እነ ኦሞት አግዋ ካቀረቡት አሰራ አንድ የከስ መቃወሚያ አስሩን ፍርደቤቱ ውድቅ አደረገው
ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያ አቃቤህግ ከሰጠው ምላሽ ጋር መርምሮ ምላሽ ለመስጠት ለዛሬ ጥር 2 ቀን 2008 ዓ.ም የቀጠረው ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያዎች ከአንዱ በሰተቀር ሁሉንም አለመቀበሉን እና ውድቅ ማድረጉን የመሃል ዳኛው ታረቀኝ አማረ በንባብ ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡
እነ አቶ ኦሞት አግዋ አዲስ አበባ በሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ታስረው ሲቀርቡ
በፍርድ ቤቱ ከአንድ መቃወሚያ በሰተቀር መቃወሚያዎቹ ውድቅ እንዲሆኑ እና ተቀባይነት እንዳያገኙ ምክኒያት የሆነው አቃቤ ህግ በማስረጃ ማሰማት ሂደት ላይ በዝርዝር እንድንሰማቸው ያደረጋል የሚል ነው፡፡
ተከሳሾች ክሳችን በእያንዳዳችን በተናጠል ቀርቦብን ሳለ አቃቤ ህግ በጋራ የከሰሰን ክስ ተነጣጥሎ ለየብቻ እንድንከሰስ ይደረግ የሚለውን የተከሳሾች መቃወሚያ ፍርድ ቤቱ የወንጀል ህጉን አንቀፅ 211 ቁጥር 7/3 በመጥቀስ ወንጀሎቹ የተለያዩ ቢሆንም የጋምቤላ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋሕነን) የጠራው ስብሰባ ላይ ኬንያ ፣ናይሮቢ ለመሳተፍ ሲሄዱ በቁጥጥር ስር የዋሉ መሆናቸውን ጠቅሶ ተከሳሾቹ በአንድ መዝገብ ሊከሰሱ ይችላሉ በማለት ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን መቃወሚያ አልተቀበለም፡፡
ተከሳሾች አባል ሆነውበታል በሚል የተጠቀሰው የጋምቤላ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋሕነን) ቡድን ህልውና እንዳለው አቃቤ ህግ በክሱ እንዲያስርዳ በተቃውሞቸው የጠየቁት ተከሳሾች፣ ቡድኑ በፍርድ ቤትም ሽብርተኛ ተበሎ አለመሰየሙን ጠቅሰው ከክሱ ላይ እንዲሰረዘላቸው ላቀረቡት መቃወሚያ ፍርድቤቱ የቡድኑን ህልውና እና ዝርዝር ማሰረጃ በክሱ ሂደት የሚሰሙ ናቸው በማለት ተቃውሞውን አለተቀበለም፡፡
በኢሜል አና በስካይፒ የተለያዩ ግንኙነቶችን ፈጥረዋል ብሎ አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ያሰቀመጠውን ተከሳሾች ከማን ጋር ግንኙነት እንዳደርጉ ሰላልጠቀሰ በክሱ ከማን ጋር ግንኙነት እንደነበራቸው በዝርዝር እንዲጠቀስ በክስ ተቃወሞው ላይ ያቀረቡትንም ተቃውሞ እንድሌሎቹ የክስ መቃወሚያዎች በተመሳሳይ ፍርድ ቤቱ የክሱ መሰረታዊ ስህተት አይደለም፣በማሰረጃ ማሰማት ሂደት ላይ እምንሰማቸው ዝርዝሮች ናቸው በማለት ተቃውሞውን ውድቅ አድርጓል፡፡
በመጨረሻም ተከሳሾች ካቀረቡት አስራ አንድ መቃወሚያዎች ፍርድቤቱ የተቀበለው በክሱ ላይ አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ አሰቀጠራቸው የተባሉት የፖሊስ አባላት ስም ዝርዝር በክሱ ተካቶ ይቅረብልን በለው ያቀርቡትን ተቃውሞ ሲሆን ፍርድቤቱ አቃቤህግ ለጥር 17 ቀን 2008 ዓ.ም. በክሱ ላይ የተጠቀሱትን የፖሊስ አባላት ስም ዝርዝር በክሱ አካቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥል፡፡
EHRP
በጋምቤላ ክልል በሙርሌ ታጣቂዎች በተፈፀመ ጥቃት የ46 ሰዎች ህይወት አለፈ
ውድነህ ዘነብ
በጋምቤላ ክልል ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ ከደቡብ ሱዳን ወደ ኢትዮጵያ ሰርገው እየገቡ በሚገኙ የሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች 46 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ፡፡

ጋምቤላ ከጥቃቱ ሰለባዎች በከፊል
ከጋምቤላ ክልል ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ የወጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ ከጥቅምት 27 እስከ መጋቢት 15 ቀን 2009 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት የ46 ሰዎች ሕይወት አልፏል፡፡ 76 ሕፃናት ታፍነው ተወስደዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ 143 ከብቶች ተነድተው ተወስደዋል፡፡ 33 ቤቶች ከነንብረታቸው ተቃጥለዋል፡፡
የጋምቤላ ክልል ቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ቢሮ ኃላፊ ሆነው የካቲት 26 ቀን 2009 ዓ.ም. የተሾሙትና ቀደም ሲል የክልሉ ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ ኡቶው ኡኮት እንደገለጹት፣ የሙርሌ ታጣቂዎች በክልሉ እያደረሱ የሚገኙት ጥቃት አይሏል፡፡
አቶ ኡቶው ባለፉት አራት ወራት ታፍነው ከተወሰዱ ሕፃናት ስድስቱ ተመልሰዋል ብለዋል፡፡ የተነዱ ከብቶች ግን አልተመለሱም፡፡ ከተገደሉ 46 ዜጎች በተጨማሪ 17 ሰዎች ቆስለዋል ሲሉ አክለዋል፡፡
የጋምቤላ ክልል ፀጥታና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ሆነው የተሾሙት አቶ ኡኩኝ ኦኬሎ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተወሰዱ ሕፃናትን ለማስመለስ ክልሉ ከፌዴራል መንግሥት ጋር በመቀናጀት እየሠራ ነው፡፡
‹‹አምና የተጀመረው ሕፃናትን ማስመለስና ችግሩ ዳግም እንዳይከሰት በዘላቂነት ለመፍታት የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ ነው፤›› ሲሉ አዲሱ ተሿሚ አቶ ኡኩኝ ገልጸዋል፡፡
በጋምቤላ ክልል የሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች የሚያደርሱት ጥቃት አዲስ ባይሆንም፣ ከ2008 ዓ.ም. በኋላ እየተባባሰ መጥቷል፡፡ ባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2008 ዓ.ም. የደቡብ ሱዳን ሙርሌ ጎሳ የታጠቁ ኃይሎች የበርካታ ዜጎችን ሕይወት ከማጥፋት በተጨማሪ፣ ከ100 በላይ ሕፃናትን አፍነው መውሰዳቸው ይታወሳል፡፡
በዚህ ወቅት የሙርሌ የታጠቁ ኃይሎች ጥቃት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ ቀስቅሶ ነበር፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት መከላከያ ሠራዊት ዘግይቶም ቢሆን ወደ ደቡብ ሱዳን በመንቀሳቀስ ሕፃናቱን ለማስመለስ ሞክሯል፡፡
የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ በቅርብ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለጹት፣ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂ ኃይሎች ጥቃት ረዥም ጊዜ ያስቆጠረና ከኋላቀር አስተሳሰብ የሚመነጭ ነው፡፡
‹‹መንግሥት ይህ ድርጊት መቀጠል የለበትም የሚል ግልጽ አቋም ወስዷል፤›› ያሉት አቶ ሲራጅ፣ ‹‹ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት አስቸጋሪ የሆነው አካባቢው ረግራጋማ፣ ጥቅጥቅ ደን ያለበትና ለጉዞ አስቸጋሪ በመሆኑ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ይህንን ችግር ለመፍታት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ትኩረት የተሰጠው መሆኑን፣ ችግሩን ለመፍታት ድልድዮችና መንገዶች እየተገነቡ መሆኑን አቶ ሲራጅ ገልጸው፣ በአካባቢው መሠረተ ልማት ከተሟላ ጥቃት አድራሾችን መቆጣጠር እንደሚቻል ማስረዳታቸውን የሪፖርተር ዘገባ አመልክቷል።
የእነ ኦሞት አግዋ ላይ ዛሬም የአቃቤ ህግ ምስክር ሳይሰማ ተቀጠረ
ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡
አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡
ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡
የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP
አቃቤህግ እነ ኦኬሎ አኳይ በከባድ ወንጀል ክስ እንዲቀጡ ጠየቀ
በሰኔ 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ የሽብር ክሰ ተመስርቶባቸው ክሳቸው በከፍተኛው ፍርድቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ አኳይ(ሰባት ሰዎች) መጋቢት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ጥፋተኛ ስለመሆናቸው ፍርድቤቱ ውሳኔ ካስተላለፍ በኃላ ከሁለቱም ተከራካሪዎች የቅጣት አስተያየት ለመስማት ለዛሬ ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቶ ነበር፡፡
ተከሳሾችም ሆኑ አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ለፍርድቤቱ ያቀረቡ ሲሆን አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
ከአንደኛ አስከ ሶስተኛ ያሉ ተከሳሾች የወ/ህ/ቁ 27/1/፣ 32/1/ሀ፣ 38 እና 241 በመተላለፍ ወንጀል ለመፈፀም በተቋቋመ ቡድን አመራር፣ አባል፣የደህንነት ዘርፍ እንዲሁም የውጭ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን፣ ገንዘብ በማሰባሰብ እና አባላትን በመመልመል ፣ የቡድኑ አባላት ወታደራዊ ስልጠና የሚያገኙበትን ሁኔታ በማመቻቸት፣ መሳሪያ በመግዛት፣የጦር መሳሪያ ድጋፍ ለማግኘት ከኤርትራ መንግስት ጋር እና ከኦነግ እና ግንቦት ሰባት ከተባሉ ቡድኖች ጋር በመደራደር በከፍተኛ አመራርነት ሲንቀሳቀስሱ የነበረ መሆኑን አቃቤህግ ጠቅሶ ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን ፍርድቤቱ የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት እንዲመድብ ጠይቋል፡፡
የቡድኑን አላማ አውቀው፣ በቡድኑ ወታደራዊ ስልጠና በመውሰድ ጥቃት ለመፈፀም በዝግጅት ላይ ነበሩ ያላቸውን ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች የወንጀል አፈፃፀማቸው በመካከለኛ ይመደብልኝ ሲል የጠየቀው አቃቤህግ ሁሉም ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አመልክቷል፡፡
ተከሳሾች በበኩላቸው በጠበቃቸው አማካኝነት ጥፍተኛ የተባሉት ከ2006 ዓ.ም በፊት ፈፅማቹኃል በተባለው ድርጊት መሆኑ ከቀረበባቸው ክስም ሆነ ፍርድቤቱ በሰጠው ውሳኔ እንድሚታወቅ አስረድተው፣ ለጥፋተኝንት ውሳኔው መሰረት የሆኑት ድርጊቶች ተፈፀሙ በተባለበት ጊዜ በስራ ላይ በነበረው እና በ2002 ዓ.ም በወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ፍርድቤቱ እንዲወስንላቸው ጠይቀዋል፡፡
የወንጀል ህጉ አንቀፅ241 ስር በተደነገገው እና ተከሳሾች ጥፋተኛ በተባሉበት የወንጀል ድርጊት በየትኛውም አካል ላይ ስለመድረሱ የተረጋገጠ የገንዘብም ሆነ የአካል ወይም የህይወት አደጋ የለም ያሉት ተከሳሾቹ ፈፀሙ በተባሉት ወንጀል የደረሰ ጉዳት ባለመኖሩ የወንጀሉ አፈፃፀም ቀላል በሚል ሊያዝ ይገባል ሲሉ አመልክተዋል፡፡ ተከሳሾች የቅጣት ማቅለያዎንም ፍርድቤቱ እንዲቀበላቸው ጠይቀዋል፡፡
ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው እንዲሆም አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ በመሆኑ እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው አመልክተዋል፡፡
ፍርድቤቱ የቅጣት አስተያየቶቹን ተመልክቶ የቅጣት ፍርድ ለመስጠት ለረቡዕ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡
ምንጭ፡-ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (EHRP)
በጋምቤላ ክልል በድጋሚ በ21 ዜጎች ላይ ግድያ ተፈጸመ
ባለፈው ሳምንት ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ በጋምቤላ ክልል የደረሰው አሰቃቂ ጭፍጨፋ የፈጠረው ሐዘን ሳይሽር፣ በድጋሚ ሌላ አሰቃቂ ግድያ በ21 ዜጎች ላይ ተፈጸመ፡፡
ሐሙስ ሚያዝያ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ረፋድ ላይ በጋምቤላ ክልል ጀዊ ስደተኞች ካምፕ የሚኖሩ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች፣ 21 ሰዎች ገድለው ሰባት ሰዎች ማቁሰላቸውን ሪፖርተር ከሥፍራው የደረሰው መረጃ አመልክቷል፡፡
የግድያው ምክንያት ሐሙስ ረፋድ ላይ በጋምቤላ ከተማ ከሚገኙ ስድስት ካምፖች አንዱ በሆነው ጀዊ ስደተኞች ካምፕ ውኃ የሚያመላልስ ቦቴ ተሽከርካሪ፣ ብስክሌት ይጫወቱ የነበሩ ሁለት ሕፃናት ስደተኞች ላይ አደጋ ማድረሱ ነው፡፡ በድንገተኛው የተሽከርካሪ አደጋ የሕፃናቱ ሕይወት ያለፈ ሲሆን፣ ስደተኞቹ ይህ አደጋ ሆን ተብሎ የደረሰ ነው በማለት ወዲያውኑ በኢትዮጵያውያን ላይ አደጋ ማድረስ ጀመሩ፡፡
በአደጋው እስካለፈው ዓርብ ድረስ የ21 ሰዎች አስከሬን ተሰብስቦ ወደ ጋምቤላ ሆስፒታል የተጓጓዘ ሲሆን፣ የሟቾች ቁጥር ከዚህ በላይ ሊሆን እንደሚችል የጋምቤላ ነዋሪዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ስደተኞቹ ደቡብ ሱዳናውያን ድንጋይ፣ ገጀራና ጦር በመጠቀም በሥፍራው በአሸዋ ማውጣት ሥራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች ላይ ጭፍጨፋ መፈጸማቸው ተነግሯል፡፡ ጭፍጨፋው የተካሄደበት ቦታ ጫካማ በመሆኑ ራሳቸውን ለማዳን ወደ ጫካ የሸሹ ሰዎች በመኖራቸው፣ በወቅቱም ያልተገኙ ሰዎች ስለነበሩ የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ምንጮች ተናግረዋል፡፡
የቆሰሉ ሰዎች ጋምቤላ ክልል ውስጥ በምትገኘው ቦንጋ ከተማ ሕክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተገልጿል፡፡ ይህ ጭፍጨፋ የተሽከርካሪ አደጋን ምክንያት ያድርግ እንጂ፣ የክልሉ ነዋሪዎች መሰንበቻውን በክልሉ የተከሰቱት ጭፍጨፋዎች ከዚህ ቀደም ታይተው በማይታወቁ መንገዶች የተፈጸሙ በመሆናቸው ከፍተኛ ሥጋት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡
ጋምቤላ ሚያዝያ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት በደረሰው ጭፍጨፋ የ182 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ፣ ከዚህ ቀደም ባሉት ቀናት ከነበረው ግድያ ጋር በድምሩ የ208 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡ 72 ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸው ይታወቃል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ 36 ሕፃናት በዕለቱ ታፍነው ሲወሰዱ ቀደም ባሉት ቀናት ከተወሰዱት ጋር የታፈኑት ሕፃናት ቁጥር 108 ደርሷል፡፡ ከ2,000 በላይ ከብቶች ተነድተዋል፡፡ ይህ ዘግናኝ ክስተት መላ ኢትዮጵያውያን ለከፍተኛ ሐዘን ዳርጎ ባለበት ወቅት፣ በድጋሚ በሳምንቱ ተመሳሳይ ጭፍጨፋ መከሰቱ ብዙዎችን አስቆጥቷል፡፡
ለሚያዝያ 7 ቀን ጥቃት መንግሥት አፀፋዊ ዕርምጃ በመውሰድና ሕፃናቱን ለማስለቀቅ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ዓርብ ሚያዝያ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች እንደገለጹት፣ ታፍነው የተወሰዱ ሕፃናት ያሉበት ቦታ ተለይቷል፡፡ አቶ ተወልደ ከዚህ በተጨማሪ በኢትዮጵያ ላይ የደረሰው ጥቃት ከጀርባው የፖለቲካ አጀንዳ መኖር አለመኖሩ፣ ጥቃቱን ያደረሰው አካል ማንነት እየተመረመረ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጋትሉዋክ ቱት ይህንን ግድያ በተመለከተ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ ሕዝቡን ለማረጋጋት በተለያዩ ቦታዎች በመንቀሳቀስ ላይ እንዳሉ ገልጸው፣ በሁለተኛው ግድያ ዙሪያ ሙሉ የተሟላ መረጃ እንደሌላቸውም ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን ችግሩ የተከሰተው በተሽከርካሪ አደጋ ምክንያት ለበቀል በተነሱ ስደተኞች መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
ኢትዮጵያ 272,648,300 የተለያዩ አገሮች ስደተኞችን ታስተናግዳለች፡፡ ከዚህ ውስጥ በጋምቤላ ክልል የሚገኘውና ይህ ጭፍጨፋ የተፈጸመበት ጀዊ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ 48,648 ስደተኞች ይገኛሉ እንደሚገኙ እና ስደተኞችን የሚያስተዳድረው የኢትዮጵያ ስደተኞችና ስደት ተመላሾች ባለሥልጣን በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጥ በሪፖርተር የተደረገው ጥረት አለመሳካቱን በመጠቆም ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
በተለይ የትናንት በስቲያውን ግድያ ተከትሎ የጋምቤላ ከተማ ነዋሪዎች ተቃውሞ በማሰማት የ21 ኢትዮጵያውያንን በአሰቃቂ ሁኔታ የገደሉ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ወደሚገኙበት ጀዊ ሲያቀኑ ከመከላከያ ሰራዊትና ከፖሊስ ግጭት በመፈጠሩ በኢትዮጵያውያኑ ግድያ ተቃውሞ ሲያሰሙ ከነበሩት መካከል ቢያንስ 2 ሰዎች በፀጥታ ኃይሉ በተወሰደ ርምጃ እንደተገደሉ የኢሳ ዘገባ አመልክቷል፡፡ አካባቢው ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አለመረጋጋት እንደሚታይበት የአከባቢው ነዋሪዎች ይናራሉ፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ እና ኢሳት