Tag Archives: Kuwamie Nukruma

የመከነው የአፍሪካ ራዕይ

 ብስራት ወልደሚካኤልau

ልክ የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ. በ1963 ዓ.ም የአፍሪካ ጥቁሮች ከባርነት ቅኝ ግዛት ለመውጣት የተወሰኑ መሪዎቿ ሽር ጉድ እያሉ ነበር፡፡ ሽርጉዱም የአፍሪካ ምድር በአውሮፓውያን ጨካኝ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ የወደቁትን ሀገሮች ነፃ ለማውጣት በጥቂት ጥቁር መሪዎች ምክክር ሊካሄድ ነው፡፡

ይሄን የሰሙት ገዥዎች በተለይም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ፖርቹጋልና፣ ጣሊያን ይበልጥ በጥቁሮች ላይ በደል መፈፀምን ተያያዙት፡፡ ይህን የተመለከቱት የአፍሪካ የአብራክ ልጆች በቁጭት በመንገብገብ ወገኖቻቸውን ከጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ መዘየድ ጀመሩ፡፡ ያኔ ግን የተለያዩ ሀገሮች በተለይም ጋና፣ ናይጄሪያና ደቡብ አፍሪካውያነ በየሀገሮቻቸው የተናጥል ትግል ያደርጉ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ትግሉ ፈቀቅ አላለም፡፡ ምክንያቱም ብቻቸውን ነበሩና፡፡

በወቅቱ ፈረንሳይ የሰሜን አፍሪካ ሀገሮችን በተለይም ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮን እንዲሁም በምዕራብ እንደ ማሊና ኮትዲቫርን በምስራቅ ጅቡቲን ይዛ ነበር፡፡ እንግሊዝ በበኩሏ በምስራቅ አፍሪካ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ሯንዳ፣ ክፊል ሱማሊያ በምዕራብ ናይጄሪያ፣ ጋና በደቡብ የቀድሞ ሮዴዥያ (ዙምባቤና ዛምቢያ)፣ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ይዛ ነበር፡፡ ፖርቹጋል ደግሞ በደቡብ ምዕራብ አንጐላን ስትቆጣጠር ጣሊያንም እንዳቅሟ ሊቢያንና ምስራቅ ሶማሊያን ተቆጣጥራ ነበር፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ለናሙና እንጂ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት የወደቁ ሌሎችም በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ነበሩ፡፡

          ነፃ ሀገር

በተፈጥሮ የበለፀገችዋ እማማ አፍሪካ ምንም እንኳ በልጆቿ ስቃይ ማቅ ብትለብስም በወቅቱ እንደሀገር ሉዓላዊነት ያላቸው ሁለት ሀገሮች ነበሯት፡፡ እነኚህም በስተምስራቅ ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እና በምዕራብ የአልማዝ ምድር የሆነችው ላይቤሪያ ናቸው፡፡ በርግጥ ላይቤሪያ እንደሀገር ብትታይም ከነ ሰንደቅዓላማዋ ከአሜሪካ ቁጥጥር ስር ውጭ ነበረች ማለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እንደ ሀገር ከመመስረቷ በፊት የማንም ያልነበረች በኋላ ግን አሜሪካ በባርነት ከአፍሪካ ተወስደው በሀገሯ እየተባዙ የመጡትን የጥቁሮች ቁጥር ስጋት ላይ እንዳይጥላት በማሰብ ወደዛሬዋ ላይቤሪያ አብዛኞቹን ጭና በማራገፍ የዛሬዎቹ ላይበሪያውያን መኖሪያ አድርጋለች፡፡

በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1888 እና በ1928 ዓ.ም በጣሊያን የቅኝ ግዛት ሙከራ ቢደረግም በጥቁር አናብስት ትግል ሳይሳካ በመቅረቱ ከአፍሪካ ብቸኛዋ ነፃ ሀገር ሆና ቆይታለች፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በዳግማዊ አጼ ምኒሊክ መሪነት የጥቁር አናብስት በጣሊያን ላይ በተቀዳጁት ድል ለሌሎችም ፋና ወጊ በመሆን የነፃነት ትግል እንዲቀጣጠል ፈር ቀዷል፡፡

         የነፃነት ናፍቆት ህብር

 

አፍሪካውያን የነፃነት ናፍቆት ቢያንገበግባቸውም ትግሉ በተናጥል ስለሆነ በተፈለገው ፍጥነት ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለዚህም የናይጄሪያውን ኢቦ ኢቢቦ፣ የጋናው አሻንቲ እና የደቡብ አፍሪካውን የነ ባሱቶ ዙሉ ትግልን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ትግሉ እንዲሰምር በገዥዎች ሀገር ይኖሩ የነበሩ የጥቁሮች የአብራክ ክፋይ እነ ኩዋሜ ኑኩሩማ፣ ጆሞ ኬንያታ የመሳሰሉት በጋራ መታገሉ የተሻለ እንደሆነ በማሰብ በነፃይቱ የጥቁር አናብስት ምድር ንጉስ ከሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ጋር መከሩ፡፡

ምክክራቸውንም በማጧጧፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገሮች ገፉበት፡፡ በዚህም ጥቁሮች ሲነቃቁ ቅኝ ገዥ አውሮፓውያን ግን ድንጋጤ ወሯቸው ነበር፡፡ በተቃራኒው ጥቁሮች ደግሞ ከፍተኛ የአሸናፊነት ወኔን ተላብሰው ለልጆቻቸው ከጭቆና ነፃ የሆነ ምድር ለማውረሰና ለራሳቸውም ነፃነት ተግተው ተፋለሙ፡፡

ይሄን የተረዱት የትግሉ ውጤት ናፋቂዎች እነ አፄ ኃ/ስላሴና ኩዋሜ ኑኩርማን ጨምሮ ሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ይላቀቁ ዘንድ አፍሪካውያን በአንድ ስም ተጠርተው የሚጠለሉበትን ተቋም መመስረት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ የዚህም ተቋም ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከቅኝ ግዛት ነፃ ማውጣት ነበር፡፡

        የአፍሪካ አንድነት ድርጅት

አፍሪካውያንን የነፃነት ድል ለማቀዳጀት ሲባል የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ ግንቦት 1963 ዓ.ም በነፃይቱ ታሪካዊት ሀገር አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረትም ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ኢትዮጵያው ንጉስ አጼ ኃ/ስላሴ ነበሩ፡፡

በወቅቱ ተቋሙ ምንም እንኳ ቢመሰረትም ወዲያው የራሱን ቢሮና ለምክክር የሚሆን አዳራሽ መገንባት የማይቻል ቢሆንም ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃ/ስላሴ መንግስታቸውና መላው የሀገራቸው ህዝብ አፍሪካውያን ወገኖቹ ነፃ እንዲወጡ እንደሚሻ ተናገሩ፡፡ በዚህም ሳያበቁ በመንግስታቸውና በህዝባቸው ስም ዛሬ የህብረቱ አሮጌው ህንፃ ለፖሊስ ጽህፈት ቤት ተብሎ የተሰራውን ከነሙሉ ግቢው በነፃ ለድርጅቱ አስረከቡ፡፡ ድርጅቱም በነፃይቱ ምድር ያለማንም ከልካይ በነፃነት በመምከር የአፍሪካውያንን መፃኢ ተስፋ ብሩህ ለማድረግ ተግቶ ይሰራ ጀመር፡፡

በድርጅቱ ያላሰለሰ ጥረትም ጋና ቀድማ ከእንግሊዞች ቅኝ ግዛት ነፃ ስትወጣ ሌሎችም ተከታትለው ነፃ ወጥተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ግን ከአሰቃቂው የአፓርታይድ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ የወጣችው ዘግይታ ነበር፡፡

ያኔ በአዲስ አበባ የተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከባርነት ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት በተጨማሪ የአህጉሪቱ ሃብት በአውሮፓውያን ተወስደው ዜጐቿ እንዳይራቆቱ ነበር፡፡ የአፍሪካ አንጡራ ሃብት በቅኝ ገዥዎች ከልጆቿ ጉሮሮ ተነጥቆ እንዳይወሰድና ልጆቿ በእናት ምድራቸው በነፃነት እንዲቦርቁ ታስቦ በቀድሞው አባቶች መልካም ፈቃድ የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት /አ.አ.ድ/ ዛሬ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ይህም የሆነበት ምከንያት ድርጅቱ የተቋቋመለትን አፍሪካውያንን ከባርነትና ጭቆና ነፃ ማውጣት የሚለውን አሳክቶ ጨርሷል በሚል ነው፡፡

የጨነገፈው ፅንስ

የቀድሞ የአፍሪካ መሪዎች ያነገቡት ወገኖቻቸውን ነፃ የማውጣት መልካም ራዕይ በአሁኖቹ የአስተሳሰብ አድማስ እሳቤ ተሳክቷል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬ 12 ዓመት ግንቦት 2ዐዐ1 (እ.አ.አ) ደቡብ አፍሪካ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ወደ አፍሪካ ህብረት ተቀይሯል፡፡ እውነት ለመናገር ዛሬም ድረስ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፤ ነፃ የነበሩትም በአብራኮቻቸው ክፋይ ቅኝ ግዛት ውስጥ ገብተዋልና፡፡

በተለይ በዛሬዎቹ መሪዎች ድርጅቱ ዓላማውን አሳክቷል፤ ግቡን መቷል በሚል የአህጉሪቱን ልማት መሰረት በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ተቋቁሞ መቀመጫውንም እዚሁ አዲስ አበባ አድርጓል፡፡

ያኔ ቅኝ ገዥዎች ባላገሮቹን በግፍ ይጨቁኑ ነበር፣ ህዝቡ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ሲያቀርብ በጥይት እሩምታ በመረሸን የቀሩትን ወደ አሰቃቂ እስር ቤት ይከቱ ነበር፡፡ ይህ ግን ነፃዋን ኢትዮጵያን አይመለከትም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንጉሷም መሪዋም ባዕድ ሳይሆኑ ያው ያብራኳ ክፋይ አፄ ኃ/ስላሴና ኢትዮጵያውያን ናቸውና በመካከል የቅኝ ገዥነት እሳቤ የለም፡፡

በወቅቱ ኢትዮጵያውያን በንጉሱ ስርዓት ቅሬታ ሲሰማቸው በነፃነት ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ለዚህም እ.አ.አ በ197ዐ ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበረውን የነዳጅ ጭማሪ ዋጋ በመቃወም የነበረውን ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል፡፡ ከዛም በፊት ወጣቶች መሬት ላራሹ ተቃውሞን በነፃነት አሰምተዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ግን የማይቻል ነው፤ ቅኝ ገዥዎች ናቸውና፡፡

ዛሬ ግን ምናልባት አንፃራዊ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት አስተዳደር ያላቸው ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ካልሆነ በስተቀር አፍሪካውያን በራሳቸው ጥቁር ገዥዎች የጭቆና ቀንበር ስር ወድቀዋል፡፡ ለዚህም በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በኮትዲቫር፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና በአልጄሪያ ያሉትን ጨቋኝ አስተዳደሮች በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት ከቅኝ ገዥዎች በባሰ በአሽከሮቻቸው ታጣቂዎች በአደባባይ የጥይት እራት ሆነዋል፡፡

በምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያም የተመለከትን እንደሆነ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ ህብረት ከተቀየረ በኋላ በቅኝ ያልተገዙት ኢትዮጵያውያን የመንግስት ገዥዎች በርካታ እኩይ ተግባራትን ለመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቢፈልጉም ለመጨረሻ ጊዜ በሚል ይመስላል እ.አ.አ በ2ዐዐ5 (በ1997 ዓ.ም) በምርጫ ወቅት ነበር የተደረገው፡፡ ከዚያም የምርጨውን ውጤት ተከትሎ በተፈጠረ ተቃውሞ አሁን በስልጣን ላይ ባለው ገዥው ቡድን መሪ በነበሩት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ ከ86ዐ በላይ ዜጐች የጥይት ናዳ አርፎባቸው እስከወዲያኛው አሸልበዋል፡፡

በኬንያና በሱዳንም ሆነ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገሮች በተመሳሳይ መልኩ ገዥዎችን ለመደገፍ ካልሆነ ለተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ለሞት ይዳርጋል፡፡ ይህንን ደግሞ ቅኝ ገዥዎች ያደርጉት የነበረው አስከፊ ድርጊት በጥቁር ቆዳ ካባ በለበሱ አምባገነን መሪዎች መደገፍ አፍሪካውያንም ሆኑ አፍሪካ ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የድጋፍ የድጋፍማ ቅኝ ገዥዎችም አሳምረው በመፍቀድ መፈክር እና ሌላ ወጭ በመሸፈን ይከናወን ነበር፤ ተቃውሞ ባይቻለም፡፡

ሌላው ያኔ በቅኝ ገዥዎች ወቅት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ተዝቆና ተሸጦ ወደ አውሮፓ ካዝና ይገባ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ በእራሳቸው በአፍሪካውያን መሪዎች ከአህጉሪቱ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቀው አንጡራ ሃብቷን ዝቀውና ሸጠው ወደ አውሮፓና እስያ ሀገሮች ካዝና ያስገባሉ፤ አፍሪካውያን ግን ዛሬም ይራባሉ፣ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ፣ ይጨቆናሉ፣ይሰደዳሉ፣ይገደላሉ፣ይዘረፋሉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመለትን ዜጐቿን ነፃ የማውጣት ራዕይ ግቡን ሳይመታና ሳያሳካ የነፃነት ፅንሱ በዚህ መልክ ጨንግፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእስያዎቹ ቻይና፣ ህንድና የአረብ ሀገራትን ጨምሮ አሜሪካና አውሮፓ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸውን አላወጡም፣ ዛሬም በዘመናዊው እጅ አዙር ቅኝ ጋዛት ቀፍድደው ይዘዋልና፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዓላማ ተጨናግፋል እንጂ ተሳክቷል ማለት አይቻልም፡፡

       በትረ ከረባት ነዳያን

የቀድሞ ለነፃነት ቀናዒ የሆኑ የአባቶቻችንን ዓላማ ተሳክቷል በሚል ክህደት የዛሬዎቹ በትረ ከረባት ነዳያን የአፍሪካ ህብረትን አቋቁመዋል፡፡ የህብረቱም ዓላማ በአፍሪካ ልማትን ማምጣትና ማፋጠን እንዲሁም ማስተሳሰር የሚል ነው፡፡ በዚህም ስም በስልጣን ላይ ያሉት የአህጉሪቱ መሪዎች የራሳቸውን ሆድና ስልጣን ታሳቢ በማድረግ በአህጉሪቱ ህዝብ ስም ከረባት አስረው ለምነው የሚያመጡትን ገንዘብ በሌላ መንገድ በስማቸው ወደ ለጋሽ ሀገሮች ካዝና ይቋጥራሉ፡፡

ለዚህም የሊቢያ፣ የግብፅ፣ የቱኒዚያና የኢትዮጵያ መሪዎችን ጨምሮ አብዛኞቹ የዚህ ባለሟል ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መሪዎችም እጃቸው ከዜጐቻቸው የግፍ ደምና የህዝቡ አንጡራ ሃብት ዝርፍያ የፀዳ አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬም ድረስ ዜጐቻቸውን እጅግ ከቅኝ ገዥዎች በባሰ መልኩ በመጨቆን አንዳንዶቹ በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሌሎቹ ደግሞ በምርጫ ስም ህዝብን በማጭበርበር በትረስልጣናቸውን እያደላደሉ ይገኛሉ፡፡

አሁን በስልጣን ላይ ያሉት የአፍሪካ ማሪዎች የእነሱ የስልጣን ዕድሜ እስከረዘመና ዝርፊያውን እስኳጧጧፉ ድረስ የአህጉሪቱን አንጡራ ሃብት ጥቅም በማዘረፍ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ በዚህም ለዜጐቻቸው ያላቸው ቀናዒነትና ተቆርቋሪነት ከቀድሞዎቹ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መስራቾች ጋር ሲነፃፀር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ የበትረ ከረባት ነዳይ ሆነው የአህጉሪቱን ሃብት እያዘረፉ  የዜጐቻቸውን ነፃ አስተሳሰብና ነፃ ሚዲያን በማፈን ከፍተኛ ጭቆና እያደረጉ ስለመሆኑ የህብረቱ ዋና መቀመጫ የሆነችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛው  አፍሪካ ሀገሮችን ማየት በቂ ነው፡፡

በአጠቃላይ አሁን እ.አ.አ. በያዝነው ግንቦት 2ዐ13 የአፍሪካ ህብረት ምስረታ 5ዐኛ ዓመት ክብረ በዓል ለመሪዎቹ ብቻ ካልሆነ በቀር ለአህጉሪቱ ህዝብ ይሄ ነው የሚባል የፈየደው ነገር አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ምክንያቱም እየተሰሩ ያሉት መሰረተ ልማቶችና ሌሎች የህዝብ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ግንባታ ሰብዓዊ ልማትን ወደጐን በመተው እየተደረገ ያለው ቅኝ ገዥዎች በጊዜያቸው ሲያደርጉት ከነበረው እምብዛም የተለየ አይደለምና፡፡ በዚህም አፍሪካ ቀድሞ የነበራት ራዕይ በአሁኖቹ በትረ ከረባት ነዳይ መክኖ ቀርቷል ማለት ይቻላል፡፡ ያኔ ቅኝ ገዥዎች ሰብዓዊ መብትን በመርገጥ በቁሳዊ ልማት ህዝቡን ለመደለል ይሹ እንደነበረው ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡

%d bloggers like this: