Tag Archives: Gonder Protest Ethiopia

የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር የነበረችው አስቴር ስዩም ተፈረደባት

(አዲስ ሚዲያ) ወጣት አስቴር ስዩም የታአሰረችው ከሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ ም ጀምሮ ትኖርበት ከነበረው ጎንደር ከእስር በተጨማሪ በርካታ ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን መቃወም ተከትሎ በደህንነት ኃይሎች ታፍነው አዲስ አበባ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ለወራት ከፍተኛ ስቃይና እንግልት ከደረሰባችው ሴቶችና ወጣቶች መካከል አንዷ ናት።

Aster Seyoum

አስቴር ስዩም

የቀረበባትም ክስ ህዝባዊ አመፅ ማነሳሳት ሙከራ በሚል  የፌደራል አቃቤ ህግ ክስ እንደነበር ያገኘው መረጃ አመልክቷል።

አስቴር ታፍና በመወሰድ ስትታሰር የ3 ወር ህፃን ልጇን ለወላጅ እናቷ ትታ የነበረ ቢሆንም፥ በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ታስራ እያለ ወላጅ እናቷ ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል።

ይሁን እንጂ፤ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት፥ የአድስ አበባ ልደታ ምድብ ችሎች ከ 23 ወራት እስርና የፍርድ ሂደት በኋላ ግንቦት 14 ቀን 2009 ዓ ም የ 4 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባታል።

በጎንደር የሰላማዊ ሰው ግድያ የቀጠለ ሲሆን፤ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተጠርቷል

(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ ነሐሴ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በአማራ ክልል ጎንደር ከተማ መንግሥት ሰላማዊ ዜጎችን ተኩሶ 1 ወጣት መግደሉን ተከትሎ ዳግም ህዝባዊ ተቃውሞ ተቀስቅሷል፡፡ በሌላ የከተማዋ አካባቢም በተመሳሳይ መልኩ በመንግሥት በተወሰደ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ የቆሰሉ እንዳሉም ተጠቁሟል፡፡ እንደ መብት አራማጆች ከሆነ፤ ነጭ ለብሰው በመንቀሳቀሳቸው ብቻ ዛሬ በጎንደር የተገደሉ ዜጎች ቁጥር 4 ደርሷል፡፡ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ከተገደለው አንድ ሰላማዊ ዜጋ በስተቀር ሌሎች ጉዳቶችን ማረጋገጥ አልተቻለም፡፡

የዓይን እማኞች እንደተናገሩት፤ዛሬ ግድያው የተፈፀመው የጎንደር ህዝብ በመንግሥት ቀጥተኛ ትዕዛዝ በግፍ የተገደሉባቸውን ሰላማዊ ሰዎችን ለመዘከር ነጭ የመልበስ መርሃ ግብርን ተከትሎ ነጭ ለብሶ ሲንቀሳቀስ የነበረ ወጣት በድብደባ ሲገደል፣ ሌሎች 3 ሰላማዊ ዜጎች ደግሞ ከወታደሮች በተተኮሰ ጥይት ተገድለዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ጋብ ብሎ የነበረው የጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ ዳግም ተቀስቅሷል፡፡
ህዝቡም ዛሬ  በግፍ የተገደለ ወጣት አስከሬን በአደባባይ ይዞ በመዞር ተቃውሞውን እያሰማ ይገኛል፡፡ ጎንደር ባለፈው ሳምንት እሁድ ጀምሮ ለ3 ቀናት ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

Gonder Amhara Protest

በከተማው ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን ተከትሎ መንግሥት አስተባባሪ የኮሚቴ አባለት ላይ የወሰደውን የኃይል ርምጃ ተከትሎ በነበሩት የፀረ አገዛዝ የህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች በመቀጠላቸው ስጋት የገባው መንግሥት፤ በርካታ የታጠቁ መከላከያ፣ ፌደራል ፖሊስ እና የፌደራል ልዩ የፀጥታ ኃይሎችን በከተማው ማስፈሩ ይታወቃል፡፡
በተያያዘ ዜና፤ በኦሮሚያ እስካሁንም ድረስ የቀጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ትናንት ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ወለጋ ደንቢዶሎ አንድ ሰላማዊ ወጣት በመንግሽት አልሞ ተኳሾች መገደሉ የታወቀ ሲሆን፤ በምስራቅ ሷ ዝዋይ ከተማ እቤቱ የነበረ አንድስ ሰላማዊ ዘጋም በመንግሥት የፀጥታ ኃይል ወታደራዊ ርምጃ መገደሉ ታውቋል፡፡

ለነገ ጠዋት በአዲስ አበባ መዳረሻውን መስቀል አደባባይ ያደረገና ሁሉም ኢትዮጵያዊ የተጋበዘበት ህዝባዊ ታላቅ  የተቃውሞ ሰልፍ ተጠርቷል፡፡የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማ፤ መንግሥት በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚወስደውን ግድያ ህዝቡ በተለይም በኦሮሚያና በአማራ ክልል ተቃውሞው የቀጠለ ሲሆን፤ መንግሥት በኦሮሚያ እና አማራ ክልል ሰላማዊ ዜጎች ላይ እየፈፀመ ያለውን ግድያና የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ፤ ነገ እሁድ ጠዋት ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ታላቅ  የተባለለት የተቃውሞ ሰልፍ መዘጋጀቱን የተቃውሞ አስተባባሪዎችና የመብት አራማጆች አስታውቀዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን በሀገር ቤት እየጠፈፀመ ያለውን የመንግሥት ግድያ፣ እስራትና አገዛዝ ድርጊትን በመቃወም በተለያዩ የአሜሪካ፣ አውሮፓ እና አፍሪካ ሀገሮችና ከተሞች ህዝባዊ ተቃውሞ እያደረጉ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡

መንግሥት ሰላማዊ ዜጎችን በአደባባይ መግደሉ እንዳሳሰበው በመጠቆም ምርመራ ማድረግ እንደሚፈልግ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ቢያስታውቅም አገዛዙ የመንግሥታቱ ድርጅትን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምርመራን እንደማይቀበልና ከላከው ምላሽ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ጉዳዩ ያሳሰባቸው የአሜሪካና የተለያዩ የአውሮፓ ሀገራት መንግሥት እየፈፀመ ያለውን ግድያ በማውገዝ ጉዳዩን በጥብቅ እየተከታተሉት እንደሆነ ማስታወቃቸው ይታወሳል፡፡

ከህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በወሰደውና እየወሰደ ባለው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በኦሮሚያ ክልል በነበሩት ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ ከ500 በላይ ሰላማዊ ዜጎች ሲገደሉ፤ ሁለተኛ ወሩን ባስቆጠረው የአማራ ክልል ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ደግሞ ከ100 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው ታውቋል፡፡

በጎንደር ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ

(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ እሁድ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ መዳረሻውን በጎንደር ፋሲለደስ መስቀል አደባባይ ያደረገ ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ፡፡ የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ምክንያት ባለፈው ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የማዕከላዊ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አንሺ ኮሚቴ አባላት ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ በሌሊት አፍኖ ወስዶ በማሰሩ፣ ከኮሚቴ አባላት መካከልም ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ እቤታቸው ሊያፍኑ የሄዱትን የፀጥታ አካላት ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፣ በሌሊት ህገወጥነት በሚል በተፈጠረ አለመግባባት የ11 የፅጥታ ኃይሎች እና 3 ሲቪሎች መገደላቸው ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢዎችን እና የፀጥታ ኃይሉ ላይ የአፀፋ ርምጃ የወሰዱትን ጨምሮ የመንግሥትን ርምጃ በማውገዝ እና ተቃውሞ ያቀረቡ የአካባቢውን ህዝብ ወንጀለኛ አድርጉ በሚዲያ በማቅረቡ የተቆጣው ህዝብ፤ ተቃውሞውን በአደባባይ ለማቅረብ ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ ህዝቡ በራሱ ተነሳሽነት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲወጣ እንዳደረገው ከአስተባባሪዎቹ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Gonder 1
ከጎንደር ፋሲለደስ ከተማ በተጨማሪ በደቡብ ጎንደር በእስቴ ወረዳ መካነ ኢየሱስ ከተማ፣በምዕራብ በለሳ እና ማክሰኝት ከተማ ተመሳሳይ ጥያቄ መነሻ ያደረገ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ታውቋል፡፡ በተለይ በጎንደሩ ሰልፍ የተለያዩ የኃይማኖት አባቶች በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ማድረጋቸውን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡

በዛሬው ተቃውሞ ሰልፍም የተለያዩ መፈክሮች የተደመጡ ሲሆን፤ በዋናነትም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ ሕገ-መንገሥታዊ መብት ነው፣ የሻዕብያ ተላላኪ ህወሃት እንጂ ወልቃይት አይደለም፣ በግፍ የታሰሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በአስቸኳይ ይፈቱ፣…የሚሉትን ጨምሮ በርካታ መፈክሮች እንደተሰሙ ለማወቅ ተችሏል፡፡


በተቃውሞ፤ ታሪክ ምስክር ነው ወልቃይት አማራ ነው ፣ አማራ ለኢትዮጵያ የግዛት አንድነትና ሉአላዊነት የተዋደቀ ታላቅ አርበኛ ሕዝብ ነው ፣ ዘረኝነትን አጥብቀን እናወግዛለን ፣ የትግራይን ሕዝብ እናከብራለን፤የህወሓትን አፋኝ የአገዛዝ ፖሊሲ አጥብቀን እናወግዛለን፣አማራነት ይከበር፣ በኦሮሞ እህት ወንድሞቻችን ላይ የሚደርሰውን ግፍና በደል አጥብቀን እንቃወማለን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ይፈልጋል፣ በኦሮሚያ የሚደረገው በወንድምና እህቶቻችን ላይ ግድያ ይቁም፣ ኢቢሲና ሌሎች መንግስታዊ ሚዲያዎች የጎንደርንና አካባቢውን ህዝብ ይቅርታ ይጠይቁ የሚሉ መሪ ቃሎች ተደምጠዋል፡፡

በተጨማሪም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ እስኪመለስ ድረስ ትግሉ ይቀጥላል፣አማራነት ወንጀል አይደለም፣ የትግራይ ወሰን ተከዜ ነው፣ ወልቃይት የአማራ ነው ፣ የሐብታሙ አያሌዉ ከአገር የመዉጣት እግድ በአስቸኳይ ይነሳለት፣ ዜጎችን በፖለቲካ አመለካከታቸዉ ማሰርና ማሰቃየት ይቁም፣ በፖለቲካ አመለካከታቸዉ የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ እና የህወሓት የበላይነት ይቁም የሚሉ መፈክሮች ጎልተው ተሰምተዋል፡፡


ይህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከሳምንት በፊት እውቅና ተጠይቆ በመንግሥት ተከልክሎ የነበረ ሲሆን፤ በድጋሚ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ቢገባም፤ መንግሥት ለህዝባዊ የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና አለመስጠቱን ከማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት ጋር በኢቢሲ እና ኤፍቢሲ ቢያሳውቅም ህዝቡን ለተቃውሞ ከመውጣት ማገድ አልቻለም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ እውቅና መንፈጉን በስሩ ባለ መገናኛ ብዙኃን ከመግለፁ በተጨማሪ በጎንደር ከፍተኛ የመከላከያ፣ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና የከተማው ሚሊሻ አባላት በበብዛት በከተማው እንዲሰፍሩ መደረጉ ታውቋል፡፡

ተቃውሞ ምንም እንኳ የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ ያድርግ እንጂ፤ ለዓመታት በአማራ ማኀበረሰብ ላይ በመንግሥት በተለይም በህወሓት/ኢህአዴግ አማራ ክልልን  ጨምሮ በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍል እየተፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ የመብት ጥሰት ተባብሶ መቀጠሉ አንዱ የተቃውሞ አካል መሆኑን የሰልፉ ታዳሚዎች ሲያስተጋቡ ተስተውሏል፡፡

በነበረው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍም፤ በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያስከትል በሰላም መጠናቀቁን የተሳታፊዎችን ጨምሮ ዓይን እማኞች እውቅና የነፈገው የመንግሥት አካል አስታውቀዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በ25 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ አረንጓዴ፣ ቢጫ ቀይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በብዛት ሲውለበለብ ታይቷል፡፡

በጎንደር በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ሰዎች ሲገደሉ፤ በአካባቢው ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው

በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በሚገኘው ጎንደር ከተማ፤ በያዝነው ሳምንት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸው ተጠቆመ፡፡ መረጃዎች እንደሚመለክቱት ከሆኑ፤ 10 ያህል ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ በወሰደው የአፀፋ እርምጃ 9 የፌደራል ፖሊስ እና 1 የመከላከያ ሰራዊት አባል ተገድለዋል፡፡

በስፍረው የሚገኙ የዓይን እማኞች በበኩላቸው የተገደሉ ሶወች ቁጥር ከተጠቀሰው እንደሚልቅ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በግጭቱ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር በተመለከተ እስካሁን ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡

Gonder Protest

ባለፈው ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት በጎንደር ለሁለት ተከታተይ ቀናት የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደሌሎች አጎራባች ከተሞች መዛመቱ ተሰምቷል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውም ሐሙስ ወደ ዳባርቅ ከተማ የተዛመተ ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ወደ ሳንጃ ወረዳ እና ወደ ሌሎች አጎራባች ከተሞችና ወረዳዎች መዛመቱ እየተነገረ ነው፡፡

car buring in Gondar

በተፈጠረው ግጭትም የሰው ህይወትን ጨምሮ የህወሃት እና የደጋፊው ናቸው የተባሉ ንብረቶች መውደምንም አስከትሏል፡፡
የግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ማንነትና ተያያዥ መብታቶቻችን ይከበሩልን የሚል ጥያቄን ለትግራይ ክልላዊ መስተዳደርና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲያቀርቡ የነበሩ ተወካይ ኮሚቴዎችን ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ የትግራይ ክልልና የፌደራሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የደህንነት አባላት ለማፈን እና ለማሰር በወሰዱት የኃይል እርምጃ በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑ ይታወቃል፡፡

በተለይ ከወልቃይት የአማራ ማንነት ተወካይ ኮሚቴዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፤ ሊያግቷቸው የመጡ የፀጥታ ኃይሎችን “ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፤ ካልሆነ በሌሊት እኔ እጄን ለማንም አልሰጥም” ማለታቸውን ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት፤ ህዝቡ የመንግሥት ኃይሎችን የሌሊት እገታና ሌሎች 4 የኮሚቴ አባላትን እስርና እገታ በመቃወም ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት እንደተፈጠረ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡

በጎንደር በተፈጠረው አለመረጋጋት የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ የአሜሪካና የእንግሊዝ መንግሥታት ዜጎቻቸው ወደጎንደርና አቅራቢያው ከመሄድ እንዲቆጠቡ አስጠንቅቀዋል፡፡ እስራኤል በበኩሏ በጎንደር የሚገኙ 6 ሺህ ቤተ እስራኤላውያንን እና በስፍራው የሚገኙ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ተወካዮችን ደህንነት በተመለከተ ከፍተኛ ቁጥጥር ወደሚደረግበት ስፍራ ጥበቃ እያደረገችላቸው መሆኑን የኢየሩሳሌም ፖስት ዘገባ አመልክቷል፡፡

በጎንደር ግጭቱ ለጊዜው የተረጋጋ ቢመስልም፤ አሁንም በአካባቢው በመንግሥትና በህዝቡ መካከል ከፍተኛ ውጥረት መኖሩ እየተገለፀ ነው፡፡

በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ እና ውጥረቱ ቀጥሏል

(አዲስ ሚዲያ) በጎንደር ከተማ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን የሚመሩ የኮሜቴ አባላትን ለማሰር በተወስደ እርምጃ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከፍተኛ ግጭት አስከተለ። ግጭቱ የተከሰተው ትናንት ሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ሌሊት ጀምሮ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የመንግሥት ደህነት እና የፀጥታ ኃይሎች የወልቃይት ማንነት ጥያቄ የሚመሩ ኮሜቴ አባላት መካከል አቶ አታላይ ዘርፌ፣ አቶ ጌታቸው አደመ፣ አቶ መብራቱ ጌታሁንና አቶ አለነ ሻማ በቁጥጥር ስር ያደረገ ሲሆን፣ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ በህግ የምትፈልጉኝ ከሆነ ሲነጋ መምጣት ትችላላችሁ በማለታቸው በተፈጠረው አለመግባባትና ግጭት በግድ እጅ እንዲሰጡ በኃይል በመንቀሳቀሳቸው ኮሎኔሉ እርምጃ መውሰዳቸው ተሰምቷል። ለምንግሥት የፀታ ኃይል እጃቸውን እንዲሰጡ በኃይል የተጠየቁት  ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ ቤታቸው በፀጥታ ኃይል መከበቡን ተሰምቷል፡፡ በተፈጠረው አለመግባባት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት በመገደላቸው በህዝቡ በተወሰደ የአፀፋ እርምጃ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም መገደላቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡

Selam Bus_Gonder
መንግሥት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደርና ወልቃይት አካባቢን በተመለከተ ማምሻውን በሰጠው መግለጫ በተፈጠረው አለመግባባት 3 የልዩ ሃይል ፖሊሶች ሲገደሉ፣ 5 መቁሰላቸውን አስታውቋል። ይሁን እንጂ መንግሥት ለግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን በቁጥጥር ስር ለማዋል መሆኑን ከመግለፅ በመቆጠብ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን እና ለማዋል የፈለጋቸውን የወለወቃይት ማንነት መብት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን ከኤርትራ መንግሥት ጋር በማያያዘ ሲወነጅል ተሰምቷል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ቀደም ሲል የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴ አባላት መካከል አቶ ሲሳይ ሊላይ የሚባሉ የኮሚቴ አባል በትግራይ ክልል ልዩ ኃይል ታግተው ከተሰወሩ በኋላ በአካባቢው ውጥረት መንገሡን ተከትሎ ወህኒ ቤት በማሰር ለፍርድ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡ የእስርና ፍርድ ጉዳያቸውም በሰቲት ሁመራ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በጎንደር የመንግሥት የኃይል ርምጃን በመቃወም ህዝቡ ንብረትነቱ የህወሓት/ኢህአዴግ የሆነውን ሰላም የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ፣ በተጨማሪ ሌላ መለስተኛ የፀጥታ ኃይሉ ተሽከርካሪ እና በጎንደር ከሚገኙ የህወሓት የንግድ ኩባንያ መደብሮች መካከል የተወሰኑት ላይ የማቃጠል ርምጃ መወሰዱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተቃውሞው ከጎንደር አዲስ አበባ ያሉ መንገዶችም በድንጋይ ተዘግተው ታይተዋል፡፡

%d bloggers like this: