ሶስቱ የሰማያዊ ፓርቲ እንስት አባላት በዓለም አቀፍ ደረጃ ዘመቻ እየተደረላቸው ነው
የአሜሪካ መንግስት ኦፊሳላዊ ድረ ገጽ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ጉዳይ አስተባባሪነት በዓለም ላይ ለተመረጡ 20 ሴት የፖለቲካ እስረኞች መካከል ሶስት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ዘመቻና ማስታወሻ እየተደረላቸው ነው፡፡
ከዛሬ 20 ዓመት በፊት ሴቶችን ለማብቃት፣ የጾታ እኩልነትን ለማስፈን እና የልጃ ገረዶችን ሰብዓዊ መብት ለማስጠበቅ የቤጂንግ መርሃ ጉዞ ተቀምጦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በእነዚህ 20 አመታት ልክ ከዓለም ሀገራት በፖለቲካ እስረኝነታቸው የተመረጡ 20 ሴት እስረኞችን ለማሰብ የሚደረገው ዘመቻ መነሻው ይህ መርሃ ጉዞ ነው፡፡
በዚህ መሰረት ከኢትዮጵያ ብሌን መስፍን፣ ንግስት ወንዲፍራው እና ሜሮን አለማየሁ የተካተቱ ሲሆን ከቻይና እንዲሁ ሦስት ሴት የፖለቲካ እስረኞች ተመርጠው እየታወሱ ነው፡፡
http://www.humanrights.gov/freethe20
ምንጭ፡ ነገረ-ኢትዮጵያ
በደብረማርቆስ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ እና በትግራይ ሑመራ የዓረና/መድረክ አባል ተገደሉ
በምስራቅ ጎጃም የሰማያዊ ፓርቲ ፀሐፊ እና ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በተደረገው ምርጫ በደብረማርቆስ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ የነበረው ወጣት ሳሙኤል አወቀ ዓለም ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ማታ ላይ በሁለት ግለሰቦች በተፈፀመበት ከፍተኛ ድብደባ ሆስፒታል ቢገባም ህይወቱ ሊትርፍ አልቻለም፡፡ ወጣቱ ቀደም ሲል ሚያዝያ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. በመንግሥት ደህንነቶችና ፖሊስ አባላት ድብደባ እንደደረሰበት ከነጉዳቱ ለህዝብ ይፋ አድርጎ ነበር፡፡
ከሚያዝያው ድብበደባ በኋላም በተደጋጋሚ የደብረማርቆስ ደህንነት አባላት፣ የከተማው የፖሊስ አዛዥን ጨምሮ የብአዴን/ኢህአዴግ ካድሬዎች ዛቻና ማስፈራሪያ ይፈፅሙበት እንደነበርና ከፖለቲካው እንቅስቃሴ እንዲወጣ አሊያም ሀገር ለቆ እንዲሄድ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ እንደሰጡት በራሱ የማኀበራዊ ሚዲያ ገፆቹ ላይ ይገልፅ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ወጣቱ ይሰጠው የነበረውን ማስፈራሪያና ዛቻም እንደማይቀበልና ሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉንም እንደሚቀጥል በተደጋጋሚ መግለፁን ከራሱ የማኀበራዊ ገፅ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተለይ በግንቦት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደርስበት ዛቻና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ መቀጠሉን እና ከሐሰት ክስ እስከ ግድያ የሚደርስ እርምጃ ሊወስዱበት እንደታሰበ ራሱ በፌስ ቡክ ገፁ የሚከተለውን ገልፆ ነበር፡-
ውድ የደብረማርቆስ ከተማ ኗሪዎች ፤ ሰማያዊ ፓርቲን የመረጣችሁ ከ25,0000 በላይ መራጮች(ኮረጆውን) እርሱት እና በተጨማሪም በ31 ዩኒቨርስቲ የምትገኙ ከ14,000 በላይ ሰማያዊ ፓርቲን የመረጣችሁ ሌሎች ደጋፊዎች እና የኢሕአዴግ አባላትም የማያፍረው ብአዴን / ኢሕአዴግ ድምፅ መቀማቱ ሳያንስ በ21/08/2007 ዓም አፍነው ደብድበው ከሞት መትረፌ ቆጭቷቸው እሰር ቤት ለመወርወር ያለመከሰስ መብቴን እንኳን ተዳፍረው የሀሰት ክሰ እየፈጠሩ ነው!!!” በስልኬ እደተደወለም ያለፍላጎቴ ደሕንነት እያስገደደኝ ይገኛል!!!!! ተገደልሁም ታሠርሁም ፤ ታፈንኩም ነፃነት አይቀርም እና ለማሰረጃነት የደሕንነቶችን ስም፤ ፎቶግራፍ ፤ እና አድራሻ እንዲሁም በሐሠት ምሰክርነት እና ከሳሽነት የተደራጁ አካላት እና ዋና ተወካዮች የደብረማርቆስ ከተማ 04 ቀበሌ አመራሮች እና ፖሊስ ለታሪክ አሰመዘግባለሁ፡፡ ማንኛውም የምከፍለው ዋጋ ለሀገሬ እና ለነፃነት ነው ከታሠርሁም ሕሊናዬ አይታሰርም ከገደሉኝም ትግሌን አደራ በተለይ የኔ ትውልድ አደራ !!!!” አገራችን የወያኔ ዘረኞች ብቻ መፈንጫ መሆን የለባትም፡፡ ትግላችን የነፃነት ጉዟችን ጎርባጣ መድረሻችን ነፃነት ታሪካችን ዘላለማዊ ነው!!!! (ከሳሙኤል አወቀ ዓለም – የሰማያዊ ፓርቲ የደብረ ማርቆስ የሕዝብ ተወካዮች እጩ ተወዳዳሪ)
የ27 ዓመቱ የህግ ባለሙያና የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረው ወጣት ሳሙኤል የቀብር ስነ ስርዓት ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም የትግል አጋሮቹ፣ ጓደኞቹና ዘመዶቹ በተገኙበት በምስራቅ ጎጃም ዞን በጎንቻ ሲሶነሴ ወረዳ ሰቀላ ቀበሌ ግንደወይን አርባይቱ እንሰሳ ቤተ ክርስቲያን ከቀኑ 11፡30 ላይ ተፈፅሟል፡፡ በዕለቱ ማታ ከቀብር መልስ ወደ ደብረማርቆስ ይመለሱ የነበሩ ወዳጆቹና ዘመዶቹ ታግተው እንደነበር የነገር ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡ የወጣት ሳሜኤል አወቀ አሟሟትን በተመለከተ እስካሁን ከመንግሥት በኩል የተሰጠ ምንም ዓይነት ምላሽ የለም፡፡
በተያያዘ ዜና የዓረና መድረክ አባል አቶ ታደሰ አብርሃ በትግራይ ክልል በቃፍታ ሑመራ ማይካድራ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆኑ ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት አካባቢ ሶስት ሰዎች አንቀዋቸው ሞተዋል ብለው ቢሄዱም ህይወታቸው እስከ ሌሊቱ 9፡15 ድረስ እንደነበርና ከዛ በኋላ ህይወታቸው እንዳለፈ የዓረና ፓርቲ መረጃ አመልክቷል፡፡ከዚህ በፊት አቶ ታደሰ ከዓረና/መድረክ ፓርቲ አባልነትና ተሳትፎ እንዲያቆሙ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያና ማስፈራሪያ ከደህነነቶችና ከህወሓት/ኢህአዴግ አመራሮች ይደርሳቸው እንደነበርና ለዚህም አማላጅ ይላክባቸው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
የ48 ዓመቱ አቶ ታደሰ አብርሃ በፖለቲካው ንቁ ተሳትፎ ያላቸው መሆኑን እና እስካሁን ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ታንቀው በተገደሉበት ወቅት በኪሳቸው የነበረው 300 ብር እንዳልተወሰደና ግድያው ፖለቲካዊ ይዘት እንዳለው ተጠቁሟል፡፡ የአቶ ታደሰ አብርሃን ገዳዮችና አሟሟታቸውን በተመለከተ አስከሬናቸው በሑመራ ሆስፒታል ምርመራ እንዲደረግ ቢሞከርም የአካባቢው ፖሊሶችና የኢህአዴግ አመራሮች መከልከላቸውም ታውቋል፡፡ በሶስት ቀናት ልዩነት የሰማያዊ እና የዐረና/መድረክ አመራሮች ተገድለዋል፡፡
ክምርጫ 2007 ዓ.ም. ጋር በተያያዘ በታህሳስ 2007 ዓ.ም. የዓረና/መድረክ አመራር የነበሩት ልጅዓለም ኻልዓዩ ማንነታቸው እስካሁን ባልታወቁ ሰዎች አዲስ አበባ ላይ ሲገደሉ በምርጫው ወቅት የኦፌኮ/መድረክ አባል በአርሲ ኮፈሌ ና በደቡብ እንዲሁ አንድ መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከምርጫ 2007 ዓ.ም. ጋር በተያያዘ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና አባላት ግድያ እስካሁን ባይቆምም፤እስካሁን በጉዳዩ ዙሪያ ከመንግሥት የተሰጠ ምንም ምላሽ የለም፡፡
የኢትዮጵያ 2007 ዓ.ም. ምርጫ ውጤት ተዓማኒነት ከወዲሁ ውግዘትና ትችቶች እየቀረቡበት ነው
ባለፈው ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የተደረገው ሀገር አቀፍ ምርጫ ውጤት በገዥው ኢህአዴግ አሸናፊነት መጠናቀቁን ምርጫ ቦርድ ይፋ ያደረገ ሲሆን፤ እስካሁን ቦርዱ ደረሱኝ ባላቸው ከ547 ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ፤ 440 መቀመጫ ውጤቶች በሙሉ ኢህአዴግ ማሸነፉን ይፋ አድርጓል፡፡ ቀሪዎቹ 107 መቀመጫ ውጤቶች አሸናፊ በቦርዱ ባይገለፅም፤ የኢህአዴግ ደጋፊ መሆኑን በድረ-ገፁ የገለፀው “አይጋፎረም” ገና ምርጫው ሳይጠናቀቅና በይደር የታለፉ ጣቢያዎች እያሉ በምርጫው ዕለት ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት ኢህአዴግ 100 ማሸነፉን ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ ድረ-ገፁ የመድረክ አንጋፋ ተወካዮች ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ እና ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ ሁሉም የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች በመላ ሀገሪቱ ሙሉ ለሙሉ በኢህአዴግ መሸናፋቸውን ይፋ ያደረገውን መረጃ፤ ከሁለት ቀናት በኋላ ሊያነሳ ችሏል፡፡ ምርጫ ቦርድም ለጊዜው በቁጥር ካስቀመጠው መቀመጫ በስተቀር ምርጫው ሳይጠናቀቅ ቀድሞ የኢህአዴግን ማሸነፍ ይፋ ካደረገው አይጋ ፎረም የተለየ መረጃ እስካሁን ሊሰጥ አልቻለም፡፡
በምርጫው ዋዜማ እና ዕለት በተለይም ከገዥው ኢህአዴግ ጋር ጠንካራ ተፎካካሪ የነበሩት የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) እና የሰማያዊ ፓርቲ ታዛቢዎች በተለያዩ የሀገሪቱ ምርጫ ጣቢያዎች በደህንነት እና ፖሊሶችታስረውና ታግተው እንዳይታዘቡ መደረጋቸውን ፓርቲዎቹ ቀድመው ማሳወቃቸው ይታወሳል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫውን ውጤትም ሆነ ሂደቱን እንደማይቀበሉት አስታውቀዋል፡፡ ኢህአዴግ በምርጫ 1997 ዓ.ም. በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ሽንፈት ገጥሞት ስልጣኑን ባይለቅም፤ በምርጫ 2002 ዓ.ም. 99.6 በመቶ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ማግኘቱን ይፋ ካደረገ በኋላ የነበረው የምርጫ ሂደትና ውጤት ላይ በሀገር ውስጥና ከውጭ የተለያዩ ቅሬታዎችን እና ትችቶችን ማስተናገዱ ባይዘነጋም፡፡
ምርጫውን የታዘበው የአፍሪካ ህብረት በሰጠው ጊዜያዊ መግለጫ ታዛቢ ቡድኑ ከታዘባቸው ከ21 በመቶ የማያንሱ የምርጫ ጣቢያዎች ኮሮጆዎች ድምፅ መስጠት ከመጀመሩ በፊት በዶ መሆናቸው ተከፍቶ እንዲታይታዛቢ ቡድኑ ቢጠይቅም፤ በየጣቢያው ያሉ የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚዎች ፈቃደኛ አለመሆናቸውን እና የድምፅ መስጫ ኮሮጆዎቹ ተከታታይነት ያለው ቁልፎች እንዳልነበሩት በመግለፅ ምርጫው ነፃ ነበር ለማለት እንደሚቸገር አስታውቋል፡፡ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያያን ሀገር አቀፍ ምርጫ ሲታዘቡ የነበሩት የአውሮፓ ህብረት እና የአሜሪካው ካርተር ማዕከል ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን እንዳልታዘቡ ታውቋል፡፡
የእሁዱ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በተደረገው ምርጫ ውጤት ግን ከቀድሞው በባሰ 100 % የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ያለምንም አማራጭ ሐሳብ በገዥው ኢህአዴግና አጋሮቹ ሊሞላ እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ውጤቱም የህዝብ ድምፅ ዘረፋና ማጭበርበር እንዲሁም የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ በደረሰው ተፅዕኖ የመጣ እንጂ በነፃ ምርጫ የተገኘ የህዝብ ድጋፍ አይደለም በሚል ከወዲሁ ውግዘትና ትችት ገጥሞታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ውጤቱ የምርጫ ቦርድን ገለልተኛነትንም የበለጠ ጥያቄ ውስጥ ቢከትም፤ ውጤቱን አስመልክቶ ከዥው ፓርቲ በኩል እስካሁን የተሰጠ ይፋ መግለጫ የለም፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ
-ህዝብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ ቀርቧል
9ኙ ፓርቲዎች በትብብር ለሚያዘጋጁትና ሰማያዊ ፓርቲ ለሚያስተባብረው የህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደረገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ ሲቀሰቅሱ እና ታሳሪዎቹን ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ በሄዱበት ወቅት የታሰሩት 6 የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ፡፡
በሌላ በኩል ለነገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ በአብዛኛው የአዲስ አበባ ክፍሎች ስኬታማ ቅስቀሳ መደረጉን የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ገልጸዋል፡፡ይህ በእንዲህ እንዳለ አገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያውያን፤ ህዝቡ በአደባባይ ስብሰባው እንዲሳተፍ በስልክ (በመደወልም ሆነ መልዕክት በመላክ)፣ በማህበራዊ ድህረገጽና ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የበኩላቸውን እንዲያደርጉ፣ ለአንድ ወሩ መርሃ ግብርም ሆነ በሌላ የትግሉ አካል ሁለገብ ድጋፍና ተሳትፎ እንዲያደርጉ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ጥሪ አድርጓል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከቅስቀሳው ጋር በተያያዘ የታሰሩትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ባቀኑበት ወቅት የታሰሩት አቶ ወሮታው ዋሴና አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድም በምሽት መለቀቃቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ እሁድ ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በአዲስ አበባ ቀበና ቤለር የጠሩት ህዝባዊ ስብሰባ በፖሊስ መበተኑ ተገለፀ፡፡