የሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አል-ሸባብ 43 የኢትዮጵያ ወታደሮች መግደሉን አስታወቀ
(አዲስ ሚዲያ) አል-ሸባብ ጥቃቱን የፈፀመው ከዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በስተሰሜን 300 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሃልገን ከተማ፤ የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ልዑክ( አሚሶም) አባል በሆኑ የኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ መሆኑን ሮይተርስ እና አል-ጀዚራን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡
በተለይ የታጣቂ ቡድኑ ወታደራዊ ክንፍ ቃል አቀባይ ሺክ አብዱዓሲስ አቡ ሙሳብ ለሮይተርስ እንደገለፁት ከሆነ፤ ትናንት ሐሙስ ሰኔ 2 ቀን 2008 ዓ.ም. በማዕከላዊ ሶማሊያ ሂራን ክልል ከተማ በሆነችው ሃልገን በፈፀሙት ጥቃት 43 የኢትዮጵያ ወታደሮችን መግደላቸውን፣ ቁጥሩን በይፋ ባይገልፁም በነበረው ውጊያ ከራሳቸው ከታጣቂ ቡድኑም የተገደሉ እንዳሉ አረጋግጠዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ በቃል አቀባዩ በኩል በኢቢሲ በኩል ባስተላለፈው መግለጫ 245 የአልሸ-ሸባብ ታጣቂዎችን መግደሉን ቢያስታውቅም፤ በውጊያው ምን ያህል የኢትዮጵያ ወታደር እንደተገደለ የገለፀው ነገር የለም፡፡
የኢትዮጵያ ጦር በኢህአዴግ ውሳኔ ወደ ሶማሊያ ከገባ ጀምሮ በርካታ ወታደሮች እንደተገደሉና ጉዳት እንደደረሰባቸው በተወሰነ ደረጃ ታጣቁ ቡድኑ በተለያየ ጊዜ ካሰራጨው የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ወታደሮች ስም እና ማንነት በስተቀር፤እስካሁን በኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ ስለደረሰ ጉዳት በመንግሥት በኩል ለህዝብ የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ የለም፡፡ ይሁን እንጂ ለተመሳሳይ ተልዕኮ በአፍሪካ ህብረት አሚሶም የተሰማሩ የኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ጅቡቲ ወታደሮች ከአል-ሸባብ ጋር በተደረጉ ውጊያዎች የደረሱ ጉዳቶችንም ሆነ ድሎች በተለያየ ጊዜ ለህዝባቸው ሲገልፁ ተስተውሏል፡፡
የኢህአዴግ መራሹ መንግሥት በይፋ ወታደሮቹን ወደ ሶማሊያ ካዘመተ ከ7 ዓመታት በላይ ቢሆንም፤ እስካሁን በኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ ስለደረሰው ጉዳት በመንግሥት በኩል ይፋ ተደርጎ ባያውቅም፤ የስርዓቱ ደጋፊ ብሎገሮች በትናንትናው የአል-ሸባብ ጥቃት 9 ያህል የኢትዮጵያ ወታደሮች ሞታቸውን እና 248 የታጣቂው ቡድንም በኢትዮጵያ ወታደሮች እንደተገደሉ ገልፀዋል፡፡
በሐሙሱ የአል-ሸባብ ጥቃት በሶማሊያ ውስጥ ስለተገደሉ የኢትዮጵያ ወታደሮች የኢትዮጵያ መንግሥት ምን የገለፀው ነገር ባይኖርም፤ ጥቃቱን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባን ኪ ሙን በይፋ አውግዘዋል፡፡
ከምርጫው ውጭ እንዲሆን የተደረገው አንድነት ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ላይ ያቀረበው ክስ ለየካቲት 27 ተቀጠረ!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በብሔራዊ ምርቻ ቦርድ አማካንነት ከግንቦቱ 2007 ዓ.ም. ሀገር አቀፍ ምርጫ ውጭ እንዲሆን መደረጉን በመቃወም በፌደራሉ ከፍኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ በፍትሐ ብሔር 11ኛ ችሎት የመሰረተው ክስ ለየካቲት 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠዋት ተቀጠረ፡፡
ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው በማኀበራዊ ሚዲያ ገፁ ላይ “ህገ ወጥ በሆነ መንገድ በምርጫ ቦርድ እና በኢህአዴግ ሴራ ለእነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ በኃይል ተላልፎ መሰጠቱ የሚታወቅ ነው። በዚህም ምክንያት ህጋዊው የአንድነት አመራር በምርጫ ቦርድ ላይ ክስ መስርተዋል፤ ፍርድ ቤቱ ልደታ በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት 11ኛ ፍትሀ ብሔር ችሎት ለየካቲት 27 ከጠዋቱ 3:30 ጉዳዩን ለማየት ቀጠሮ ሰጥተዋል፤ በመሆኑም በቅርብ የምንገኝ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች በችሎቱ ላይ በአካል በመገኘት ለህጋዊው አንድነት ያለንን አጋርነት እንድናሳይ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።” ብሏል፡፡
ብሔራዊ ምርጫ ቦር ከተመሰረተ ጀምሮ ከገዠው ህወሓት/ኢህአዴግ ጋር ጠንካራ ተፎካካሪ ናቸው ተብለው የሚገመቱትንና በከደፍተኛ ደረጃ የህዝብ ተቀባይነት ያላቸውን የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለይም ከዚህ በፊት የኦሮሞ ብሔራዊ ኮንግረንስ(ኦብኮ)ን ያፈረሰ ሲሆን፤ በቅርቡ ደግሞ የግንቦቱ ምርጫ 2007 ዓ.ም. ዋዜማ ላይ አንድነት ፓርቲን እና መኢአድን በማፍረስ ምርጫ ቦርድ ያፈረሳቸውን ፓርቲዎች ስም ለፈለጋቸው ሰዎች መስጠቱን ማሳወቁ ይታወሳል፡፡
ሰበር ዜና፤ ምርጫ ቦርድ አንድነትና መኢአድን ፓርቲን ለእነ ትግስቱ አወሉና ለእነ አበባው መሐሪ ሰጠ
- ‹‹እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው›› -ፕሮፌሰር መርጋ በቃና
ምርጫ ቦርድ አንድነትን ለእነ ትግስቱ አወሉ፣ እንዲሁም መኢአድን ለእነ አበባው መሃሪ መስጠቱን ዛሬ ጥር 21 ቀን 2007 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አሳወቀ፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹የእነ በላይ በፍቃዱ ቡድን›› በጠቅላላ ጉባኤ እንዳልተመረጠ፣ አምስት አባላት ያሉት አስመራጭ ኮሚቴ አባላት እንዳልመረጠ፣ የተመረጡበትም 51 ሲደመር አንድ መርህ አለመሆኑን፣ ጠቅላላ ጉባኤ ሲያደርግ ሪፖርት አለማድረጉንና ለአባላቱና ለፓርቲው ክብር የሌለው በመሆኑ ፓርቲውን ማስቀጠል እንደማይችል ገልጾአል፡፡
በሌላ በኩል የትግስቱ አወሉ ቡድን መርህ ይከበር እያለ እየታገለ በመሆኑ፣ የኢ/ር ግዛቸው ካቤኔ አባላት ተገፍተው የወጡ በመሆናቸው፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ለቦርዱ ሪፖርት እንዳደረጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን›› ፈቃደኛ ባለመሆኑ እንጂ እነሱ ችግራቸውን በውይይት ለመፍታት ፈቃደኛ በመሆናቸው እንዲሁም ለአባላቶቻቸውና ለፓርቲው ክብር ስላላቸው እውቅናውን ለእነሱ ሰጥቻለው ብሏል፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹ምርጫ የሚገባ ፓርቲ በማስፈለጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን ፓርቲውን የሚያስቀጥለው ባለመሆኑና ፓርቲውን እንደ ፓርቲ እንዲቆይ ስለሚፈለግ ዛሬ ጥር 21 ቦርዱ ባደረው አስቸኳይ ስብሰባ እነ ትግስቱ አወሉ ወደ ምርጫ እንዲገቡ ወስኗል›› ብሏል፡፡
የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ያካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ ስለመሆኑ በምን ታረጋግጡልናላችሁ?›› በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ‹‹ሁለቱም ችግር አለባቸው፡፡ እኛ ያየነው በአንጻራዊነት ነው፡፡ የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ችግር ቢኖርበትም ከዛኛው የተሻለ ነው፡፡ እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ እነ ማሙሸት አማረ በጠቅላላ ጉባኤ ባለመመረጣቸው፣ ለተከታታይ 3 ወራት ወርሃዊ መዋጮ ያላወጣ አባል ከአባልነት የሚሰረዝ በመሆኑና ከፓርቲ አባልነትም ስለተባረሩ እንዲሁም ህገ ወጥ ማህተም በማሳተማቸው እውቅና እንዳልሰጣቸው ገልጾአል፡፡ በሌላ በኩል 2005 ዓ.ም ላይ አበባው መሃሪ የተመረጡበት ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ እንዳልነበር ቢታመንም በተደረገ ምርመራ የተሟላ መሆኑ በመታወቁ፣ በትክክለኛው ማህተም ስለሚጠቀም፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጉ በተባለበት ወቅት ጠቅላላ ጉባኤ በማድረጉና ሪፖርቱንም ስላቀረበ ወደ ምርጫው እንዲገባ ወስኛለሁ ማለቱን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡
ይሁን እንጂ ፓርቲዎቹ ምርጫ 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰናቸውን ተከትሎ ህወሓት/ኢህአዴግ በምርጫ ቦርድ አማካኝነት ሊያፈርሳቸው የተለያየ ህገወጥ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፣ ቦርዱ ገለልተኛ እና ነፃ አለመሆኑን በድርጊቱ እየገለፀ ነው ሲሉ በተደጋጋሚ ተቃውሞና ቅሬታ እያቀረቡ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
የመከነው የአፍሪካ ራዕይ
ልክ የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ. በ1963 ዓ.ም የአፍሪካ ጥቁሮች ከባርነት ቅኝ ግዛት ለመውጣት የተወሰኑ መሪዎቿ ሽር ጉድ እያሉ ነበር፡፡ ሽርጉዱም የአፍሪካ ምድር በአውሮፓውያን ጨካኝ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ የወደቁትን ሀገሮች ነፃ ለማውጣት በጥቂት ጥቁር መሪዎች ምክክር ሊካሄድ ነው፡፡
ይሄን የሰሙት ገዥዎች በተለይም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ፖርቹጋልና፣ ጣሊያን ይበልጥ በጥቁሮች ላይ በደል መፈፀምን ተያያዙት፡፡ ይህን የተመለከቱት የአፍሪካ የአብራክ ልጆች በቁጭት በመንገብገብ ወገኖቻቸውን ከጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ መዘየድ ጀመሩ፡፡ ያኔ ግን የተለያዩ ሀገሮች በተለይም ጋና፣ ናይጄሪያና ደቡብ አፍሪካውያነ በየሀገሮቻቸው የተናጥል ትግል ያደርጉ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ትግሉ ፈቀቅ አላለም፡፡ ምክንያቱም ብቻቸውን ነበሩና፡፡
በወቅቱ ፈረንሳይ የሰሜን አፍሪካ ሀገሮችን በተለይም ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮን እንዲሁም በምዕራብ እንደ ማሊና ኮትዲቫርን በምስራቅ ጅቡቲን ይዛ ነበር፡፡ እንግሊዝ በበኩሏ በምስራቅ አፍሪካ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ሯንዳ፣ ክፊል ሱማሊያ በምዕራብ ናይጄሪያ፣ ጋና በደቡብ የቀድሞ ሮዴዥያ (ዙምባቤና ዛምቢያ)፣ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ይዛ ነበር፡፡ ፖርቹጋል ደግሞ በደቡብ ምዕራብ አንጐላን ስትቆጣጠር ጣሊያንም እንዳቅሟ ሊቢያንና ምስራቅ ሶማሊያን ተቆጣጥራ ነበር፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ለናሙና እንጂ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት የወደቁ ሌሎችም በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ነበሩ፡፡
ነፃ ሀገር
በተፈጥሮ የበለፀገችዋ እማማ አፍሪካ ምንም እንኳ በልጆቿ ስቃይ ማቅ ብትለብስም በወቅቱ እንደሀገር ሉዓላዊነት ያላቸው ሁለት ሀገሮች ነበሯት፡፡ እነኚህም በስተምስራቅ ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እና በምዕራብ የአልማዝ ምድር የሆነችው ላይቤሪያ ናቸው፡፡ በርግጥ ላይቤሪያ እንደሀገር ብትታይም ከነ ሰንደቅዓላማዋ ከአሜሪካ ቁጥጥር ስር ውጭ ነበረች ማለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እንደ ሀገር ከመመስረቷ በፊት የማንም ያልነበረች በኋላ ግን አሜሪካ በባርነት ከአፍሪካ ተወስደው በሀገሯ እየተባዙ የመጡትን የጥቁሮች ቁጥር ስጋት ላይ እንዳይጥላት በማሰብ ወደዛሬዋ ላይቤሪያ አብዛኞቹን ጭና በማራገፍ የዛሬዎቹ ላይበሪያውያን መኖሪያ አድርጋለች፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1888 እና በ1928 ዓ.ም በጣሊያን የቅኝ ግዛት ሙከራ ቢደረግም በጥቁር አናብስት ትግል ሳይሳካ በመቅረቱ ከአፍሪካ ብቸኛዋ ነፃ ሀገር ሆና ቆይታለች፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በዳግማዊ አጼ ምኒሊክ መሪነት የጥቁር አናብስት በጣሊያን ላይ በተቀዳጁት ድል ለሌሎችም ፋና ወጊ በመሆን የነፃነት ትግል እንዲቀጣጠል ፈር ቀዷል፡፡
የነፃነት ናፍቆት ህብር
አፍሪካውያን የነፃነት ናፍቆት ቢያንገበግባቸውም ትግሉ በተናጥል ስለሆነ በተፈለገው ፍጥነት ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለዚህም የናይጄሪያውን ኢቦ ኢቢቦ፣ የጋናው አሻንቲ እና የደቡብ አፍሪካውን የነ ባሱቶ ዙሉ ትግልን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ትግሉ እንዲሰምር በገዥዎች ሀገር ይኖሩ የነበሩ የጥቁሮች የአብራክ ክፋይ እነ ኩዋሜ ኑኩሩማ፣ ጆሞ ኬንያታ የመሳሰሉት በጋራ መታገሉ የተሻለ እንደሆነ በማሰብ በነፃይቱ የጥቁር አናብስት ምድር ንጉስ ከሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ጋር መከሩ፡፡
ምክክራቸውንም በማጧጧፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገሮች ገፉበት፡፡ በዚህም ጥቁሮች ሲነቃቁ ቅኝ ገዥ አውሮፓውያን ግን ድንጋጤ ወሯቸው ነበር፡፡ በተቃራኒው ጥቁሮች ደግሞ ከፍተኛ የአሸናፊነት ወኔን ተላብሰው ለልጆቻቸው ከጭቆና ነፃ የሆነ ምድር ለማውረሰና ለራሳቸውም ነፃነት ተግተው ተፋለሙ፡፡
ይሄን የተረዱት የትግሉ ውጤት ናፋቂዎች እነ አፄ ኃ/ስላሴና ኩዋሜ ኑኩርማን ጨምሮ ሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ይላቀቁ ዘንድ አፍሪካውያን በአንድ ስም ተጠርተው የሚጠለሉበትን ተቋም መመስረት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ የዚህም ተቋም ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከቅኝ ግዛት ነፃ ማውጣት ነበር፡፡
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት
አፍሪካውያንን የነፃነት ድል ለማቀዳጀት ሲባል የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ ግንቦት 1963 ዓ.ም በነፃይቱ ታሪካዊት ሀገር አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረትም ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ኢትዮጵያው ንጉስ አጼ ኃ/ስላሴ ነበሩ፡፡
በወቅቱ ተቋሙ ምንም እንኳ ቢመሰረትም ወዲያው የራሱን ቢሮና ለምክክር የሚሆን አዳራሽ መገንባት የማይቻል ቢሆንም ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃ/ስላሴ መንግስታቸውና መላው የሀገራቸው ህዝብ አፍሪካውያን ወገኖቹ ነፃ እንዲወጡ እንደሚሻ ተናገሩ፡፡ በዚህም ሳያበቁ በመንግስታቸውና በህዝባቸው ስም ዛሬ የህብረቱ አሮጌው ህንፃ ለፖሊስ ጽህፈት ቤት ተብሎ የተሰራውን ከነሙሉ ግቢው በነፃ ለድርጅቱ አስረከቡ፡፡ ድርጅቱም በነፃይቱ ምድር ያለማንም ከልካይ በነፃነት በመምከር የአፍሪካውያንን መፃኢ ተስፋ ብሩህ ለማድረግ ተግቶ ይሰራ ጀመር፡፡
በድርጅቱ ያላሰለሰ ጥረትም ጋና ቀድማ ከእንግሊዞች ቅኝ ግዛት ነፃ ስትወጣ ሌሎችም ተከታትለው ነፃ ወጥተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ግን ከአሰቃቂው የአፓርታይድ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ የወጣችው ዘግይታ ነበር፡፡
ያኔ በአዲስ አበባ የተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከባርነት ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት በተጨማሪ የአህጉሪቱ ሃብት በአውሮፓውያን ተወስደው ዜጐቿ እንዳይራቆቱ ነበር፡፡ የአፍሪካ አንጡራ ሃብት በቅኝ ገዥዎች ከልጆቿ ጉሮሮ ተነጥቆ እንዳይወሰድና ልጆቿ በእናት ምድራቸው በነፃነት እንዲቦርቁ ታስቦ በቀድሞው አባቶች መልካም ፈቃድ የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት /አ.አ.ድ/ ዛሬ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ይህም የሆነበት ምከንያት ድርጅቱ የተቋቋመለትን አፍሪካውያንን ከባርነትና ጭቆና ነፃ ማውጣት የሚለውን አሳክቶ ጨርሷል በሚል ነው፡፡
የጨነገፈው ፅንስ
የቀድሞ የአፍሪካ መሪዎች ያነገቡት ወገኖቻቸውን ነፃ የማውጣት መልካም ራዕይ በአሁኖቹ የአስተሳሰብ አድማስ እሳቤ ተሳክቷል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬ 12 ዓመት ግንቦት 2ዐዐ1 (እ.አ.አ) ደቡብ አፍሪካ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ወደ አፍሪካ ህብረት ተቀይሯል፡፡ እውነት ለመናገር ዛሬም ድረስ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፤ ነፃ የነበሩትም በአብራኮቻቸው ክፋይ ቅኝ ግዛት ውስጥ ገብተዋልና፡፡
በተለይ በዛሬዎቹ መሪዎች ድርጅቱ ዓላማውን አሳክቷል፤ ግቡን መቷል በሚል የአህጉሪቱን ልማት መሰረት በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ተቋቁሞ መቀመጫውንም እዚሁ አዲስ አበባ አድርጓል፡፡
ያኔ ቅኝ ገዥዎች ባላገሮቹን በግፍ ይጨቁኑ ነበር፣ ህዝቡ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ሲያቀርብ በጥይት እሩምታ በመረሸን የቀሩትን ወደ አሰቃቂ እስር ቤት ይከቱ ነበር፡፡ ይህ ግን ነፃዋን ኢትዮጵያን አይመለከትም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንጉሷም መሪዋም ባዕድ ሳይሆኑ ያው ያብራኳ ክፋይ አፄ ኃ/ስላሴና ኢትዮጵያውያን ናቸውና በመካከል የቅኝ ገዥነት እሳቤ የለም፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያውያን በንጉሱ ስርዓት ቅሬታ ሲሰማቸው በነፃነት ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ለዚህም እ.አ.አ በ197ዐ ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበረውን የነዳጅ ጭማሪ ዋጋ በመቃወም የነበረውን ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል፡፡ ከዛም በፊት ወጣቶች መሬት ላራሹ ተቃውሞን በነፃነት አሰምተዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ግን የማይቻል ነው፤ ቅኝ ገዥዎች ናቸውና፡፡
ዛሬ ግን ምናልባት አንፃራዊ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት አስተዳደር ያላቸው ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ካልሆነ በስተቀር አፍሪካውያን በራሳቸው ጥቁር ገዥዎች የጭቆና ቀንበር ስር ወድቀዋል፡፡ ለዚህም በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በኮትዲቫር፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና በአልጄሪያ ያሉትን ጨቋኝ አስተዳደሮች በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት ከቅኝ ገዥዎች በባሰ በአሽከሮቻቸው ታጣቂዎች በአደባባይ የጥይት እራት ሆነዋል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያም የተመለከትን እንደሆነ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ ህብረት ከተቀየረ በኋላ በቅኝ ያልተገዙት ኢትዮጵያውያን የመንግስት ገዥዎች በርካታ እኩይ ተግባራትን ለመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቢፈልጉም ለመጨረሻ ጊዜ በሚል ይመስላል እ.አ.አ በ2ዐዐ5 (በ1997 ዓ.ም) በምርጫ ወቅት ነበር የተደረገው፡፡ ከዚያም የምርጨውን ውጤት ተከትሎ በተፈጠረ ተቃውሞ አሁን በስልጣን ላይ ባለው ገዥው ቡድን መሪ በነበሩት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ ከ86ዐ በላይ ዜጐች የጥይት ናዳ አርፎባቸው እስከወዲያኛው አሸልበዋል፡፡
በኬንያና በሱዳንም ሆነ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገሮች በተመሳሳይ መልኩ ገዥዎችን ለመደገፍ ካልሆነ ለተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ለሞት ይዳርጋል፡፡ ይህንን ደግሞ ቅኝ ገዥዎች ያደርጉት የነበረው አስከፊ ድርጊት በጥቁር ቆዳ ካባ በለበሱ አምባገነን መሪዎች መደገፍ አፍሪካውያንም ሆኑ አፍሪካ ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የድጋፍ የድጋፍማ ቅኝ ገዥዎችም አሳምረው በመፍቀድ መፈክር እና ሌላ ወጭ በመሸፈን ይከናወን ነበር፤ ተቃውሞ ባይቻለም፡፡
ሌላው ያኔ በቅኝ ገዥዎች ወቅት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ተዝቆና ተሸጦ ወደ አውሮፓ ካዝና ይገባ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ በእራሳቸው በአፍሪካውያን መሪዎች ከአህጉሪቱ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቀው አንጡራ ሃብቷን ዝቀውና ሸጠው ወደ አውሮፓና እስያ ሀገሮች ካዝና ያስገባሉ፤ አፍሪካውያን ግን ዛሬም ይራባሉ፣ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ፣ ይጨቆናሉ፣ይሰደዳሉ፣ይገደላሉ፣ይዘረፋሉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመለትን ዜጐቿን ነፃ የማውጣት ራዕይ ግቡን ሳይመታና ሳያሳካ የነፃነት ፅንሱ በዚህ መልክ ጨንግፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእስያዎቹ ቻይና፣ ህንድና የአረብ ሀገራትን ጨምሮ አሜሪካና አውሮፓ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸውን አላወጡም፣ ዛሬም በዘመናዊው እጅ አዙር ቅኝ ጋዛት ቀፍድደው ይዘዋልና፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዓላማ ተጨናግፋል እንጂ ተሳክቷል ማለት አይቻልም፡፡
በትረ ከረባት ነዳያን
የቀድሞ ለነፃነት ቀናዒ የሆኑ የአባቶቻችንን ዓላማ ተሳክቷል በሚል ክህደት የዛሬዎቹ በትረ ከረባት ነዳያን የአፍሪካ ህብረትን አቋቁመዋል፡፡ የህብረቱም ዓላማ በአፍሪካ ልማትን ማምጣትና ማፋጠን እንዲሁም ማስተሳሰር የሚል ነው፡፡ በዚህም ስም በስልጣን ላይ ያሉት የአህጉሪቱ መሪዎች የራሳቸውን ሆድና ስልጣን ታሳቢ በማድረግ በአህጉሪቱ ህዝብ ስም ከረባት አስረው ለምነው የሚያመጡትን ገንዘብ በሌላ መንገድ በስማቸው ወደ ለጋሽ ሀገሮች ካዝና ይቋጥራሉ፡፡
ለዚህም የሊቢያ፣ የግብፅ፣ የቱኒዚያና የኢትዮጵያ መሪዎችን ጨምሮ አብዛኞቹ የዚህ ባለሟል ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መሪዎችም እጃቸው ከዜጐቻቸው የግፍ ደምና የህዝቡ አንጡራ ሃብት ዝርፍያ የፀዳ አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬም ድረስ ዜጐቻቸውን እጅግ ከቅኝ ገዥዎች በባሰ መልኩ በመጨቆን አንዳንዶቹ በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሌሎቹ ደግሞ በምርጫ ስም ህዝብን በማጭበርበር በትረስልጣናቸውን እያደላደሉ ይገኛሉ፡፡
አሁን በስልጣን ላይ ያሉት የአፍሪካ ማሪዎች የእነሱ የስልጣን ዕድሜ እስከረዘመና ዝርፊያውን እስኳጧጧፉ ድረስ የአህጉሪቱን አንጡራ ሃብት ጥቅም በማዘረፍ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ በዚህም ለዜጐቻቸው ያላቸው ቀናዒነትና ተቆርቋሪነት ከቀድሞዎቹ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መስራቾች ጋር ሲነፃፀር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ የበትረ ከረባት ነዳይ ሆነው የአህጉሪቱን ሃብት እያዘረፉ የዜጐቻቸውን ነፃ አስተሳሰብና ነፃ ሚዲያን በማፈን ከፍተኛ ጭቆና እያደረጉ ስለመሆኑ የህብረቱ ዋና መቀመጫ የሆነችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛው አፍሪካ ሀገሮችን ማየት በቂ ነው፡፡
በአጠቃላይ አሁን እ.አ.አ. በያዝነው ግንቦት 2ዐ13 የአፍሪካ ህብረት ምስረታ 5ዐኛ ዓመት ክብረ በዓል ለመሪዎቹ ብቻ ካልሆነ በቀር ለአህጉሪቱ ህዝብ ይሄ ነው የሚባል የፈየደው ነገር አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ምክንያቱም እየተሰሩ ያሉት መሰረተ ልማቶችና ሌሎች የህዝብ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ግንባታ ሰብዓዊ ልማትን ወደጐን በመተው እየተደረገ ያለው ቅኝ ገዥዎች በጊዜያቸው ሲያደርጉት ከነበረው እምብዛም የተለየ አይደለምና፡፡ በዚህም አፍሪካ ቀድሞ የነበራት ራዕይ በአሁኖቹ በትረ ከረባት ነዳይ መክኖ ቀርቷል ማለት ይቻላል፡፡ ያኔ ቅኝ ገዥዎች ሰብዓዊ መብትን በመርገጥ በቁሳዊ ልማት ህዝቡን ለመደለል ይሹ እንደነበረው ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡