Tag Archives: African Democracy

ከምርጫው ውጭ እንዲሆን የተደረገው አንድነት ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ላይ ያቀረበው ክስ ለየካቲት 27 ተቀጠረ!

 udj

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በብሔራዊ ምርቻ ቦርድ አማካንነት ከግንቦቱ 2007 ዓ.ም.  ሀገር አቀፍ ምርጫ ውጭ እንዲሆን መደረጉን በመቃወም  በፌደራሉ ከፍኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ  በፍትሐ ብሔር 11ኛ ችሎት የመሰረተው ክስ ለየካቲት 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠዋት ተቀጠረ፡፡

ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው በማኀበራዊ ሚዲያ ገፁ ላይ “ህገ ወጥ በሆነ መንገድ በምርጫ ቦርድ እና በኢህአዴግ ሴራ ለእነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ በኃይል ተላልፎ መሰጠቱ የሚታወቅ ነው። በዚህም ምክንያት ህጋዊው የአንድነት አመራር በምርጫ ቦርድ ላይ ክስ መስርተዋል፤ ፍርድ ቤቱ ልደታ በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት 11ኛ ፍትሀ ብሔር ችሎት ለየካቲት 27 ከጠዋቱ 3:30 ጉዳዩን ለማየት ቀጠሮ ሰጥተዋል፤ በመሆኑም በቅርብ የምንገኝ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች በችሎቱ ላይ በአካል በመገኘት ለህጋዊው አንድነት ያለንን አጋርነት እንድናሳይ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።” ብሏል፡፡

ብሔራዊ ምርጫ ቦር ከተመሰረተ ጀምሮ ከገዠው ህወሓት/ኢህአዴግ ጋር ጠንካራ ተፎካካሪ ናቸው ተብለው የሚገመቱትንና በከደፍተኛ ደረጃ የህዝብ ተቀባይነት ያላቸውን  የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለይም ከዚህ በፊት የኦሮሞ ብሔራዊ ኮንግረንስ(ኦብኮ)ን ያፈረሰ ሲሆን፤ በቅርቡ ደግሞ የግንቦቱ ምርጫ 2007 ዓ.ም. ዋዜማ ላይ  አንድነት ፓርቲን እና መኢአድን በማፍረስ ምርጫ ቦርድ ያፈረሳቸውን ፓርቲዎች ስም ለፈለጋቸው ሰዎች መስጠቱን ማሳወቁ ይታወሳል፡፡

ምርጫ ቦርድ ከ200 በላይ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ሰረዘ

  • “ምርጫ ቦርድ ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ እንዲቆይ አይፈልግም” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት

ELEC

ሰማያዊ ፓርቲ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ በምርጫ ቦርድ ትዕዛዝ እንደተሰረዙበት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በመላ አገሪቱ በተለይም በደቡብ ወሎ፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወላይታ፣ በቤንች ማጅ፣ በምዕራብ ጎጃም፣ በሲዳማ፣ በከምባታ፣ በጋሞጎፋ፣ አዲስ አበባ፣ በደቡብ ጎንደርና ጉጅን ጨምሮ በሌሎችም የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ አንድን ዕጩ ለመሰረዝ የሚያበቃ ምንም አይነት ህጋዊ ምክንያት ሳይኖር “ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደብዳቤ ታዘናል” በማለት ለህዝብ ተወካዮች ምክርቤትና ለክልል ምክር ቤቶች ያስመዘገብናቸው ዕጩ ተወዳዳሪዎቹን በመሰረዝ ከምርጫው ውድድር ውጪ እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሆነ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት አስረድተዋል፡፡

በየክፍለ ሀገሩ የተሰረዙት ዕጩዎች “ፓርቲው ትብብር የሚባል ህገ ወጥ አደረጃጀት መስርቷል፣ የሌሎች ፓርቲዎች አባላት ናችሁ” የመሳሰሉ ምክንያቶችና ደብዳቤ የተሰጣቸው ሲሆን በአንጻሩ በአዲስ አበባ የተሰረዙት ዕጩዎች ከምርጫ አስፈጻሚዎች ምንም አይነት ምክንያትና ደብዳቤ እንዳልተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዕጩዎቹ “የተሰረዝንበትን ምክንያት ንገሩን፣ ደብዳቤ ልትሰጡን ይገባል” ቢሉም የምርጫ አስፈጻሚዎቹ “እኛ እናንተን ለመመዝገብ ችግር የለብንም፡፡ ግን ከበላይ አካል እንዳንመዘግብ ተነግሮናል፡፡ ደብዳቤም ልንሰጣችሁ አንችልም፡፡” የሚል መልስ እንደሰጧቸው ገልፀዋል፡፡

Semayawi-Party

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች መሰረዛቸውን ተከትሎ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የቦርዱን ሰብሳቢ ፕ/ር መርጋ በቃናን ለማግኘት ቢጥሩም “ከከተማ ውጭ ናቸው፡፡ አሁን አታገኟቸውም” የተባሉ ሲሆን ፕ/ር መርጋ የህወሓትን 40ኛ አመት ለማክበር መቀሌ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በትናንትናው ዕለት በጉዳዩ ላይ ከቦርዱ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ነጋ ዱፌሳ ጋር የተነጋገሩ ሲሆን አቶ ነጋ “ማመልከቻ አስገቡ” ከማለት ውጭ ዕጩዎቹ ለመሰረዛቸው ተጨባጭ ምክንያት መስጠት እንዳልቻሉ  ኢ/ር ይልቃል ገልጸውልናል፡፡

“የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ያለ አግባብ የሚሰርዙት ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ ጫና መፍጠር ስለሚችል በሂደቱ እንዲቆ ስለማይፈልጉ ነው” ያሉት ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፤ ሆኖም ይህ የምርጫ ቦርድ ውሳኔ ለነጻነት የሚያደርጉትን ትግል ትክክለኛ እንደሆነ እንዳስረገጠላቸው፣ ይህን የነፃነት ትግልም አጠናክረው እንደሚቀጥሉና የካቲት 22 ፓርቲያቸው ከትብብሩ ፓርቲዎች ጋር በ15 ከተሞች በተመሳሳይ ጊዜ በ15 ከተሞች የሚያደርገው ሰልፍ የዚሁ የነጻነት ትግል አካል እንደሆነ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በ15 ከተሞች የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጠራ

“ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚልመርህ የሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ የካቲት 22 ቀን 2007 ዓም በ15 ከተሞች እንደሚካሄድ ትብብሩ አስታውቋል።

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

“የሙስሊም ማህበረሰቡ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም በኑር መስጂድ ፣ የካቲት 6 ቀን 2007 ዓም ደግሞ በአንዋር መስኪድ ያደረገው ተቃውሞ እንዲሁም የባህርዳር ከተማ ህዝብ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም ያሳየው ህዝባዊ እምቢተኝነት ትግል በሃይል ሊዳፈን ቢችልም እንደማይጠፋ ትምህርት ሰጥቷል” ሲል በመግለጫው አስታውቋል፡፡ ትብብሩ፣ ገዢው ፓርቲ እያደረሰ ያለው የመብት ረገጣ፣ የሙስና መስፋፋትና የመልካም አስተዳደር እጦት የህዝቡን የለውጥ ፍላጎትና የትግል ተነሳሽነት እንዳሳደገው ገልጿል።

ትብብሩ ገዢው ፓርቲ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ከቃላት ያለፈ እምነትም ሆነ ቁርጠኝነት እንደሌለው በመግለጽ፣ ምርጫ ቦርድን በቁጥጥር ስር በማዋል ጠንካራ ፓርቲዎችን ከመጪው ምርጫ ለማግለል እየሰራ መሆኑን የአንድነትና መኢአድን ጉዳይ በመግለፅ አብራርተዋል።

ከሰሞኑ ኢቢሲ ያቀረበው የተቃዋሚ ፓርቲዎችን የመኖር ትርጉም ዋጋ የሚያሳጣው ‹‹መንግስትንና የመንግስት አስፈጻሚዎችን ከተቻችሁ፣ ካላከበራችሁ ወይም ጸጥ ለጥ ብላችሁ የምርጫ አጃቢ ካልሆናችሁ እስከ 15 ዓመት ትታሰራላችሁ›› የሚል አንድምታ ያለው በ ‹‹ባለሙያዎች ትንታኔ ›› ሥም የተላከው የማስፈራሪያ መልዕክትና የሌሉ የፈጠራ ክሶችን ለመፈብረክ በአባል ፓርቲዎቻችን ላይ ‹‹የሞተ ጉዳይን ከመቃብር በመቀስቀስ›› እና በአዲስ መልክ የተጀመረው የሚዲያ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ በግልጽ ያስተላለፈው ገዢው ፓርቲ የመድብለ ፓርቲ ስርአት እንዳይኖር መፈለጉን ነው ሲል አክሏል።

የእኛ፣ የአገራችንና ዜጓቿ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ በሁለት አማራጮች ላይ የተንጠለጠለ ነው የሚለው ትብብሩ አንድም ያለውን አምባገነናዊ ሥርዓት ተቀብለን፣የአገራችን ሉዓላዊነት በጥያቄ ውስጥ ባለበት፣ የጭቆና ቀንበር ተሸክመን በከፋ ውርደት ሥር ሰጥ ለጥ ብሎ መገዛት፤ አሊያም አምባገነንነትና ጭቆናን “በቃ” በማለት በሕዝባዊ የተቀናጀ ሰላማዊ ትግል ለአገራችን ሉዓላዊነትና የዜግነት ክብራችንን ለማስመለስ በህገ መንግስታዊ መብታችን ተጠቅመን ትግላችንን እስከማይቀረው ለውጥ/ ድል ደጃፍ ድረስ በቆራጥነት መቀጠል፣ ናቸው ብሏል፡፡

ሁሉን አቀፍ የነፃነትና ክብርን የማስመለስ ሰላማዊ ትግል ለ9ኙ ፓርቲዎች ብቸኛ አማራጭ መሆኑም ትብብሩ አስምሮበታል፡፡

ፓርቲዎቹ በመጨረሻም በሚደረገው አገራዊ፣ ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል በማይቀረው የሥርዓት ለውጥ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር በአንድነትና በቆራጥነት ህዝቡ እንዲነሳና በየካቲት 22 የተቃውሞ ሰልፍ ላይ እንዲገኝ በመግለጫቸው ጥሪ አቅርበዋል።

የዞን 9 ብሎገሮችና 3ቱ ጋዜጠኞች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ

∙ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ እንዳልፈጸሙ ተናግረዋል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው 6ቱ የዞን 9 ብሎገሮችና 3ቱ ጋዜጠኞች ዛሬ የካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ለ20ኛ ጊዜ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ሲሆን፣ በዚህ መሰረትም ተከሳሾች ከችሎት እንዲነሱ አቤቱታ ያቀረቡባቸው ሰብሳቢ ዳኛ ሳይቀየሩ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ተደርገዋል፡፡ በመሆኑም ከሁለተኛ ተከሳሽ በፍቃዱ ኃይሉ ጀምሮ እያንዳንዳቸው ‹‹በክሱ ላይ የተጠቀሰውን ወንጀል ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም?›› የሚል ጥያቄ እየቀረበላቸው ቃላቸውን እንዲሰጡ ተደርጓል፡፡

በዚህ መሰረት ሁሉም ተከሳሾች የቀረበባቸውን የሽብር ክስ እንዳልፈጸሙ ለችሎቱ ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ 2ኛ ተከሳሽ በፍቃዱ ኃይሉን ጨምሮ ተከሳሾቹ ክሱን በተደጋጋሚ ቢያነቡትም ግልጽ ሊሆንላቸው እንዳልቻለ ቢገልጹም የእምነት ክህደት ቃላቸውን መስጠት እንዳለባቸው ተገልጾ ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
3ኛ ተከሳሽ ናትናኤል ፈለቀ የተጠቀሰውን ክስ እንዳልፈጸመ በመግለጽ “ህግ የተከበረበት ሀገር ቢሆን ኖሮ በእኔ ቦታ ከሳሾቼ ነበሩ መቆም ያለባቸው” ብሏል፡፡ ሌሎችም እንዲሁ ድርጊቱን አለመፈጸማቸውን አስረድተዋል፡፡ 10ኛ ተከሳሽ ተስፋለም ወልደየስ በበኩሉ፣ “እኔ ጋዜጠኛ ነኝ፤ ጋዜጠኝነት ወንጀልም ሽብርም አይደለም፡፡ ጥፋተኛ አይደለሁም” ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾቹ የእምነት ክህደት ቃላቸውን መስጠታቸውን ተከትሎ አቃቤ ህግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ከመጋቢት 21-23  ቀን 2007 ዓ.ም ለሶስት ተከታታይ ቀናት ቀጠሮ መስጠቱን የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አቤቱታ ላይ ቀጠሮ ሰጠ

prisoners

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘላለም ወርቃገኘው ክስ መዝገብ የተከሰሱት የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በማረሚያ ቤት አስተዳደር ላይ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጠ፡፡ በዛሬው ችሎት የተከሳሾቹ ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ‹‹ህዳር 12 ለ 13 ቀን 2007 ዓ.ም አጥቢያ ድንገተኛ ፍተሻ ተደርጎ የተጠርጣሪዎቹ ንብረት ተወስዶባቸዋል፣ የሰብአዊ ጥሰት ተፈጽሞባቸዋል፣ ድንገተኛ ፍተሻው ህገ ወጥ ነው›› በሚል በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ላይ ላቀረቡት አቤቱታዎች ማረሚያ ቤቱ የሰጠውን መልስ ሰምቷል፡፡

የማረሚያ ቤቱ መልስ በጽሁፍ ከቀረበ በኋላ በቃልም እንዲቀርብ በታዘዘው መሰረት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የቀጠሮ ማረፊያ አስተዳደር አስተዳዳሪ ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አምባዬ ክቡር ፍተሻው መካሄዱን አምነው ነገር ግን፤ ‹‹ፍተሻው የተከናወነው በፍርድ ቤት ትዕዛዝ ከጠዋቱ 12 ሰዓት በኋላ ነው፡፡ ፍተሸውም በአቤቱታው ላይ እንደቀረበው ባልታወቁ ሰዎች ሳይሆን በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ጥበቃዎች ነው የተከናወነው›› ሲሉ መልስ ሰጥተዋል፡፡ የፍተሻውን አላማም ‹‹የታራሚዎችን ደህንነት ለመጠበቅ ሲባል የተከለከሉ ነገሮችን ፈትሾ ለማስወገድ ነው፡፡ በፍተሸውም ሚስማር፣ ስለት ነገሮች፣ እንዲሁም ብጥብጥ የሚቀሰቅሱ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡›› ብለዋል፡፡

ባለፈው የአብዛኛዎቹ ተከሳሾች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ሲደረግ የ7ኛ ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞን፣ እንዲሁም 8ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማ የተወሰኑ የክስ ማሻሻያዎች እንዲያደርግ ትዕዛዝ ሰጥቶ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በዚህ መሰረት በዛሬው ዕለት በሁለቱ ተከሳሾች ላይ አሻሽየዋለሁ ያለውን ክስ አቃቤ ህግ ይዞ ቀርቦ በንባብ አሰምቷል፡፡

በመጨረሻም በፍተሻው ወቅት ተፈጽሟል በሚል በተከሳሾቹ ጠበቃ የቀረበውን አቤቱታና ማረሚያ ቤቱ የሰጠውን መልስ አገናዝቦ ውሳኔ ለመስጠት እንዲሁም፤ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የቀረበው ማሻሻያ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ‹‹ተሸሽለዋል ወይንም አልተሸሻሉም›› የሚለውን ለመወሰን ለየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ጠዋት 3 ሰዓት ላይ ቀጠሮ መሰጠቱን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

%d bloggers like this: