በአዲስ አበባ እና በባህርዳር ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች እና ፖለቲከኞች ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለቀናት በአደራ እስር ላይ ይገኛሉ
(ዳጉ ሚዲያ) በቅርቡ የተደረገውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ከዓመታት እስር በኋላ የተለቀቁ ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች፥ ፖለቲከኞችን ጨምሮ ሌሎች የመብት ተሟጋቾችን ጨምሮ ያለ በቂ ምክንያት ከመጋቢት 16 ቀን 2010 ዓ.ም.ጀምሮ በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ከነበሩበት የምሳ እና የ “እናመሰግናለን” ግብዣ ላይ በነበሩበት ወቅት በድጋሚ ታስረዋል።
በድጋሚ ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፥ አቶ አንዷለም አራጌ፥ ጦማሪ ዘላላም ወርቃገኘው፥ ወ/ት ወይንሸት ሞላ፥ ጦማሪ ማህሌት ፍንታሁን፥ ጦማሪና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ሀይሉ፥ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፥ አቶ ይድነቃቸው አዲስ፥ አቶ አዲሱ ጌታነህ፥ አቶ ተፈራ ተስፋዬ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ልዩ ስሙ ጎተራ ፖሊስ በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከመደበኛ ሥራቸው ተይዘው ከታሰሩት መካከል የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋችና ጦማሪ ስዩም ተሾመ እንዲሁም የመብት ተሟጋች እና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የፍትህ ቢሮ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደዓ በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ወህኒ ቤት ታስረው ይገናሉ።
በቅርቡ ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች መካከል በከፊል
በተያያዘ ዜና የአማራ ህዝብን ከአገዛዙ ጥቃት ለመከላከል በሚል በህጋዊ መንገድ የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅት ለመመስረት በይፋ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ የአካባቢ አስተባባሪዎች መካከል ከሌሎች ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በጋራ በመሆን ሰኞ መጋቢት 17 ቀን 2010 ዓ ም ባህርዳር ከተማ ተሰብስበው እራት ሲመገቡ በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው ከታሰሩ በኋላ ድብደባ እንድተፈፀመባቸው ተጠቆመ። ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በበእስር ላይ የሚገኙት ምሁራን፥ ፖለቲከኞች እና በዕለቱ በጓደኝነት እራት ግብዣው ላይ የተገኙ ጋዜጠኞች በባህርዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ይገኛሉ።
በባህር ዳር ከተማ ተይዘው ከታሰሩት መካከል ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ (ባህርዳር ዩንቨርሲቲ መምህርና የጣና ደህንነትና የአካባቢ ጥበቃ ማህበር ፕሬዚደንት እና ተመራማሪ፣ ረዳት ፕሮፊሰር)፥ ጋሻው መርሻ (የአንጸባቂው ኮከብ መጽኃፍ ከታቢ፤ አዲስ አበባ በማስተማር ሙያ ላይ ይገኛል)፥ የሱፍ ኢብራሂም (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበረና በአሁንኑ ወቅት ጠበቃ)፥ ተመስገን ተሰማ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር፤የወሎ ዩኒቨርስቲ የህግ ትምህርት ቤት መስራች፣ ረዳት ፕሮፊሰር እና አማራ ነን የሚለው መዝሙርም ገጣሚ)፥ በለጠ ሞላ ( ተባባሪ ፕሮፊሰር ፡አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ ጋዜጠኛ ንጋቱ አስረስ (የአማራ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ(አርታኢ)፤ከ1997 እስከ 1999 የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአማራ ተማሪዎች ማህበር ፕሬዜዳት፤)፥ ጋዜጠኛ በለጠ ካሳ (የቀለም ቀንድ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረ)፥ አቶ ሲሳይ አልታሰብ( ሲቪል ኢንጅነር)፥ አቶ ዳንኤል አበባው፥ አቶ መንግስቴ ተገኔ፥ አቶ ቦጋለ አራጌ፥ አቶ ካሱ ኃይሉ (የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ መምህር፡የማህበረሰብ ሳይንስ ተመራማሪ)፥ አቶ ተሰማ ካሳሁን፥ አቶ ድርሳን ብርሃኔ፥ አቶ በሪሁን አሰፋ፥ አቶ ፍቅሩ ካሳው፥ አዲሱ መለሰ (የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ አቶ ተመስገን ብርሃኑን ጨምሮ አንድ ስማቸው ያልተጠቀሰ ግለሰብም በእስር ላይ ይገኛሉ።
በአዲስ አበባ እና በባህርዳ ይታሰሩት ሁሉም ተከሳሾች ክስ እንዳልቀረበባቸውና የታሰሩበትም ምክንያት እንዳልታወቀ የተገኘው መረጃ አመልክታል። ይህንንም ተከትሎ ሐሙስ ምሽት መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ ም የተለያዩ ማኀበራዊ ሚዲያን በመጠቀም #ሁሉም_የፖለቲካ_እስረኞች_ይፈቱ የሚል ዘመቻ የተደረገ ሲሆን፤ ከአሰራቸው የመንግሥት አካል ግን የተሰጠ ምላሽ የለም።
ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ 5 ዓመት ከ4 ወር ቅጣት እስር ተበየነበት
( አዲስ ሚዲያ) የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ላይ 5 ዓመት ከ4 ወር የእስር ቅጣት ተበየነበት፡፡ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የደ ብርሃን ድረ-ገፅ ተባባሪ ብሎገር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ድህረ-ምረቃ ተማሪ የነበረ ሲሆን፤ በውጭ ሀገር የኢንተርኔት ደህንነት ስልጠና ለመውሰድ ማመልከቱ “ለሽብር ተግባር ተሰናድተዋል” በሚል በተመሰረተበት ክስ ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ሲል መበየኑ ታውቋል፡፡
በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ዘለዓለምን ጨምሮ 10 ተከሳሾች ከሰኔ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየታየ የነበረ ቢሆንም፤ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ሃታሙ አያሌው እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረው የሺዋስ አሰፋ፣ የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አባል አቶ አብርሃ ደስታ እንሁም መምህር አብርሃም ሰለሞን በተመሰረተባቸው ክስ በነፃ መሰናበታቸው ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ አቶ አብርሃ ደስታ ይህ ዜና እስከተዘገበበት ድሰር አሁንም በእስር ላይ ይገኛል፡፡
እነ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ጥፋተኝነት ሲበየንባቸው፣ አቶ በቀለ ገርባ እና ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጣቸው
በእነ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ከ600 ቀናት በላይ ፍርድ ቤት ሲመላሱ የቆዩት ተከሳሾች ላይ ዛሬ ብይን ተሰጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ሰለሞን ግርማ ፣ መምህር ተስፋዬ ተፈሪ ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡ በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ባህሩ ደጉ እና ዬናታን ወልዴ በነጻ ተሰናብተዋል፡፡
በተመሳሳይ የክስ ፋይል አብረው የተከሰሱት የፓቲካ ፓርቲ አመራሮች ( አብርሃ ደስታ ፣ ሃብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሸዋስ አሰፋ) እና መምህር አብርሃም ሰለሞን መከላከል ሳያስፈልጋቸው ነጻ መባላቸው ይታወሳል፡፡
ለአራት ወር ለሚጠጋ ጊዜ ማእከላዊ ምርመራ የከረሙት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው እና አብረው የታሰሩ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ተጨማሪ አንድ ሳምንት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ እስካሁን ድረስ በሽብር ከመጠርጠር ውጪ ክሳቸው በውል ያልታወቀው ፣ አቶ በቀለ ገርባ ፣ አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራውን ጨምሮ ኦሮሚያ ላይ የተነሳው ህዝባዊ አመጽ ተከትሎ ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል፡፡
ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት ቀርበው ለዛሬ ክሳቸው እዲነበብ የተቀጠሩት 33 በአዲስ አበባ ከተማ ቦሌ ቡልቡላ አካባ ኦነግ ተዋጊነት የተጠረጠሩት እነ ሃብታሙ ሚልኬሳ ዛሬም ክሳቸው ሳይሰማ ለሚያዝያ 20 ሌላ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ተላልፏል፡፡
ምንጭ፡- EHRP
ለመከላከያ ምስክርነት የተጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ “ሊቀርቡ ባለመቻላቸው” ምስክርነታቸው ውድቅ ተደረገ
*አብርሃ ደስታ 4 ወራት፣ የሺዋስና ዳንኤል 2 ወራት እስር ይቀራቸዋል
በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ አንደኛ ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ በቀረበበት የሽብር ክስ ላይ ከግንቦት ሰባት ዋና ጸሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጋር ተጻጽፈሃል የሚል ማስረጃ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት በመግለጽ ይህን እንዲከላከሉለት አቶ አንዳርጋቸውን ለምስክርነት ቢጠራቸውም በተደጋጋሚ ቀጠሮ ሊቀርቡ ባለመቻላቸው ከፍተኛው ፍርድ ቤት ምስክሩ በተከሳሽ በኩል እንደተተው ይቆጠራል በሚል በይኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ዛሬ የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም ብይኑን ሲያሰማ እንደገለጸው ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ ምስክሩን በተመለከተ በተደጋጋሚ እንዲቀርቡለት ጠይቆ እንዳልቀረቡለት በመግለጽ ‹‹ምስክሩ የማይቀርቡልኝ ከሆነ ከምስክሩ ጋር በተያያዘ የቀረበብኝ ክስ ፍሬ ነገር ከክሱ ወጥቶ ብይን ይሰጠኝ›› የሚል አቤቱታ አቅርቧል፡፡
አቃቤ ህግ በበኩሉ ተከሳሹ ምስክሩን አቅርቦ የማሰማት ግዴታ እንዳለበት በመጥቀስ ተከሳሹ የጠየቀው የፍሬ ነገር ይውጣልኝ አቤቱታ የህግ አግባብን የተከተለ ስላልሆነ ምስክሩን እንደተዋቸው ተቆጥሮ ብይን እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡
ችሎቱ በበኩሉ ለምስክሩ የተጻፈው የመጥሪያ ትዕዛዝ ደርሷቸው እንደቀሩ ማረጋገጫ ስለሌለ በተከሳሽ የቀረበው አቤቱታ ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ምስክሩ እንደተተው ቆጥሮ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ በመዝገቡ ላይ በተካተቱት አምስት ተከሳሾች ላይ የፍርድ ብይን ለመስጠት ለመጋቢት 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ከዚህ ቀጠሮ በፊት የክርክር ማቆሚያ ካላቸው ግራቀኙም በጽህፈት ቤት በኩል በጽሁፍ ማቅረብ እንደሚችሉ ፍርድ ቤቱ ገልጹዋል፡፡
በሌላ በኩል ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በዚሁ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ከተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ነጻ ናቸው በሚል የተበየነላቸው እነ አብርሃ ደስታ በዚሁ ችሎት፣ ‹‹ችሎት ደፍራችኋል›› በሚል የተላለፈባቸው ቅጣት ከመቼ ጀምሮ እንደሚታሰብ ግልጽ አድርጓል፡፡
በዚህም አመት ከአራት ወር የተፈረደበት አቶ አብርሃ ደስታ እና እያንዳንዳቸው አንድ አመት ከሁለት ወር የተፈረደባቸው አቶ የሺዋስ አሰፋ እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ በሚታሰብ እስር መቀጣታቸውን ገልጹዋል፡፡ በመሆኑም አብርሃ አራት ወራት፣ እና እነ የሺዋስ ሁለት ወራት እስር ይቀራቸዋል ማለት ነው፡፡
እነ አብርሃ ደስታ አቃቤ ህግ በጠየቀባቸው ይግባኝ ላይ ብይን ለማግኘት ለመጋቢት 30 ቀን 2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀጠሮ እንዳላቸው ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የምስክርነት ቃሉን ሰጠ
*”የህሊና እስረኛ ነኝ” እስክንድር ነጋ
በሽብርተኝነት ወንጀል ጥፋተኛ ተብሎ 18 ዓመት እስር ተፈርዶበት በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የመከላከያ ምስክርነት ቃሉን ሰጥቷል፡፡
በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ አንደኛ ተከሳሽ ለሆነው አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ መከላከያ ምስክር ሆኖ ልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከእስር ቤት የቀረበው ጋዜጠኛ እስክንድር ጥር 27 ቀን 2008 ዓ.ም ምስክርነቱን ሊያሰማ ችሏል፡፡
ያለጠበቃ በግሉ የሚከራከረው ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ጋዜጠኛ እስክንድር እንዲያስረዳለት የሚፈልገው ጭብጥ ጡመራ ምንድነው፣ ከወንጀል ጋርስ ግንኙነት አለው ወይ፣ እና ሰብዓዊ መብት እና ዴሞክራሲ ላይ ስልጠና ስለሚሰጡ ድርጅቶችና የስልጠናው ይዘትን በተመለከተ እንደሆነ ቢያስታውቅም በጭብጡ ላይ አቃቤ ህግ ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡ በዚህም አቃቤ ህግ ጡመራ ምንድነው፣ ወንጀልስ ነው ወይ የሚለው በምስክር ሳይሆን በህግ ድንጋጌዎች የሚረጋገጥ እንደሆነ በመግለጽ ተቃውሟል፡፡ ፍርድ ቤቱም ግራ ቀኙን ከሰማ በኋላ ጡመራ ወንጀል ስለመሆን አለመሆኑ የተያዘውን ጭብጥ ውድቅ በማድረግ ስለ ስልጠናውና አሰልጣኝ ተቋማት የተመዘገበው ጭብጥ ላይ ምስክሩ እንዲመሰክሩ ብይን ሰጥቷል፡፡
ብይኑን ተከትሎ ምስክሩ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ችሎት ፊት የቀረበ ሲሆን በመጀመሪያ በፍርድ ቤቱ የቀረቡለትን ጥያቄዎች መልሷል፡፡ ምስክሩ ሙሉ ስሙን፣ እድሜውን፣ ስራውንና ለምን እንደመጣ፣ እንዲሁም ከተከሳሾች ጋር ስለመተዋወቁ ለቀረቡለት ጥያቄዎች መልስ ሰጥቷል፡፡ እስክንድር ‹‹ስራ›› ተብሎ ሲጠየቅ፣ ‹‹ጋዜጠኛ ነበርኩ›› ብሏል፡፡ ‹‹አሁንስ›› የሚል ጥያቄ ፍርድ ቤቱ አቅርቦለት፣ ‹‹አሁን የህሊና እስረኛ ነኝ›› ሲል መልሷል፡፡
ተከሳሹ ዘላለም ወርቃገኘሁ በዋና ጥያቄ ተከሳሹ ውጭ ሀገር ሊወስደው ነበር ተብሎ በክሱ ላይ ስለተጠቀሰው ስልጠና ምስክሩ እንዲያብራሩለት ጠይቋል፡፡ ምስክሩም ‹‹ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ሌሎች ሀገራትንም የሚያሳትፍ ስልጠና በሰብዓዊ መብት፣ በሚዲያ ‹ኢቲክስ›፣ እና በዴሞክራሲ ላይ ይሰጣሉ፡፡ ድርጅቶቹ የተለያዩ ቢሆንም በሰብዓዊ መብት ጉዳይ ላይ መርሃቸው ተመሳሳይና ዓለም አቀፍ ነው›› በማለት መስክሯል፡፡
ድርጅቶቹን በስም መጥቀስና የሚገኙበትንም ሀገር ለፍርድ ቤቱ መግልጽ ይቻል እንደሆነ ምስክሩ ተጠይቆ ‹‹የተቋማቱ መገኛ ምዕራቡ ዓለም ነው፡፡ በዴሞክራሲ የዳበሩ ሀገራት ነው ዋና መቀመጫቸው፡፡ ሲ.ፒጄ፣ ፍሪደም ሀውስ፣ አምንስቲ ኢንተርናሽናል እና አርቲክል 19 የመሳሰሉትንም በስም መጥቀስ ይቻላል፡፡ እኔም ከነዚህ ተቋምት ውስጥ በአንዱ የተሰጠ ስልጠና አዲስ አበባ ላይ ተካፍየ ነበር፡፡ ስልጠናው ስለ ሰብዓዊ መብት፣ ስለ ሚዲያ፣ ስለ ዴሞክራሲ የሚያስተምር ነው፡፡ ስልጠናው ከሽብር ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፤ ይህ እንደማስረጃ መቅረቡ ኢትዮጵያን ትዝብት ውስጥ የሚከትና የሚያሳዝን ነው›› ሲል ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ መቼ እንደታሰረ በመስቀለኛ ጥያቄ ተጠይቆ ‹‹መስከረም 2004 የሀሰት ክስ ቀርቦብኝ፣ በግፍ ተፈርዶብኝ ታስሬ እገኛለሁ›› ሲል መልሷል፡፡ እስክንድር ነጋ ጥቁር ሱፍ በደብዛዛ ሸሚዝ ለብሶ፣ ሙሉ ጥቁር መነጸር አድርጎና ነጠላ ጫማ ተጫምቶ ችሎት ፊት ቀርቧል፡፡
አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ምስክሩ ምስክርነቱን ማጠቃለሉን ተከትሎ በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡለት የጠራቸው ሌላኛው ምስክር አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በተደጋጋሚ እንዲቀርቡለት ትዕዛዝ እንዲሰጥለት የጠየቀ ቢሆንም እስካሁን አለመቅረባቸው መንግስት ግለሰቡን ለማቅረብ ፍላጎት እንደሌለው ያሳያል ሲል ቅሬታውን አሰምቷል፡፡ ‹‹አሁን የተረዳሁት ነገር ከሳሼ የሆነው መንግስት አቶ አንዳርጋቸውን ከሚያቀርብ እኔን በነጻ መልቀቅ እንደሚቀለው ነው›› ብሏል ተከሳሹ፡፡
ተከሳሹ ከአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ጋር በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች እንደተገናኜ አቃቤ ህግ መጥቀሱን በማስታወስ ምስክሩ መቅረባቸው ያለውን ተገቢነት አስረድቷል፡፡ ‹‹ምስክሩ እንዲቀርቡልኝ እፈልጋለሁ፡፡ ይህ የማይሆን ከሆነ ግን ፍርድ ቤቱ ከምስክሩ ጋር በተገናኘ ያለውን የክሱ ፍሬ ነገር አውጥቶ በቀሪው ላይ ብይን ይስጥልኝ›› ብሏል ተከሳሹ አቶ ዘላለም፡፡
ፍርድ ቤቱም ምስክሩ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲቀርቡ ትዕዛዝ በመስጠት ምስክርነታቸውን ለመስማት በሚል ለየካቲት 16 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ