የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ታሰረ
ስዩም ተሾመ
በአምቦ ዩኒቨርስቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ወሊሶ ግቢ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ታሰረ፡፡ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ከሚኖርበትና ከሚሰራበት ወሊሶ ከተማ ዛሬ ቅዳሜ መስከረም 21 ቀን 2009 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ መታሰሩ ተጠቁሟል፡፡ ስዩም ተሾመ በአምቦ ዩኒቨርስቲ ወሊሶ ግቢ የማናጅመንት ትምህርት ክፍል ኃላፊ እና መምህር ሲሆን፤ ከማኀበራዊ ሚዲያ በተጨማሪ በ ”ኢትዮቲንክታንክ” እና የገዥው ስርዓት ደጋፊ እንደሆነ በሚታወቀው ”ሆርንአፌይርስ” ድረ-ገፅ ጭምር በመፃፍ ይታወቃል፡፡
በተለይ ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በመንግሥት እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው አለመግባባት ችግሮች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ እና ሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ መፍትሄ ሊሆኑ ይችላሉ ያላቸውን ምክረ ሐሳቦችን በመሰንዘርም ይታወቃል፡፡
10ኛ ወሩን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በአማራ እና በደቡብ ኮንሶ ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች መቀጠላቸውን ተከትሎ ከ820 ያላነሱ ሰላማዊ ዜጎች በፀጥታ ኃይሉ ወታደራዊ ርምጃ ሲገደሉ፤ በሺህዎች የሚቆጠሩ ቆስለው፣ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ታፍነው ታስረዋል፡፡ ከተገደሉ፣ ከቆሰሉና ከታሰሩት መካከል ህፃናት እና አዛውንት፣ መምህራን፣ ጋዜጠኞችና ብሎገሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና ተማሪዎች ይገኙበታል፡፡ በተለይ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በተለያዩ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ከተሞችና ወረዳዎች የመንግሥት ግድያና እስር እንደቀጠለ ነው፡፡
በደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ
በባህር ዳር በአበባ እርሻዎችና በሌሎች ንብረቶች ውድመት ደርሷል
– የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ አሳስቦኛል አለ
በአማራ ክልል በደቡብ ጎንደር ዞን ዋና ከተማ ደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት በደረሰ ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ፡፡ የመከላከያ ሠራዊት እስረኞች እንዳያመልጡ ዙሪያውን ከቦ እንደነበርና ሊያመልጡ የነበሩ በርካታ እስረኞች መሞታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የእሳት አደጋው የተከሰተው ሐሙስ ነሐሴ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ እስረኞቹ ከአደጋው ለማምለጥ መሞከራቸውን አስረድተዋል፡፡ ይሁን እንጂ አካባቢውን በፍጥነት የከበበው የመከላከያ ሠራዊት እስረኞቹ እንዳያመልጡ ሲተኩስ እንደነበር ተናግረዋል፡፡
በእሳት አደጋው ሳቢያ ከፍተኛ ጉዳት በማረሚያ ቤቱ ላይ መድረሱንና ሊያመልጡ በነበሩ እስረኞች ላይም ጉዳት እንደደረሰ ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የደቡብ ጎንደር ማረሚያ ቤቶች መምርያ ኃላፊ ምክትል ኮማንደር መንጌ ከበደ ቃጠሎው የተነሳው በኤሌክትሪክ መስመሮች መገናኘት መሆኑን ገልጸው፣ ሊያመልጡ የነበሩ ሁለት እስረኞች መገደላቸውንና ከእስረኞች ደግሞ ሁለት መቁሰላቸውን አስረድተዋል፡፡
በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተስፋፋ የሚገኘው አመፅ፣ ከመንግሥት ጋር ቁርኝት አላቸው በተባሉ የግል ባለሀብቶች ንብረቶችና የሕዝብ አገልግሎት መስጫ ተቋማት ላይ ያነጣጠረ ጉዳት እያደረሰ መሆኑም ተገልጿል፡፡
ኢስመራልዳ (Esmeralda Farms) የተባለው በባህር ዳር የሚገኘው የኔዘርላንድ ባለሀብቶች የአበባ እርሻ በእሳት ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡
መቀመጫውን በኔዘርላንድ ያደረገው የአበባ ኩባንያው ዋና ቢሮ ባወጣው መግለጫ፣ በፖለቲካ ተቃውሞው ምክንያት በባህር ዳር የሚገኘው የአበባ እርሻ (ኮንዶር ፋርም) በእሳት ሙሉ በሙሉ መውደሙንና የኩባንያው አጠቃላይ ኢንቨስትመንት አሥር ሚሊዮን ዩሮ እንደሆነም አስታውሷል፡፡
በኢትዮጵያ ከሚገኘው ቢሮ ጋር መገናኘት አለመቻሉን የሚገልጸው መግለጫው፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጃችን በቀውሱ ምክንያት ከአካባቢው በመልቀቃቸው መረጃዎችን ማግኘት አልተቻለም፤›› ብሏል፡፡
በመንግሥት ላይ የተነሳው ተቃውሞ በአካባቢው በሚገኙ የአበባ እርሻዎች ላይ ጉዳት ማድረስ መቀጠሉንና አሥር ያህል የአበባ እርሻዎች መቃጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ኮንዶር ፋርም የተባለው የአበባ እርሻ ሲቃጠል በአካባቢው የመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች የነበሩ ቢሆንም፣ ጉዳቱን ያደረሱት ከፀጥታ ኃይሎች ቁጥር በብዛት የሚበልጡ በመሆናቸው ማዳን አለመቻሉን ኩባንያው ገልጿል፡፡
መጋዘኖች፣ የማቀዝቀዣ ክፍሎች፣ ትራክተሮች፣ የጭነት ተሽከርካሪዎች፣ ኮንቴይነሮችና ማሸጊያዎች በሙሉ በእሳት መውደማቸውን አስታውቋል፡፡
‹‹ሁሉም ጠፍቷል፡፡ የአሥር ሚሊዮን ዩሮ ኢንቨስትመንትና የረጅም ዓመታት ጥረት በአንድ ቀን ወድሟል፤›› ሲል በመግለጫው የደረሰውን ጉዳት አመልክቷል፡፡
ሌላው በየመኑ ባለሀብት መሐመድ አልካሚን የተቋቋመውና ከ500 በላይ ሠራተኞች የነበረው የአበባ እርሻ ይገኝበታል፡፡
ለባህር ዳር ከተማ የውኃ አቅርቦት ምንጭ የሆነው እንፍራንዝ ከተማ አካባቢ የሚገኘው የጥቁር ውኃ የውኃ ማጠራቀሚያ ጋንም ቃጠሎ ደርሶበታል፡፡ ይህም በከተማዋና በአካባቢዋ የውኃ አቅርቦት ላይ እጥረት እንደሚያስከትል እየተነገረ ነው፡፡
በተያያዘ ዜና በክልሉ ውስጥ ያለው ተቃውሞ እየተባባሰና በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ የሚደርሰው ጉዳት እየጨመረ መምጣቱን መረጃዎች እያሳዩ ነው፡፡
በተለይም ማክሰኞ ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትሩ በክልሉ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ ለማስቆም የፀጥታ ኃይሉ ሕግ እንዲያስከብር ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን ከገለጹ ጀምሮ ሰዎች መሞታቸውን፣ የዘር ጥቃት ተፈጸመባቸው የተባሉ ደግሞ ወደ ጎረቤት አገር እየተሰደዱ መሆናቸው እየተገለጸ ነው፡፡
በተለይ በአምባ ጊዮርጊስ፣ በደብረ ታቦር፣ በመተማ ዮሐንስና በአጎራባች አካባቢዎች የሰው ሕይወት መጥፋቱን የሚገልጹ ቁጥሮችም እየጨመሩ ስለመውጣታቸው መረጃዎች እየጠቆሙ ይገኛል፡፡ ነገር ግን በመንግሥት በኩል እስካሁን ምንም ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልተሰጠም፡፡
ሪፖርተር ከምንጮች ማረጋገጥ እንደቻለው በክልሉ የተለያዩ ከተሞች የመከላከያ ሠራዊት እየገባ ሲሆን፣ የከባድ መሣሪያ ተሽከርካሪዎች መታየታቸውን ለማወቅ ችሏል፡፡
የአማራ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን፣ በክልሉ ምዕራባዊ አካባቢዎች ሁከት መከሰቱን ተናግረዋል፡፡ በአንዳንድ ፀረ ሰላም ኃይሎች የተነዛ መረጃ ሕዝቡን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ መምራቱንና በተፈጠረው ሁከትም በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ እየተከሰተ ያለው ግጭት እያሳሰበው መምጣቱን ጠቁሞ፣ ሁሉም ወገኖች ከማንኛውም ግጭት እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የኮሚሽኑ ዋና ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ ዓርብ ነሐሴ 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ ‹‹በአገሪቱ የማኅበራዊ ፖለቲካው የሰው ሕይወት ማጥፋት፣ በንብረቶች ላይ ውድመት ማስከተል፣ እንዲሁም የቴሌኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት እስከማቋረጥ ደረጃ መድረሱ አሳሳቢ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ሊቀመንበሯ አክለው ሁሉም ወገኖች ወደ ሰላማዊ ሁኔታ በማመዘን ለሕግ መከበር እንዲተጉ፣ ሰላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብትና የዴሞክራሲ ባህልና መርሆችን እንዲያከብሩ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ
በአዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ እስረኞች ህይወት አለፈ
(አዲስ ሚዲያ)ዛሬ ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት ቃጠሎ ከ25 ያላነሱ እስረኞች መሞታቸው ተጠቆመ፡፡ በጥበቃ ላይ የነበሩ ወታደሮችም ከእሳቱ ለማለጥ የሞከሩ እስረኞች ላይ ሲተኩሱ እንደነበር ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
ከቃጠሎው በፊት በነበረው ተኩስ ምን ያህል እስረኞች ላይ ጉዳት እንደደረሰ እስካሁን ማረጋገጥ ባይቻልም፤ በነጋታው ጠዋት በነበረው የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ ሰዎች መሞታቸውን ከቅዱስ ጳውሎስ፣ ሜክሲኮ በሚገኘው ፖሊስ ፣ ጥሩነሽ ቤጂንግ እና የካቲት 12 ሆስፒታል ምንጮች ለማወቅ ተችሏል፡፡ በቃጠሎው ጉዳት የደረሰባቸውና በህይወት የተረፉትም አብዛኞቹ ፖሊስ ሆስፒታልና የካቲት 12 ሆስፒታል በጥበቃ ስር ሆነው ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡
በወህኒ ቤቱ ታስረው ከሚገኙት መካከል ስመጥር እና ህዝባዊ ተቀባይነት ያላቸው በርካታ የፖለቲካ እስረኞች ያሉበት ሲሆን በተለይም፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ፖለቲከኞች፣ የመብት አራማጆች እና ጋዜጠኞች እንደሚገኙበት ይታወቃል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ብቻ ከአዲስ አበባ አቃቂ ከሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በተጨማሪ በርካታ የፖለቲካ እስረኞች የሚገኙባቸው ጎንደር፣ አምቦና ደብረ ታቦር ወህኒ ቤት በተመሳሳይ መልኩ የእሳት አደጋ ሰለባ መሆናቸው አይዘነጋም፡፡ በነበሩ አደጋዎች መንስኤ እና ጉዳትን በተመለከተ የሚመለከተው የመንግሥት አካልም ከመግለፅ መቆጠቡ ይታወቃል፡፡
በተለይ የአቃቂ ቂሊንጦውን እሳት ቃጠሎ ተከትሎ በርካታ የታሳሪ ቤተሰቦች፣ ወዳጆች እና ደጋፊዎች ስጋት እንዳደረባቸው በተለያየ መድረክ ከመግለፅ በተጨማሪ በአዲስ አበባና አጎራባች አካባቢ ያሉ ሰዎች የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለማጣራት ሙከራ ቢያደርጉም በወህኒ ቤቱ አስተዳደር እንዳልተፈቀደ ተረጋግጧል፡፡ በወህኒ ቤቱ የታሰሩ ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ ከተለያዩ የክልል ከተሞች የመጡ ሰዎችም ወደ እስር ቤቱ ግቢም ሆነ ከግቢ ውጭ በቅርብ ርቀት እንዳይጠጉ በመከልከላቸው ወደየመጡበት መመለሳቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በአደጋው የደረሰውን ጉዳትና ምክንያት በተመለከተ የወህኒ ቤቱ አስተዳደርም ሆነ መንግሥት እስካሁን የሰጡት መረጃ የለም፡፡ ይሁን እንጂ የተለያዩ ሰዎች አደጋው በመንግሥት ሆን ተብሎ የተቀነባበረና የፖለቲካ እስረኞችን ለመጉዳት የታሰበ የገዥው ስርዓት የተለመደ ስልት እንደሆነ የሚገልፁ ቢኖሩም፤ ስለ አደጋውና አጠቃላይ መረጃ ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት ለማወቅ አልተቻለም፡፡
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል፤ በኦሮሚያ ኢኮኖሚ ተኮር ተቃውሞ እንደሚጀመር ይፋ ተደረገ
ብስራት ወልደሚካኤል
(አዲስ ሚዲያ)የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ አድርጎ በጎንደር ፋሲል ከተማ የተጀመረው ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የተለያዩ የሰሜን እና ደቡብ ጎንደር ወረዳና ከተሞችን ጨምሮ ወደ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም እንዲሁም ወደ ሰሜን ወሎ መቄት እና ሸዋ ሮቢት መስፋፋቱን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡
በተለይ ነሐሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ጎጃም ፍኖተ ሰላም ከተማ፣ ነሐሴ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ቡሬ ወምበራ ወረዳ ቡሬ ከተማ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር በተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ተቃውሞዎች እና የመንግሥት የኃይል ርምጃዎችም የቀጠሉ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡
በጎንደር፣ ባህርዳር እና ደብረማርቆስ ከተሞች ከቤት ያለመውጣት ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች የተደረጉ ሲሆን ከነሐሴ 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ በተመሳሳይ ምልኩ በደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር ከተማ ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ እንደሚደረግ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በአማራ ክልል ባሉ ሰሞንኛ ተቃውሞች በተለይ በማክሰኝት፡በገደብዬ፡በእንፍራንዝ፣ በአብደራፊ፣ በአርማጭሆ፣ በፍኖተ ሰላም፡ቡሬ፡ ጅጋ እና ማንኩሳ በተባሉ ወረዳዎች ህዝባዊ ተቃውሞዎች የበረቱባቸው መሆኑን ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡ በነኚህ ስፍራዎች የነበሩ ተቃውሞች መካከልም የተወሰኑ በማኀበራዊ ሚዲያዎች ሲሰራጩ መዋላቸውን ለመታዘብ ተችሏል፡፡
በነበሩ የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞች ሁለት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት መገደላቸው የተጠቆሙ ሲሆን፤ በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች በነበሩ ተቃውሞች ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በኦሮሚያ ክልልም ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞች የቀጠሉ ሲሆን፤ በዚህም በምዕራብ ሐረርጌ መሰላ ወረዳ በሚገኙ ዋልተሲስ እና ጎሮ በተባሉ መንደሮች በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ አራት ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ መገደላቸው ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሀገሪቱ ያለውን የመንግሥትን ግድያ፣ እስርና እና አፋና በመቃወማቸው በአዲስ አበባ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች በተለይም እነ አቶ በቀለ ገርባ በሀገሪቱ ከነሐሴ 19-21 ቀን 2008 ዓ.ም. ብሔራዊ የሀዘን ቀን በሚል ታስቦ እንዲውል ያደረጉት ጥሪ ከወዲሁ በተለያዩ ደጋፊዎቻቸው ተግባራዊ መደረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡
የመንግሥት የኃይል ርምጅና ግፍ በመቃወም በሚደረግ ብሔራዊ የሀዘን ቀንም ፀጉር መላጨት፣ ጥቁር ልብስ መልበስ፣ ጥቁር ባንድራ(ጨርቅ) ማውለብለብ፣ ሻማ ማብራት፣ በተቃውሞ ትግሉ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቤተሰቦችን መጎብኘት እና ተሰብስቦ ህዝባዊ ውይይት በማካሄድ እንዲተገበር ጥሪ ማስተላለፋቸውን ተከትሎ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ባሉ ዜጎች ከወዲሁ ተግባራዊ መደሩ የሚያመለክቱ የተለያዩ ምስሎች በማኀበራዊ ሚዲያዎች ላይ መሰራጨታቸውን ማየት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ ካለው የፖለቲካና ማኀበራዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ከጳጉሜ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞችም እንደሚተገበሩ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች እና የመብት አራማጆች ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞው ምን ላይ እንደሚያተኩር በዝርዝር የተቀመጠ ነገር ባይኖርም፤ ወደፊት ይፋ እንደሚደረግ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡
በታቀደው መሰረት በኦሮሚያ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ መንግሥት በክፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪ እጥረትና አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ይጠበቃል፡፡ በተለይም መንግሥት ከክልሉ በከፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪና የሀገሪቱ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የሆኑት እንደ ቡና፣ የጫት፣ የአበባ፣ የቁም እንሰሳትና፣ የቆዳና ሌጦ እንዲሁም የምግብ ነክ የሆኑ የብግርና ምርቶች እንዲሁም ወርቅና የመሳሰሉ የማዕድን ሃብቶች ከክልሉ እንዳይወጡና ወደ ማዕከላዊም ሆነ የክልሉ ገበያ ንግድ ላይ የማይውሉ ከሆነ ምን አልባትም በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ፈተና በመንግሥት ላይ ሊደርስ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡
የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ በቀጣይ ወደሌሎች ክልሎች በተለይም አማራ እና ደቡብ ክልል የሚዛመት ከሆነ ደግሞ የመንግሥት 90% የገቢ ምንጭ በማድረቅ ስርዓቱን ሙሉ ለሙሉ አደጋ ላይ እንደሚጥለው ይገመታል፡፡ በተለይ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ብቻ የሀገሪቱን 54% የሆነውን ህዝብ ቁጥር እንደሚሸፍኑ እና ከ65% የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪና የገቢ ምንጭም መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ከባለፈው ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ የተቀጣጠለው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መላው ኦሮሚያ ክልልን በማዳረስ፤ ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አማራ ክልል ተዛምቷል፡፡ በሁለቱም ክልሎች ዘገባው እስከተጠናቀረበት ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞዎቹ በተለያዩ ወረዳዎችና ከተሞች ቀጥሏል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በሁለቱም ክልሎች ባሉ የተለያዩ ቦታዎች መደበኛ የመንግሥት ስራን ጨምሮ የተለያዩ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋቶች እየታዩ ነው፡፡
አስረኛ ወሩን ባስቀጠረው ህዝባዊ ተቃውሞ በሁለቱም ክልሎች ከ650 በላይ ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ ሲገደሉ፣ ከ 1,250 ያላነሱ ዜጎች ቆስለው በግምት ከ35,000 በላይ ሰዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉ እና የቆሰሉ ሰዎች በተለያየ ጊዜ ስማቸውና ምስላቸው በሰፊው በማኀበራዊ ሚዲያ እየተገለፀ ይገኛል፡፡ በሁለቱም የኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የወጣው ህዝብ አንዱ ለሌላው በተለያዩ ጊዜና ቦታ ያሳዩት የርስ በርስ አጋርነት፤ መንግሥትን ከፍተኛ ድንጋጤ ላይ እንደጣለው ባለስልጣናቱ በስራቸው ባሉ መገናኛ ብዙኃን ሲናገሩ የተደመጡ ሲሆን፤ በዚህም ስጋት እንዳደረባቸው ባለስልጣናቱና ደጋፊዎቻቸው በይፋ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎችና ከሚሰነዝሯቸው አስተያየቶች መረዳት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ፤የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ”የጋራ ልማት የተቀናጀ ማስተር ፕላን” በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ገበሬዎች የሚያፈናቅልና ለጎዳና ህይወት የሚዳርግ ነው በሚል ቀደም ሲል የነበረውን ተቃው ከዓመት በኋላ በማገርሸት በምዕራብ ሸዋ ጊንጪ ከተማ መጀመሩ ይታወቃል፡፡ በአማራ ክልል ደግሞ የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ ህዝባዊ ወኪሌ ኮሚቴ አባላት ላይ መንግሥት በሌሊት በመኖሪያቸው አካባቢ የፀጥታ ኃይሎችን በመላክ የኃይል ርምጃ መውሰዱን ተከትሎ በጎንደር ከተማ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ ስለደረሱ አጠቃላይ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶች በተመለከተ በመንግሥት ጉዳዩን ለመሸፋፈን ከመሞከር በዘለለ ትክክለኛውን ቁጥርና የጉዳት መጠለን ለመናገር አልደፈረም፡፡ ቀደም ሲል ሀገር በቀል በሆነው የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ) እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች በሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች (HRW) አማካኝነት በተወሰኑ ወረዳዎችና አካባቢዎች የተደረጉ ምርመራዎች ይፋ ከመደረጋቸው በስተቀር አጠቃላይ በደረሱ የሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጉዳቶች የተደረገ ምርመራም ሆነ ሪፖርት የለም፡፡ ይህን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ምት ኮሚሽን ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ እንዲደረግ በይፋ ጥያቄ ቢያቀርብም በስልጣን ላይ ያለው መንግሥት በበኩሉ የመንግሥታቱን ድርጅት ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ምላሽ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
በጎንደር የሰላማዊ ሰው ግድያ የቀጠለ ሲሆን፤ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተጠርቷል
(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ ነሐሴ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በአማራ ክልል ጎንደር ከተማ መንግሥት ሰላማዊ ዜጎችን ተኩሶ 1 ወጣት መግደሉን ተከትሎ ዳግም ህዝባዊ ተቃውሞ ተቀስቅሷል፡፡ በሌላ የከተማዋ አካባቢም በተመሳሳይ መልኩ በመንግሥት በተወሰደ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ የቆሰሉ እንዳሉም ተጠቁሟል፡፡ እንደ መብት አራማጆች ከሆነ፤ ነጭ ለብሰው በመንቀሳቀሳቸው ብቻ ዛሬ በጎንደር የተገደሉ ዜጎች ቁጥር 4 ደርሷል፡፡ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ከተገደለው አንድ ሰላማዊ ዜጋ በስተቀር ሌሎች ጉዳቶችን ማረጋገጥ አልተቻለም፡፡
የዓይን እማኞች እንደተናገሩት፤ዛሬ ግድያው የተፈፀመው የጎንደር ህዝብ በመንግሥት ቀጥተኛ ትዕዛዝ በግፍ የተገደሉባቸውን ሰላማዊ ሰዎችን ለመዘከር ነጭ የመልበስ መርሃ ግብርን ተከትሎ ነጭ ለብሶ ሲንቀሳቀስ የነበረ ወጣት በድብደባ ሲገደል፣ ሌሎች 3 ሰላማዊ ዜጎች ደግሞ ከወታደሮች በተተኮሰ ጥይት ተገድለዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ጋብ ብሎ የነበረው የጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ ዳግም ተቀስቅሷል፡፡
ህዝቡም ዛሬ በግፍ የተገደለ ወጣት አስከሬን በአደባባይ ይዞ በመዞር ተቃውሞውን እያሰማ ይገኛል፡፡ ጎንደር ባለፈው ሳምንት እሁድ ጀምሮ ለ3 ቀናት ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
በከተማው ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን ተከትሎ መንግሥት አስተባባሪ የኮሚቴ አባለት ላይ የወሰደውን የኃይል ርምጃ ተከትሎ በነበሩት የፀረ አገዛዝ የህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች በመቀጠላቸው ስጋት የገባው መንግሥት፤ በርካታ የታጠቁ መከላከያ፣ ፌደራል ፖሊስ እና የፌደራል ልዩ የፀጥታ ኃይሎችን በከተማው ማስፈሩ ይታወቃል፡፡
በተያያዘ ዜና፤ በኦሮሚያ እስካሁንም ድረስ የቀጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ትናንት ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ወለጋ ደንቢዶሎ አንድ ሰላማዊ ወጣት በመንግሽት አልሞ ተኳሾች መገደሉ የታወቀ ሲሆን፤ በምስራቅ ሷ ዝዋይ ከተማ እቤቱ የነበረ አንድስ ሰላማዊ ዘጋም በመንግሥት የፀጥታ ኃይል ወታደራዊ ርምጃ መገደሉ ታውቋል፡፡
ለነገ ጠዋት በአዲስ አበባ መዳረሻውን መስቀል አደባባይ ያደረገና ሁሉም ኢትዮጵያዊ የተጋበዘበት ህዝባዊ ታላቅ የተቃውሞ ሰልፍ ተጠርቷል፡፡የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማ፤ መንግሥት በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚወስደውን ግድያ ህዝቡ በተለይም በኦሮሚያና በአማራ ክልል ተቃውሞው የቀጠለ ሲሆን፤ መንግሥት በኦሮሚያ እና አማራ ክልል ሰላማዊ ዜጎች ላይ እየፈፀመ ያለውን ግድያና የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ፤ ነገ እሁድ ጠዋት ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ታላቅ የተባለለት የተቃውሞ ሰልፍ መዘጋጀቱን የተቃውሞ አስተባባሪዎችና የመብት አራማጆች አስታውቀዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን በሀገር ቤት እየጠፈፀመ ያለውን የመንግሥት ግድያ፣ እስራትና አገዛዝ ድርጊትን በመቃወም በተለያዩ የአሜሪካ፣ አውሮፓ እና አፍሪካ ሀገሮችና ከተሞች ህዝባዊ ተቃውሞ እያደረጉ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡
መንግሥት ሰላማዊ ዜጎችን በአደባባይ መግደሉ እንዳሳሰበው በመጠቆም ምርመራ ማድረግ እንደሚፈልግ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ቢያስታውቅም አገዛዙ የመንግሥታቱ ድርጅትን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምርመራን እንደማይቀበልና ከላከው ምላሽ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ጉዳዩ ያሳሰባቸው የአሜሪካና የተለያዩ የአውሮፓ ሀገራት መንግሥት እየፈፀመ ያለውን ግድያ በማውገዝ ጉዳዩን በጥብቅ እየተከታተሉት እንደሆነ ማስታወቃቸው ይታወሳል፡፡
ከህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በወሰደውና እየወሰደ ባለው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በኦሮሚያ ክልል በነበሩት ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ ከ500 በላይ ሰላማዊ ዜጎች ሲገደሉ፤ ሁለተኛ ወሩን ባስቆጠረው የአማራ ክልል ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ደግሞ ከ100 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው ታውቋል፡፡