Tag Archives: Semayawi party Ethiopia

ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሚ የሰማያዊ ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ

አንደኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ለሁለት ቀናት በአዲስ አበባ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲ ኢ/ር ይልቃል ጌትነትን በድጋሜ የፓርቲው ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል፡፡
ትናንት ነሀሴ 16/2007 ዓ.ም ጉባኤውን የጀመረው ፓርቲው በዛሬው ሁለተኛና የማጠቃለያ ውሎው የፓርቲውን ሊቀመንበር፣ የብሄራዊ ምክር ቤት አባላት እንዲሁም የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላት ምርጫን አድርጓል፡፡
ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሜ ለቀጣዩ ሦስት አመታት ፓርቲውን እንዲመሩ የተመረጡ ሲሆን፣ አምስት የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላትም በጉባኤው ተመርጠዋል፡፡ ጉባኤው የፓርቲውን የብሄራዊ ምክር ቤት አባላትንም መርጧል፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ የ2007 ዓ.ም. 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ

የሰማያዊ ፓርቲ የ2007 ዓ.ም. 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ

ለፓርቲው ሊቀመንበርነት ቀደም ብለው ፓርቲውን ለሁለተኛ ዙር ለመምራት ራሳቸውን በእጩነት ያቀረቡት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ብቻ ሲሆኑ፣ ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን ለመቀበል ባቀረበው ሀሳብ መሰረት ራሱን በእጩነት የሚያቀርብ ይኖራል ተብሎ ቢጠበቅም በእጩነት ራሱን ያቀረበ አልነበረም፡፡
በመሆኑም በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን በጥቆማ ለማወዳደር ተገድዷል፡፡ በዚህም ጉባኤው ስድስት እጩዎችን የጠቆመ ቢሆንም አምስቱ ‹‹አንወዳደርም›› በማለታቸው ከተጠቆሙት መካከል አቶ ዮናታን ተስፋዬ ብቻ ለመወዳደር ፍላጎታቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ፓርቲውን በህዝብ ግንኙነት ማገልገላቸው የሚታወስ ሲሆን ዛሬ ደግሞ ለሊቀመንበርነት መወዳደር ችለዋል፡፡
ለሊቀመንበርነት እጩ ሆነው የቀረቡት ሁለቱ እጩዎች በጉባኤው ፊት በተመደበላቸው ጊዜ ገደብ ውስጥ ራሳቸውን ካስተዋወቁና የምረጡኝ ቅስቀሳ ካደረጉ በኋላ ወደ ድምጽ መስጠት መግባት ተችሏል፡፡ በተሰጠው ድምጽ መሰረትም ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲን ለቀጣይ ሦስት አመታት እንዲመሩ በአብላጫ ድምጽ ተመርጠዋል፤ በዚህም ኢ/ር ይልቃል ከተሰጠው ድምጽ 136 ድምጽ አግኝተው ሲያሸንፉ፣ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በበኩላቸው 60 ድምጽ በማግኘት ፉክክር አድርገዋል፡፡

ይልቃል ጌትነት ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

ይልቃል ጌትነት ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

የምርጫ ውጤቱ ይፋ መሆኑን ተከትሎ ንግግር ያደረጉት ተመራጩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲ በሁለቱ ቀናት ጉባኤው ያነሳቸውን ችግሮች ለመፍታት እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ጠቅላላ ጉባኤ በዛሬው ውሎው ቀጣይ የፓርቲውን እንቅስቃሴ አስመልክቶም በጉባኤው አባላት አጠቃላይ ውይይት አድርጓል፡፡ በዚህም ፓርቲው ወደፊት ማደራጀት ላይ አተኩሮ መስራት እንደሚገባው ጉባኤው አጽንኦት ሰጥቶበታል፡፡
ጠቅላላ ጉባኤው የብሄራዊ ምክር ቤትና የፓርቲው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ያቀረቡት ሪፖርት ላይ ተወያይቶ ሪፖርቶቹ የፓርቲው ሰነድ ሆነው እንዲፀድቁ በአብላጫ ድምፅ ወስኗል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ያካሄደውን ጉባኤ ዛሬ ነሐሴ 17 ቀን 2007 ዓ.ም ማጠናቀቁን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች አባላቱ እየታሰሩና እየተደበደቡ መሆናቸው ገለፀ

በጋሞጎፋ ዞን በርካታ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች እየታደኑ እየታሰሩ መሆኑን የዞኑ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች ገልጸዋል፡፡ ከትናንት ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ጋሞ ጎፋ ዞን ጎፋ ወረዳ ሳውላ ከተማው ውስጥ በርካታ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች መታሰራቸውን የጋሞ ጎፋ ዞን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

Election

በተመሳሳይ በትናንትናው ዕለት በጋሞጎፋ ዞን ዳራማሎ ወረዳ ቅስቀሳ ላይ የነበሩ 17 የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ታስረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በጋሞጎፋ ዞን ቦንኬ ወረዳ ለፖሊስ “ለሰማያዊ ፓርቲ የሚቀሰቅስ ማንኛውም አካል ላይ እርምጃ ውሰዱ” የሚል ትዕዛዝ መተላለፉን የዞኑ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች ገልፀዋል፡፡

በሰሜን ወሎ ዞን ሀብሮ ወረዳ ጎራና ቀበሌ የሰማያዊ ፓርቲ የተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ የሆነው አቶ ዮናታን ሰይድ በካድሬዎች ድብደባ እንደተፈፀመበት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ አቶ ዮናታን ዛሬ ከዋቱ 3፡20 አካባቢ ጊራና ከተማ ላይ የምርጫ ቅስቀሳ እያደረገ በነበረበት ወቅት የብአዴን/ኢህአዴግ ካድሬዎች ‹‹ለምን ትቀሰቅሷላችሁ? ደፍራችሁናል!›› በማለት ድብደባ እንደፈፀሙበት ገልጾአል፡፡ ሆስፒታል ሆኖ በስልክ ያነጋገረን አቶ ዮናታን በተለይ እግሩ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ገልጾአል፡፡

መንግስት ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም አይ ኤስ አይ ኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ሰበብ እየታደኑ እየታሰሩ መሆኑን የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ ሀሙስ ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም ብሌን መስፍንና ተዋቸው ዳምጤ ከመስሪያ ቤት ተይዘው የታሰሩ ሲሆን ሚያዝያ 24 ቀን 2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርበው ‹‹ሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተደረገውን አመጽ መርታችኋል፡፡›› በሚል ፖሊስ ክስ እንዳቀረበባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተመሳሳይ ዛሬ ሚያዝያ 26 ቀን 2007 ዓ.ም ማቲያስ መኩሪያ ቤቱ ውስጥ እያለ በፖሊስ ተይዞ ታስሯል፡፡ ማቲያስ፣ ብሌንና ተዋቸው ወረዳ 10 (ላዛሪስት ፖሊስ ጣቢያ) ታስረው ይገኛሉ፡፡ ይህንን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ የሚደረገው እስርም “መንግስት በሰማያዊ ፓርቲ ላይ የጀመረውን የሀሰት ክስ እውነት ለማስመሰል የታቀደ ነው፡፡ ፖሊስ ምርመራ ሳይጨርስ በሀሰት 20 አባላትንና 6 አመራሮችን አስረናል ብለው ነበር፡፡ እነሱ የፈለጉት ይህን ሚዲያ ላይ ወጥተው በሀሰት የፈፀሙትን ውንጀላ ማሰመሰል ነው፡፡” ሲል አቶ ዮናታን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡

በሌላ ዜና በየ ክፍለ ሀገሩ የሚገኙ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ ደህንነትና ፖሊስ የሚፈፅመው ድብደባ አሁንም መቀጠሉ ተገልጾአል፡፡ የደብረማርቆስ ከተማ ነዋሪና የሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆነችው የሀሳብ ጌታቸው “ለሰማያዊ ፓርቲ ወረቀት በትነሻል” በሚል ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀሙባት ተገልጾአል፡፡

ፖሊስ በ”በሁከትና ብጥብጥ” ተጠርጣሪዎች ላይ ሦስት መዝገብ አደራጅቻለሁ አለ

•እነ ወይንሸት ለሁለተኛ ጊዜ 6 ቀን ተቀጥሮባቸዋል
•”ወይንሸት ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ስታሸብር ነበር” ፖሊስ

ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ላይ “ሁከትና ብጥብጥ አስነስታችኋል፤ ተካፍላችኋልም” በሚል ፖሊስ ባሰራቸው ሰዎች ላይ ሦስት የተለያዩ መዝገቦች ማደራጀቱን አስታውቋል፡፡

protest 2

ሚያዝያ 22 ቀን 2007ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የቀረቡ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ሌሎች በዕለቱ የተያዙ ሰዎችን በተመለከተ ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ እንደገለጸው፣ ፖሊስ የራሱን ቡድን በማዋቀር ተጠርጣሪዎችን በሦስት መዝገቦች ስር እንደየተሳትፏቸው አደራጅቻለሁ ብሏል፡፡ በዚህ መሰረት በሶስተኛው መዝገብ ላይ ያካተታቸውን በርካታ ታሳሪዎች አጣርቶ መልቀቁን የገለጸው ፖሊስ፣ በሁለተኛውና በአንደኛው መዝገብ ላይ ባሉት ተጠርጣሪዎች ግን ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጹዋል፡፡
አንደኛው መዝገብ ላይ በእነ ወይንሸት ሞላ መዝገብ 5 ሰዎች የተካተቱ ሲሆን አራቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፤ አንደኛዋ ተጠርጣሪ ደግሞ ፖሊስ የፓርቲው አባል እንደሆነች የሚገልጸው፣ እሷ ግን አባል አለመሆኗን የገለጸች መሆኗን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ስለሆነም በዚህ መዝገብ የተካተቱት ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ማስተዋል እና የፓርቲው አባል ያልሆነችው ቤተልሄም ይገኙበታል፡፡ ማስተዋል በዛሬው ዕለት ቀደም ብሎ የተሰጠው የቀጠሮ ቀን ስላልደረሰ ፍርድ ቤት አልቀረበም፡፡ ቤተልሄም ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባል ሳልሆን አባል ነሽ እየተባልኩ ምርመራ ይደረግብኛል፤ ሌሊት እየተጠራሁ እመኝ እየተባልኩ ነው›› ስትል ለፍርድ ቤቱ ገልጻለች፡፡

Semayawi-Weyeneshet

በሁለተኛው መዝገብ ላይ ደግሞ 15 ተጠርጣሪዎች ተካትተዋል፡፡ ፖሊስ በዚህ መዝገብ በተካተቱ ተጠርጣሪዎች ላይ ክሱን ሲያሰማ እንዲህ ብሏል፤ “ተጠርጣሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ሲያደርጉ ‹ጠንካራ መሪ እንጂ ጠንጋራ መሪ አንፈልግም›፣ ‹ወያኔ አሳረደን›፣ ‹ፍትህ የለም! በማለት ሁከት እንዲነሳ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡”
የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በምርመራ ወቅት የገጠማቸውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ ያሰሙ ሲሆን፣ በተለይ የሚደረግባቸው ምርመራ ከፓርቲው ጋር የተያያዘ እንጂ ከተጠረጠርንበት ጉዳይ ጋር የተያያዘ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ምርመራው ከጉዳዩ ጋር የሚገናኝ አይደለም፤ ሌሊት ሌሊት እየተጠራሁ ምርመራ ይደረግብኛል፡፡ የፓርቲ አባል መሆን ወንጀል እስኪመስለኝ በፓርቲ አባልነቴ ጫና ይደረግብኛል፡፡ በዚያ ላይ የጤና እከል ገጥሞኛል፤ ህክምና ያስፈልገኛል” ስትል ለፍርድ ቤቱ ያስረዳችው ወይንሸት ሞላ፣ ፍርድ ቤቱ የዋስትና መብት እንዲሰጣት ጠይቃለች፡፡

በሁለቱም መዝገብ የተካተቱት ሁሉም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፖሊስ በበኩሉ በመጀመሪያው መዝገብ ላይ ያሉት እነ ወይንሸት ላይ የምርመራ ስራውን እንዳልጨረሰ በመግለጽ 14 ቀን ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ በተለይ ወይንሸት ሞላ ላይ ፖሊስ፣ “ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ተመሳስላ በመልበስ ስታሸብር ነበር” በማለት ዋስትና እንዳይሰጥና የጠየቀው የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ በሁለተኛው መዝገብ ላሉት ደግሞ 7 ቀን ፖሊስ ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ በሁለቱም መዝገብ ላይ በተመሳሳይ የ6 ቀን ጊዜ በመስጠት ለሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

መንግስት በጠራው ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ወጣቶች እስር አሁንም እንደቀጠለ የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ በትናንትናው ዕለትም ሦስት የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አባላት (አንደኛው አሁን ላይ የሰማያዊ አባል) መታሰራቸው ይታወሳል፡፡
በተያያዘ ዜና ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ሳይጀመርና ከሰልፉ በኋላ ተይዘው የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ቤት ተበረበረ፡፡ ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ትናንት ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ለሁለተኛ ጊዜ ቀርበው የ6 ቀን ቀጠሮ ከተሰጠባቸው በኋላ ምሽት ላይ ቤታቸው መበርበሩንና ንብረቶቻቸው መወሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡

በብርበራው ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በሰላማዊ ሰልፍና በሌሎች አጋጣሚዎች የሚለብሱት የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ የምርጫና ሌሎች ቅስቀሳ ወረቀቶችም ለ‹ምርመራ› ተወስደዋል፡፡
ቤታቸው ለሰዓታት የተበረበረባቸው ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ማስተዋል ፍቃዱ ሲሆኑ ወይንሸት ሞላ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ወረቀቶች፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ ሲዲዎች፣ አርማ የሌለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ (በተናጠል አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የሆነ)፣መጽሐፎች እና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች እንደተወሰዱባት ገልጻለች፡፡ ዳንኤል ተስፋዬ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ በአንድ ላይ ያስጠረዛቸው የፋክትና የአዲስ ጉዳይ እትሞች፣ ሲዲዎችና ካሴቶች ተወስደውበታል፡፡ በተመሳሳይ ኤርሚያስ ጸጋዬ ዴስክ ቶፕ ኮምፒውተር፣ የሰማያዊ ፓርቲ ሰነዶች፣ ሲዲዎች፣ ማስታወሻ ደብተሮችና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች ተወስደውብኛል ብሏል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር ዋስትና የከለከላቸውን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እየወሰደ እየመረመረ ነው፡፡ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ላይ የታሰሩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ጠዋት በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ቀርበው የ6000 ብር የሰው ዋስትና እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር በእስር አቆይቷቸዋል፡፡

ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ጥሶ በአሁኑ ወቅት ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ አስሯቸው የሚገኙትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ እየወሰደ እየመረመረ ይገኛል፡፡ በዛሬው ዕለት ዳንኤል ተስፋዬ ወደ ማዕከላዊ እስር ቤት ተወስዶ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ውስጥ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ምንጮች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ በከፍተኛ ደረጃ ለተቃዋሚዎች ድጋፍ እየሰጠ መሆኑን ተከትሎ ገዥው ፓርቲ ኦህዴድ/ኢህአዴግ ምርጫውን ከወዲሁ ማስጀመሩ ተገለፀ

ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ገዥው ፓርቲ ምርጫውን ከአሁኑ እንደጀመረው ምንጮች ገለፁ፡፡ በተለያዩ የኦሮሚያ ክፍሎች የገዥው ኢህአዴግ ካድሬዎች መራጮችን በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ እያደራጁ “ኦህዴድ/ኢህአዴግን መርጫለሁ” በሚል እያስፈረሙና ፎርም እያስሞሉ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ ተደራጅተው ‹‹ኦህዴድን መርጠናል›› ብለው እንዲፈርሙ የተደረጉ ዜጎች ፎርሙን ከሞሉበት ቀን ጀምሮ የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ መሪዎቻቸው እንደሚሰጡ ታውቋል፡፡ የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ መሪዎችም ኢህአዴግን ከአሁኑ መርጠዋል ተብለው የተደራጁ ዜጎችን ስምና የምርጫ ካርድም ለኦህዴድ/ኢህአዴግ ከፍተኛ ካድሬዎች እንደሚሰጡ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

OFC_MEDREK

የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ግንቦት 16 ቀን በፊት የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ለሴልና ለኔትወርክ መሪዎች የሚሰጡትን ዜጎች ቤት ለቤት እየዞሩ እያስፈረሙ እንደሚገኙ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ በጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ ተደራጅተው ኦህዴድ/ኢህአዴግን ከአሁኑ እንደመረጡ በፊርማቸው አረጋግጠዋል የተባሉት ዜጎች ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም በሚደረገው ምርጫ እንደማይሳተፉ የታወቀ ሲሆን አብዛኛዎቹ በግዳጅና በማስፈራሪያ እየሞሉ እንደሚገኙ ተገልጾአል፡፡

የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ እንዲሁም የመራጮች ስምና ፊርማቸው እየሰፈረበት ከግንቦት 16 በፊት እንደመረጡ ተደርጎ ዜጎች እንዲሞሉት የሚደረገውና ከስር የሚታየው ቅጽ ካድሬዎች በአርሲ ዞን በቆጅ ወረዳ ቤት ለቤት ሲያስሞሉ መገኘቱ ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይም በምዕራብ ኢትዮጵያ እዚሁ ኦሮሚያ ክልል ተመሳሳይ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዶ/ር መረራ ጉዲና የሚመራው ቡድን በአካባቢው የተጠናከረ የምርጫ ቅስቀሳ በማድረጋቸውና ኦፌኮ/መድረክ በአካባቢው ህዝብ ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘቱን ተከትሎ የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ከአካባቢው የፀጥታ ኃይል ጋር በመሆን የተቃዋሚ ደጋፊዎችና የአካባቢው እጮዎች ጭምር ድብደባና እስራት እየፈፀመባቸው መሆኑን ምንጮችን ጠቅሶ ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል ፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ መንግስት የከፈተበትን የጥላቻ ዘመቻ በአስቸኳይ እንዲያቆም አሳሰበ

መንግስት ሊቢያ ውስጥ ኢትዮጵያውያን ላይ አሰቃቂ እርምጃ የወሰደውን አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም ራሱ በጠራው ሰልፍ ላይ ከህዝብ የገጠመውን ተቃውሞ ተከትሎ ሰማያዊ ላይ የጥላቻ ዘመቻ እንደከፈተበትና ይህንን የጥላቻ ዘመቻውን እንዲያቆም ሰማያዊ ፓርቲ በሰጠው መግለጫ አሳስቧል፡፡
መንግስት የጠራውን ሰልፍ ከማንም ተቃዋሚ ፓርቲ ቀድሞ የደገፈው ሰማያዊ እንደሆነ የገለጸው መግለጫው “የዜጎችን ስቃይ ለፖለቲካ ፍጆታ ማዋል የፈለገው ህወሓት/ኢህአዴግ ሰማያዊ ፓርቲ በወገኖቻችን ላይ ለሚደርሰው በደል መፍትሄ እንዲሰጥ መወትወቱ፣ የፖለቲካ ልዩነታችንን ወደ ጎን አድርገን በሰልፉ ላይ መገኘታችን እንዳላስደሰተው ከሰልፉ ቀን ጀምሮ በፓርቲያችን ላይ የተከፈተው ዘመቻ ትልቅ ማሳያ ነው፡፡” ብሏል፡፡
ከሰልፉ ማብቃት ጀምሮም ጉዳዩን ገና ፖሊስ ሳይመረምረው የመንግስት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ሚኒስትር ሬድዋን ሁሴን ሰማያዊ ፓርቲ ሁከትና ብጥብጥ ለማስነሳት እየጣረ ነው በሚል መወንጀላቸውን፣ የመንግስት ሚዲያዎች ሰማያዊ ፓርቲ ሁከትና ብጥብጥ ሊያስነሳ ነው ብለው ሚዛናዊ ያልሆነ መረጃ ማሰራጨታቸውንና አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም ተብለው በተጠሩ ሰልፎችም ሁሉ መንግስት ሰማያዊ ፓርቲ ለመቃወም እየተጠቀመባቸው መሆኑን መግለጫው አትቷል፡፡
በተጨማሪም በሰልፉ ዕለት የሰማያዊ አባላት ገና ሰልፉ ሳይጀመርና መስቀል አደባባይ ሳይደርሱ እንዲሁም ሰልፉ ካበቃ በኋላ እየታደኑ ሲታሰሩ መስቀል አደባባይ ላይ የተያዙት የኢህአዴግ አባላት ከቀበሌ ደብዳቤ እያመጡ መፈታታቸው መንግስት ሰማያዊን በሀሰት ለመወንጀል መነሳቱን ያሳያል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል 6 ያህል የሰማያዊ አባላት በታሰሩበት ሁኔታ መንግስት 7 አመራሮችና 20 ያህል አባላት ታስረዋል ማለቱ ትክክል አለመሆኑንና ከመጀመሪያውም 6 አባላቱ የታሰሩበት መንገድና አሁንም በሰማያዊ ላይ የሚቀርበው ክስ መሰረተ ቢስ ነው ብሎታል፡፡

Semayawi party

“ይህ በህወሓት/ኢህአዴግ መንግስት አማካኝነት እየቀረበ ያለው ክስ እና የሀሰት ፕሮፓጋንዳ ህወሓት/ኢህአዴግ ለዜጎች ህይወት የማይጨነቅ እና በዜጎች ሞት የራሱን የፖለቲካ ትርፍ ለማጋበስ እና ጠንካራ ተቃዋሚ የሆነውን ሰማያዊ ፓርቲን ለማጥቃት እየተጠቀመበት መሆኑን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው፡፡” ሲልም የመንግስትን ተግባር ተቃውሟል፡፡ በፍርድ ቤት ውሳኔ ያልተሰጠበትን ጉዳይ ተጠርጣሪ ከማለት ይልቅ ወንጀለኞች ናቸው በማለት በህገወጥ ስራ እንደተሰማራ ያሳያል ሲልም ወቅሷል፡፡

“መንግስት እና የመንግስት መገናኛ ብዙኃን ከዚህ አኩይ ተግባራቸው የማይታቀቡ ከሆነ፣ የሰማያዊን ስም በሀሰት በማጠልሸት ስራ ላይ የተሰማሩ የመንግስት ተቋማትን እና ግለሰቦችን በህግ ፊት ለማቆም ይገደዳል” ያለው መግለጫው ሌሎች ተከታታይነት ያላቸውን እርምጃዎችም እንደሚወስድና መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሰማያዊ ፓርቲ ለሚያደርጋቸው ህዝባዊ ጥሪዎች በንቃት ተዘጋጅቶ እንዲጠብቅ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

%d bloggers like this: