Tag Archives: Ethiopian political prisoners

በአዲስ አበባ እና በባህርዳር ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች እና ፖለቲከኞች ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለቀናት በአደራ እስር ላይ ይገኛሉ

(ዳጉ ሚዲያ) በቅርቡ የተደረገውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ከዓመታት እስር በኋላ የተለቀቁ ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች፥ ፖለቲከኞችን ጨምሮ ሌሎች የመብት ተሟጋቾችን ጨምሮ ያለ በቂ ምክንያት ከመጋቢት 16 ቀን 2010 ዓ.ም.ጀምሮ በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ከነበሩበት የምሳ እና የ “እናመሰግናለን” ግብዣ ላይ በነበሩበት ወቅት በድጋሚ ታስረዋል።

በድጋሚ ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፥ አቶ አንዷለም አራጌ፥ ጦማሪ ዘላላም ወርቃገኘው፥ ወ/ት ወይንሸት ሞላ፥ ጦማሪ ማህሌት ፍንታሁን፥ ጦማሪና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ሀይሉ፥ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፥ አቶ ይድነቃቸው አዲስ፥ አቶ አዲሱ ጌታነህ፥ አቶ ተፈራ ተስፋዬ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ልዩ ስሙ ጎተራ ፖሊስ በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከመደበኛ ሥራቸው ተይዘው ከታሰሩት መካከል የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋችና ጦማሪ ስዩም ተሾመ እንዲሁም የመብት ተሟጋች እና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የፍትህ ቢሮ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደዓ በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ወህኒ ቤት ታስረው ይገናሉ።

Ethiopian re-arrested political Prisoners
በቅርቡ ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች መካከል በከፊል

በተያያዘ ዜና የአማራ ህዝብን ከአገዛዙ ጥቃት ለመከላከል በሚል በህጋዊ መንገድ የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅት ለመመስረት በይፋ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ የአካባቢ አስተባባሪዎች መካከል ከሌሎች ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በጋራ በመሆን ሰኞ መጋቢት 17 ቀን 2010 ዓ ም ባህርዳር ከተማ ተሰብስበው እራት ሲመገቡ በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው ከታሰሩ በኋላ ድብደባ እንድተፈፀመባቸው ተጠቆመ። ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በበእስር ላይ የሚገኙት ምሁራን፥ ፖለቲከኞች እና በዕለቱ በጓደኝነት እራት ግብዣው ላይ የተገኙ ጋዜጠኞች በባህርዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ይገኛሉ።

በባህር ዳር ከተማ ተይዘው ከታሰሩት መካከል ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ (ባህርዳር ዩንቨርሲቲ መምህርና የጣና ደህንነትና የአካባቢ ጥበቃ ማህበር ፕሬዚደንት እና ተመራማሪ፣ ረዳት ፕሮፊሰር)፥ ጋሻው መርሻ (የአንጸባቂው ኮከብ መጽኃፍ ከታቢ፤ አዲስ አበባ በማስተማር ሙያ ላይ ይገኛል)፥ የሱፍ ኢብራሂም (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበረና በአሁንኑ ወቅት ጠበቃ)፥ ተመስገን ተሰማ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር፤የወሎ ዩኒቨርስቲ የህግ ትምህርት ቤት መስራች፣ ረዳት ፕሮፊሰር እና አማራ ነን የሚለው መዝሙርም ገጣሚ)፥ በለጠ ሞላ ( ተባባሪ ፕሮፊሰር ፡አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ ጋዜጠኛ ንጋቱ አስረስ (የአማራ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ(አርታኢ)፤ከ1997 እስከ 1999 የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአማራ ተማሪዎች ማህበር ፕሬዜዳት፤)፥ ጋዜጠኛ በለጠ ካሳ (የቀለም ቀንድ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረ)፥ አቶ ሲሳይ አልታሰብ( ሲቪል ኢንጅነር)፥ አቶ ዳንኤል አበባው፥ አቶ መንግስቴ ተገኔ፥ አቶ ቦጋለ አራጌ፥ አቶ ካሱ ኃይሉ (የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ መምህር፡የማህበረሰብ ሳይንስ ተመራማሪ)፥ አቶ ተሰማ ካሳሁን፥ አቶ ድርሳን ብርሃኔ፥ አቶ በሪሁን አሰፋ፥ አቶ ፍቅሩ ካሳው፥ አዲሱ መለሰ (የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ አቶ ተመስገን ብርሃኑን ጨምሮ አንድ ስማቸው ያልተጠቀሰ ግለሰብም በእስር ላይ ይገኛሉ።

በአዲስ አበባ እና በባህርዳ ይታሰሩት ሁሉም ተከሳሾች ክስ እንዳልቀረበባቸውና የታሰሩበትም ምክንያት እንዳልታወቀ የተገኘው መረጃ አመልክታል። ይህንንም ተከትሎ ሐሙስ ምሽት መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ ም የተለያዩ ማኀበራዊ ሚዲያን በመጠቀም #ሁሉም_የፖለቲካ_እስረኞች_ይፈቱ የሚል ዘመቻ የተደረገ ሲሆን፤ ከአሰራቸው የመንግሥት አካል ግን የተሰጠ ምላሽ የለም።

የተከሳሾች እና ከሳሾች ወግ ትዝብት

በጌታቸው ሺፈራው

“ቶርች ሲያስደርጉን የነበሩት ጌታቸው አምባዬ ናቸው። እግርና እጃችን በካቴና አሳስረውናል።” 36ኛ ተከሳሽ ካሳ መሃመድ
~”አማራ፣ ጉራጌ፣ ኦሮሞ፣ ሙስሊም በመሆናችን ብቻ ተከሰናል። እኔ የተከሰስኩት ጉራጌ ስለሆንኩ ነው። የዶ/ር ብርሃኑ ነጋ፣ የዶ/ር ታደሰ ብሩ ዘመድ ነህ እየተባልኩ ነው የተመረመርኩት። “22ኛ ተከሳሽ ሚስባህ ከድር
~”እኔ ከዚህ ፍርድ ቤትም፣ ከአምባገነኑ መንግስትም ፍትህ አልጠብቅም። ለታሪክ ነው የምከራከረው። ” 1ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ
~”የሰውን ልጅ እንደሰው አለመቁጠር፣ ህሊና ቢስነት ነው።” 13ኛ ተከሳሽ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ
~”እኛ የተከሰስነው ለምን ከእሳትና ከጥይት ተረፋችሁ ተብለን ነው።” 31ኛ ተከሳሽ ጌታቸር እሸቴ
~”ማረሚያ ቤት አንድ ቀን ባደርኩ ቁጥር ለህይወቴ እሰጋለሁ” 5ኛ ተከሳሽ አግባው ሰጠኝ
~”በሌላ ሀገር ከእግዚያብሔር ቀጥሎ ፍትሕ የሚሰጥ ፍርድ ቤት ነው። በእኛ ሀገር ግን በደሕንነት ብጣሽ ውቀትና ስልክ ትዕዛዝ ነው የሚሰራው።” 3ኛ ተከሳሽ አሸናፊ አካሉ
~”እነዚህን ዐቃቤ ሕግ ብሎ መጥራት አይቻልም። ዐቃቤ ሕግ ማለት በጥላቻ ግለሰብን የሚያጠቃ፣ ህሊና ቢስ አይደለም።” 25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ
~”ከአሁን በኋላ ወደ ፍርድ ቤት መመላለስ አልፈልግም። ፍርድ ቤት በሌለሁበት የሚወስነውን ውሳኔ በማረሚያ ቤት ሆኜ እቀበላለሁ” 18ኛ ተከሳሽ አንጋው ተገኘ
~”እኔ ለህሊናዬ የምኖር ሰው ነኝ። ስሜ መጥፋት የለበትም። እኔ እንደዛ ባደርግ እንኳ ተቋሙ ነው የሚከራከረው።” መኩሪያ አለሙ (ዐቃቤ ሕግ)
~”በሚዲያ የሚነገር ነገር አለ።ተፅዕኖ ያመጣል። ምስክሮችም ላይመጡ ይችላሉ። ከሳሽ የለሁበትም ሲል ወዲያውኑ ማንሳት አለበት። …” ፍርድ ቤቱ

ዐቃቤ ሕግ በቂሊንጦ ቃጠሎ ሰበብ በታሰሩት፣ በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ክስ መዝገብ (38) ተከሳሾች ላይ 85 ምስክር አስቆጥሯል። ዐቃቤ ሕግ ተደጋጋሚ ቀጠሮዎች ተሰጥተውት ምስክሮችን አሰምቷል። ከነሃሴ 1 እስከ ነሃሴ 12/2009 በነበረው ተከታታይ ቀጠሮ የተወሰኑ ካሰማ በኋላ፣ የ5 ወር ቀጠሮ ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010 ዓም በተሰጠው ቀጠሮ ጥቂት ምስክሮችን አሰምቷል። በዚህ ቀጠሮ ለተከታታይ 5ቀን ምስክር ሳያቀርብ ተከሳሾች ተመላልሰዋል። በ5ቱ ተከታታይ ቀናት ጉዳዩን የማያውቁ ዐቃቤ ሕጎች ተመላልሰዋል።ዛሬ ጉዳዩን የሚያውቁት ሶስት ዐቃቤ ሕጎች ተሰይመው ቀሪ 28 ምስክር ስላላቸው ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። አንድ ዐቃቤ ሕግ ቀጠሮው እስከ ጥር 7/2010 ስለመሰላቸው፣ በዚህ ጊዜ ለማቅረብ ሀሳብ እንደነበራቸው ገልፀዋል። ዐቃቤ ሕጎች ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጥያቄ ካቀረቡ በኋላ ጠበቆችና ተከሳሾች ተቃውሞ አቅርበዋል። በተለይ ተከሳሾች ምሬታቸውን ጭምር ገልፀዋል። ዐቃቤ ሕግ ተዘለፍኩ ብሏል። ፍርድ ቤቱ በመሃል ገብቷል። የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የነበረው ክርክር ከሞላ ጎደል እንደሚከተለው ቀርቧል።

~3ኛ ተከሳሽ አሸናፊ አካሉ:_ “በዚህ ችሎት 5አመት ተመላልሻለሁ። ዐቃቤሕግ ይጀምራል። ዐቃቤ ሕግ ይጨርሳል። ዐቃቤ ሕጉ መኩሪያ አለሙ ቀጠሮው እስከ ጥር 7/2010ዓም ስለመሰለኝ ነው ብሏል። በጣም ያሳዝናል። አምስት አመት በሙሉ ምንም ፍትሕ ሳላገኝ ተጨማሪ ቀጠሮ ይሰጠኝ የሚለው ሌላ ስድስተኛ አመት እንድታሰር ነው። እንደአለመታል ሆኖ እንጅ በሌላ ሀገር ከእግዚያብሔር ቀጥሎ ፍትሕ የሚሰጥ ፍርድ ቤት ነው። በእኛ ሀገር ግን በደሕንነት ብጣሽ ውቀትና ስልክ ትዕዛዝ ነው የሚሰራው። እስኪ ስልጣናችሁን ተጠቀሙበት! በጣም ያሳዝናል።”

~18ኛ ተከሳሽ አንጋው ተገኘ:_”(ዐቃቤ ሕጎች) ባህሪያቸው እንደዚህ ነው። ነሃሴ ላይ በነበረው ቀጠሮው ምስክር ሳያቀርቡ ብዙ ቀን አሳልፈዋል። እኛ ትግስት ያደረግነው እውነቱ እንዲወጣ ነው። 5ወር ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ምስክር ማቅረብ አልቻሉም። እነሱ በ5ውስጥ የወር ደሞዛቸውን ይወስዳሉ።……ምስክር የተባሉት ሰዎች አንመሰክርም ብለዋል። የመሰከሩትም “ቶርች”ተደርገው የመሰከሩ ናቸው። ከአሁን በኋላ ወደ ፍርድ ቤት መመላለስ አልፈልግም። ፍርድ ቤት በሌለሁበት የሚወስነውን ውሳኔ በማረሚያ ቤት ሆኜ እቀበላለሁ”
~13ኛ ተከሳሽ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ:_ “ሁሉ ነገር በፅሑፍ የለም። ዳኝነትም በህሊና ነው። ዐቃቤ ሕግ ቤተሰብ የምናስተዳድር፣ ህይወት የምንመራ ሰዎችን አስሮ በህይወታችን ላይ ቀልድ ነው የያዘው። በመጀምርያው 10 ቀን እንድታቀርብ ተብሎ በራሱ ቁጥጥር ስር ያሉትን ማቅረብ አልቻለም። ባለፈው ቀጠሮ ፖሊስ ምስክር ስላላመጣ ዐቃቤ ሕጉ ፖሊስ ያላቀረበው ቀጠሮው ለአንድ ቀን ብቻ ስለመሰለው ነው ብሎ ነበር። ላለፉት 5 ቀናት አላመጣም። በ5 ቀን ያላመጣውን በመላ ኢትዮጵያ ተፈላልገው ይምጡልኝ ማለት የሰውን ልጅ እንደሰው አለመቁጠር፣ ህሊና ቢስነት ነው።”

~1ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ:_ “ዐቃቤ ሕግን እንደተቋም ነው የምናየው። እነሱም ይላሉ። ከሆነ በየቀኑ የሚመጡት ዐቃቤ ሕጎች ተመሳሳይ ነገር መናገር ነበረባቸው። የሚሰጡት ማስተባበያ አሳፋሪ ነው። ለህግ እውቀት ላላቸው ደግሞ ይበልጥ ያሳፍራል። እኔ ከዚህ ፍርድ ቤትም፣ ከአምባገነኑ መንግስትም ፍትህ አልጠብቅም። ለታሪክ ነው የምከራከረው። የተገደሉት ወንድሞቻችን እንደኛ በማንነታቸው ተከሰው እስር ቤት የገቡ ናቸው። ከዐቃቤ ሕግ ለእኛ ይቀርባሉ። እኛም ሞት ተፈርዶብን ነበር። እንደ እድል ሆኖ በህይወት አለን።……… የተገረፍነውን ግርፋት ረስተን፣ ችለን ከዐቃቤ ሕግ ጋር እየተከራከርን ነው። እኛ ሞትን ተጋፍጠን ነው እየተከራከርን ያለነው። የታፈነው የነሃሴ 28/2010 (የቂሊንጦ ቃጠሎ) ታሪክ ትተነው የምናልፈው አይደለም። በዚህ ችሎት በተደጋጋሚ ቀርቤያለሁ። በዚህ ችሎት ምንም አይነት እምነት የለኝም። እናንተ ለእኛ መልካም ስትሆኑ በሙስና ትከሰሳላችሁ፣ለእኛ ክፉ ስትሆኑ ደግሞ ሹመት ይሰጣችኋል። ከዚህ አምባገነን መንግስት ጋር ተከራክሬ ፍትህ አገኛለሁ ብየ አልጠብቅም።

ውሃ እንኳን በህግ አምላክ ሲባል ይቆማል የሚል ማህበረሰብ ነው ያሳደገኝ።……እኔ በሙያዬ ስለ አየር ኃይል ልከራከር እችላለሁ። ስለ ፍትህ መከራከር ያለባችሁ እናንተ ናችሁ።”
~5ኛ ተከሳሽ አግባው ሰጠኝ:_” እኛ ያለነው በማረሚያ ቤት ነው። አንድ ቀን ባደርኩ ቁጥር ለህይወቴ እሰጋለሁ። እናንተ እስረኞችን በአደራ በማረሚያ ቤት አስቀምጣችኋቸው ሲሞቱ ለምን ሞቱ ብላችሁ አልጠየቃችሁም። እኔም በማረሚያ ቤት አንድ ቀንም እንድቆይ የሚያደርግ ቀጠሮ እንዲቀጠርብኝ አልፈልግም።”

~31ኛ ተከሳሽ ጌታቸር እሸቴ:_”እኛ የተከሰስነው ለምን ከእሳትና ከጥይት ተረፋችሁ ተብለን ነው። ክራውን ፍርድ ቤት ስንቀርብ መኩሪያ (ዐቃቤ ሕግ) አዎ ቀርጬሃለሁ ብሎኛል። የቀረፀኝ ለእኔም ለፍርድ ቤቱም ስለሚጠቅም እንዲያቀርብልኝ እፈልጋለሁ።30ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር ከመቀሌ ይመጣሉ ተብሏል። በእርግጥ ከመቀሌ ካልሆነ ከየትም ሊመጡ አይችሉም።……በድሉ በላይ የተባለ ምስክር በነፍስ የገባ፣ ሲገባ እኔ የተቀበልኩት ሰው ነው። ነፍስ አጥፍቶ የታሰረ ሰው መስክሮ ተፈትቷል። ምስክሮች ወንጀላቸው እየተነሳላቸው ከእስር በተፈቱበት ሁኔታ አላገኘናቸውም ማለት በእኛ ላይ ቁማር መጫወት ነው። ”
~38ኛ ተከሳሽ ከድር ታደለ:_ “……ከዐቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግራችሁ ነው የምትሰሩት? መስክሩ የሚባሉት ተገደው ነው። የተፈቱት መመስከር ስለማይፈልጉ ይጠፋሉ። ማረሚያ ቤት ውስጥ ያሉት መስክሩና ትፈታላችሁ ስለሚባሉ ይመሰክራሉ። መስክሩ ከእስር ትለቀቃላችሁ እየተባሉ ነው። ዛሬ ዐቃቤ ሕጎች እንደሰርግ አጃቢ ተሰብስበው የመጡት ቀጠሮ ለማስቀጠር ነው። እስከዛሬ ጉዳዩን የማያውቅ ዐቃቤ ሕግ ነበር የሚልኩት ። ፍርድ ቤቱ በዐቃቤ ሕግ ጥያቄ መሰረት ቀጠሮ የሚፈቅድ ከሆነ ከዐቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግሮ እንደሚሰራ 100 % ማረጋገጫ ይሆናል።

25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ:_ ምስክሮች ተለይተው አንድ ቦታ ነበር የተቀመጡት። እየመከሯቸው ይሆናል።…ዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን በጥንቃቄ መያዝ ነበረበት።…ከጫፍ እስከጫፍ መብቱን የጠየቀውን ስንት ሰው የሚያስር መንግስት ምስክሮችን ማምጣት አይከብደውም ነበር።……እነዚህን ዐቃቤ ሕግ ብሎ መጥራት አይቻልም። ዐቃቤ ሕግ በጥላቻ ግለሰብን የሚያጠቃ፣ ህሊና ቢስ አይደለም። መኩሪያ ሸዋሮቢት እስር ቤት መጥቶ “የመንግስት ስም ከሚጠፋ እናንተ ብትጠፉ ይሻላል” ብሎናል።……
~አንተነህ አያሌው (ዐቃቤ ሕግ):_ እኛ እዚህ የምንቀርበው ህጋዊ ክርክር ለማድረግ እንጅ ማንም እንዲሰድበን አይደለም። እስካሁን ባደረግነው ክርክር የማንንም ተከሳሽ፣ ወይም ጠበቃ ስም አንስተን አልዘለፍንም። ማንም እየተነሳ ህሊና ቢስ እያለ እያደበን ፍርድ ቤቱ ዝም እያለ ቆመን ቆመን መከራከር አንችልም። ተከራካሪ ወገኖችን ለማሸማቀቅ እየተሰራ ነው። እኛ፣ ፍርድቤቱ እና ህብረተሰቡ እየተዘለፈ ነው።
~መኩሪያ አለሙ(ዐቃቤ ሕግ):_ የህግ ባለሙያ ነኝ ተቋሙ በላከኝ ቦታ ሄጄ እሰራለሁ።ሸዋሮቢት የተከሳሾችን አያያዝ አጣራ ተብሎ ሄጃለሁ። እንደ ባለሙያ ሁለት ተከሳሾችን አነጋግሬያለሁ። እዛ ቦታ ላይ የተነገረውን ብናወራው ተከሳሾችን ይጎዳል። እኔ ለህሊናዬ የምኖር ሰው ነኝ። ስሜ መጥፋት የለበትም። እኔ እንደዛ ባደርግ እንኳ ተቋሙ ነው የሚከራከረው። የተማርኩትም ያሳደገኝ ማህበረሰብም እንዲህ ነገር አላስተማረኝም።

~ካሳሁን አውራሪስ (ዐቃቤ ሕግ):_ በዚህ አይነት ክርክር የግለሰብ ስም በመጥራት መከራከር ጉዳዩን አቅጣጫ የሚያስቀይር ነው። ችሎት ተደፈረ የሚባለው ችሎቱ ሲዘለፍ ብቻ አይደለም። ህሊና ቢስ እየተባልን እየተዘለፍን ነው።……
~ፍርድ ቤቱ (መሃል ዳኛው):_ ሰው መብቱን ለመጠቀም ተብሎ የሚናገረውን ቃል ከወጣ በኋላ መመለስ አይቻልም። ነገር ግን የችሎቱን ክብር በሚጠብቅ መልኩ ማነገር ይገባል። … ዐቃቤ ሕግ ያቀረቡትም ይህን ነው። የዳኛ ስራ ከትምህርት ቤት የተለየ ነው። የተከሰሰ፣ ከሳሽ፣ የተጎዳውም ሀሳቡን የሚያቀርበው ፍርድ ቤት ነው። ሀሳቡን ሲገልፅ ግን ለዳኞች ፈተና ነው። እንደትምህርት ቤት አይደለም። ጎጅውም ተጎጅውም በአካል ነው የሚመጡት።ዳኞች ፈተና ውስጥ ይገባሉ። ፈተናውን ለመቋቋም የችሎቱ ሂደት ሰላማዊ መሆን አለበት።…… ትርፍ ነገር ይነገራል። ይህን ስንገድብ ሌላ ይቀራል በሚል እንታገሳለን። መታገሱ ለህግ የበላይነት ይጠቅማል። ኮሽ ባለ ቁጥር አይተኮስም እንደተባለው ነው። በተናገራችሁ ቁጥር 1 አመት ብንቀጣ 25 አመት ይደርሳል። መሳደብ አይጠቅምም። አፍ መያዝ ግን አንችልም።…… በሚዲያ የሚነገር ነገር አለ።ተፅዕኖ ያመጣል። ምስክሮችም ላይመጡ ይችላሉ። ከሳሽ የለሁበትም ሲል ወዲያውኑ ማንሳት አለበት። ……የፍርድ ቤት ክብር የእኔ አይደለም። በክብር የተቀመጠው ሰው ጭምር ነው።…”
~25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ:_ የፍትህ አካሉንም እውነቱ እንዲወጣ እንከራከራለን። የተገደሉት ወንድሞቻችን ናቸው። ሲገደሉ በአይናችን አይተናል። ያም ሆኖ ገድላችኋቸዋል ተብለን ተከሰናል። ይህ ሁሉ ስሜታዊ ያደርገናል።…… ዐቃቤ ሕግ የሚያቀርባቸው ምክንያቶች ምክንያታዊ የሚያደርጉ አይደሉም። ፍርድ ቤቱ ይህን አይቶ ውሳኔ እንዲሰጥ ነው።

~22ኛ ተከሳህ ሚፍታህ ከደር:_ በዚህ ሀገር የዐቃቤ ሕግ ስልጣን ገደብ ሊኖረው ይገባል። ከታሰርኩ አራት አመት ሊሞላኝ ነው። ባልተጣራ ክስ ከሶኝ ነፃ ተብያለሁ። አሁን ደግሞ ሌላ ክስ አቅርቦብኛል። የተከሰስኩት በማንነቴ ነው። በፈለገው ወንጀል እየከሰሰ የፈለገውን ያህል ያስራል። ይህን በማድረጉ አይጠየቅም። እኛ ደግሞ አንካስም። የተወሰኑ ሰዎች እንዳይከሰሱ ሲባል ዐቃቤ ሕግ ሸዋሮቢት ሄጀ አነጋግሬያቸዋለሁ ብሏል። ስለተፈፀመብን ነገር ግን አልገለፀም። ሰብአዊ መብት ግን ጥፍራችን መነቀሉን፣ ጣታችን መሰበሩን…መገረፋችን ገልፆአል። የትኛው ነው እውነቱ? ገዳይ ነው እየመሰከረብን ያለው። ኦፊሰር ገ/ማርያመው ሲገድል እያየን ነው መጥቶ የመሰከረብን። ክሱ ላይ ያልተጠቀሰ 24ኛ ሰው መሞቱን መስክሮ ሄዷል። ቴዎድሮስ የሚባለው ሟች በክሱ አልተጠቀሰም።…… በማናውቀው ጉዳይ ነው የተከሰስነው። ከፍተኛ በደልና ስቃይ እየደረሰብን ነው። አንድ ፍራሽ ላይ ለሁለት ነው የምንተኛው።

~34ኛ ተከሳሽ ፍፁም ጌታቸው:_ ለሞቱት ነው የምንከራከረው ብለዋል። የሞተውኮ ከ150 ሰው በላይ ነው። ዞን 5 አርማዬ ዋቄ ተደብስቦ ነው የተገደለው። እነዚህ ገዳዮች አይጠየቁም? ……ከዚህ ችሎት ከሚከታተለው መካከል የሟች ቤተሰብ አለ? በመኪና አደጋ የሞተ ሰው ቤተሰብ እንኳ ችሎት ይታደማልኮ!
~36ኛ ተከሳሽ ካሳ መሃመድ:_ፍርድ ቤቱ ማረሚያ ቤት ውስጥ ያለውን ችግር ይወቅልን። ዞን 5 ያለን እስረኞች ኦፊሰር ገብረማርያም መስክሮ ከሄደ በኋላ ማስፈራሪያ እየደረሰብን ነው። ኦፊሰር ጉኡሽ መለስ ምስክርነቱ ይለቅና እንተያያለን እያለ እየዛተብን ነው። በህይወት እንድንቆይ ካስፈለገ ማረሚያ ቤቱ ጉዳይ መስተካከል አለበት።አሁንም እኛን ገድለው ሌላ የአማራና የኦሮሞ ልጆችን እኛን ገደላችሁ ብለው ይከሷቸዋል። እዚህ ወንበር ላይ የመሰከረው ገብረማርያም በጥይት እደፋሃለሁ ብሎኛል። እነ ካሳ መሃመድ፣ ተመስገን ማርቆስ፣አሸናፊ መለስ፣ ሚስባህ ከድር፣ አጥናፉ አበራ ቀይ መስመር አልፈዋል ዋጋቸውን ያገኛሉ ተብለናል። እኔ የድንግል ማርያም ልጅ ነኝ፣ በእናቴ ፀሎት እወጣለሁ። የእኛ አልበቃ ብሎ ሀገራቸውን ለማገልገል የመጡ ምሁራን ከእኛ ጋር ተከሰው እየተሰቃዩ ነው። ……ከእነ አግባው ጋር ዝዋይ ተወስደን፣ ራቁታችን በፓንት ብቻ ሆነን ተደብድበናል።……ይህ የለበስኩት ልብስ የተገደለው ጓደኛዬ የአርማዬ ዋቄ ልብስ ነው። ጫማውም የእሱ ነው። ከዝዋይ ስንመለስ ገድለውታል። እነ ገብረማርያም የህወሓትን ተልዕኮ ለማስከበር ነው። እኛ ደግሞ መብታችን ለማስከበር ፍርድ ቤት እንናገራለን። ቶርች ሲያስደርጉን የነበሩት ጌታቸው አምባዬ ናቸው። እግርና እጃችን በካቴና አሳስረውናል።… በሀገራችን ተገልብጥን ተገርፈናል። ኩላሊት በሽተኛ ሆነን ነው ተገልብጠን የተገረፍነው። ኧረ ስለመድሃኒያለም! እነሱ የተጨመቀ ቡና ሲጠጡ እኛ እየተጨነቅን ነው። እነሱ ዝልዝልና ቁርጥ ሲበሉ እኛ እየተዘለዘልን ነው።

(ፍርድ ቤት ዐቃቤ ሕግ ቀሪ 28 ምስክሮችን ለማቅረብ ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው ያነሳውን ጥያቄ፣ የተከሳሽ ጠበቆችና ተከሳሾች የዐቃቤ ሕግን ጥያቄ በመቃወም ምስክርነቱ ታልፎ ብይን እንዲሰጥ ያቀረቡትን ተቃውሞ ለመበየን ለነገ ጥር 4/2010ዓም ቀጠሮ ይዟል። በሌላ በኩል የቂሊንጦ ጥበቃና ደህንነት ኃላፊ ምስክርነት ከሰጡ በኋላ ኃላፊውን በችሎት ተናግራችኋል በሚል በማረሚያ ቤት ዛቻ እየደረሰብን ነው ያለው ካሳ መሃመድ አቤቱታውን በፅሁፍ አቅርቦ እንዲጣራ ፍርድ ቤቱ ገልፆለታል። ጉዳዩ ከምስክር አሰማም ጋር የተገናኘና ዝም ተብሎ መታለፍ ስለሌለበት ይጣራል ብሏል።)

ማሰርና ማሳደድ መፍትሄ ይሆናል?

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

በቀድሞ ታጣቂዎች እንደ ጭራቅና አውሬ ይሳል የነበረው የደርግ ስርዓት ወድቆ ስልጣን በአማፂዓን እጅ ከገባ 23 ዓመታት አልፈዋል፡፡ ነገር ግን የታሰበው ለውጥ ዛሬም ቢሆን መናፈቁን አልተወም፡፡ ምክኔቱም ያኔ ማሰር ነበር፤ ዛሬም ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ያኔም መወንጀልና መፈረጅ ነበር ዛሬ ግን ተባብሷል፡፡ ለእኔ ከድሮ የተለየ ተቀይሮ ያገኘሁት በዋናነት የመሪዎች ስምና ልብሳቸው እንጂ ስራቸው ያው ነው፡፡

በዘመነ ደርግ ጠባብነትና ዘረኝነትን እንዲሁም ኢትዮጵያ ላይ ጥላቻ ያላቸውን በሙሉ ስልጣኑን ሊቀናቀኑ ካሰቡት እኩል በጠላትነት ይፈረጃሉ፡፡ በዘመነ ኢህአዴግ ደግሞ ኢትዮጵያዊነትን ማስቀደምና ለኢትዮጵያውያን በእኩል ዓይን መቆምና መቆርቆር እንደ ወንጀል ይታያል፡፡ሁለቱም ወደ ስልጣን ሲወጡ በጠብመንጃ ሲሆን፤ ስልጣናቸውንም ያስጠበቁትን የሚያስጠብቁት እንዲ በጦር መሳሪያ ነው፡፡ምን አለፋችሁ፤ ልዩነቱን “…ጃሃ ያስተሰርያል” የሚለው የአርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (የቴዲ አፍሮ) ሙዚቃ በደንብ ይገልፀዋል፡፡

sssበሁለቱ መካከል ያለው መሰረታዊ ልዩነት ደርግ የማይፈልገውን ነገር በግልፅ በአዋጅ ይደነግጋል፤ከአዋጅ ወይም ህግ ውጭ ይቀጣል፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ የሚፈልገውንም ሆነ የማይፈልገውን በህገ መንግስት እውቅና ሰጥቶ የማይፈልገውን በሌላ አዋጅ ይቀጣል፣ያስራል፡፡ ልዩነታቸው የመሪዎች ስም፣ የለበሱት ልብስና አካሄዳቸው እንጂ መሰረታዊ የልዩነት ባህርይ አይታይባቸውም፡፡ ለዚህም አሁን በስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ ከደርግ በባሰ ያከናወናቸውን እና እያከናወናቸው ካሉት አሉታዊ ተግባራት መካከል በዋናነት የእስር ዘመቻውን ማንሳቱ በቂ ነው፡፡

በተለይ በምርጫ 1997 ዓ.ም. ኢህአዴግ በአደባባይ መሸነፉን እና የህዝብን ድምፅ መቀማቱን የሚያሳብ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ዋናው ገመናውን የሚያጋልጡና በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት ያላቸውን በሰበብ አስባቡ አስሮ ማሰቃየትን እንደ ትልቅ አማራጭ መጠቀም ጀመረ፡፡ ለዚህ በምርጫው ያሸነፉት የቀድሞ ቅንጅት አመራሮችን ከወነጀለበት በኢትዮጵያ 2000 ዓ.ም. ዋዜማ ከእስር ከፈታ በኋላ አዲሱ ቀዳሚ እስረኛ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ነበር፤ የእስርዓ ምዕት ኢትዮጵያ ጅማሮ እስረኛ፡፡ ይህም አዲስ አበባና አስመራን ጨምሮበመላው ዓለም ጥያቄና ተቃውሞ ከማስነሳቱ በተጨማሪ ከእስር ሲፈታም የህዝብ ድጋፍ በመላው ዓለም ተጠናክሮ እስከዛሬም ድረስ ዘልቋል፡፡

ከዚህ በኋላ የኢህአዴግ ጥላቻ እየተባባሰ፣ ለስልጣን ያለው ጥማት ሰርክ እንደ አዲስ ወይን እየጣመው ይሄድ ጀመር፡፡ ከስልጣናቸው በዕድሜ ይፍታህ የተሰናበቱት ሟቹ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በስልጣናቸው እስከ መቃብር አፋፍ ዋስትና ይሆናል ያሏቸውን አፋኝ ህጎች ፀድቀው ተግባር ላይ እንዲውሉ ቀን ከሌት ኳተኑ፡፡ በዚህም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኀበራት አዋጅ፣ የፕሬስ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ፣…ይገኙበታል፡፡

በተለይ በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች እና የነፃ ጋዜጠኞች ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ሰኔ 30 ቀን 2001 ዓ.ም. ፀድቆ ለምርጫ 2002 ዓ.ም. ማፈኛ ተዘጋጀ፡፡ የዚህም ገፈት የዴሞክራሲ እንቅስቃሴዎችን ገድቦ የነበረውን ተስፋ መቀመቅ ውስጥ ከተተው፡፡ ከዚህ በኋላ በየካቲት 2003 ዓ.ም. በቱኒዚያ መሐመድ ቡዓዚዝ የተጀመረው የአረቡ ፀደይ አብዮት በሰሜን አፍሪካን እና መካከለኛ ምስራቅ አረብ ሀገሮች መቀጣጠሉን የተመለከቱት አቶ መለስና ተከታዮቻቸውና አጋሮቻቸው በኢትዮጵያም ይከሰታል በሚል የአስር አደኑንን አጣደፉት፡፡

የአረቡን አብዮት ተከትሎ በኢትዮጵያ የእስር ሰንሰለቱን የጀመሩት እንደ ታሰበው ጋዜጠኞች እና የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ናቸው፡፡ በቀዳሚነትም በወርሃ ሰኔ 12 ቀን 2004 ዓ.ም. ከፖለቲከኛ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሔር፣ ሰኔ 14 ቀን 2003 ዓ.ም. ደግሞ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት አለሙ፤ ከዚያም በክረምት 2003 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባና አቶ ኦልባና ሌሊሳ የእስር ሰለባ ሆኑ፡፡

andሌላው ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ሁለት ሲውድናውያን ጋዜጠኞች ማርቲን ሸብይ እና ጆሃን ፐርሰን ሽብርተኝነትን ደግፈዋል በሚል በዚሁ የፀረ-ሽብርተኝነት ሰለባ በመሆን ከ14 ወራት የሰቆቃ እስር በኋላ በዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ጫና መስከረም 1 ቀን 2004 ዓ.ም.ተለቀዋል፡፡ በመቀጠል መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ደግሞ ታዋቂው የፖለቲካ ተንታኝ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣በብዙ ወጣቶች ዘንድ በቅንነቱና ፍቅርን በመስጠት እንዲሁም ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልን አጥብቆ በመደገፍ የሚከራከረው የአንድነት/መድረክ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ሌሎች የአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ናትናኤል መኮንን፣አቶ ዮሐንስ ተረፈና ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለምንና አቶ አንዱዓለም አያሌውን ጨምሮ አቶ ክንፈ ሚካኤል ደበበና ሌሎች ሰዎችም በሽብርተኝነት ስም ወደ ወህኒ ወረዱ፡፡ በዚህም አፍቃሬ መንበር አቶ መለስ የፈሩትን የአረቡን አብዮት በዚህ ያለፉ ይመስል ጀብደኝነት ተሰምቷቸው፤ ተጠርጣሪዎቹ ገና በፍርድ ቤት ብይን ሳይሰጥባቸው አሸባሪዎች ናቸው ሲሉ ለተወካዮቻቸው አረጋገጡ፡፡
ያሰሯቸው ላይ ቀድመው ወንጀለኛ በማለት ፍርድ በመስጠት መከራን የደገሱት አቶ መለስ ባልጠበቁት ሁኔታ በጠና ታመው በአውሮፓ ቤልጄየም ብራሰልስ አንድ የዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል ተኙ፡፡ በመጨረሻም እንደ ሆስፒታሉ ምንጮች ከሆነ ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደወጡ ላይለመሱ ብዙ ለመኖር ያሰቡበትን በ21 ዓመታት የስልጣን ዘመናቸው እንደ ግል ርስታቸው ያስቡት የነበረውን ቤተመንግስት ጥለው እስከወዲያኛው ተሰናበቱ፡፡

bekይሁን እንጂ አጋሮቻቸውና የቅርብ የኢህአዴግ አመራሮች መታመማቸውን እንኳ ለህዝብ ሳይገልፁ በድንገት የሞቱትን ሰውዬ ከጋዜጠኞች ጥያቄ ቢበረታባቸው በቅርቡ ተመልሰው ስራ ይጀምራሉ የሚል መልስ ሰጡ፡፡ በኋላም የተባለው ሳይሆን ፈጣሪ የወሰነው ሞት እርግጥ መሆኑ እና ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ሌሊት እንዳረፉ ተደርጎ ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም. ማለዳ አንድ ለእናቱ በሆነው ሀገሪቱ ቴሌቪዥን ኢቴቭ ይፋ ተደረገ፡፡ ከዚያም ነሐሴ 27 ቀን 2004 ዓ.ም. ግብዓተ መሬታቸው እንደ ተከናወነ በግብረ-አበሮቻቸውና በመንግስት ሹማምንት ከተገለፀ በኋላ “…የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን!” የሚል መፈክር መሰማት ጀመረ፤የተባለው ራዕይ ኑዛዜ አሁንም ባያበቃም፡፡

በርግጥ አቶ መለስ ራዕይ ነበራቸው ከተባለ፤ እስከ ህልፈታቸው ድረስ የትኛውንም መንገድ ተጠቅመው ከቤተመንግስት ሳይወጡ ተቀናቃኞቻቸውን በማሰርና በማጥፋት በስልጣን መቆየት ነው፡፡ ነበራቸው የተባለው ራዕይ አሳቸው ሲሞቱ አብሮ ሞቷል፡፡ ይህ ደግሞ ራዕይ ሳይሆን የስልጣን ጥም እንጂ ህዝባዊና ሀገራዊ አይደለም፡፡ ተከታዮቻቸውም እናስቀጥላለን ያሉት ይህንኑ በመሆኑ ልክ እንደሳቸው ተመሳሳይ ድርጊት መፈፀሙትን እንደ ትክክለኛ እና ቅዱስ ተግባር ማከናወን ጀመሩ፡፡ ለአብነትም መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ተከትሎ ለኢህአዴግና አመራሮቹ ስልጣን ማክተሚያ ምክንያት ይሆናሉ ብለው ያሰቧቸውን ማጥመድ፣ ማሰርና መፈረጁን ተያያዙት፡፡ የዚህ ሰለባ ከሆኑት መካከል በሚያዝያ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬና ጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድ፤ እንዲሁም የኢትዮጵያው ዞን 9 ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ዘለዓለም ክብረት፣ አቤል ዋበላ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣አጥናፍ ብርሃኔ እና ናትናኤል ፈለቀ ቀዳሚዎቹ ናቸው፡፡

mesበ2004ዓ.ም. ዛሬም ድረስ ምላሽ እንዳላገኘ የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጥያቄ ጋር በተያያዘ የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት፣ጋዜጠኛ ዩሱፍ ጌታቸውና ጋዜጠኛ ሰለሞን ከበደ ታስረው እስካሁን በወህኒ ቤት ይገኛሉ፡፡ ምንም እንኳ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት የተያዘ ቢሆንም እስካሁን ብይንም ሆነ እልባት አላገኘም፡፡ ይሄ ሁሉ በአቶ መለስ አገዛዝ ዘመን የተጀመረ እስር ነው፡፡
በመቀጠልም በሀገር ውስጥ የኢህአዴግ መንግስት እውቅና ያልተቸረውና በሽብርተኝነት የተፈረጀው የግንቦት 7 የፖለቲካ ማኀበር ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን ፀጥታ ኃይሎች ታግተው ለኢትዮጵያው ገዥ ተላልፈው ተሰጥተዋል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ቀደም ሲል የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርጋችኋል በሚል በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ ክስ መዝገብ ከነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር በሌሉበት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸውል፡፡ የሞት ፍርድ ተፍርዶባቸው የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው እንደገና በ2005 ዓ.ም. ደግሞ በነ አንዱኣለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ክስ በሌሉበት የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡ ይሁን አንጂ ወደፊት ትናው ክስ ተፈፃሚ እንደሚሆንና በቀጣይ ስለሚኖረው የፍርድ ሂደት ዕድሜ ከሰጠን አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው እንዳለ እስሩ ተጠናክሮ በመቀጠል በሀገር ውስጥ በገዥው ስርዓት ህጋዊ እውቅና ተችሯቸው የሚንቀሳቀሱየፖለቲካ ፓርቲ ወጣት አመራሮች ተለቅመው ታሰሩ፡፡ እነኚህም መካከል በማኀበራዊ ሚዲያ የተለያዩ በሳል ፅሑፎችን በመፃፍ የሚታወቀው፣ የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህርና የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፤ ከአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም ከሰማያዊ ፓርቲ አቶ የሺዋስ አሰፋ ይገኙበታል፡፡አራቱም ወጣት ፖለቲከኞች በፓርቲያቸውም ይሁን በሀገሪቱ ሰለማዊ የፖለቲካ ትግል በጎ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች መሆናቸው ይነገርላቸዋል፡፡
ሌላው እየተወሰደ ያለውን እስር በመሸሽ ከምርጫ 1997 ዓ.ም. ወዲህ ከ2005 ዓ.ም.ጀምሮ እስከ ያዝነው 2006 ዓ.ም. ድረስ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ተሰደዋል፡፡ ለዚህም በዋነኝነት እንደ አስረጂ ሊጠቀስ የሚችለው በአሁን ሰዓት በጅምላ እየተፈፀመ ያለው እስር ነው፡፡ በአቶ መለስ ዜናዊ የስልጣን ዘመን የተጀመረው የጋዜጠኞችና ብሎገሮች እስር በአሁን ወቅት ሶስት የውጭ ዜጎችን ጨምሮ 20 የደረሰ ሲሆን፤ ከላይ በስም ከተጠቀሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በተጨማሪ በርካታ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ማኀበር አባላትም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ዴሞክራሲያዊ መብቶች ዝግ ከነበሩበት የደርግ ጊዜ ጋር ሲነፃፀር፤ በኢህአዴግ ጊዜ 20 ጋዜጠኞችና ብሎገሮችን በማሰር በሀገሪቱ ታሪክ ቀዳሚውን አሉታዊ ስፍራ እንድይዝ ያደርገዋል፡፡ በዚህም በፀታ ኃይሉና በፍትህ ተቋማቱ ላይ ተጨማሪ የስራ ጫና ከመፍጠር በዘለለ የታሰበውን የፖለቲካ ትርፍ ያስገኛል ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እንደ ገዥው ስርዓት አመራሮች፣ ደጋፊዎችና የፀጥታ ኃይሎች ገለፃ ከሆነ እስሩ የሚቆም አይደለም፡፡ በቀጣይ የዚህ ሰለባ ማን እንደሚሆን ባይታወቅም፤ እንደተባለው የሚተገበር ከሆነ በድጋሚ ቀሪ ጋዜጠኞች እና ፖለቲካኖች የእስር ስለባው ሊሆኑ እንደሚችሉ አያጠያይቅም፡፡ ምክንያቱም ከሌላው በተሻለ መብቶቻቸውን እየተገበሩና እየተጠቀሙ ማኀበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ በመፍጠር የስርዓቱ ስልጣን ፈተና ይተረጎማሉና፡፡ አቶ መለስ ከመሞታቸው በፊት ምርጫ ሲደርስና ለስልጣናቸው የሚያሰጋቸው ነገር ብልጭ ሲልባቸው የሚወስዷቸው ርምጃዎች አሁን በስልጣን ላይ ባሉ ተከታዮቻቸው ተጠናክረው መቀጠላቸው አንዱ የመለስ ራዕይ ነው ሊያስብል ይችላል፡፡ ይህም አመራሮቹ እናስቀጥለዋለን ያሉት የአቶ መለስ ራዕይ አንዱ አካል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ያኔ በሳቸው ዘመን የተጀመረው ዛሬም በቃ ሊባልና መቋጫ ሊበጅለት አልቻለምና፡፡

አሁን በመንግስት አመራሮች ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና ፖለቲካኞች ላይ ትኩረት ያደረገ የእስር ዘመቻ ከዚህ በፊት እንደ ተወዳጅ ነጠላ ዜማ ሲዜም የነበረውን “የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን” አባባል የሚታየው የእስር ዘመቻ መሆኑን በማሳበቅ በደጋፊዎቻቸው እንደ ሊቀ ሊቃውንትና ባለራዕይ የተወሰዱት ሟቹ ሰውዬ እንዲኮነኑ ማድረጉ አይቀርም፡፡ በየትኛውም ዓለም እንደሚታየው የፖለቲካ ርምጃና ተሞክሮ ሰዎችን ያውም ዜጎችን አሸባሪ ብሎ ማሰር በስልጣን ለመቆየትም ሆነ ለመረጋጋት መፍትሄ ሊሆን አይችልም፡፡ እንዲህ ዓይነት ርምጅ መፍትሔ ቢሆን ኖሮ የሊቢያው መሪ ኮሎኔል ሙዓመር ጋዳፊ፣ የግብፁ ሆስኒ ሙባረክ፣የየመኑ ዓሊ አብደላ ሳላህ በስልጣን ላይ መቆየት በቻሉ ነበር፤ግን አልሆነም፡፡

ነገርን ግን የህዝቡን ቁጣ በመቀስቀስ በውርደት ከስልጣን እንዲወርዱ አስገደዳቸው እንጂ መፍትሄ አልሆናቸውም፡፡ ስለዚህ በስልጣን ለመቆየት ጉጉቱ ካለ እንኳ የዜጎችን መብት፣ፍላጎትና ጥቅም ማክበርና ማስጠበቅ የተሻለ አማራጭ ነው፡፡ መፍትሔውን ልክ እንደ ጥሎ ማለፍና ፍፃሜ የአትሌቲክስ ውድድር ዜጎችን በማሰርና እንዲሰደዱ በማድረግ ዙሩን ማክረር ታምቆ የቆየውን የህዝብን ስሜት ባልተጠበቀ ሰዓት እንዲፈነዳ በማድረግ ሌላ ችግር ሊወልድ ይችላል፡፡የሚፈራው ችግር የሚከሰት ከሆነ ደግሞ የበለጠ ለገዥዎችም፣ ለህቡም ሆነ ለሀገሪቱ አሉታዊ ተፅዕኖ ማስከተሉ እሙን ነው፡፡

%d bloggers like this: