሐሰትና የተጠና ነው!” ጠበቃቸው

Mamushet Amare

አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም መንግስት ከጠራው ሰልፍ አንድ ቀን ቀድሞ ከለቅሶ ቤት ወደ ቤተ መንግስት ለተደረገውና ለዋናው (ለሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም) ሰልፍ አነሳስቷል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው የቀድሞው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዘዳንት አቶ ማሙሸት አማረ ዛሬ ነሃሴ 20 ቀን 2007 ዓ.ም አራዳ ምድብ ችሎት ቀርቦ ለነሃሴ 22 ቀን 2007 ዓ.ም ለውሳኔ ተቀጠሯል፡፡ አቶ ማሙሸት አማረ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በተካሄደው ሰልፍ ላይ ሁከትና ብጥብጥ ፈጥሯል በሚል ተከሶ የነበር ቢሆንም በወቅቱ ከምርጫ ቦርድ ጋር በነበረው ክርክር ሰልፉ ላይ አለመገኘቱን የሚያጋግጥ መረጃ በማቅረቡ በነፃ እንዲለቀቅ ተወስኖ ነበር፡፡ ነገር ግን ክሱ ወደማነሳሳት ተቀይሮ እስር ቤት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡

አቶ ማሙሸት በአዲሱ ክስ የአቃቤ ህግን ምስክሮች ለመስማት ከ5 ጊዜ በላይ ፍርድ ቤት እንደተመላለሰ የተገለፀ ሲሆን በተለይ አንዱ ምስክር በፖሊስ ተይዞ እንዲመጣ ቢጠየቅም ፖሊስ ሳያስፈፅም ቀርቷል፡፡ ከአራቱ ምስክሮች መካከል ሶስቱ ዛሬ የመሰከሩ ሲሆን “አቶ ማሙሸት አማረ 300 ብር ከፍሎ ሰልፍ እንድንወጣ አድርጎናል” ሲሉ መስክረዋል፡፡

ይሁንና ምስክሮቹ ከማሙሸት ጋር በተገናኙበት ወቅት እንዲሁም ገንዘቡ ሲሰጣቸው፣ ሰልፉ ያለፈባቸውን ቦታዎችና ስለ ሌሎችም ጉዳዮች ሲጠየቁ ‹‹አላስታውሰውም›› ከማለት ባለፈ ዝርዝር የምስክርነት ቃል ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ከምስክሮቹ መካከል ሁለቱ አቶ ማሙሸትን ያስያዙ ደህንነቶች መሆናቸውን አቶ ማሙሸትና ጠበቃው በችሎቱ የገለፁ ሲሆን ምስክሮቹ በበኩላቸው ስራቸውን ሲጠየቁ ‹‹የግል›› እያሉ ከመመለስ ውጭ የመንግስት ስራ እንደማይሰሩ ተናግረዋል፡፡ ሆኖም የመንግስት ሰራተኛ መሆናቸውን የሚያሳይ መታወቂያ ሲጠየቁ ሊያሳዩ አልቻሉም፡፡ ከሶስቱ ምስክሮች መካከል አንደኛው ስራውን ሲጠየቅ “የግል” ብሎ የነበር ቢሆንም በመስቀለኛ ጥያቄ የቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ጥቃቅንና አነስተኛ አመራር መሆኑን አምኗል፡፡

ከምስክሮቹ መካከል ሁለቱ የመኢአድ ደጋፊዎች መሆናቸውን ሲጠቅሱ አንደኛው አቶ ማሙሸት ባቀረቡበት የመስቀለኛ ጥያቄ ከምርጫ በኋላ የወጣቶች ሊግና የኢህአዴግ አባል መሆኑን አምኗል፡፡ የኢህአዴግ አባል ሆኖም ቢሆን መኢአድን እንደሚደግፍም ገልጾአል፡፡ ዳኛው “በሁለት ወር ውስጥ እንዴት ብለህ የወጣቶች ሊግ አባል መሆን ቻልክ?” ሲሉት መልስ ሳይሰጥ አልፎታል፡፡

የአቶ ማሙሸት አማረ ጠበቃ ሶስቱም ምስክሮች አብዛኛዎቹን ጉዳዮች እንደማያስታውሱ በመግለፃቸው የተጠና የምስክርነት ቃል መሆኑን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡ በተጨማሪም ከ7 አመት በላይ አዲስ አበባ ውስጥ ኖረው መስቀል አደባባይን ጨምሮ ሰልፉ አመራባቸው የተባሉትን ቦታዎች አናውቃቸውም ማለታቸው፣ መተዳደሪያ ስራቸውን መደበቃቸውና መታወቂያ ለማሳየትም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ምስክርነቱ የሀሰት እንደሆነ ስለሚያረጋግጥ ደንበኛቸው በነፃ እንዲለቀቁ መጠየቃቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
አቶ ማሙሸት አማረ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. አይ ኤ አይ ኤልን ለመቃወም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተጠራው ሰልፍ ላይ ረብሻ አንስተዋል በሚል በተመሰረተባቸው ክስ ሰዓትና ቀን፤ ፓርቲያቸው መኢአድ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሌላ እንዲሰጥ መወሰኑን በመቃወም ፍርድ ቤት ክስ መስርተው ለክርክር በተጠቀሰው ሰዓትና ዕለት ችሎት ላይ እንደነበሩ የሚያስረዳ ደብዳቤ ፍርድ ቤቱ መፃፉ ይታወሳል፡፡

ሰበር ዜና፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ሶስት ጋዜጠኞችን እና ሁለት የዞን 9 ብሎገሮችን ከእስር መልቀቁን አስታወቀ

ከሚያዚያ አጋማሽ 2007 ዓ.ም. በፌደራሉ አቃቤ ህግ በ”ሽብርተኝነት” ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ እየታየ ከነበረው የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች መካከል፤ ሶስቱን ጋዜጠኞች እና ሁለቱን ብሎገሮች ክሳቸው በፍትህ ሚኒስቴር ውድቅ ተደርጎ መፈታታቸውን የገዥው መንግሥት ደጋፊ የሆነው ሬዲዮ ፋናን ዋቢ በማድረግ አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡
ዛሬ ሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ከእስር የተፈቱት ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ፤ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን እንደሆኑ ታውቋል፡፡
እንደሬዲዮ ፋና ዘገባ ከሆኑ ቀሪዎቹ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል በእስር ላይ የሚገኙት በፍቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ የክስ ጉዳዩን እንደሚቀጥል የፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ ማስታወቁን ጨምሮ ዘግቧል፡፡

ከግራ ወደቀኝ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ማህሌት ፋንታሁን

ከግራ ወደቀኝ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ማህሌት ፋንታሁን

ጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮች ቀደም ሲል በፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ በ”ሽብር ወንጀል” ተከሰው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ለብይን ተቀጥሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ወደ ሳሙኤል አወቀ መኖሪያ ቤት ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ

• ከአዲስ አበባ ወደ ጎጃም ለሌላ ለቅሶ በመሄድ ላይ የነበሩ ዜጎች ተደብድበው ተመልሰዋል

ተደብድቦ የተገደለው ወጣት ሳሙኤል አወቀ

ተደብድቦ የተገደለው ወጣት ሳሙኤል አወቀ

የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ሰኔ 8/2007 ዓ.ም ደብረማርቆስ ከተማ የተገደለው የሳሙኤል አወቀ ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ፡፡ አመራሮቹና አባላቱ ዛሬ ሰኔ 13/2007 ዓ.ም በጠዋት ከአዲስ አበባ ተነስተው የሳሙኤል አወቀ ቤተሰቦች ወደሚገኙበት ምስራቅ ጎጃም ዞን ግንደወይን እያቀኑ በነበረበት ወቅት አባይ ድልድይ ላይ በፌደራል ፖሊስ ታፍነው ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ጎሃ ፂዮን ከተማ ውስጥ እስከ ምሽቱ 2 ተኩል ድረስ ታግተው ውለዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን ወደ ለቅሶ እንዳይሄዱ ያገዱት ከአዲስ አበባ የሄዱና ከቦታው ተዘጋጅተው ሲጠብቁ የነበሩ የፌደራል ፖሊሶች እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አመራሮቹና አባላቱ ለፖሊስ ቃል ሲሰጡ ከሳሙኤል አወቀ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት፣ በፓርቲው ውስጥ ያላቸውን ኃላፊነት፣ ሳሙኤልን ማን እንደገደለው የሚመለከቱ ጥያቄዎች ቀርበውላቸዋል፡፡ ለቅሶ እንዳይደርሱ ከተከለከሉትና ታተው የዋሉት
1. ኢ/ር ይልቃል ጌትነት/ የፓርቲው ሊቀመንበር
2. ይድነቃቸው ከበደ/ የፓርቲው የህግ ጉዳይ ኃላፊ
3. ወሮታው ዋሴ /የፓርቲው የፋይናንስ ጉዳይ ኃላፊ
4. ሀብታሙ ደመቀ/ የኦዲትና ኢንስፔክሺን አባል
5. ጌታቸው ሺፈራው/ የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ
6. ጋሻው መርሻ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
7. እምላሉ ፍስሃ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
8. ሜሮን አለማየሁ/ አባል
9. ጥላሁን አበጀ/ አባል
10. ጠና ይታየው/ አባል
11. እስጢፋኖስ በኩረጽዮን /አባል
12. ኃይለማሪያም ተክለ ጊዮርጊስ/ አባል
13. ጋሻነህ ላቀ/ አባል
14. ግርማ ቢተው አባልና
15. የመኪናው ሾፌር ናቸው

ከምሽቱ 2 ሰዓት ተኩል ከአዲስ አበባ በመንገድ ትራንስፖርት ሰራተኞችና ትራፊክ ፖሊሶች ህጋዊ መሆኑ ተረጋግጦ ያለፈው እንዲሁም ለአራት ቀን ከፓርቲው ጋር ውል የያዘው መኪና እንዳይንቀሳቀስ ተከልክሎ ከፍተኛ አመራሮቹና አባላቱ ከእስር ተለቀዋል፡፡ በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ ልዑካን ይዘዋቸው የነነበሩ ቁሳቁሶች ለምርመራ በሚል በፖሊስ ተይዘዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ከአዲስ አበባ ተነስተው ምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወደ ሌላ ለቅሶ ሲሄዱ የነበሩ ዜጎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ከታፈኑ በኋላ ደጀን ላይ ተይዘው ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸው በግዳጅ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ተመልሰው ወደ ለቅሶው ቢሄዱ እስከ 10 ሺህ ብር ሊቀጡ እንደሚችሉ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል፡፡ እነዚህ ዜጎች በተያዙበት ወቅት ሰማያዊ ፓርቲ ደብረማርቆስና ባህርዳር ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ሊያደርግ እንደሆነ እንደተገለጸላቸው፤ እነሱም የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ላይ ትገኛላችሁ ተብለው ተጠርጥረው እንደሆነ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

ከምርጫው ጋር በተያያዘ 4ኛ ሌላ የመድረክ አባል ተገደሉ

ባለፈው ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ምርጫን ተክትሎ የሚገደሉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 2፡00 ሰኣት ላይ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) አመራር አካል የነበሩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ መገደላቸውን መድረክ አስታውቋል፡፡ አቶ ብርሃኑ በደቡብ ክልል ሀዲያ ዞን በሚገኘው ሶሮ ወረዳ በዳና ቶራ ቀበሌ የፓርቲው የኮሚቴ አመራር አባልና በምርጫው ቅስቀሳም ላይ ንቁ ተሳትፎ እንደነበራቸውም ፓርቲው በመግለጫው አስታውቋል፡፡

Medrek 2
በወቅቱ ግድያውን የፈፀሙት ብርሃኑ ደቦጭ እና ታዲዮስ ጡምቦ የተባሉ ፖሊሶች እንደሀኑ እና ከዛ በፊትም እነኚህ ፖሊሶች የመድረክ አመራሮች እና አባላቱን ሲያስፈራሩና ሲዝቱባቸው እንደነበርም ተጠቁሟል፡፡ በተለይ አቶ ብርሃኑ ኤረቦ በሁለቱ ፖሊሶች መኖሪያ ቤታቸው ደጅ ተይዘው ከተደበደቡና ከተገደሉ በኋላ አስከሬናቸው ባካባቢው ባለ ወንዝ ተጥሎ እንደተገኘ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ አቶ ብርሃኑ ኤረቦ የተገደሉበት ሶሮ ወረዳ በምርጫ ዋዜማ መምህር ጌታቸው የተባሉ የመድረክ ዕጩ በኢህአዴግ በደረሰባቸው ጫና እና አስተዳደራዊ በደል በወረዳው አስተዳደር ፊት ራሳቸውን አቃጥለው ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ ወረዳው የኢህአዴግ ተወካይ እና የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሆኑት ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም የተወዳደሩበት ወረዳ መሆኑ ታውቋል፡፡
መድረክ ከግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አቶ ብርሃኑ ኤረቦን ጨምሮ የተገደሉት የክልል አመራሮቹ ቁጥር አራት የደረሰ ሲሆን፤ እነኚህም በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ አቶ ጊዲሳ ጨመዳ፣ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ አርሲ ዞን ቆራ ወረዳ አቶ ገቢ ጥቤ፣ ከትግራይ ክልል ምዕራብ ትግራይ ዞን ማይካድራ ከተማ አቶ ታደሰ አብርሃ እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በምርጫው ወቅት ከፍተኛ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ የመድረክ አባላትና ደጋፊዎች በተለይም በደቡብ፣ በኦሮሚያ እና በትግራይ በርካታ ሰዎች እንደታሰሩ፣በጥይት ተደብድበው እንደቆሰሉ እና ቤቶቻቸው እንደተቃጠለ ከፓርቲው የተገኘ መረጃ አመልክቷል፡፡ በተመሳሳይም በአማራ ክልል ምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረማርቆስ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ አመራርና የህዝብ ተወካዮች ዕጩ የነበረው ወጣት ሳሙኤል አወቀም ተደብድቦ መገደሉ ይታወቃል፡፡ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ አባሎቻቸው የተገደሉት በኢህአዴግ መሆኑን እንደሚያምኑ ገልፀዋል፡፡