Tag Archives: PM Hailemariam Desalegn

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥራ መልቀቂያ አስገቡ

ጠቅላይ ሚኒስትር እቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን ዛሬ የካቲት 8 ቀን 2010 ዓ. ም. በፅህፈት ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አረጋግጠዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥራ መልቀቂያቸውን በቅድሚያ በስልጣን ላይ ያለው የገዥው ፓርቲ አባል ለሆነውና ተወክለው ለመጡበት ለደኢህዴን እና ኢህአዴግ ከሊቅመንበርነት ለመልቀቅ ያስገቡት ጥያቄ ተቀባይነቱን ማግኘቱን አስታውቀዋል። ይህንንም ተከትሎ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ኃላፊነት ለመነሳት ለገዥው ኢህአዴግ ምክር ቤት ጥያቄ ማስገባታቸውንና ውሳኔያቸው ተቀባይነት አግኝቶ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲፀድቅላቸው እንደሚንሱ ይጠበቃል።
Hailemariam Desalegn
አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ

ለረጅም ጊዜ በሥላጥን ላይ ቆይተው በሞት የተለዩት አቶ መለስ ዜናዊን በመተካት ከነሐሴ 2004 ዓ. ም. ጀምሮ በሥልጣን ላይ ያሉት አቶ ኃይለማርያም፤ ዛሬ በፅህፈት ቤታቸው በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በሰጡት ይፋዊ የሥራ መልቀቂያ መግለጫ እንዳስታወቁት ከሆነ በእርሳቸው ምትክ በፓርላማው ሌላ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር እስኪሾም ድረስ ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ አስታውቅዋል። የሥልጣን መልቀቃቸውም በሀገሪቱ ያለውን ችግር ለመፍታት የመፍትሄ አካል አድርገው እንዳሰቡትም አስታውቀዋል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መራዘም እና የሚያስከትለው መዘዝ

ብስራት ወልደሚካኤል

ያለምንም የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት የአስችኳይ ጊዜ አዋጅ አውጥቶ ላለፉት 6 ወራት ከቆየ በኋላ ለተጨማሪ 4 ወራት ማራዘሙን ገዥው ስርዓት ይፋ አድርጓል:: ይሄ የሚያሳየው ህወሓት/ኢህአዴግ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የማስተዳደር አቅሙ መዳከሙን፥ ህዝባዊ ተቀባይነት ማጣቱን እና ህዝባዊ እምቢተኝነቱ በወታደራዊ እዝ የተዳፈነ ቢመስልም ጭራሽ እንዳልጠፋ ነው የሚነግረን::

Siraje Fergesa

በርግጥ የአዋጁ መራዘም የዜጎችን መብት በማፈን እና በመጨቆን ተጨማሪ የመብት ጥሰትን ዕድል የሚከፍት ነው። ይሁን እንጂ ስርዓቱ አዋጁን ህዝባዊ ተቃውሞዎችን ለማፈን የተጠቀመበት ቢሆንም በሌላ በኩል በራሱ ላይ ተጨማሪ የማያባራ ችግር እየፈጠረ ይገኛል። ምክንያቱም በህዝባዊ የፖለቲካ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ጥያቄ ተቃውሞ ምክንያት አስቸኳይ አዋጅ በታሰሩበት ሀገር ምንም ዓይነት የመብት ዋስትና ስለማይኖር ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባ የኢንቨስትመንት፥ የቱሪስት፥የዕርዳታ እና ትብብር እንቅስቃሴዎች በእጅጉ ይቀንሳሉ አሊያም ይቆማሉ::

በዚህም የውጭ ምንዛሪ እና የሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ይገደባል/ይደክማል:: ምክንያቱም በዜጎች የመብት ጥያቄ ምክንያት በአስቸኳይ አዋጅ ወታደራዊ ዕዝ ውስጥ ባለች ሀገር ውስጥ ምንም የደህንነት ዋስትና ስለማይኖር ደፍሮ መዋዕለ ነዋይ የሚያፈስ ባለሃብትና ጎብኚ አይኖርም:: ይህን ተከትሎ ከዚህ በፊት ሀገር ውስጥ የነበሩ የውጭ ባለሃብቶች በስራቸው የነበሩ ሰራተኞቻቸውን በማሰናበት ጓዛቸውን ጠቅልለው እንዲሄዱ በማድረግ የስራ አጡን ቁጥር በእጅጉ እንዲጨምር ያደርጋል::

በተጨማሪም የንግድ እንቅስቃሴ መዳከም እና የአቅርቦት እንዲሁም የሸቀጦችና መሰረታዊ ፍጆታዎች ዋጋ የበለጠ እየናረ እንዲሄድ ያደርገዋል:: ይሄ ደግሞ ለህዝባዊ ተቃውሞ ተጨማሪ ጉልበት ይሰጠዋል:: በመላ ሀገሪቱ ችግሮቹን ለመቆጣጠር የሚያስችል የገንዘብም ሆነ ፈቃደኛ የሚሆን የሰው ኃይል አይኖርም:: ስለዚህ የአስችኳይ ጊዜ አዋጁ መራዘም የዜጎችን መብቶችን ከመጨፍለቅ በተጨማሪ የመብት ጥያቄዎች እንዲበራከቱና ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በማድረግ የስርዓቱን ውድቀት ያፋጥነዋል::

ምናልባት ገዥው ስርዓት የተፈጠረውን የውጭ ምንዛሪ እና የገንዘብ ችግር በጊዜያዊነት ለመቅረፍ ሲባል በሀገሪቱና በዜጎች ላይ ዘመን ተሻጋሪ የሆኑ ሌሎች ጎጂ ርምጃዎችንም ሊወስድ ይችላል:: ከነዚህም አንዱ በሀገሪቱ አሉ የሚባሉና እስካሁን በከፊል በሽርክናም ሆነ በሙሉ በሽያጭ ወደግል ያልተላለፉ የመንግሥት/የህዝብ የንግድ ኩባንያዎች እና ተቋማትን ለሽያጭ ሊያቀርብ ይችላል:: በዚህም የደህንነት ዋስትና በሌለበትና በእቸኳይ አዋጅ ወታድራዊ ዕዝ ስር ባለ ሀገር ነገ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ስለምይታወቅ፤ ምናልባት በኢትዮጵያና በቀጠናው ላይ የፖለቲካ የበላይነት ለመያዝ ዙሪያ ጥምጥም ከሚያንዣብቡ የአረብ ባህረ-ሰላጤ ሀገራት በስተቀር የሚደፍር አይኖርም:: ይሄ ደግሞ ለስርዓቱ ተጨማሪ ራስ ምታት ነው::

ስለዚህ ያለው ብቸኛ የመፍትሄ አማራጭ ከተለመደውና ከተሰላቸው የስርዓቱ ኋላ ቀር ብልጣብልጥነት ፖለቲካ አካሄድ በመውጣት፤ የአስችኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳት፥ ከትዕቢትና እብሪት በዘለለ የህዝቡን ጥያቄ በተገቢው መንገድ በቀናነት መስማትና መመለስ፥ በግፍ የታሰሩ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞችን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መፍታት፥ ለህዝብና ለሀገር መብትና ጥቅም ከቆሙ በሀገር ውስጥና በውጭ ካሉ ተፎካካሪ የፖለቲካ ጅርጅቶች/ፓርቲዎች ጋር በገለልተኛ አካላት የሚመራና ገለልተኛ ስፍራ ግልፅ ድርድር ማድረግ ግድ ይላል። እንዲሁም ሐሳብን በነፃት የመግለፅና የፕሬስ ነፃነት ትግበራን ጨምሮ ቢያንስ በሀገሪቱ ሕግ መንግሥት ወረቀት ላይ የሰፈሩ መሰረታዊ የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ ማድረግ።

ገዥው ስርዓት የህዝቡን ጥያቄ ወደጎን በመግፋት ወደተለመደው አፈና እና ጭቆና ለመመለስ ጊዜ መግዣ ይሆነኛል በሚል በሌለ ገንዘብና አቅም ወጣቱን በማይጨበጥ ማናባዊ የኢኮኖሚ አብዮት ለማታለል ከመሞከር ይልቅ፤ በሰጥቶ መቀበል መርህ ተግባራዊ የሚሆን ስምምነት ላይ በመድረስ የወታደራዊ ዕዙን በመደበኛ/ሲቭል አስተዳደር በመመለስ የአፈና የግድያ ተልዕኮ ፈፃሚ እና አስፈፃሚ የደህንነትና ወታደራዊ አካላት ከህገወጥ ድርጊታቸው ታቅበው ወደ መደበኛ ስፍራዎቻቸውና ስራዎቻቸው እንዲመለሱ ማድረግ የተሻሉ አማራጮች ናቸው:: አለበለዚያ አሁን ባለው መንገድ ነገሮች የሚቀጥሉ ከሆነ ችግሮቹ ተባብሰው በመቀጠል የሀገሪቱን እና የህዝቡን ህልውና እና ደህንነት አደጋ ላይ ከመጣል ባለፈ የስርዓቱን ውድቀት ያፋጥነው እንደሆነ እንጂ መፍትሄ ሊሆን አይችልም::

በጋምቤላ ክልል በሙርሌ ታጣቂዎች በተፈፀመ ጥቃት የ46 ሰዎች ህይወት አለፈ

ውድነህ ዘነብ

በጋምቤላ ክልል ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ ከደቡብ ሱዳን ወደ ኢትዮጵያ ሰርገው እየገቡ በሚገኙ የሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች 46 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ፡፡

Gambella Victims

ጋምቤላ ከጥቃቱ ሰለባዎች በከፊል

ከጋምቤላ ክልል ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ የወጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ ከጥቅምት 27 እስከ መጋቢት 15 ቀን 2009 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት የ46 ሰዎች ሕይወት አልፏል፡፡ 76 ሕፃናት ታፍነው ተወስደዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ 143 ከብቶች ተነድተው ተወስደዋል፡፡ 33 ቤቶች ከነንብረታቸው ተቃጥለዋል፡፡

የጋምቤላ ክልል ቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ቢሮ ኃላፊ ሆነው የካቲት 26 ቀን 2009 ዓ.ም. የተሾሙትና ቀደም ሲል የክልሉ ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ ኡቶው ኡኮት እንደገለጹት፣ የሙርሌ ታጣቂዎች በክልሉ እያደረሱ የሚገኙት ጥቃት አይሏል፡፡

አቶ ኡቶው ባለፉት አራት ወራት ታፍነው ከተወሰዱ ሕፃናት ስድስቱ ተመልሰዋል ብለዋል፡፡ የተነዱ ከብቶች ግን አልተመለሱም፡፡ ከተገደሉ 46 ዜጎች በተጨማሪ 17 ሰዎች ቆስለዋል ሲሉ አክለዋል፡፡

የጋምቤላ ክልል ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ሆነው የተሾሙት አቶ ኡኩኝ ኦኬሎ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተወሰዱ ሕፃናትን ለማስመለስ ክልሉ ከፌዴራል መንግሥት ጋር በመቀናጀት እየሠራ ነው፡፡
‹‹አምና የተጀመረው ሕፃናትን ማስመለስና ችግሩ ዳግም እንዳይከሰት በዘላቂነት ለመፍታት የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ ነው፤›› ሲሉ አዲሱ ተሿሚ አቶ ኡኩኝ ገልጸዋል፡፡

በጋምቤላ ክልል የሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች የሚያደርሱት ጥቃት አዲስ ባይሆንም፣ ከ2008 ዓ.ም. በኋላ እየተባባሰ መጥቷል፡፡ ባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2008 ዓ.ም. የደቡብ ሱዳን ሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች የበርካታ ዜጎችን ሕይወት ከማጥፋት በተጨማሪ፣ ከ100 በላይ ሕፃናትን አፍነው መውሰዳቸው ይታወሳል፡፡
በዚህ ወቅት የሙርሌ የታጠቁ ኃይሎች ጥቃት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ ቀስቅሶ ነበር፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት መከላከያ ሠራዊት ዘግይቶም ቢሆን ወደ ደቡብ ሱዳን በመንቀሳቀስ ሕፃናቱን ለማስመለስ ሞክሯል፡፡
የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ በቅርብ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለጹት፣ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂ ኃይሎች ጥቃት ረዥም ጊዜ ያስቆጠረና ከኋላቀር አስተሳሰብ የሚመነጭ ነው፡፡

‹‹መንግሥት ይህ ድርጊት መቀጠል የለበትም የሚል ግልጽ አቋም ወስዷል፤›› ያሉት አቶ ሲራጅ፣ ‹‹ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት አስቸጋሪ የሆነው አካባቢው ረግራጋማ፣ ጥቅጥቅ ደን ያለበትና ለጉዞ አስቸጋሪ በመሆኑ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ይህንን ችግር ለመፍታት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ትኩረት የተሰጠው መሆኑን፣ ችግሩን ለመፍታት ድልድዮችና መንገዶች እየተገነቡ መሆኑን አቶ ሲራጅ ገልጸው፣ በአካባቢው መሠረተ ልማት ከተሟላ ጥቃት አድራሾችን መቆጣጠር እንደሚቻል ማስረዳታቸውን የሪፖርተር ዘገባ አመልክቷል።  

ዶ/ር መረራ ጉዲና ያቀረቡት የዋስትና መብት ጥያቄ ውድቅ ተደረገባቸው

(አዲስ ሚዲያ) ባለፈው የካቲት 24 ቀን 2009 ዓ. ም. በነበረው ቀጠሮ ዶ/ር መረራ ጉዲና በጠበቃቸው አማካኝነት የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጥያቄ አቅርበው ነበር። በዚህም ምክንያት የካቲት 30 ቀን 2009 ዓ. ም. አቃቤ ህግ ባቀረበው የዋስትና ጥያቄ ላይ ያለውን ተቃውሞ አቅርቦ፤ ለመጋቢት 1 ቀን 2009 ዓ. ም. ተይዞ የነበረው ቀጠሮ በዋስትናው ጉዳይ ላይ መርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር።

Dr.Merera Gudina

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዳኞች በሁለቱም ወገን የቀረበውን ክርክር መመርመራቸውን ገልፀዋል፥ የዋስትና መብት በህገ መንግስቱ የተደነገገ ቢሆንም ፍፁም መብት ሳይሆን በህግ አግባብ ሊገደብ የሚችል እንደሆነ ጠቅሰው ዶ/ር መረራ ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ከዚህ አግባብ መታየት ያለበት ጉዳይ እንደሆነ ተናግረዋል።

ዳኞች በማስከተልም የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ስነ-ስርዐት አንቀፅ 63 ንዑስ አንቀፅ 1 ላይ “ማንኛውም የተያዘ ሰው የተከሰሰበት ወንጀል የሞት ቅጣትን ወይም አስራ አምስት አመት ወይም በላይ የሆነ ፅኑ እስራት የማያስቀጣ ከሆነ እና ወንጀል የተፈፀመበት ሰው በደረሰበት ጉዳት የማይሞት የሆነ እንደ ሆነ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ወረቀት አስፈርሞ መልቀቅ ይችላል፡፡” እንደሚል ጠቅሰው፤ ዶ/ር መረራ ላይ የቀረበባቸው የመጀመሪያ ክስ (ወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ 32፣ 38 እና 238) የሚያስቀጣው የእድሜ ልክ እስራት ወይም የሞት ቅጣት በመሆኑ የዋስትና መብት እንደማይፈቀድላቸው ገልፀው ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሆነው ክሳቸውን እንዲከታተሉ አዘዋል።

ዶ/ር መረራም የዋስትና መብት እንዳልተፈቀደላቸው ከሰሙ በኋላ

“1ኛ.ከእነ ጄኔራል መንግስቱ ንዋይና ጄኔራል ታደሰ ብሩ ዘመን ጀምሮ ከአንድ ትውልድ በላይ ገዳዮችን፣ ሟቾች፣ አሳሪዎችና ታሳሪዎች በበዙበት የሃገራችን የፓለቲካ አላማ ውስጥ በመቆየት አንድ ከሆዱ በላይ ለሃገሩ የሚያስብ ምሁር ማድረግ እንዳለበት ሁሉ ከአርባ አምስት ዓመታት በላይ ለሃገሬ የተሻለ ለውጥ እንዲመጣ መታገሌ እየታወቀ ወደ ጎን መገፋቱ ፤
2ኛ. ለሁላችንም የምትሆንና በእኩልነት የምታስተናግደን፣ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትፈጠር ነፃ የፍትህ ስርአት በሃገራችን እንዲሰፍን ላለፉት 25 አመታት በመታገሌ፤ መከሰሴ አንሶ የሃገሪቱ ፓርላማ አባል ጭምር የነበርኩ ሰው ለተራ ወንጀለኛ የሚፈቅድ የዋስ መብት በመከልከሌ የተሰማኝ ጥልቅ ሃዘን ለራሴ ብቻ ሳይሆን እኛም ሆነ ልጆቻችን በሰላም ይኖሩበታል ለምንለው መከረኛ ሃገራችን አላልፍለት ብሎ ሲታመስ ለሚኖረው መከረኛ ህዝባችን ጭምር መሆኑን እንዲታወቅልኝ ነው።” ሲሉ ተናግረዋል።

በመጨረሻም በክሱ ላይ የሚቀርብ መቃወሚያ ለመቀበል ለሚያዚያ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል። የተቀሩት ተከሳሾችን በተመለከተ በጋዜጣ እንዲወጣ የታዘዘው የጥሪ ማስታወቂያን ለማየት ለመጋቢት 29 ቀን 2009 ዓ. ም. የተያዘው ቀጠሮ እንደተጠበቀ መሆኑን በመግለፅ በዕለቱም ዶ/ር መረራ መቅረብ እንዳለባቸው ፍርድ ቤቱ ሲናገር ተደምጧል።

ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ክስ ተመሰረተባቸው

(አዲስ ሚዲያ) ከ3 ወር በፊት በአውሮፓ ፓርላማ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ተጋብዘው ንግግር ያደረጉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተይዘው ለ 3 ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከታሰሩ በኃላ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ።ም በገዥው መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ህግ አማካኝነት በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ክስ ተመሰረተባቸው።

merera-gudina-and-berehanu-nega

ዶክተር  መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ

የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የነበሩት እና የኦፌኮ ሊቀመንበር እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶክተር መረራ ክስ የተመሰረተባቸው፥ በአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ንግግር ለማድረግ ተጋብዘው ሲመለሱ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር እና ሊቀመንበር ከሆኑት ከፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ታይተዋል በሚል እንደነበር ይታወቃል።

በዶ/ር መረራ ስም የተከፈተው በዚሁ የክስ መዝገብ ፥ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሁለተኛ ተከሳሽ ፣ አቶ ጃዋር መሃመድ ሶስተኛ ተከሳሽ በመሆን በልይሉበት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ ሶስቱም ተከሳሾች የተከሰሱት በወንጀለኛ መቅጫ ህጉን የተለያዩ አንቀጾች በመተላለፍ ሲሆን አራተኛ እና አምስተኛ ተከሳሽ የሆኑት የኢትዮጵያ ሳተላይ ቴሌቪዥን ( ኢሳት) እና ኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ( ኢኤም ኤን) ሲሆኑ፥ ተቋማቱ የፀረ ሽብር ህጉን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡

ዶ/ር መረራ ሌላ ተጨማሪ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መተላፍ በሚል ክስ ተመስቶባቸዋል፡፡ የክሱ ጭብጥም ተከሳሾች በዋና አድራጊነት ሽብር ተግባር መፈጸማቸውን እና ለኦሮሚያ እና አማራ ክልል አመጾች ማነሳሳት እና ንብረት መውደም ተጠያቂ መሆናቸው በክሱ ላይ ተጠቅሷል።

የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤትም ክሱን ለማየት ለየካቲት 24 ቀን 2009 ዓ ም ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በተለይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከዚህ በፊት በሌሉበት በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው ሲሆን፥ በነ አቶ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ደግሞ የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን፥ የአሁኑ ከነ ዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር የተመሰረተባቸው ክስ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል።

መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ ም ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ፥ በአማራ ክልል እና በደቡብ ክልል ኮንሶ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት ወታደራዊ ኃይል ሲገደሉ፥ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሲታሰሩ ከ15 ሺህ ያላነሱ በተለያየ ጊዜ ከእስር መልቀቁን መንግሥስት ቢያስታውቅም አሁንም ድረስ ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ የታሰሩና ሰብዓዊ መብቶቻቸው እየተጣሰ ያሉ ዜጎች መንግሥስት ከእስር ልቅቄያቸዋለሁ ክሚለው ቁጥር እንደሚልቅ ይግመታል።

ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት መንግሥት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ አማካኝነት ለህዝባዊ አምፁ ተጠያቂ ራሱ መንግሥት እና አመራሮች እንደሆኑ ቢይሳውቁም፥ ለግድያ፥ እስርና እንግልት የተዳረጉት ግን ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መግለፃቸው ይታወሳል።

%d bloggers like this: