ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ዋስትና ተከለከለ
ከሽብርተኝነት ክስ ነጻ ተብሎ በመደበኛ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንዲከላከል ብይን የተሰጠው የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው የዋስትና ጥያቄው ውድቅ ተደርጎበታል፡፡
የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 13 ቀን 2009 ዓ.ም ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ከቀረበበት የሽብር ክስ ነጻ በማለት ክሱ ወደ መደበኛ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ ተቀይሮ አንቀጽ 257 (ሀ) ላይ የተመለከተውን እንዲከላከል ሲል ብይን መስጠቱ ይታወሳል፡፡
ይህን ተከትሎ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ቋሚ የመኖሪያ አድራሻ እንዳለውና ለአንድ አመት በእስር መቆየቱን በማንሳት አሁን ተከላከል የተባለበት የህግ ክፍል የዋስትና መብት እንደማይከለክል ጠቅሶ የዋስ መብቱ እንዲከበርለት ታህሳስ 19 ቀን 2009 ዓ.ም ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ነበር፡፡ በዕለቱ አቃቤ ህግ ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ከሀገር ሊወጣ ስለሚችል የዋስትና ጥያቄው ውድቅ እንዲደረግለት ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ታህሳስ 25 ቀን 2009 ዓ.ም በተነሳው የዋስትና ጥያቄ ላይ መርምሮ ብይን ሰጥቷል፡፡ በዚህ መሰረት ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ‹‹ከሀገር ሊወጣ እንደሚችል ግምት የተወሰደ በመሆኑ›› የዋስትና ጥያቄው ተቀባይነት አላገኘም ሲል ፍርድ ቤቱ ዋስትና ከልክሎታል፡፡ ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ከሀገር ሊወጣ ይችላል የሚለውን ግምት ለመውሰድ የቀረበለት ማስረጃ ስለመኖሩ በብይኑ ላይ አላመለከተም፤ አቃቤ ህግ ተቃውሞውን ባስመዘገበበት ወቅትም ተቃውሞውን በማስረጃ አስደግፎ አላቀረበም ነበር፡፡
‹‹ተከሳሹ ተከላከል የተባለበት የህግ አንቀጽ በመርህ ደረጃ ዋስትና ባያስከለክልም፣ በሁኔታ የሚከለከልበት ጊዜ ግን ስለመኖሩ ተመልክቷል፡፡ እኛም ይህን ተከሳሹ ከሀገር ሊወጣ ይችላል የሚለውን ሁኔታ አይተን በሙሉ ድምጽ ተከሳሹ ዋስትናው ይነፈግ ብለን ወስነናል›› ብሏል ችሎቱ የዳኞችን ውሳኔ በተመለከተ ሲገልጽ፡፡
ፍርድ ቤቱም መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ሌላ ተለዋጭ ቀጠሮ ለየካቲት 7 ቀን 2009 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፦ EHRP
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል
*ጌታቸው ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል
ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ለፍርድ ቤት ሰጥቷል፡፡
አርብ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ መሆኑን ተከትሎ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ በችሎቱ ተጠይቆ ‹‹የቀረበብኝን የወንጀል ድርጊት አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛም አይደለሁም›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡
መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሹ ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያን መርምሮ ብይን ለመስጠት ሲሆን፣ ጉዳዩን የሚያየው 14ኛ ወንጀል ችሎት የተከሳሹን መቃወሚያ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡ ችሎቱ የመቃወሚያ ብይኑን በንባብ ከማሰማት ይልቅ በጥቅሉ “የቀረበውን መቃወሚያ ውድቅ አድርገነዋል” ሲል ለተከሳሹ ገልጹዋል፡፡
”በአጭሩ የክስ አቀራረቡ ከተጠቀሰው የወንጀሉ ክፍል አለመጣጣምን በተመለከተ የቀረበው መቃወሚያ አልተቀበልነውም፤ ዝርዘሩን ማስረጃ ስንመዝን እናየዋለን፡፡ የቀረበው ክስ ግልጽ አይደለም የተባለውን በተመለከተም፣ ክሱን ስንመለከተው በተብራራ መልኩ የቀረበ መሆኑን ስለተገነዘብን ውድቅ አድርገነዋል” በማለት የመቃወሚያው ውድቅ መሆንን ችሎቱ በቃል ለተከሳሹ አስረድቷል፡፡
ችሎቱ ተከሳሹ የእምነት ክህደት ቃሉን ሲሰጥ ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ጥፋተኛም አይደለሁም ማለቱን ተከትሎ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህጉ በበኩሉ ከክስ ማመልከቻ ጋር ያያያዘው የሰነድ ማስረጃ ተመርምሮ ብይን እንዲሰጥለት አመልክቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም የሰነድ ማስረጃውን መርምሮ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ ከሳሽ ያቀረበበት የሰው ማስረጃ እንደሌለ በችሎቱ ተገልጹዋል፡፡
ምንጭ፡- EHRP
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ባቀረበው መቃወሚያ ላይ አቃቤ ህግ መልስ ሰጥቷል
ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም ላቀረበው የክስ መቃወሚያ አቃቤ ህግ መልስ ሰጥቷል፡፡
የፌደራል አቃቤ ህግ ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ በተከሳሹ የክስ መቃወሚያ ላይ ለተነሱ ነጥቦች በጽሁፍ መልሱን ለችሎቱ አስገብቷል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው አቃቤ ህግ ያቀረበበት ክስ ‹‹በማናቸውም መልኩ በሽብር ተግባር መሳተፍ›› የሚለው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመን ድርጅት ስም መጥራት፣ የሽብር ድርጅቱ በሚጠቀምበት ሚዲያ መጠቀም ወይም የሽብር ድርጅት አባል ነው የተባለን ሰው ለሽብር ድርጅቱ አንዳችም ፋይዳ በሌለው ነገር ላይ ማነጋገር ሁሉ ይጨምራል በሚል ተለጥጦ መቅረብ እንደሌለበት ላቀረበው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ድንጋጌውና የወንጀል ዝርዝሩ በሚመጣጠን መልኩ ክሱ ቀርቧል ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡ ስለሆነም መቃወሚያው በአግባቡ ያልቀረበ በመሆኑ ውድቅ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡
ተከሳሽ አቃቤ ህግ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ስለነበሩ ክስተቶች የሽብር ድርጅት አመራር ናቸው ላላቸው ሰዎች መረጃ ማስተላለፍን በሽብር ድርጅቱ ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ስህተት ብቻ ሳይሆን ከህጉ አላማም በእጅጉ የራቀ ነው፣ የህጋዊነት መርህንም የተከተለ አይደለም በሚል ላቀረበው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ክሱ የህጋዊነትን መርህ ባከበረ መልኩ የቀረበ መሆኑን በመጥቀስ የወንጀል ድርጊቱ በማስረጃ የሚረጋገጥ ይሆናል በማለት መቃወሚያው ውድቅ ይደረግልኝ ሲል አመልክቷል፡፡
አንድ ድርጊት ወንጀል ነው አይደለም የሚለው ፍ/ቤት ማስረጃ ከሰማ በኋላ የሚወሰን ስለመሆኑ ጥር 27 ቀን 2007 ዓ.ም ፌደራል ሰበር ሰሚ ችሎት አስገዳጅ ውሳኔ መስጠቱን በማስታወስ የወንጀል ድርጊቱ ላይ የተነሳው መቃወሚያ ከማስረጃ መሰማት በፊት ሊነሳ የማይገባው ነጥብ ስለሆነ ውድቅ ይደረግልኝ ብሏል፡፡ አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ የወ/መ/ሥ/ሥ/ሕጉ አንቀጽ 111 እና 112 መሰረት አድርጎ ተሟልቶ መቅረቡንም በመልሱ ላይ ገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ እንደተቀበለ ከመጠቀሱ በቀር ተልዕኮው ምን እንደሆነ፣ መቼ፣ ከማን እና በምን አይነት መንገድ ተልዕኮውን እንደተቀበለ ከሳሽ ግልጽ አላደረገም በሚል ለጠቀሰው መቃወሚያ፣ አቃቤ ህግ ‹‹ተልዕኮ መቀበል ሲባል የሽብር ቡድኑ አላማን በመቀበል የድርጅቱን አላማ በማራመድ በመንግስት ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ህብረተሰቡን ለማስፈራራትና የሀገሪቱን መሰረታዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ህገ-መንግስታዊ፣ ኢኮኖሚያዊ…ተቋማትን ለማናጋትና ለማፈራረስ በሚንቀሳቀስ የሽብር ቡድን ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ›› እንደሆነ ገልጾ የመቃወሚያው መቅረብ የህግ መሰረት የሌለው በመሆኑ ውድቅ ይደረግልኝ ሲል አመልክቷል፡፡
አቃቤ ህግ በአጠቃላይ ያቀረብኩት ክስ ህጉን መሰረት ያደረገና የክስ ዝረዝርና የህግ ድንጋጌውን ባጣጣመና በተገቢው መንገድ የቀረበ ስለሆነ በከሳሽ በኩል የቀረበው መቃወሚያ ውድቅ ተደርጎ ክርክራችንን እንድንቀጥል ሲል ጠይቋል፡፡
ችሎቱ ተከሳሹ ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ላይ አቃቤ ህግ የሰጠውን መልስ አገናዝቦ ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በዛሬው የችሎት ውሎ 14ኛ ወንጀል ችሎት ቦታው በሙሉ በተከሳሾች ተይዟል በሚል ችሎቱን ለመታደም የቻለ የለም፡፡
ምንጭ፡- EHRP
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የቀረበበት ክስ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት አመልክቷል
ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ክሱ ተሰርዞለት በነጻ እንዲሰናበት በክስ መቃወሚያው አምልክቷል፡፡
ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው አራት ገጽ ያለው የክስ መቃወሚያውን ለችሎቱ አስገብቷል፡፡
ተከሳሹ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀጽ 7(1)ን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበበት ክስ “በማናቸውም መልኩ በሽብር ተግባር መሳተፍ” የሚለው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመን ድርጅት ስም መጥራት፣ የሽብር ድርጅቱ በሚጠቀምበት ሚዲያ መጠቀም ወይም የሽብር ድርጅት አባል ነው የተባለን ሰው ለሽብር ድርጅቱ አንዳችም ፋይዳ በሌለው ነገር ላይ ማነጋገር ሁሉ ይጨምራል በሚል ተለጥጦ መቅረብ እንደሌለበት በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡
ተከሳሽ አቃቤ ህግ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ስለነበሩ ክስተቶች የሽብር ድርጅት አመራር ናቸው ላላቸው ሰዎች መረጃ ማስተላለፍን በሽብር ድርጅቱ ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ስህተት ብቻ ሳይሆን ከህጉ አላማም በእጅጉ የራቀ ነው ሲል ተከሳሹ ተቃውሟል፡፡
ስለሆነም የአዋጁን አንቀጽ 7(1) ጠቅሶ ክሱን ማቅረብ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕጉ አንቀጽ 112 ላይ በወንጀል ጉዳይ በሚቀርብ ክስ ስለ ወንጀሉ እና የወንጀሉ ሁኔታ ስለሚሰጠው ዝርዝር ወንጀለኛው የፈጸመውን ተግባር ወንጀል ከሚያደርገው ሕግ አነጋገር ጋር የተቀራረበ መሆን አለበት የሚለውን አስገዳጅ ድንጋጌ የሚጥስ በመሆኑ የአዋጁ አንቀጽ መጠቀሱ አግባብ አይደለም ተብሎ ክሱ እንዲሰረዝለት አመልክቷል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው በሁለተኛነት ያቀረበው መቃወሚያ የህጋዊነት መርህን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ ህገ-ወጥነቱ በህግ ያልተደነገገን ድርጊት ወይም ግድፈት እንደወንጀል ሊቆጥረውና ቅጣት ሊወስንበት እንደማይገባ በማስታወስ በክሱ ዝርዝር ላይ የተመለከቱ በህግ ወንጀል ናቸው ተብለው ያልተደነገጉ ድርጊቶችን ጠቅሶ ክሱ እንዲሰረዝለት የሚጠይቀውን መቃወሚያ አስገብቷል፡፡
ተከሳሹ በሦስተኝነት ያቀረበው የመቃወሚያ ነጥብ የተከሰሰበትን ወንጀል ለይቶ በማወቅ መልስ ለመስጠት እንዲያስችለው ግልጽ ሊሆኑለት የሚገቡ ነጥቦችን በመጥቀስ ነው፡፡ በዚህ መቃወሚያ ስር ተከሳሹ ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ እንደተቀበለ ከመጠቀሱ በቀር ተልዕኮው ምን እንደሆነ፣ መቼ፣ ከማን እና በምን አይነት መንገድ ተልዕኮውን እንደተቀበለ ከሳሽ ግልጽ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡ ተከሳሹ ‹‹የሽብር ቡድኑ በሚጠቀምበት ሚዲያ›› በሚል የቀረበበት ክስ በህግ ቋንቋ ምን ማለት እንደሆነም አልተገለጸም ሲል ጠቃውሟል፡፡
በመሆኑም ከሳሽ እነዚህና ሌሎች በመቃወሚያው ላይ የተመለከቱ ነጥቦችን ግልጽ እንዲያደርግ፣ ይህን ማድረግ የማይችል ከሆነ ግን ክሱ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት ተከሳሹ ለችሎቱ በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡
ችሎቱ አቃቤ ህግ ተከሳሹ ያቀረበውን የክስ መቃወሚያ ተመልክቶ መልስ እንዲሰጥበት ለመጠባበቅ ለሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡-EHRP
በጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው የሽብር ክስ በንባብ ተሰምቷል
*ተከሳሹ ጥቁር ልብስ ለብሰሃል በሚል በቀጠሮው ሰዓት አለመቅረቡ ታውቋል
የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በሆነው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. የመሰረተው የሽብር ክስ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡
ተከሳሹ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርቦ ክሱ ሊነበብለት የነበር ቢሆንም ከጠበቃው ጋር ሳይመካከር ክሱ እንዲነበብለት እንደማይፈልግ በመግለጹ በቀጠሮ ሰንብቶ ዛሬ ተነቦለታል፡፡ ከክስ ዝርዝሩ መረዳት እንደተቻለው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው ክስ የጸረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ሆኗል፡፡
አቃቤ ህግ በክሱ ላይ እንዳመለከተው ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል ጠቅሷል፡፡
ተከሳሹ ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡
ችሎቱ ክሱን በንባብ አሰምቶ ሲያጠናቅቅ በተከሳሹ ላይ የተጠቀሱ የአቃቤ ህግ የማስረጃ ዝርዝሮችን በተመለከተ እንደገለጸው፣ ተከሳሹ የተጠቀሰበት ማስረጃ የሰነድ ማስረጃ ብቻ መሆኑ ተገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኝ ሲሆን፣ በዛሬው የችሎት ቀጠሮ በጠዋት እንዲቀርብ የሚል ቢሆንም የእስር ቤቱ አስተዳደር ‹‹ጥቁር ልብስ ለብሰህ ፍርድ ቤት መሄድ አትችልም›› በሚል ጠዋት ሳያቀርቡት ከቆዩ በኋላ ከሰዓት ሊያቀርቡት ችለዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሽ የክስ መቃወሚያን ለመቀበል ለሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- EHRP