Tag Archives: TPLF/EPRDF democracy

ሶስቱ የሰማያዊ ፓርቲ እንስት አባላት በዓለም አቀፍ ደረጃ ዘመቻ እየተደረላቸው ነው

የአሜሪካ መንግስት ኦፊሳላዊ ድረ ገጽ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ጉዳይ አስተባባሪነት በዓለም ላይ ለተመረጡ 20 ሴት የፖለቲካ እስረኞች መካከል ሶስት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ዘመቻና ማስታወሻ እየተደረላቸው ነው፡፡

ከዛሬ 20 ዓመት በፊት ሴቶችን ለማብቃት፣ የጾታ እኩልነትን ለማስፈን እና የልጃ ገረዶችን ሰብዓዊ መብት ለማስጠበቅ የቤጂንግ መርሃ ጉዞ ተቀምጦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእነዚህ 20 አመታት ልክ ከዓለም ሀገራት በፖለቲካ እስረኝነታቸው የተመረጡ 20 ሴት እስረኞችን ለማሰብ የሚደረገው ዘመቻ መነሻው ይህ መርሃ ጉዞ ነው፡፡

በዚህ መሰረት ከኢትዮጵያ ብሌን መስፍን፣ ንግስት ወንዲፍራው እና ሜሮን አለማየሁ የተካተቱ ሲሆን ከቻይና እንዲሁ ሦስት ሴት የፖለቲካ እስረኞች ተመርጠው እየታወሱ ነው፡፡

Blue member
http://www.humanrights.gov/freethe20
ምንጭ፡ ነገረ-ኢትዮጵያ

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ 28 ቀን ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

ከግራ ወደቀኝ  ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

ከግራ ወደቀኝ ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ትናንት መጋቢት 21 አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ እነ ብርሃኑ ተክለያሬድን ‹‹ለግንቦት 7 አባላትን መልምለው ወደ ኤርትራ በመላክና ቡድኑን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ተይዘዋል›› ብሏል፡፡

ጠበቃው እነ ብርሃኑ ተ/ክለያሬድ ለግንቦት ሰባት ሲመለምሉም ሆነ አባል ሲሆኑ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ እንደሌለ በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምመረምራቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ሌሎች የምንይዛቸው ግብረ አበሮችም አሉ፡፡ መረጃ ያጠፉብናል፡፡›› በሚል ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆ 28 ቀን ተፈቅዶለታል፡፡ ሚያዚያ 19 ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡

ፖሊስ ሌሎች ሰዎች ይዘውት የተነሱትን መሳሪያ በማሳየትም እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ እንደነበር ለማሳየት በመረጃነት አቅርቧል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹የማህበራዊ ሚዲያ ላይ ምርመራ ለማድረግና መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተጠርጣዎቹን ማሰር ተገቢ አልነበረም፡፡ ሌሎች ሰዎች የያዙትን መረጃ እነሱን ለመክሰስ መጠቀም ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ ተቃውመዋል፡፡

በሌላ በኩል ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ የታሰረበት ቤት መብራት ስለማይጠፋ አይኑ ላይ ለከፍተኛ ችግር እንዳደረሰበት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ለ15 ደቂቃ ፀኃይ እንዲሞቁ ከሚፈቀድላቸው ውጭ ወደ ከታሰሩበት ቤት ውጭ መውጣት እንደማይፈቀድላቸውና ቤተሰቦቻቸውም እንዲጠይቋቸው እየተደረገ አለመሆኑን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡

የዞን9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ቃል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡

ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ ተሰሙት ምስክሮች

7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡

8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡

9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡

10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)

11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡

12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡

በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡

Ethiopia-Federal-High-Court-300x194

ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡

ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡

ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡

ምንጭ፡- ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ

የማለዳ ወግ … ለሃጅ ጸሎት መጥቶ ሳውዲ የቀረው ገበሬ እንግልት

ነብዩ ሲራክ

(ከሳውዲ ዓረቢያ)

ወንድም ራያ ጀማል የ5 ወንድ እና የ3 ሴት ልጆች ጎልማሳ አባት ነው። ወደ ሳውዲ የመጣው ድህነት ፣ የኑሮ ውድነት ፣ የፖለቲካው ሙቀት አለያም የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ገፍቶት አይደለም ። ሳውዲ የመጣው ፣ በእስልምና እምነቱ በሚያዘው መሰረት በህይወት ዘመኑ የሚጠበቅበትን ለማድረግ ከብቶቹን ሽጦ የሃጅ ጸሎት ለማድረግ ነበር … ዳሩ ግና የጅማው ገበሬ ራያ ጀማል እንደ ቀሩት ጓደኞቹ ጸሎቱን አድርጎ ለመመለስ አልቀናውም! ከሀጃጅ ጓደኞቹ ተለይቶ ከቤተሰብ እንደራቀ ፣ ላለፉት ሁለት አመት ከመንፈቅ ገደማ ሳውዲ በእንግልት ጊዜውን ሊገፋ ግድ ብሎታል ። ምክንያቱም የሃጅ ጸሎቱን ከውኖ መካ ውስጥ መኪና አደጋ ደረሰበትና ነው !

የራያ ጀማል ጉዳት …

ራያ ጀማል በደረሰበት የመኪና ግጭት የተለያየ የአካሉ ክፍል በጠና ስለተጎዳ በከፍተኛ ህክምና መካ ውስጥ ለሁለት አመት ተኩል ገደማ በሳውዲ የመንግስት ሆስፒታል ሲረዳ ቆይቷል። የመጓጓዣ የማረፊያና የኢንሹራንስ እስከ 55 ሽህ ብር የሚደርስ ገንዘብ ከፍሏቸው ለጸሎት ያማጡት የሃጅ ኮሚቴዎችም ሆኑ የጅዳ ቆንስል ራያ ጀማልን ሊረዱት ቀርቶ ሊያዩት አልቻሉም! ይህ የሆነው ስለ ራያ ጀማል መረጃ ስላልነበራቸው አይመስለኝም ፣ ይህን ስል መረጃው እንደነበራቸው እኔም መረጃ አለኝና ነው!

ለሃጅ ጸሎት መጥቶ ስለደረሰበት የመኪና አደጋ በያዝነው ሳምንት የ50 ኢዩቬልዩ በአሉን ባከበረው የጀርመን ራዲዮ ዜናውን አቅርበነው ነበርና የቆንስሉም የሃጅ ኮሚቴ ኃላፊዎች ያውቃሉ ! ከዚህ ሁሉ በኋላም ልክ የዛሬ አንድ አመት ገደማ የጅዳ ቆንስል ተወካይ ራያ ጀማል በነበረበት የሽሻ ሆስፒታል ለሌላ ጉዳይ ሄደው አግኝተውትም እንደነበር ተገፊው ወንድም አጫውቶኛል ። ተወካዩ ራያ ጀማልን ስላጋጠመው የመኪና አደጋ በዝርዝር ጠይቀውት መመለሳቸውን ከተጎጅው ጋር በያዝነው ሳምንት ባንድ ምሽት ከወደቀበት የጅዳ ቆንስል አካባቢ በሚገኘው የአንድ አረብ ሃብታም አጥር ኩርትም ብሎ ባገኘሁት አጋጣሚ አጫውቶኛል። ይህ ሁሉ ሆኖ የዜጎች ጉዳይ የሚለመከታቸው የቆንስል ኃላፊዎች ራያ ጀማልም ሆነ ጉዳዩ የት ደረሰ ? ብለው አልጠየቁም !

ራያ ጀማልን ሳገኘው …

የወንድም ራያ ጀማልን ወደ ጅዳ መምጣትና አቤቱታ የማቅረቡ መረጃ ደረሰኝ ። ፈልጌ አጣሁት ። አንድ ምሽት ወደ ኮሚኒቲ ካፍቴሪያ ሳዘግም ከግቢው ውጭ ባለ አጥር ታዛ ተኝቶ አየሁት ። ራያ ጀማል ነው ግን አላልኩም። ተጠግቸ ለማነጋገር ብሞክርም መተኛቱን ተረዳሁና ትቸው ሄድኩ። በካፍቴሪያ አካባቢ ስለወደቀው ወንድም ጠየቅኩ ፣ ራያ ጀማል ለመሆኑ በቂ ምልክቱ በምርኩዝ “ክራንች ” እየታገዘ እንደሚመላለስ ሲነገረኝ አገግሞ ከመካ ሽሻ ሆስፒታል የወጣው ራያ ጀማል መሆኑን ተረዳሁ።

ራያ ጀማልን በቀጣዩ ቀን አግኝቸው አወጋን ። ከሁለት አመት በላይ በሳውዲ የመንግስት ሃኪም ቤት በህክምና ሲረዳ የቆየው ኢትዮጵያዊ በቀኝ ጎኑ ደገፍ በሚልባት ምርኩዝ “ክራንች” እየታገዘ ፣ አያነከስ ጉዳዩን ለማስፈጸም ላይ ታች ይላል። ፍትህ ሊያገኝና ወደ ሀገሩ ሊሸኝ ፣ የሞት መርዶውን ሰምተው ያለቀሱ ቤተሰቡን ተሰናክሎም ቢሆን ይቀላቀል ዘንድ ተስፋ ሰንቆ ከመጣበት ቤቱ የሚደግፈውም ሆነ ፣ ለጎኑ ማሳረፊያ መጠለያ የሚሰጠው አጥቷል ። የገዛ ሃገሩ ሰዎች ክብር አልሰጠነውምና በዚህ ሙቀት ከቆንስሉ ርቆ ባለው የአረብ ግንብ ጠጋ ብሎ ውሎ ያድራል …

አቶ ራያ ጀማል በሳውዲ ዓረቢያ አደጋ ከደረሰበት በኋላ

አቶ ራያ ጀማል በሳውዲ ዓረቢያ አደጋ ከደረሰበት በኋላ

ራያ ጀማልን ከፍ ሲል ኢትዮጵያዊነቱ ፣ ዝቅ ሲል ቋንቋውን የሚናገሩት የቀየው ልጆች ሞልተው ተርፈዋል ፣ ሁላችንም ግን ጉዳቱን እንኳ ጠጋ ብለን መጠየቅ ገዶናል ። አቅም የለሾቹ በጥድፊያው ብንወጠር ጧትና ማታ የሚያዩት የቆንስል ዲፕሎማቶችና የልማት ማህበር አባላት ብሶቱን ሰምተው ለምን ጨከኑበት ? ማለቴ አልቀረም …መልስ የለኝምና አዘንኩ !

የወንድም ራያ ጀማልን ጉዳይ በቅርብ ርቀት ላለፉት ሁለት ሳምንታት ላላነሰ ጊዜ ስከታተል ቆየሁ ። ጉዳዩ በቆንስ ኃላፊዎች በኩል ለጉዳይ ፈጻሚው ተላልፎ ጉዳዩ ሲንከባለል ቢሰነብትም ወደ መጨረሻ ራያ ጀማል ወደ ሀገሩ ለመላክ መወሰኑና ቲኬት ኮሚኒቲው እንዲያቀርብ ትብብር በቆንስል ሸሪፍ የመጠየቁ መረጃ ከአንድ የኮሚኒቲ የምክር ቤት አባል መረጃው ደረሰኝ ።
( በዚህ ዙሪያ ትናንት ባቀረብኩት ተመሳሳይ መረጃ ቅሬታ ያቀረቡልኝ አንድ ጠቋሚ ሃሳብ በመቀበል ሳጣራ ግን ቆንድል ሸሪፍ ኬሩ ራያ የ ጀማል የቲኬት ጥያቄውን ለኮሚኒቲ እንዲያቀርብ በስሙ ደበዳቤ ጽፈው ማዘጋጀታቸውንና ለኮሚኒቲው ምክትል በስልክ “ተባበሩት “ማለታቸውን ማረጋገጥ ችያለሁ)

ከቆንስሉ ግቢ ለቀን ወደ ኮሚኒቲ ጉዳዩን ለማጣራት ራያና እኔ ተያይዘን ስንወጣ ከቆንስሉ ባለጉዳዮች መግቢያ በር ነጻ ግልጋሎት የሚሰጡትን የድርጅትና የኦሮሞ ልማት ማህበር አባል ጋር ተገናኘን ። ሳያቸው በስጨት አልኩና ስማቸውን ጠርቸ ” የዚህ ወንድም ጉዳይ ወደ ሃገሩ ለመላክ ሲወሰን አንድም እንደ ዜጋ አለያም እንደ ተወላጅ ለምን መብቱን ማስከበር ለምን ተሳናችሁ? ” ስል ጠየቅኳቸው ። ግራ ተጋብተው …” ይህ ወንድም እንደ ተገልጋይ ሲወጣ ሲገባ ከማየት ውጭ ታሪኩን አላውቅም! ” ብለው ሲመልሱልኝ ራያን እንዲጠይቁት አድርጌ በኦሮምኛ አውርተው ጨረሱ ፣ወደኔ መለስ ብለው ” እውነት እልሃለሁ ፣ ምንም አይነት መረጃ የለኝም!” በማለት በአግርሞት መልሰውልኝ በእንግልቱ ዙሪያ ስናወጋ ሌላው የጅዳ ኮሚኒቲና የኦሮምያ ድርብ ስልጣን ያላቸው እድሜ ጠገብ ወዳጀን አገኘኋቸው …

ለኃላፊው ኮሚኒቲውም ቲኬት እንዲያቀርብ መጠየቁን በማውሳት “ራያው ጀማል ጉዳዩን ሳይጨርስ ለምን ቲኬት ለመስጠት ተስማማችሁ? ” ብየ ጠየቅኳቸው ። ኃላፊውም ስለ ቲኬቱ ጥያቄው መቅረቡን ከማመን ባለፈ በጉዳዩ ላይ ውሳኔ አለመሰጠቱን ጠቁመው ጉዳዩን ከቆንስል ሸሪፍ ኬሩ ጋር እየተነጋገሩበት እንደሆነ ጠቁመውኛል ። ከእኒህ ወዳጀ ጋር ውይይታችን እንደቀጠልን ወደ ካፍቴርያው አመራን። በድጋሜ ከራያ ጀማል ማግኘት አለባቸው የምለውን መረጃ ጠይቀው እንዲረዱ አደረግኩ ። መጠለያን በሚመለከትም ሃላፊነቱን ቆንስሉ ከወሰደ መጠጊያ እንደማይጠፋ በመጠቆም ፈቃድ ያመጡልኝ ዘንድም አሳሰብኳቸው ። ከሰነበተበት ሜዳ ወደ የግል መጠለያ ለመውሰድ ፍቃዱን እንደሚጠይቁልኝ አጫወቱኝ ። ኃላፊው የሰጡኝን ምላሽ ሁሉንም ለማመን ሞከሬ እንዲከታተሉት ጭምር ተመካክረን ተለያየን !

ይህ ከሆነ ከአንድ ቀን በኋላ የኦሮሞ ተወላጆች ማህበር አመታዊ በአላቸውን ሊያከብሩ ስለ አከባበሩ ዝግጅት መክረው ሲወጡ የኦሮሞው ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ራያ ጀማል ጉዳይ በተሰብሳቢዎች ተነስቶ ራያ ጀማልን ማነጋገራቸውን ሰማሁ ። ሁሉም በሆነው አዝነው በተለይም የድርጅት አባላቱ በቁጭት ለመፍትሄው ከቆንስሉ ጋር እንደሚመክሩ ጠቁመው ፣ ማረፊያ እስኪ ያዘጋጁለት በቆንስሉ ግቢ እንዲያድር አድረገው ተለያዩ ።

መሽቶ ነጋ ፣ የተባለው ደረሰ ፣ ቃል የገቡት የውሃ ሽታ ሆነው ቀሩ ! ባዩት ያዘኑት ሰብዕና አስገድዷቸው ለወንድም ራያ ጀማል ጎኑን የሚያሳርፍባት ፍራሽና መላብስ እንባቸውን እያዘሩ አቀብለውት ብቻ አልሄዱም ። እስከ ዛሬ ደረስ አደየመጡ ይጠይቁታል ! ራያ ጀማል ከዚያች ቀን በኋላ በኦሮሚያ ማህበር አባላት የዚያች ምሽት ተማጽኖ ከኮሚኒቲው ግቢ ማደር ቢችልም በቀጣዩ ቀናት ከቆንስሉና ከኮሚኒ ቲው ግቢ እንዳያድር ተከለከለ ! ወንድም ራያ ጀማል ያገገመው ስብራቱ በእንግልቱ እየተቀሰቀሰ እየወጋው እየተሰቃየ ነው ። ከሃገሩ ባንዴራ የቅርብ ርቀት ባሉት የአረብ ሃብታሞች አጥር ታዛ ኑሮን በመከራ በመግፋት ላይ ነው !

“ጉዳዩ ተሸፋፍኖ ሊሄድ ነው!” ብለን የሰጋነው የራያ ጀማል ጉዳይ ብዙዎቻችን ያስቆጨ ቢሆንም ዛሬ ነገሮች ተቀያይረዋል ብየ ነበር ከቀናት በፊት ። ይህንንም ያልኩት የቆንስሉ ጉዳይ ፈጻሚ አቶ መሃዲና ወንድም ራያ ጀማል ወደ መካ በማቅናት ከመካ ትራፊክ ፖሊስ ጋር የመነጋገራቸውን ሰናይ መረጃ ሰምቸ ነበርና ነው … እቀጥልበታለሁ ብየ ጉዳዩን በእንጥልጥል የተውኩት ጉዳይ ፈጻሚውና ወንድም ራያ ጀማል ከመካው ጉዞ ያገኙትን ውጤት ይዠ ለማምጣት ይቻለኛልና ነበር ። አነሆ ጉዳዩ የተያዘበትን የመካ ትራፊክ ፖሊስን ያነጋገሩት ጉዳይ ፈጻሚ የራያን መዝገብ አስቀርበው የገጨውን መኪና ባለቤት በስልክ ማነጋገራቸውን ተገፊው ወንድም አጫውቶኛል። ከዚህ ቀደም ራያ በሆስፒታል እያለ 10 ሽህ የሳውዲ ሪያል ሊሰጡት ፈቃደኛ ሆነው የነበሩት ሳውዲ ዛሬ 3 ሽህ ሪያል ካሳ ሊከፍሉ ፍቃደኛ መሆናቸውን መግለጻቸው ይህም ካልተቀበሉ ወደ ፍርድ ቤት መሄድ እንደሚችሉ መነገራቸውን ራያ ጀማል ገልጾልኛል። ወንድም ራያ ከአመት በፊት የሆነውን እያስታወሰ ይህው ሳውዲ የገጨው መኪና ባለቤት ወደ ሆስፒታል መጥተው “10 ሽህ ሪያል ካሳ ልክፈልህ እና ሹፊሬ ከእስር ይፈታ !” ብለው የሆስፒታሉ ዶክተሮች መቃወማቸውን ይናገራል። ምክንያታቸው ደግሞ “ጉዳቱ ከፍተኛ በመሆኑ በክፍያው ማነስ የተነሳ ኢንባሲ ቢጠይቀን አደጋ እንወድቃለን” በማለት ዶክተሮች ፈቃደኛ ባለመሆናቸውን ጉዳዩ መጨናገፉን ራያ ጀማል ከኦሮምኛና አረብኛውን ከአማርኛ ጋር እየቀላቀለ በቁጭት አጫውቶኛል።

ትናንት ምሽት ወንድም ራያ ጀማልን ደጋግሞ ስልክ ደውሎ እንድጎበኘው ጠይቆኝ ላነጋግረው ሄድኩ …ጉዳዩን ሰምቶ ብዙዎች ተስፋ ሰጥተነው የነበረው ተስፋ ተሟጦበት አገኘሁት ። ዛሬስ ምን አዲስ ነገር አለ ምን ሆንል አልኩት!
” አይይ አቶ ነቢዩ ትናንትና ዛሬ ሙቀቱም ነው መሰል ወገቤን መላ የተጎዳ አካሌን ይጠዘጥዘኛል፣ ያመኛል፣ ማረፊያ የለኝም ፣ ሜዳ ላይ ለ18 ቀናት ስሰቃይ ማረፊያ ያልሰጡኝ የሚረዱኝ አይመስለኝም ፣ ጉዳየን አሁን አንደዚህ በሜዳ ላይ ሆኘ በፍርድ ቤት ለመከታተል አልችልም!

አቶ ራያ ጀማል በሳውዲ ዓረቢያ አደጋ ከደረሰበት በኋላ

አቶ ራያ ጀማል በሳውዲ ዓረቢያ አደጋ ከደረሰበት በኋላ

እዚህ ላይ ራያ ጀማል አደጋ ከደረሰበት ጊዜ ጀምሮ አይተውት የማያውቁት የሃጅ ኮሚቴ ሃላፊዎችም ሆኑ የጅዳ ቆንስል የት ነበሩ? አልልም ። የጅዳን ኮሚኒቲ ቲኬት ከመጠየቁ በፊት መደረግ የነበረበት ጉዳይ ለምን ክትትል አልተደረገም ? አልልም ! የራያ ጀማል ጉዳይ አይነት እና ከዚያም የከፉ የመብት ጥሰቶች ተፈጽመው ቆንስል መስሪያ ቤቱ እያሸማገለ የጨረሳቸው ጉዳዮች በርካታ ናቸው። ያም ሆኖ ጉዳትን ከግምት ያሰረገባ ሽምግልና ነበር ብሎ ለማናገር እንቸገራለን። ይህ ካልሆነ ደግሞ ቢቀር ይሻላል። የመብት ጥሰትን በተልካሻ ካሳ ከማሸማገል ወደ ተገቢ ህጋዊ ፍርድ ቤት ማድረስ ይቀላልና ቢታሰብበት መልካም ነው ። ይህ ከማድግ ባለፈ እያሸማገሉ ጉዳዩን ሸፋፍኖ ተበዳይን ወደ ሀገር መሸኘት ሊቆም ይገባል ! ትናንት በቆንስል መስሪያ ቤቱ ዙሪያ የምናውቀው ፣ ጩኸን ማስቆም ያልቻልነው ጉዳይ በሽፍንፍንና በግዴለሽነት ዛሬ ሁነኛ ኃላፊ መጥተው ነገሮች እየተስተካከሉ ባለበት ሁኔታ በደል በቆዩት ዲፕሎማቶችና በሰራተኞች በእንዝላልነትና በሽፍንፍን ሲያልፍ ማየት ግን ነፍሴ አትፈቅድም !

በራያ ጀማል ጉዳይ እሱ እንዳለው ወራት የሚጨርሰውን ጉዳዩን እዚህ ሆኖ ለመከታተል ይከብዳል። ማረፊያ የለውምና ለከፋ ችግር ላይ ነው ። ራያ ጀማል ያለው ተጨባጭ አማራጭ አንድም መሄድና ወክልና መላክ ፣ መጠላያ አግኝቶ ጉዳዩን መከታተል ፣ ይህ ካልሆነም የሚሰጡትን ተቀብሎ ወደ ቀየው መቀላቀል ብቻ ነው። በእኒህ ውስብስብ አማራጮች ላይ ብቻውን ይወስን ለማለት የሚከብደው የሚሰጠው ሀሳብ ከችግር ጭንቀቱ አንጻር ይሆናልና ተበዳዩ ይጎዳል። የቆንስል ሃላፊዎችና የሚመለከታቸው በዚህ ረገድ አማራጮችን ከህግ አንጻር ተመልክተውና አዋቂ አመካክረው አስፈላጊውን ድጋፍ ቢያደርጉለት ቤተሰቡን በትኖ ለከፋ አደጋ በተዳረገው ወንድም ነፍስ መታደግ መቻል በምድርም በሰማይ ጽድቁ ለራስ ነው! ስለ ራያ ጀማል የማጠቃለው መብቱ እናስከብርለት ፣ የቻልን እንደ አቅማችን እንርዳው በማለት ነው ፣ የምለው ከዚህ ያለፈ አይደለም !

ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው

የህግ ባለሙያና ጠበቃ ተማም አባቡልጉ

የህግ ባለሙያና ጠበቃ ተማም አባቡልጉ

በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቃገኘው የክስ መዝገብ የተከሰሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በመያዝ የሕግ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው፡፡ ድብደባው የተፈፀመባቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ..ም. እነ አብርሃ ደስታ በነበራቸው የፍርደ ቤት ቀጠሮ ተገኝተው የሚጠበቅባቸውን የሕግ አገልግሎት ሰጥተው ከፍርደ ቤት ከወጡ በኋላ ብሔራዊ አረቄ ፋብሪካ አካባቢ ወደ አዋሳ ለሌላ የህግ አገልግሎት ለመስጠት እያመሩ በነበረበት ወቅት በማያውቁት ግለሰብ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክታል፡፡

ደብዳቢው ግለሰቡ ድብደባ ከፈፀመ በኋላ እሮጦ ለማምለጥ ሲሞክር በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ትብብር የተያዘ ሲሆን፤ በወቅቱም ደብዳቢው የአእምሮ ችግር እንዳለበት ለመምሰል ከሞከረ በኋላ የብአዴን-ኢህአዴግ አባል እንደሆነና 400 ብርም እንደተከፈለው መናገሩን እንዲሁም አዲስ አበባ ለቡ አካባቢ 105 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቶት ቤት እየሰራ እንደሆነ መግለፁን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ጠበቃ ተማም ነገ አዋሳ ላይ ሌላ የነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የፍርድ ቤት ጉዳይ ስላለ ዛሬ የግድ ሄደው ማደር ስለነበረባቸው ደብዳቢውን እንዲለቀቅ አድርገው ወደ አዋሳ ማምራታቸው ታውቋል፡፡

ጠበቃ ተማም ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በተጨማሪ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎችን፣ የተለያዩ ጋዜጠኞችን፣በሀገር ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን እና ሌሎች በርካታ የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ለማኀበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ከጥብቅና አገልግሎት በተጨማሪ በተለያዩ ጋዜጦች የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ይፅፉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ በዚህም ከመንግሥትና ከስርዓቱ ደጋፊዎች ከፍተኛ ጫና እየተደረገባቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡

%d bloggers like this: