Category Archives: Social and Culture

በጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀመው የዘረኝነት ጥቃት እና ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት

ብስራት ወልደሚካኤል

በዶ/ር አብይ አህመድ እና አቶ ለማ መገርሳ የሥልጣን ዘመን በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ከደረሰባቸው ወገኖች መካከል የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የደረሰው ከፍተኛው ነው። ነገር ግን በተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀሙ ጥቃቶችና በደሎች አቶ ለማ መገርሳም ሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዶ/ር አብይ አህመድ ጠንቅንቀው ያውቃሉ። ባለፈው ክረምት የተፈፀመው በደል በኦነግ እንደሆነ ብዙ ሸፋፍኖ ለማለፍ ተሞክሮ ነበር። ግን አልነበረም። መጀመሪያ ላይ የተፈፀመው ማፈናቀልና አካላዊ ጥቃት በምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ባሉ የኦህዴድ/ኦዴፓ ከፍተኛ እና የወረዳ አመራሮች ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው የሚጠሩ ወጣቶችን በማስተባበር ጭምር እንደተሳተፉ የጥቃቱ ሰለባዎችና ድርጊቱን የተቃወሙ የጉጂ ዞን ሌሎቹ አመራሮች አጋልጠው ከኦሮሚያ ክልል ሪፖርት አድርገው ነበር። ይሄንንም የክልሉ ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ምክትላቸው ወ/ሮ ጠይባ ሐሰን ያውቃሉ። ለዚህም ነው አቶ ለማ መገርሳ ተፈናቃዮቹ ያሉበት ጉጂ ዞን በአካል ሄዶ የጎበኘውና ድርጊቱን ኮንኖ ሀዘኑን የገለፀው። ይህም ብቻ አይደለም በድርጊቱ የተሳተፉና መረጃ የተገኘባቸው ናቸው ያየተባሉት ላይ ወዲያውኑ ከሥራ ማገድ እስከ እስር ርምጃ መውሰዳቸውን ያሳወቁት። በወቅቱ የነበረውን የዘረኝነት ቅስቀሳና ማፈናቀሉን የተቃወሙ አመራሮችና የሀገር ሽማግሌዎች ቢኖሩም አደጋውን ከመቀነስ ባለፈ ማስቆም አልቻሉም ነበር። ምክንያቱም ጥቃቱ በመሳሪያ የታገዘ ስለነበር። ድርጊቱ ከዚህ ቀደም ሱማሌ ክልልና ወሰን አካባቢ በአብዲ ኢሌ እና አጋዦቹ በምስኪኑ ኦሮሞ ላይ ከተፈፀመው ጋር ተመሳሳይ ነው። ያንን አውግዘን እና ኮንነን ይሄን መሸፋፈን አይቻልም። ወንጀል የትም በማንም ላይ ይፈፀም ያው ወንጀል ነው።

ድርጊቱ የተፈፀመው በፖለቲካ መሪዎችና የፀጥታ ኃይሉ እንጂ በህዝቡ አለነበረም። ታዲያ በአብዲ ኢሌ የተፈፀመውን ኮንነን እና አውግዘን ስናብቃ ምስኪኑ የጌዲዖ ማኅበረሰብ መፈናቀልን እና የፖለቲካዊ የርሃብ ጥቃት መሸፋፈን ለምን አስፈለገ? የጌዲዖ መፈናል እና ሰብዓዊ ርዳታ ልክ ኦሮሞ በክፉ ሥራው የተጋለጠ ለማስምሰል ሌላ ጥፋት ነው። አንድም የግለሰቦችን ወንጀል ለምስኪኑ ኦሮሞ ማላከክ አሊያም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ ስም ማጥፋት አስመስሎ ማስፈራራት እና ወንጀሉን ለመሸፋፈን የመሞከር ወንጀል። ይሄ ጊዜ ያለፈበት ነው። ልክ የሶማሌ ማኅበረሰብ ኦሮሞ ከአስተዳደር ክልላቸው የኦሮሞ ማኅበረስብ እንዲፈናቀል ለእነ አብዲ ኢሌ ትዕዛዝ እና ድጋፍ እንዳላደረገ ሁሉ በምስኪን የጌዲዖ ማኅበረሰብ ከጉጂ ዞኖች መፈናቀል የኦሮሞ ማኅበረስብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ድጋፍ አድርጓል ብሎ የሚያምን የለም። የአካባቢው የኦህዴድ/ኦዴፓ ፅንፈኞችና ዘረኛ አመራሮች ግን አድርገውታል። ይሄን መካድ አይቻልም። ለዚህም በሁለት ዙር በግፍ የተፈናቀሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብን ሰቆቃ በአካል ሄዶ ማየት በቂ ነው። ይሄ ደግሞ ከህግም፥ ከሞራልም ሆነ ከሰብዓዊነት አንፃር መጋለጥና መወገዝ ያለበት ወንጀል ነው። ያውም “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት። ያኔ በህወሓት እና አብዲ ኢሌ ፖለቲካዊ ወንጀል የኦሮሞ ማኅበረሰብ ከሶማሌ ክልል በግፍ ሲፈነቀል ከሀገሩ ሊፍናቀል አይገባም ብለን በጋራ እንደተቃወምነው ሁሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብ በግፍ መፈናቀልንም ልናወግዝ ይገባል እንጂ ጉዳዩ ተጋለጠ ብሎ በርሃብና ሞት እንዲቀጡ መሸፋፈን ትክክል አይደለም። ይሄ ጭካኔ የተሞላበት ኢ- ሰብዓዊነት ነው።
Gedeo crises
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በማንነታቸው የተፈናቀሉ የጌዲዮ ማኅበረሰብ በከፊል (ፎቶ፡ የጌዲዮ ዞን ኮሚኒኬሽን ጽህፈት ቤት)
በተለይ አቶ ለማ መገርሳ ከፌደራል የደኢህዴን አመራሮች መካከል ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል እና ከደቡብ ክልል ደግሞ አቶ ሚሊዮን ማቴዎስ እንዲሁም በችግሩ ቅርበት ያለው የጌዲዖ ዞን አመራሮች የጥቃቱ ሰለባዎች የሚገኙበት ጊዜያዊ መጠለያ ቦታ ድረስ በመሄድ አረጋግጠው፤ ጉዳዩ በሽምግልና እንዲፈታ፥ የተፈፀመባቸው ጥቃትም ወደ አደባባይ እንዳይወጣ ብዙ ሞክረው ነበር። ጉዳዩን አለዝቦ “በጉጂ ኦሮሞ እና በጌዲዖ ማኀበረሰብ ተከስቶ የነበረው ግጭት በሀገር ሽማግሌዎች ርቀሰላም ተፈቷል” በሚል ለዘብ ያለ የዜና ሽፋን ሁሉ ተሰጥቶት ነበር። ያውም ከቪዲዮ ምስል ጋ ተያይዞ። እንደ ጥቃቱ ሰለባዎች ገለፃ ከሆነ ግጭቱ የተቀሰቀስውም ሆነ የተቀነባበረው በጉጂ ኦሮሞ ማኀበረሰብና ብጌዲዖ ማኀበረብ መካከል ሳይሆን በምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን በሥልጣን ላይ ባሉ አካላትና የ“ብሔር” እና ጥላቻ ቅስቀሳ ሲያደርጉ በነበሩና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች እና የማኀበራዊ ሚዲያ “አክቲቪስቶች” ነበር። በተለይ ከአካባቢው ጋር በተያያዘ በማኀበራዊ ሚዲያ ጭምር በኦሮሚኛ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥላቻ ቅስቅሰሳ ይደርግ ሁሉ እንደነበር አስታውሰዋል።

በወቅቱ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት የደረሰባቸው የዘረኝነት ጥቃት መካከል፡-

1ኛ. በርካቶች ቤቶቻቸው እየተመረጠ ተቃጥሎባችዋል።
2ኛ. የእርሻ ማሳ ላይ ያለ ቡና እና ሰብሎችን ጨምሮ ንብረቶቻቸው ተዘርፈዋል፥ መሬቶቻቸውም በአካባቢው ባለሥልጣናትና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች የተነጠቁም ይገኙበታል።
3ኛ. እናቶችን ጨምሮ ወጣት ሴቶች ተደፍረዋል።
4ኛ. በዚህ ወቅት ሊታሰብ የማይችል አሰቃቂ ግድያ ተፈፅሞባቸዋል። ከሞት የተረፉትም በዲላ እና ይርጋለም ሆስፒታሎች ሳይቀር ህክምና ርዳታ ያገኙ ነበሩ። በወቅቱም የኦሮሚያና የደቡብ ክልል ባለሥልጣናትም እንደተጎበኙ መረጃው አለ። ለውጡ እንዳይደናቀፍ በሚል ችላ ከተባለ በኋላ ዘግይቶ ጥቃቱ ግን በኦነግ ላይ ብቻ ተሳቦ ተሸፋፍኖ ታልፏል። ይሁን እንጂ የኦሮሚያ ክልልም ሆነ የደቡብ ክልል ባለሥልጣናት እውነታውን በደንብ ያውቁት ነበር። ከዚያም አቶ ለማ መገርሳ በጥቃቱን የተሳተፉ የምስራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን አመራሮችን ከሥልጣን በማንሳት እንዲታሰሩና በህግ እንዲጠየቁ ማድረጋቸውን በአደባባይ በዕርቀ ሰላሙ ወቅት ተናግረው ነበር። ጥቃቱ የደረሰባቸው ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ በተጨማሪ አጎራባች የደቡብ ክልል ጌዲዖ ዞን ወረዳዎች የነበሩ ምስኪን ገበሬዎችም ጥቃት ደርሶባቸው ተፈናቅለዋል። በተለይ አጎራባች በጌዲዖ ዞን ትምህርት ቤቶች ሁሉ በጥቃቱ ወድመዋል። ከዛም በመንግሥት ግፊት፥ በሀገር ሽማግሌዎችና አባገዳዎች ድርድር አማካኝነት ነሐሴ 30 ቀን 2010 ዓ. ም. ወደ 359 ሺህ የሚሆኑ ተፈናቃዮች ወደ ቀድሞ ቀዬያቸው እንዲመለሱ ተደርጎም ነበር።

ነገር ግን የመንግሥትን እና የሀገር ሽማግሌዎችን ጥሪ ተቀብለው ወደ ቀዬያቸው ሲመለሱ የተዘረፉና ንብረቶቻቸውን እና የተወረሱ መሬቶቻቸውን ተከልክለው ድጋሚ ሌላ ጥቃት ደርሶባቸዋል። በዚህም ወደ 175 ሺህ ያህ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት በድጋሚ እንዲፈናቀሉ ተደርጓል። የሁለተኛው መፈናቀል ላይ ከኦህዴድ/ኦዴፓ የአካባቢው አመራሮች በተጨማሪ የኦነግ ታጣቂዎችም እንደተሳተፉ የተገለፀ ሲሆን፤ ድርጊቱን አውግዘው የተቃወሙ የጉጂ የሀገር ሽማግሌዎች በጥቃት አድራሽ የአካባቢው አመራሮች፥ ወጣቶችና ታጣቂዎች ማስፈራሪያና ዛቻ እንደደረሰባቸው ለኦሮሚያ ባለሥልጣናት ጭምር አሳውቀዋል። ይሄን በደል ያጋለጡ እና ለኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ሪፖርት ያደረጉ አካላት አሁንም አሉ። ይሁን እንጂ ተፈናቃዮቹ ከኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናትም ሆነ የሚመለከተው የፌደራል መንግሥት ተገቢውን የሰብዓዊ እና የህግ ከለላ ድጋፍ ካለማግኘታቸው በተጨማሪ ፥ የተዘረፉና የተወረሱባቸው ንብረቶች እና የእርሻ ማሳዎች ሳይመለሱ ለረጅም ጊዜ በታፈነ አነስተኛ ጊዜያዊ የሸራ መጠለያ እንዲቆዩ መደረጉንም ያስታውሳሉ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ያለሰብዓዊ ድጋፍ በመጠለያ እያሉ የህግ ከለላና ድጋፍ ባለማግኘታቸው በተወስኑ ተመላሾች ላይ በፅንፈኞቹ ተደጋጋሚ የዘረኝነት ጥቃት ሲደርስባቸው በድጋሚ ከጉጂ ዞን ጊዜያዊ መጠለያዎቻቸውም ተፈናቅለው ወደ ጌዲዖ ዞን በተለይም ገደብ፥ ይርጋጭፌ እና ወናጎ ባሉ ወረዳዎች ተሰደው በአብያተ ክርስቲያናት አዳራሽ መኝታ አልባ ወለል ላይ እንዲሁም በሸራ በተወጠረ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ተፋፍገው ይገኛሉ። ከርሃቡ በተጨማሪም ለተለያየ ተላላፊ በሽታም የተጋለጡ ይገኝበታል። በድጋሚ ከተሰደዱትና በከፍተኛ ደረጃ ለርሃብ ከተጋለጡት መካክለ ከ45 ሺህ በላይ የሚሆኑት በጌዲዖ ዞን ገደብ ወረዳ ባሉ ቤተክርስቲያኖችና ትምህርት ቤቶች የተጠለሉ ቢሆንም በድጋሚ ወደ ቀዬያችሁ ካልተመለሳችሁ በሚል በፌደራል፥ በደቡብ እና ኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናት ግፊት ሰብዓዊ ድጋፍ እንዳይደረግላቸው መደረጉን መረጃዎች ይፋ ከሆኑ ሁለተኛ ሳምንቱን ይዟል። በዚህም በአማካይ በቀን ከ2 እስከ 3 ሰዎች በርሃብ እየሞቱ እነደሆነ፥ ቀሪዎቹ ለከፍተኛ ርሃብ በመጋለጣቸው አስቸኳይ የምግብ፥ የጤና እና መሰል የሰብዓዊ ድጋፍ ካላገኙ በአጭር ጊዜ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ አባላት ለሞት እንደሚጋለጡ የገደብ ወረዳ አመራሮች፥ የአካባቢው የመካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጉዳዩን አጋልጠዋል።
Gedeo
ከኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ጉጂ ዞን ከተፈናቀሉና የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰለባ ከሆኑ እናቶች መካከል አንዷ ናቸው።(ፎቶ፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ድርጊቱን ያጋለጡ የዲላ ዩኒቨርስቲ በጎ ፈቃደኞች እና ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ የተወሰደ)

መረጃው የደረሳቸው የዲላ እና ይርጋጨፌ ከተማ ነዋሪዎች እንዲሁም የተወሰኑ የዲላ ዩኒቨርስቲ ማኅበረሰብ አባላት ፈጥነው በመድረስ የተቻላቸውን ሰብዓዊ ድጋፍ በማድረግ ጉዳዩን ለቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስና አስቸኳይ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ከምስል ጋር ይፋ አድርገዋል። ይሁን እንጂ የደቡብ ክልል፥ የጌዲዖ ዞን፥ የኦሮሚያ ክልል እና የፌደራል ከፍተኛ አመራሮች በተለይም የሰላም ሚኒስቴር እና የፌደራል አደጋ መከላከል ዝግጁነት አመራሮች ጉዳዩን እያወቁ ለማስተባበል ሞከረው የነበረ ቢሆንም፤ በድጋሚ በቪዲዮ ማስረጃ ጭምር ከተጋለጠ በኋላ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያ ካሚልና የደቡብ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ልክ ጉዳዩን እንደማያውቅ በመምሰል ተፈናቃይ ተጎጂዎችን በአካል ጎብኝተዋል።

በተለይ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ እና የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል በከፍተኛ ርሃብ የተጋለጡ ከ45 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ያሉበትን ገደብ ወረዳ መካከል ኮቲት ቀበሌን ብቻ ጎብኝተው በመመለስ የገጎጂዎቹን ቁጥር 13 ሺህ ናቸው በሚል ዝቅ ለማድረግና አደጋውንም ለማሳነስ ሞክረዋል። ይሄ የቀዳማዊ አጽ ኃይለሥላሴ ዘመን የትግራይና ወሎ ርሃብ እንዲሁም የደርግ ዘመን የ1977ቱ ርሃብ መደበቅ ጋር ተመሳሳይ ተግባር መሆኑ ነው። የጌዲዖ ርሃብ የሚለው ርሃቡ በተፈጥሮ ድርቅ ምክንያት የተከሰተ ሳይሆን በአመራሮች እና ጽንፍ የያዙ ዘረኞች የተቀናጀ ቅጣት መሆኑ ነው። ርሃቡን ለመሰበቅ ብቻ ሳይሆን ለማስተባበልም በሶስት ቀን ውስጥ ብቻ የተለያየ ይሐሰት ማስተባበያ መረጃ ለማሰራጨት ተሞክሯል። ግን ለምን? ሰው እንዴት በወገኑ ላይ ይህን ያህል ይጨክናል? ይባስ ብሎ ራሳቸው የኦሮሞ “ጠበቃ” ያደረጉ እና ዘረኝነት በተደጋጋሚ ሲያቀነቅኑ የነበሩ አካላት የመፈናቀሉና ርሃቡ መጋለጡ ለምን አስቆጣቸው? ምናልባት የማፈናቀሉና የርሃቡ ቅጣት ላይ ተባባሪ ነበሩ ወይስ በምስኪን ህፃናትና ሞት የሚገኝ ሌላ ትርፍ ፍለጋ? ያሳዝናል።

የጌዲዖ ማኅበረሰብ “ብሔር” ተኮር ዘረኝነት ላይ መሰረት አድርጎ የተፈፀመው መፈናቀል እና የአመራሮች የተቀናጀ የርሃብ ቅጣት በዝምታ መታለፍ የለበትም። ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ ተደርጎበት ተሳታፊዎችና ጉዳዩን ለመሸፋፈን የሞከሩ የሚመለከታቸው አካላት በህግ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄ በዋናነት የምሥራቅ ጉጂ፥ ምዕራብ ጉጂ እና ጌዲዖ ዞኖች፥ የደቡብ ክልል እንዲሁም የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ካቢኔያቸው፥ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ የፌደራል፥ የኦሮሚያ እና የደቡብ ክልል አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ቋቋሚያ) አመራሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን በህግ ሊጠየቁና መልስ ሊሰጡ ይገባል። ምክንያቱን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ በስተቅር የተጠቀሱ አካላት እና አመራሮች ከዚህ ቀደም ችግሩን በአካል ድረስ ሄደው አይተዋልና። ስለዚህ ለተጎጂው የሚደረገውን የሰብዓዊ ድጋፍና ርዳታ ለማጣታልና ከኦሮሞ ህዝብ ጋራ ማያዝ ተገቢ አይደለም። ይሄ የባሰውኑ የለየለት ዘረኝነትና ጥላቻ ነው። ቢያንስ ሰብዓዊነት ተሰምቶን ለተጎጂዎች ቀና ትብብር ማድረግ ቢያቅተን እንኳ ደጋግና ቅን ሰዎች ድጋፍ ሲያደርጉ ከ”ኦሮሞ ብሔር” ስም አስታከን ለምን ተጋለጠ በሚል ግብዝነት ዓይናችን ሊቀላ አይገባም። ስለሆነም ተጎጂዎቹ የጌዴዖ ማኀበረሰብ አባላት በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰላባም ጭምር መሆናቸው ሊታወቅ ይገባል።

የጌዲዮ ማኀበረስብ የአረንጓዴ ወርቅ “ቡና” የበለፀጉ ታታሪ ገበሬና ነጋዴዎች ናቸው። በድርቅ ምክንያት በርሃብ የሚጎዱ የአካባቢውን ወገን ከመርዳት ባለፈ በርሃብ ምክንያት ለልመና እጅ የሚሰጡም አይደሉም። በዛ ላይ በዓለም ላይ ውድ የሆነውን እና የኢትዮጵያ ቡና (ኮፊ አረቢካ) ልዩ ተፈጥሯዊ ጣዕም የይርጋጨፌ ቡና ብራንድ ብቸኛ አምራችም ናቸው። ጥራት ያለው ተፈጥሯዊ ልዩ የይርጋጭፌ ቡና ወደዓለም አቀፍ ገበያ በመላክምለሀገራችን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከማስገኘት በተጨማሪ የተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃም የተካኑና የተመሰገኑ ታታሪዎች ናቸው። ዛሬ ቀን ጎድሎና በዘረኝነት የፖለቲካ ጥቃት ሰለባ ሆነው ለርሃብ ሲጋለጡ ቢያንስ በሰብዓዊነት ልናዝንላችውና ልንደርስላቸው ይገባል እንጂ ለምን ጥቃታችውና ርሃባቸው ተጋለጠ፥ ለምን ተረዱ በሚል ቡራ ከረዩ ማለት ያስገምታል። ቢያንስ እኮ የክፉ ቀን ደራሽ ባለፀጎች እንጂ በሥንፍና ደኽይተው ለርሃብ የተጋለጡ አልነበሩም። የደረሰባቸው “ብሔር” ተኮር ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት እንጂ። ይሄ በኢትዮጵያ ያልነበረ አዲስ አስቀያሚና ልዩ ታሪክ ነው። ምንም እንኳን ዴሞክራሲያዊና በህዝብ የተመረጠ መሪ ኖሮን ባያውቅም፤ በሀገራችን የነበሩ ርሃቦች በተፈጥሮ የድርቅ አደጋ ተከስተው መሪዎች ለግል ፖለቲካ ስብዕናቸው ሲሉ (አጼ ኃይለሥላሴና መንግሥቱ) ደብቀዋል እንጂ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ደርሱ ዜጎች ተፈናቅለው ፖለቲካዊ ርሃብ ጥቃት ደርሶ አያውቅም።

የተፈፀመባቸው እኮ የዘረኝነት ጥቃት ብቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣትም ጭምር ነው። በዚህ ልናፍርና ሊሰማን ይገባ ነበር። ጉዳዩ ለታሪክም መመዝገብ አለበት። ህዝብን ማፈናቀልና በርሃብ መቅጣት ወንጀል። ይሄ ወንጀል የተፈፀመው በምስኪኑ ኦሮሞ ህዝብ ድጋፍና ይሁንታ አይደለም፤ በአመራሮቹና በደጋፊዎቻቸው እንጂ። ይሄ ደግሞ በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን “የመብት” አራማጅና ወኪል አድርገው የሚቆጥሩ “አክቲቪስቶች” ሚና ቀላል አልነበረም። ለዚህም በተለይ ከ2008 ዓ. ም. ጀምሮ የአቶ ጃዋርን፥ አውስትራሊያ ሜልቦርን የሚገኘው አቶ ፀጋዬ አራርሳ፥ ኖርዌይ ኦስሎ የነበረው አቶ ግርማ ጉተማ፥ ሀገር ውስጥ ያለው አቶ አየለ ደጋጋ ፥ አሜሪካ ያለው ኢታና ሀብቴ እንዲሁም አንዳንድ በ #OMN_TV እና #ONN_OnlineTV ላይ በተለያየ ጊዜ “ብሔር” ተኮር ጥላቻ አዘል ንግግሮች እና ውይይት ላይ ሲሳተፉ የነበሩት ተጠቃሾችን ማኀበራዊ ገፅና ቪዶዮ መመልከት ይቻላል። ይሁን እንጂ እስካሁን ድረስ ግለሰቦች አሊያም የፖለቲካ ድርጅቶች በ”አሮሞ” ስምና ሰቆቃ ከመነገድ እና ራስን የህዝብ “እንደራሴ” አድርጎ ከማቅረብ ባለፈ ማንም ጥላቻና ዘረኝነት እንዲሰብክም ሆነ ዜጎችን እንዲያፈናቅል ሥልጣን አሊያም ውክል የሰጠው ኦሮሞም ሆነ ሌላ ብሔር የለም።
Gedeo displacement
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን ተፈናቅለው በጌዲዮ ዞን ገደብ ወረዳ መጠለያ ካሉ የጌዲዮ ተጎጂዎች በከፊል (ፎቶ፡ የጉጂ ዞን ኮሚኒኬሽን)
በአጠቃላይ በሀገርም ሆነ በብሔር ወይም በፖለቲካ ፓርቲ ወይም ድርጅት ከአቻዎቹ ጋር ተወዳድሮና አማራጭ ሐሳብ አቅርቦ በህዝብ ተመርጦ የተወከለ ማንም የለም። ለደረሱትም ሆነ እየደረሱ ላሉ ጥፋቶች ተጠያቂዎች የበደሉ ፈፃሚዎችና ተባባሪዎቻቸው እንጂ ህዝብ አይደለም። ምክንያቱም ህዝብ እንደ ህዝብ አይበድልም፤ በህዝብ የተወከለም የለምና። የበደል ውክልናም ሆነ ውርስ የለም። ስለዚህ በየትኛውም ቦታ ከክፉዎች ጋር አትተባበር።

እውነታው ከላይ የተጠቀሰው ሆኖ ሳለ ራሳቸውን የ”ኦሮሞ” ማኅበረሰብ ተወካይ ወኪል አድርገው የሾሙና ራሳቸውን የመብት አራማጅ አድርገው የሚቆጥሩ አካላት ፤ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ፖለቲካዊ ርሃብና ጥቃቱ መጋለጥ ለምን አስቆጣቸው? የምስኪኖች ርሃብና ስቃይ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር ምን ያገናኘዋል? ርግጥ ነው። የተፈናቀሉትም ሆነ በደል የደረሰባቸው በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ ነው። በደሉ የተፈፀመባቸው ደግሞ በኦህዴድ/ኦዴፓ ፥ በዘረኝነት ጥላቻ የተገፋፉ ወጣቶች እና በኋላም በአካባቢው በነበሩ የኦነግ ታጣቂዎች ነው። እዚህ ላይ የደቡብ ክልልና፥ በተለይ ለርካሽ ጊዜያዊ ሥልጣናቸው ሲሉ በግፍ ተፈናቃይ ህዝብ ላይ በተፈፀመው ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት ላይ የደቡብ ክልልና የጌዲዖ ዞን አመራሮች እንዲሁም የተወሰኑ የፌደራል ባለሥልጣናት እጅ አለበት። በተለይም በርሃብ መቅጣትና መሸፋፈኑ ላይ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና ህግ ካለ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄን መካድ አይቻልም።

ሌላው አስቂኝ ነገር መልካም ነገር ሲሆን “እኔ ይህን አድርጌ፥ እገሌ ይህን አድርጎ” ይሉናል፥ ሲወደሱም ምስጋናው እና ውዳሴውን ለግላቸው ጠራርገው ይወስዱና ስንት ዋጋ የከፈለውን እና አስተዋፅዖ ያበረከቱትን ስም ቅርጫት ውስጥ ይጥሉታል። ያው ባለሥልጣን ወይም “አክቲቪስት” ሲበድልና ግፍ ስፈፅም ልክ ኦሮሞን አማክረውና አስፈቅደው ያደረጉ ይመስል፤ በደሉንም ውግዘቱንም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ በማስመስል ለማስፈራራት ይሞክራሉ። ወዴት ወዴት!? ይሄ ግብዝነት ብቻ ሳይሆን ድንቁርናም ነው። የቀድሞው ጭካኙ አቶ ጌታቸው አሰፋ በወንጀል ሲጠየቅ ተመሳሳይ የህወሓት ደናቁርት አቶ ጌታቸውን ከምስኪኑ የትግራይ ህዝብ ጋር አያይዘው “ የትግራይ ህዝብ ላይ የተቃጣ ጥቃት” አስመስለው ካድሬዎቻቸው ህዝቡን አስገድደውና አታለው ሰልፍ አስወጥተው ነበር። ይሄንንም ራሳቸውን ተረኛ ባለሥልጣንባለጊዜ አድርገው የሚያቀርቡልን ድኩማን የኦህዴድኦዴፓ ካድሬዎችን ጭምሮ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሲኮንኑ ነበር። በዛ እኔም እስማማለሁ። ምክንያቱም አቶ ጌታቸውም ሆነ የህወሓት አመራሮች እንደዛ አረመኔና ጨካኝ እንዲሆኑ የትግራይ ህዝብ ውክልናም ሆነ ድጋፍ አልሰጣቸውምና። ቀድሞንስ የተበደለ ካልሆነ ማን ያውቅና? ህዝቡ ሚኒገረው ልክ እንደዛርው እንደነ ጠቅላይ ሚኒስር ዶ/ር አብይና ካድሬዎቻቸው የምናቧን ኢትዮጵያ አልነበር? የህወሓት አመራሮችን በተለይም የነ መለስ ዜናዊ እና ጌታቸው አሰፋ የፈፀሙትን በደል ከትግራይ ህዝብ እንደለያችሁት ሁሉ በጉጂዎች የተፈፀመውንም በደል ከኦሮሞ ጋር አታገናኙት። በደለኛው ራሱ ይጠየቅ፥ ሥራው ያውጣው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ አቶ ለማ መገርሳም ቢሆኑ ሰዎች እንጂ መላዕክት አይደሉም። አንዳንዱም ፈጣሪ አድርጎ ሊስላቸው ሚዳዳው ሁሉ አለ። ይቅር በለን እንጂ። ትናንት ጅልጣን ላይ የነበሩም ሆነ ዛሬ በህዝብ ማዕበል ተገፍተውና ተደግፈው ወደ ሥልጣን የመጡት እነ አብይ፥ ደመቀ፥ ለማ፥ ገዱ ያው ኢህአዴግ ናቸው፤ እንደየ ድርሻቸው የተለያየ ወንጀልብደል ላይም ተሳትፎ የነበራቸው ናቸው። ይሄን እነሱም ሚክዱት አይመስለኝም። ያው ከነበረው የ27 ዓመታት ሰቆቃ ወደ ለውጥ መግባታችን ጥሩ፥ “የሚታየውን ብሩህ ለውጥ” ማጨለምና እንቅፋት መሆን ጥሩ አይደለም በሚል እንጂ እያንዳንዱ ዶሲው ከቢሮው መደርደሪያ ቢፀዳም ከያንዳንዱ የጥቃት ሰለባ ወገን እና ተባባሪዎቻቸው ህሊና ሊጠፋ አይችልምና ድጋፉንም ቢሆን በልክ እናድርገው። በየትኛውም ቦታና ጊዜ በደልን እንፀየፍ። መልካም ነገሮችን እናበረታታ። ከዛ ውጭ የሚፈፀሙ በደሎችን ደብቁልን እያሉ ከምስኪኑ ህዝብ ጋር ለማገናኘት መጋጋጥ የትም አያደርስም። የህወሓትም ሰዎችም ቢሆኑ ይህንንም ነበር ያደረጉት። ግን አልጠቀማቸውም። እና ያንን የቆሸሸ መንገድ መልሶ መድገም ጭፍኑ እና ላሞኛችሁ” ዓይነት የጅል ጨወታ ስልሆነ ጉድፍና ቆሻሻን ነገር ከ”ብሔር” ጋር ማያያዝ ተውትይቅርባችሁ። በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን ባጩ “ልሂቃን” እና “አክቲቪስቶች” በስሙ፥ በአስከሬኑ እና ሰቆቃው እየተነገደ ለነበረው ኦሮሞ ማኅበረሰብ ልክ ለፖለቲካ መቆመሪያ የያ ርካሽ ትውልድ እንዳደረገው ዛሬም የልቅሶና የበታችኘት፥ የማስፈራሪያና ዛቻ ስሜት ቅስቀሳን ፖለቲካ አይመጥነውም።

በሰው በደል የሚደሰት ኦሮሞ፥ አማራ፥ ትግሬ፥ ሶማሌ፥ ጌዲዖ፥ አፋር፥ ሲዳማ፥ አኝዋክ፥ ጋሙ፥ ሀዲያ፥ ጉራጌ፥ ስልጤ፥ ሐረሬ፥ … ወዘተረፈ የለም። ህዝብ እንደህዝብ በደል የለበትም፤በጅምላ አንዱን ወገን ከሌላው በመለየት በደልም አያደርስም። ልክ ውዳሴና ሙገሳውን ለግላችሁ እንደምታደርጉት የፈፀማችሁትን በደልና ልለበደሉ ያላችሁን ተሳትፎም ኃላፊነቱን ለወንጀለኞችና ተባባሪዎች እንተው። የተጎዱ ወገኖቻችንን ግን እንታደግ። ሰብዓዊነት ዜግነትም ሆአ ብሔር የለውም። ብሔር ሰውን አልፈጠረም፤አይፈጥርም። ሰው ነው ብሔርንም፥ ባህልንም የፈጠረው። ስለዚህ ቅድሚያ ሰው እንሁን፤ ለሰብዓዊነት ይሰማን። በዛ ላይ የኦሮሞ ማኀበረሰብ እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ማኀበረሰብ ነው። ማኅበራዊ ህይወት የሚመቸው፥ ከመንደርና ቀበሌኛ አስተሳሰብ ይልቅ ሰፋ ያለ ቦታና አድማስን የሚያስቀድም፥ ቀናዒ፥ ኃይማኖትና ሥርዓት ያለው ማኅበረሰብ ነው።

በስሙ የምትነግዱ “ሊሄቃን” እና አክቲቪስቶች” ግን በተቃራኒው ጥላቻ፥ ቀበሌኛ፥ መንደርተኛ፥ የበታችነትና ተጠቂነት ስነ ልቦና ላይ ቆሞ የቀረ ጊዜ ያለፈበት ኋላቀር አስተሳሰብ ላይ ናችሁ። በዛ ላይ ትውልዱም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ሆኖ ከአድማስ ወዲያ አስቦና ሰርቶ፤ ራሱን፥ ቤትሰቡን፥ ማኅበረሰቡን፥ ሀገሩን፥ አህጉሩን እና ዓለምን ሊረዳ የሚችልበት ጉልበቱን፥ አእምሮና ጊዜውና በጥላቻ፥ በተጠቂነት፥ መንደርተኝነትና ቀበሌኛ ስነልቦና ውስጥ አታስቀሩት። የትናንቷ ዓለም ዛሬ የለችም። የዛሬዋ ደግሞ ነገ አትኖርም። ነገ ደግሞ ከዛሬው የበለጠ ብዙ ፈታኝ ውስብስብ የውድድር ዓለም ነው የሚጠብቀን። ከትንሽ ጊዜ በኋላ አይደለም የመንደር “ብሔር” ተኮር ቀበልኛ ኋላ ቀር አስተሳሰብ ቀርቶ ኢትዮጵያ ራሷ ትንሽዬ መንደር የምትሆንበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። ያውም ዓለም በመሰረተ ልማትና በዲጅታል ትክኖሎጂ ከምናስበው ፍጥነት በላይ እየተሳሰረ ባለበት በዚህ ወቅት። እንኳን የስግብግብ መንደርተኛ ፖለቲካ ላይ እኝኝ ብለን ቀርቶ ምሥራቅ አፍሪካ እንኳ አንድ ላይ ብንቀናጅ እየመጣ ያለውን ፈታኝ የውድድር ህይወት መቋቋም አንችልም። ከመቼው ጊዜ በላይ የጠነከረ ህብረት፥ አንድነትና መከባበር ያስፈልጋል። ለአንዱ ሚያስፈልገው መልካም ነገር ሁሉ ለሌላውም ያስፈልገዋል። አንዱ ላይ የንፈፅመው በደልና ጥላቻ ሁሉ ይዋል ይደር እንጂ አፀፋዊ መልስ ይዞ መምጣቱ የማይቀር ነው። በዛ ላይ መቶ ዓመት ለማንኖርባት ጊዜያዊ ዓለም።

በርግጥ አውቃለሁ። በ”ኦሮሞ” ስም የሚነግዱ ኋላቀር እና የዘረኝነት ቅስቃሳና ፖለቲካ የሚያራምዱ በምቾት የሚኖሩበት የሌላ ሀገር ፓስፖርትና መኖሪያ ቤት አንዳንዶቹ በአሜሪካ፥ አውሮፓና አውስትራሊያ አላቸው። እንደ ሀገር ኢትዮጵያ ብትጎዳ፥ ወይም እንደ ህዝብ ኦሮሞ ቢጎዳ እነሱ ሌላ የምቾት መኖሪያሌላ ሀገር ስላላቸው ሳይነግሩህ በቦሌ ተሳፍረው ነው ሚሄዱት። ከዛ ባንተ አስከረንና ሰቆቃ ገንዘብ ይለቃቅማሉ። አለቀ። አንተ ሰላም ከሆንክና አተመቸንህ ግን ባንተ ስም ገቢ የላቸውም። ከዚህ የተለየ ግብ አላቸው ካልክ በስምህ ምለው ተገዝተው የሚነግዱትን ፍላጎታቸውና ዓላማቸውን እንዲሁም ምክንያታቸውን ጠይቅ። ከዛ ለምን የሌላ ሀገር ፓስፖርት ይዘው እንደሚኖሩ ጠይቅና፤ ከዛ እሱን ትተውካንተ ጋ ያለውን ተካፍለው እንዲኖሩ ጠይቃቸው። ያኔ ምላሽና ተግባራቸውን ተመልከት። በነጋታው ቻዎ እንኳን ሳይሉህ ደጋግ፥ ሥልጡን እና ሰብዓዊነት የሚሰማቸው ሰዎች ወደሰጧቸውና ወደፈቀዱላቸው የምቾት ሀገር ይመጣሉ። የሚያሳዝነኝ ምስኪኑ ወጣት ነው። አጣችም ደኽየችም ያለችው ያቺው ምስኪን አንዲት ኢትዮጵያ ናት። ተከባብሮ በአንድነት በሰላም ኖሮና ሰርቶ ፤ወጣቱ ተረጋግቶ እንዳይኖር በሰቆቃው የጉስቁልናው ህይወቱ ለሚነግዱ መቆመሪያ ማድረጉ ነው። ወዳጄ! ከሞት በኋላ ትንሳኤ ኃይማኖት ላይ እንጂ ምድርና ፖለቲካ ላይ የለም። ከሞትክ ሞትክ ነው፤ አበቃ። ስትሞትና ስትጎዳ ምታጎለው ራስህን እና ቤትሰብህን ሌላ ማንንም አይደለም። በሞትህ የሚጠቀመው ደግሞ፥ የሬሳ ሳጥን ሻጭ፥ የመቃብር ጉድጓድ ቆፋሪና በሞትህና ስቃይ ቆምሮ የሚከብር አረመኔን ብቻ ነው። ስለዚህ ነፃ ሆነህ፥ ሰልጥነህ፥ ጤናማ ደስተኛ ሆነህ ከሁሉም ጋር በፍቅር ኑር።

አንተ ላይ እንዲፈፀም የማትፈልገውን መጥፎ ነገር በሌሎች ላይ አታድርግ፤ ላንተ እንዲሆንል የምትመኘውን መልካም ነገር ሁሉ ያለምንም አድሎ ለሌሎችም አድርግ!! ምክንያቱም ሌላውም ሰው ልክ እንዳንተ መልካም ነገሮች የሚያስፈልጉት ሰው ነውና።

የለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር ቤቶችን የማፍረስ ዕርምጃና የተፈናቃዮች ጩኸት

ሻሂዳ ሁሴን

በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከማስተር ፕላን ውጪ ተገንብተዋል የተባሉ ከ12,000 በላይ ቤቶች እንዲፈርሱ መወሰኑና ቤቶቹም መፍረስ መጀመራቸው ውዝግብ አስነስቷል፡፡ እስካሁን በከተማው በሚገኙ ሁለት ቀበሌዎች ማለትም ቀበሌ 03 የካ ዳሌና ቀበሌ 01 አባ ኪሮስ በመባል በሚታወቁ ሥፍራዎች ከ930 በላይ የሚሆኑ ቤቶች መፍረሳቸው ተነግሯል፡፡ የአካባቢዎቹ ነዋሪዎች የተሰጣቸው የማስጠንቀቂያ ጊዜ አጭር መሆኑን፣ እየፈረሱ ያሉትም የተመረጡ ቤቶች ናቸው ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ ካርታ ለማግኘት ተመዝግበው በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎች ቤቶች እየፈረሱ እንደሆነ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ገልጸዋል፡፡ ድርጊቱንም የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ለማ መገርሳ እንዲያስቆሙ ነዋሪዎች ጠይቀዋል፡፡ የኦሮሚያ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አድማሱ ዳምጠው፣ ሕገወጥ ግንባታዎችን የማፍረስ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል፡፡

Legetafo_social crises 2019 በገለጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር እንዲፈርሱ ከተወሰነባቸው ከ12,300 በላይ ቤቶች ውስጥ አንዱ

ሪፖርተር በሥፍራው ተገኝቶ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ሜዳ ላይ መበተናቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይ በቀበሌ 03 የመፍረስ ዕጣ ከገጠማቸው ቤቶች የአንዱ ይህንን ይመስላል፡፡

ሦስት ክፍሎች ያለው ቤት ግድግዳው በከፊል ፈርሷል፡፡ ጣራውም ሙሉ ለሙሉ ተነስቷል፡፡ በርና መስኮትም የለውም፡፡ ሊወድቅ ቋፍ ላይ የደረሰውን የጭቃ ግድግዳ ተደግፎ ከቆመው መሰላል ውጪ ምንም አይታይም፡፡ ከወንዝ ዳርቻ የተሠራው ቤት ወደ ፍርስራሽነት የተቀየረው ዕድሜ ተጭኖት ወይም የቦምብ ፍንጣሪ መትቶት አይደለም፡፡ ሕገወጥ ግንባታ ነው ተብሎ በአፍራሽ ግብረ ኃይል በትዕዛዝ የፈረሰው ረቡዕ ረፋዱ ላይ ነበር፡፡

‹‹ጠላ ሸጬ ነው ቤቱን የሠራሁት፤›› የሚሉት ወይዘሮ ግን ቤቱ ከፈረሰ ሰዓታት ያለፉት ቢሆንም አልተፅናኑም፣ ከድንጋጤያቸውም አልተላቀቁም፡፡ ‹‹ሕገወጥ›› የተባለው ቤታቸው እንደሚፈርስና ንብረታቸውን እንዲያወጡ የሚገልጽ ደብዳቤ የደረሳቸው ቅዳሜ የካቲት 9 ቀን 2011 ዓ.ም. እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በሰዓቱ ደብዳቤውን የተቀበለችው ኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ የምትማር ልጃቸው በድንጋጤ መታመሟን፣ እስካሁንም እንዳልተሻላትና ወደ ትምህርት ገበታዋ እንዳልተመለሰች ሲናገሩ እያነቡ ነው፡፡ ‹‹ለነገሩ ደንዳና ነኝ፤›› የሚሉት ወይዘሮዋ ቢሆኑም፣ አፍራሽ ግብረ ኃይሉ ግድግዳውን በላያቸው መናድ ሲጀምር ራሳቸውን ስተው እንደ ነበር ይናገራሉ፡፡ መናገርና መስማት አትችልም የሚሏት ትንሽ ልጃቸው ቤታቸውን እያፈረሱ የነበሩትን ሰዎች ልብስ እየጎተተች ስትለምናቸው እንደበር የሰሙትም፣ ከወደቁበት ሲነሱ ሰዎች ነግረዋቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹ቤቱን ለቃችሁ ውጡ› የሚለው ደብዳቤ ሲደርሳቸው፣ ‹‹እውነት አልመሰለኝም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ የተሰጣቸው የአራት ቀናት ቀነ ቀጠሮም አጭር ነበርና መፍትሔ ለማፈላለግም ሆነ ንብረታቸውን ለማውጣት በቂ ስላልነበረ፣ ከማስፈራሪያነት ያለፈ ሚና ይኖረዋል ብለው እንዳላሰቡ ተናግረዋል፡፡ ረቡዕ የካቲት 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ረፋዱ ላይ አፍራሽ ግብረ ኃይሉ ግድግዳቸውን መናድ ሲጀምር ግን እያነቡ ከመለመን ባለፈ ንብረታቸውን ለማውጣት እንኳን ፋታ አለማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡

“ነገሮች ከአዕምሮዬ በላይ ራሴን ስቼ ወደቅኩ፤” ብለው፣ ወደ ራሳቸው ሲመለሱ ጠላ ሸጠው የገነቡት ቤት ወደ ፍርስራሽነት ተቀይሮ እንዳገኙት ተናግረዋል፡፡ የቀረላቸው ነገር ቢኖር በቆርቆሮ በር የሚዘጋው ትንሹ ኩሽናቸው ነው፡፡ በማንኛውም ሰዓት ሊያፈርሱት ይችላሉ ብለው በሚሠጉበት ኩሽናቸው ውስጥ አዳራቸውን ማድረጋቸውን፣ ከፍርስራሹ ውስጥ የወጣ ንብረታቸውን ደግሞ ቤታቸው እንደሚፈርስ ቀነ ቀጠሮ በተሰጣቸው ጎረቤቶቻቸው ቤት በታትነው ማስቀመጣቸውን አስረድተዋል፡፡

ባለትዳርና የአምስት ልጆች እናት የሆኑት ወይዘሮዋ ያለ ወትሯቸው ሜዳ ለሜዳ ይዞራሉ፡፡ አፉን ከፍቶ የቀረ ቤታቸው የሚያርፉበት ባይሆንም ቤት እንዳለው ሰው ወደ ፍርስራሹ ያመራሉ፡፡ ‹‹ከእነ ልጆቼ ሜዳ ላይ ቀርቻለሁ፤›› አሉ ትንሽ ልጃቸውን አዝለው ወደ ተቆለለው ፍርስራሽ ላይ እየወጡ፡፡ በመንደሩ ተመሳሳይ ችግር የደረሰባቸው ብዙዎች ስለሆኑ እየዞሩ ሌሎችንም ያፅናናሉ፡፡

እንደ ወይዘሮዋ ሁሉ መውደቂያ ባያጡም ጎረቤታቸው ወ/ሮ መቅደስ ተሰማ ግን እውነታውን መቀበል ተስኗቸዋል፡፡ ‹‹ሊፈርስ ነው የሚባል ነገር ከሰማሁ ቀን ጀምሮ እንዳለቀስኩ ነው፡፡ ደብዳቤው ቅዳሜ ዕለት በእጃችን ሲገባ ያልሄድንበት ቦታ የለም፡፡ ነገር ግን ማንም የደረሰልን አካል የለም፡፡ የቀን ጨለማ ነው የሆነብን፡፡ ይኼንን ቤት ለመሥራት የለፋሁትን እኔ ነኝ የማውቀው፤›› አሉ ወደ ተከመረው ፍርስራሽ በእጃቸው እያመለከቱ፡፡

በአካባቢው ይኖሩ ከነበሩ ከአንድ ግለሰብ የገዙትን ቤት አድሰውና ባለው ትርፍ ቦታም ቤት ገንብተው ኑሮ ለመጀመር ነገሮች ቀላል አልነበሩም ይላሉ፡፡ በአንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ተቀጥረው እንደሚሠሩና በወር የሚያገኙትም 3,000 ብር እንደማይሞላ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ያለው ሰው እኮ እዚህ አይኖርም፡፡ አማራጭ የሌለን ድሆች ነን እዚህ ገዝተን የምንገባው፤›› በማለት ዕንባቸውን አዘሩ፡፡

የፈረሰባቸውን መኖሪያ ቤት ለመሥራት ለዓመታት እንደተቸገሩ ይናገራሉ፡፡ ቆርቆሮ ለመምታት፣ ግድግዳ ለማቆም በወር ከሚያገኙት ላይ እየቆጠቡ ዕቁብ መጣል እንደነበረባቸው ያስታውሳሉ፡፡ የዋናው ቤት ግንባታው ባያልቅም ቀስ በቀስ ያልቃል በማለት ከአራት ዓመታት በፊት ገብተው መኖር እንደጀመሩም ያስረዳሉ፡፡ በአንዱ ዕቁብ በር፣ በሌላው ኮርኒስ እያሠሩ መደበኛ ቤት ለመሆን አንድ መስኮትና የፍሳሽ ማስወገጃ ሲቀረው፣ ሕገወጥ ግንባታ ተብሎ ረቡዕ ዕለት መፍረሱን ተናግረዋል፡፡ የቀራቸው ለተከራይ የሰጡት ሰርቪስ ቤት ቢሆንም፣ የቱ እንደሚፈርስና የቱ እንደሚቀር ስለማይታወቅ መጨረሻቸውን አላወቁም፡፡ “የዋናውን ቤት የተወሰነ ክፍል አፍርሰው ይኼ ቀርቶልሻል እጠሪው ካሉ በኋላ ነው ተመልሰው የቀረውን ሆ ብለው ያፈረሱት፡፡ አሁን ጭንቀት ሊገድለኝ ነው፡፡ የማይወለድ ልጅ ማማጥ ሆኖብኛል፤” አሉ እንደገና እያነቡ፡፡

አራት ልጆች የማሳደግ ኃላፊነት እንዳለባቸው፣ ከዘራቸውን ተደግፈው የሚቆዝሙ ወላጅ አባታቸውን የማስተዳደር ኃላፊነትም የእሳቸው መሆኑን መኖሪያ ቤታቸው በላያቸው የፈረሰባቸው ወ/ሮ መቅደስ ይናገራሉ፡፡ አንገት ማስገቢያ ጎጆ ለመቀለስ ባወጡት ወጪና ልፋት ውጤቱን ሳያዩ ስለፈረሰባቸው ሐዘን እንደሰበራቸው አክለዋል፡፡ ቤቱን ለመሥራት ከፍለው ያልጨረሱት የዕቁብ ዕዳም ዕረፍት ነስቷቸዋል፡፡ በሁኔታው ተስፋ ቆርጠው አፍራሾቹን ቆመው ሲመለከቱ እንደነበር፣ ንብረታቸውን ያወጡላቸውም ዕድርተኞቻቸው እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ አለኝ የሚሏቸው የቤት ዕቃዎች ወደ አንድ ጎን ተከምረው አቧራ ይጠጣሉ፡፡ 276 የሚል የቤት ቁጥር የሠፈረበትን ቆርቆሮ የያዘ የብረት በር ከአንዱ ጥግ ተሸጉጧል፡፡ ወይዘሮ መቅደስ የቤት ቁጥር ከተሰጣቸው ዓመታት እንደተቆጠሩ ይናገራሉ፡፡

በራፋቸው ላይ ከተተከለው የኤሌክትሪክ ፖልም የኤሌክትሪክ ኃይል ያገኛሉ፡፡ ከዓመታት በፊት አንድ ክፍል ቤት ያለውን ግቢ የገዙት በግል ውል ነበር ይላሉ፡፡ ‹‹ማዘጋጃ ቤት በሊዝ ለባለሀብት ይሸጣል እንጂ ለምን ለእኔ ይሸጥልኛል? ባለሀብት ደግሞ እንዲህ ዓይነት ቦታ ላይ ምን ይሠራል?›› ሲሉ ለኑሮ የማይመቹ ቦታዎች ላይ ተገፍቶ የሚወጣው አማራጭ ያጣ እንደ እሳቸው ያለ ደሃ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡

ቦታው ላይ ሲኖሩ ካርታ ባያገኙም ሕጋዊ መሆናቸውን የሚያመላክቱ የልማት እንቅስቃሴዎች ውስጥ ተሳታፊ እንደነበሩ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹የአከራይ ተከራይ ግብር ለመክፈል የሚመለከተው አካል ከቀናት በፊት አነጋግሮን ነበር፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ይኼንን እየተነጋገርን ባለንበት ሰዓት ደብዳቤው እንደ ዱብ ዕዳ ዓርብ ወጪ ተደርጎ ቅዳሜ እጃችን ላይ ገባ፡፡ በአራት ቀናት ውስጥ ምን ማድረግ እንችላለን?›› ብለው ሌላው ቢቀር እንዲወጡ የተሰጣቸው የጊዜ ገደብ ነገሮችን ያላገናዘበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ቀረልኝ የሚሉት ተከራዮች ይኖሩበት የነበረው ቤትም እንደማይፈርስ ማረጋገጫ የለም ይላሉ፡፡ ምክንያቱም ከቀናት በፊት በእጃቸው የገባው በኦሮሚፋ የተጻፈው ደብዳቤ የቱ እንደሚፈርስና የቱ እንደሚቀርላቸው አይገልጽም፡፡

አካባቢውን በአንድ ጊዜ ወደ ፍርስራሽነት የቀየረው ዘመቻ በርካቶችን ሐዘን ላይ ጥሏል፡፡ ለገጣፎ የሚገኘው የካ ዳሌ 03 ቀበሌ ልጅ አዋቂ ሳይል ሁሉም በአንድነት የሚያነባበት መንደር ሆኖ ነበር ያረፈደው፡፡ እንደ ነገሩ ተበታትነው ከሚታዩ የቤት ዕቃዎች፣ የቆርቆሮና የፍርስራሽ ክምር ባሻገር የሚገቡበትን ያጡ በትካዜ የተዋጡ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡ ማረፊያ እንዳጡ ሁሉ በየመንገዱና በየጥጋጥጉ እንደቆሙ ይተክዛሉ፡፡ የደረሰባቸውን የሰሙ ዘመድ አዝማዶች ከያሉበት እየሄዱ እከሌን ዓይታችኋል እያሉ የዘመዶቻቸውን አድራሻ ሲፈልጉ ታይተዋል፡፡ ጥቂት የማይባሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ‹ቤት ለእምቦሳ› ብለው የመረቁላቸው ቤቶች ወደ ፍርስራሽነት ተቀይረዋልና ሜዳ ላይ ቆመው ያወራሉ፡፡ ምርር ብለው የሚያለቅሱ ዘመዶቻቸውን ያፅናናሉ፡፡ ሰብሰብ ሲሉ ‹የአንተም ቤት ፈረሰ?› እየተባባሉ የቁም ቅዠት የሆነባቸው ክስተት በሌላው ላይ ደርሶ እንደሆነ ይጠያየቃሉ፡፡ ‹የእኔ ቤት እዚያ ጋ ነበር› እያሉ ነው የፈረሰባቸውን ለሰዎች የሚያሳዩት፡፡ የፈረሰባቸውን ሲያፅናኑ የቆዩ ደግሞ ተራው የእነሱ ሆኖ ቤታቸው ሲፈርስ እያዩ እንደ አዲስ ይደነግጣሉ፣ ያለቅሳሉ፡፡

“100 የሚደርሱ ሰዎች ሆ ብለው መጥተው አንድ፣ ሁለት፣ ሦስት ብለው ግድግዳ ገፍተው ሲንዱ ማየት ግራ ያጋባል፡፡ ከማልቀስ ውጪ ምንም ማድረግ አይቻልም፤” ይላሉ ወይዘሮ መቅደስ፡፡ የሚፈርሰውን ቤት መታደግ ባይቻልም ጥረው ግረው ያፈሩት ንብረት በፍርስራሽ እንዳይዋጥ ጎረቤት ተሯሩጦ ለማትረፍ ይረባረባል፡፡

ቄስ ኪሮስ ዓለምነህን ሪፖርተር ያገኛቸው ከፈረሰው ቤታቸው ውስጥ የወጣ ንብረታቸውን በጎረቤቶቻቸው ዕገዛ ወደ አንድ በኩል ሲቆልሉ ነበር፡፡ ቄሱ በሆነው ነገር ከመደንገጣቸው የተነሳ ግራ መጋባት ይታይባቸዋል፡፡ ጎረቤቶቻቸው ግቢያቸውን ሞልተው የተበተነውን ንብረታቸው ዝናብ እንዳይመታው ቆርቆሮ ይመቱላቸዋል፡፡

እናቶች በየጥጋጥጉ እንደተቀመጡ ያለቅሳሉ፡፡ ከአርሶ አደር ላይ በ250 ሺሕ ብር የገዙትን ቤት አፍርሰው በሚፈልጉት ዲዛይን ለማሠራት ብዙ ገንዘብ ማፍሰሳቸውን፣ ቤቱን የሠሩትም በ2003 ዓ.ም. እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ቦታውን ገዝቶ ቤት ለመሥራት ከዘመድ አዝማድ ብዙ ገንዘብ መበደራቸውንና እስካሁንም ያልተከፈለ 80 ሺሕ ብር የሚሆን ውዝፍ ዕዳ እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡

ቄስ ኪሮስ በአካባቢው ሕጋዊ ነዋሪ መሆናቸውን የሚያሳይ የቀበሌ መታወቂያ አላቸው፡፡ ለመንገድ፣ ለውኃና ለኤሌክትሪክ የከፈሉበት ደረሰኝም አላቸው፡፡ በሌሎች ማኅበራዊ ግዴታዎች ክፍያ የፈጸሙባቸው ሕጋዊ ደረሰኞች ይዘዋል፡፡ የመኖሪያ ቤት ሽያጭ ውልም በእጃቸው ይዘዋል፡፡

‹‹ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ዕዳ ላይ ነው ያለሁት፡፡ ቤቱን ለመገንባት ከ500 ሺሕ ብር ከላይ አውጥቻለሁ፤›› በማለት፣ ዕዳቸውን ከፍለው በወጉ መኖር ሳይችሉ የቤታቸው መፍረስ የተደበላለቀ ስሜት እንዳሳደረባቸው ይናገራሉ፡፡ ቤቱን በአስቸኳይ ለቀው እንዲወጡ የሚያሳስበው ደብዳቤ የተጻፈውና እጃቸው ላይ የደረሰው በአጭር ጊዜ ነው በማለት፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ጊዜው እጅግ አጭር እንደሆነና ነገሩን ለመረዳትም ፋታ ሳይሰጣቸው ሕይወታቸው እንዳልነበረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡

ሌላው ቢቀር ቀልባቸውን ሰብስበው ንብረታቸውን በመልክ መልኩ ለማሰናዳት እንኳ አልሆነላቸውም፡፡ ሕጋዊ ነዋሪ መሆናቸውን የሚመሰክሩ ሰነዶችን ቅጂ እንደያዙ ፍርስራሽ የዋጠው ቅጥር ግቢ ውስጥ ቆመዋል፡፡ ዕዳ ገብተው የሠሩት ቤት ፈራርሶ ማየታቸው በቤታቸው እንግድነት እንዲሰማቸው እንዳደረጋቸው ይናገራሉ፡፡

ከጎናቸው ሆኖ የሚያፅናናቸው የ29 ዓመቱ አቶ ቀናው በላይ ደግሞ 150 ካሬ ላይ ያረፈው ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ፈርሶበት ሜዳ ላይ መቅረቱን ይናገራል፡፡ ደሳሳ ቤት የነበረውን ቦታ በ2004 ዓ.ም. ገዝቶ ከ300 ሺሕ ብር በላይ አውጥቶ የብሎኬት ቤት እንደሠራ፣ ባለትዳርና የልጅ አባት መሆኑን፣ በቴክኒክና ሙያ ከሰባት ዓመታት በፊት በዲፕሎማ ቢመረቅም፣ በተማረበት ሙያ ሥራ ማግኘት አለመቻሉን ያስረዳል፡፡

ቤተሰቡን የሚያስተዳድረውም ፑል ቤት ተቀጥሮ እየሠራ በሚከፈለው 1,500 ብር ቢሆንም፣ የራሱ የሚለው ቤት ስለነበረው ግን ብዙም እንደማይቸግረው፣ ዓለም የተደፋበት የመሰለው ሕገወጥ ነህ ተብሎ ቤቱ ሲፈርስበት መሆኑን ገልጿል፡፡ ‹‹ቤቴ የፈረሰው ማክሰኞ ነው፡፡ ‹‹አሁን ያለሁት አንድ ወዳጄ ዘንድ ተጠግቼ ነው፡፡ መንግሥት አካባቢውን ለማልማት ፈልጎ ከሆነ ደስ ይለናል፣ ግን እኛ የት ሄደን እንውደቅ?›› ሲል ይጠይቃል፡፡ ‹‹ከአሁን በኋላ የሚጠብቀኝ የጎዳና ሕይወት ነው፡፡ ሚስቴንም ወደ ቤተሰቦቿ እልካለሁ፡፡ ከቻሉ ሁላችንንም ወደ ትውልድ ቀዬአችን የምንመለስበትን ገንዘብ ይስጡን፤›› ይላል፡፡

ቴሌቪዥን፣ ፍሪጅ፣ ቁም ሳጥን ሳይወጣ የፈረሰባቸው፣ ፅዋ እንኳ ሳይወጣ በላያቸው የፈረሰባቸው፣ እንዲሁም ሁኔታው በፈጠረባቸው ድንጋጤ ከታመሙና ራሳቸውን ስተው ከወደቁ ባሻገር የከፋ ነገር የገጠማቸውም መኖራቸው ይሰማል፡፡

ጎረቤቶቿ ዓረብ አገር ሠርታ ባጠራቀመችው ገንዘብ ከጎናቸው ቤት ገዝታ እንደምትኖር፣ ቤቱ ላይዋ ሲፈርስ ግን ተስፋ ቆርጣ ራሷን ማጥፋቷንና አፍራሽ ግብረ ኃይሉ በአምቡላንስ እንደወሰዳት የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡ አስከሬኗ የትና በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንዳለም አይታወቅም ብለዋል፡፡ ዘመድ ይኑራት፣ አይኑራት የደረሰባትን ይስሙ፣ አይስሙ የሚያውቅ የለም ብለው ወደ ፍርስራሽነት የተቀየረው ቤቷና እሷ በአንድ አፍታ ታሪክ ሆነው መቅረታቸውን ይናገራሉ፡፡

ዱብ ዕዳ የሆነ ክስተት እንደ አቶ ጌታቸው ህያሴ ያሉ በአካባቢው ተሰሚነት ያላቸውን ሰዎች እንኳ አላለፈም፡፡ አቶ ጌታቸው ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ በአካባቢው እንደሚኖሩ ይናገራሉ፡፡፡ ዓምና ደግሞ የቀበሌውን ሊቀመንበር አስፈቅደው በዘመናዊ መንገድ ከብቶች ማርባት ጀምረዋል፡፡ በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር የካ ዳሌ 03 ቀበሌ አሉ የተባሉና ጠንካራ የልማት እንቅስቃሴ የሚያደርጉ እንደሆኑ ይነገርላቸዋል፡፡ ‹‹ይኼ ሁሉ ነገር ሲሠራ አብረውን ነው፡፡ ሁሉንም ነገር ያውቃሉ፡፡ ገና ሲጀመር ማስቆም ይችሉ ነበር፤›› ይላሉ፡፡ እንደ እሳቸው ገለጻ፣ ከብቶቹን ለማርባት ከ500 ሺሕ ብር በላይ ወጪ አድርገው ወደ ሥራ ሲገቡ የከለከላቸው አልነበረም፡፡ በዘመናዊ መንገድ የገነቡት የከብቶች በረት እንዲፈርስ ሲደረግ ግን ብዙ ነገር ማጣታቸውን ይናገራሉ፡፡

አቶ ጌታቸው የአካባቢው ወጣቶች የልማት ኮሚቴ አባል ናቸው፡፡ ነዋሪዎች ገንዘብ እያዋጡ መንገድና የተለያዩ የመሠረተ ልማት አውታሮች እንዲሟሉ እያስተባበሩ ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ሲሠሩ መቆየታቸው ይነገርላቸዋል፡፡ ነዋሪዎች ለተለያዩ የልማት እንቅስቃሴዎች አሥር፣ አሥር ሺሕ ብር እንዲከፍሉ ተደርጎ አካባቢው መልማቱን፣ ቤታቸው ሕገወጥ ተብሎ ከፈረሰባቸው ነዋሪዎች መካከል ሪፖርተር ያነጋገራቸው አብዛኞቹ ገንዘብ አዋጥተው አካባቢውን ማልማታቸው ይነገራል፡፡ ‹‹ኮሚቴአችን በልማት አንደኛ ተብሎ የተሰጠን የምስክር ወረቀት ቤት አለኝ፤›› የሚሉት አቶ ጌታቸው፣ ‹‹ከማዘጋጃ ቤቱ ጋር ተባብረው አካባቢውን ሲያለሙ የነበሩ ነዋሪዎች ሳይቀሩ ሕገወጥ መባላቸው ግር አሰኝቶኛል፤›› ይላሉ፡፡

የአካባቢው ነዋሪዎች ይህንን ያህል ገንዘብ አውጥተው ቤት ሲገነቡና አካባቢውን ሲያለሙ ዝም ተብሎ አሁን እንዲፈርስ መደረጉ ብዙዎችን አስቆጥቷል፡፡ ግንባታውን ከጅምሩ ማስቆም ሲቻል ገንዘብ እየተቀበሉ ፈቃድ የሚሰጡ የአመራር አካላት መኖር፣ ሌሎችም እንዲገነቡ ያደፋፍር እንደነበር ነዋሪዎቹ እየተናገሩ ነው፡፡ አብዛኞቹ ቤቶች ሲገነቡ አሥር ሺሕ ብርና ከዚያ በላይ ለቀበሌው አስተዳደር አካላት ይከፈል ነበር ተብሏል፡፡

ሕጋዊ ነዋሪ እንደሆኑ የሚያሳይ የቤት ቁጥር፣ የነዋሪነት መታወቂያ፣ የኤሌክትሪክና የውኃ አገልግሎት ካገኙ በኋላ ሕገወጥ ተብለው መፈናቀላቸው ሌላ አስተዳደራዊ ችግር ቢኖር ነው ያሉም አሉ፡፡፡ በቀናት ውስጥ ቤታቸውን እንዲለቁ የሚያዘው ደብዳቤ እንደደረሳቸው በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን በኩል ድምፃቸውን ያሰሙም፣ ‹ማስፈራሪያ እየደረሰን ነው፡፡ የምንንቀሳቀሰውም ተደብቀን ነው፡፡ አብረውን ችግሩን በተመለከተ በሚዲያ የተናገሩ ሁለት ሰዎችም ተይዘዋል› ብለዋል፡፡ ቤቶቹን ሲያፈርሱም ‹እስቲ ሚዲያዎች ይድረሱላችሁ፣ እናያለን› መባላቸውን ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

ቤቶቹን ሲያፈርሱ ከነበሩት መካከል በሦስቱ ላይ ግድግዳ ተደርምሶ ጉዳት እንደ ደረሰባቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡ አንደኛው ተጎጂ ሕይወቱ ወዲያው እንዳለፈ ቢናገሩም፣ የከተማው የኮሙዩኒኬሽን ባለሙያ የሞተ እንደሌለ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ቤቶቹን የማፍረስ ኃላፊነት የተሰጠው በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከንቲባ የሚመራው ገብረ ኃይል፣ አስለቃሽ ጭስና መሣሪያ በታጠቁ የፀጥታ አካላት ታጅቦ እንደነበር ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡

የለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ ሐቢባ ሲራጅ ከቀናት በፊት በሰጡት መግለጫ፣ ቤቶቹ እንዲፈርሱ የተወሰነው ከተማዋን በማስተር ፕላን የምትመራ ለማድረግ፣ እንዲሁም ምቹና ፅዱ ቦታ ለመፍጠር ነው ብለዋል፡፡ ይፈርሳሉ የተባሉ ከ12,000 በላይ የሚሆኑ ቤቶችም የከተማውን ማስተር ፕላን በመጣስ፣ ለአረንጓዴ ልማት የተተውና የተከለከሉ የወንዞች ዳርቻዎች ላይ የተገነቡ በመሆናቸውም እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ በሕግ ከተፈቀደላቸው ቦታ ውጪ ተጨማሪ ቦታ አጥረው የያዙ ባለሀብቶችም የዚሁ አካል ናቸው ብለዋል፡፡

ዓርብ የካቲት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. የጠቅላይ ሚኒስትር ፕሬስ ሴክሬታሪ አቶ ንጉሡ ጥላሁን፣ የክልሉ ገዥ ፓርቲ ኦዴፓ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የገጠርና ፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋና ሌሎች የክልሉ ሹማምንት በለገጣፎና አካባቢው ጉብኝት አድርገው ነበሩ፡፡ ከንቲባዋ ወ/ሮ ሐቢባ በሰጡት ገለጻ መሠረት፣ ከ12,300 በላይ ካርታ የሌላቸው ቤቶች በከተማዋ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ እየፈረሱ ያሉ ቤቶች በመንግሥት ይዞታ ውስጥ የሚገኙ መሆናቸውን ገልጸው፣ የማፍረስ ዕርምጃ ከመወሰዱ ሁለት ወራት በፊት ደብዳቤ ለባለ ይዞታዎቹ ደርሷል ብለዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ከመመሥረቱ ሦስት ዓመት በፊት ግብር የከፈሉበት ደረሰኝ ማቅረብ አለመቻላቸውን አስረድተዋል፡፡

‹‹ውኃና መብራት ማስገባት ዋስትና አይሆንም፤›› ያሉት ሪፖርተር ያነጋገራቸው የከተማው የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ ነፃነት ከበደ በበኩላቸው፣ ቤቶቹን የማፍረስ ዘመቻው በማስተር ፕላኑ መሠረት ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ግንባታ የተከናወነባቸው አንዳንዶቹ ቦታዎች መንግሥት ለልማት የሚፈልጋቸውና ካሳ የከፈለባቸው እንደሆኑም አስረድተዋል፡፡ ከአርሶ አደሩ እየገዙ የሠፈሩም አሉ ብለዋል፡፡ አለ ለሚባለው ችግር ተጠያቂው ከዚህ በፊት የነበረው የአስተዳደር አካል እንደሆነ፣ ከእነዚህም ውስጥ በሕግ እየተጠየቁ ያሉ ሰዎች መኖራቸውንና አሁንም ተጠያቂ የሚደረጉ ሌሎች መኖራቸውን፣ ከአርሶ አደሮችም የሚጠየቁ እንደሚኖሩ አስረድተዋል፡፡

ቤት የፈረሰባቸው ነዋሪዎችን የፌዴራል ዕንባ ጠባቂ ተቋም ባለሙያዎች ዓርብ የካቲት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በቦታው ተገኝተው እንዳነጋገሯቸው ታውቋል፡፡ ዘገባው የሪፖርተር ነው።

ድብቁ የኢትዮጵያ እስር ቤት ግፍ እና የወልቃይቱ ተወላጅ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ

ለገሠ ወልደሃና

Ethiopian General Attorney

አቶ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ የወልቃይት ጠገዴ ተወላጅ ነው። በአዲስ አበባ በንግድ ስራ ተሠማርቶ ውጤታማ ነገዴ መሆን የቻለ ሰው ነበር። በአዲስ አበባ ላይ ጎጆ ቀልሶ ንግዱን እያከናወነ ይኖር የነበረው አቶ ዘካርያስ ነሐሴ 14 ቀን 2000 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ በደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ። በቁጥጥር ስር ያዋሉት ግለሰቦች መጀመሪያ አዲስ አበባ ፓሊስ ኮሚሽን (በተለምዶ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ)አሰሩት። ከተወሰነ ወራት በኋላ ወደ ቦሌ ፓሊስ መምሪያ ቀየሩት። እንደገና ከወራት በኋላ አራዳ ክ/ከተማ የሚገኝ ፓሊስ ጣቢያ አዛወሩት። ከዚህም ከወራት በኋላ ልደታ ክ/ከተማ የሚገኝ ፓሊስ ጣቢያ ያዛወራል። ከልደታ ወደ ቃሊቲ ተወስዶ ለወራት ከታሰረ በኋላ ወደ ቅሊንጦ በመጨረሻም አሁን ወደሚገኝበት ቃሊቲ አዛውረው ያስሩታል።

ከእስር ቤት እስር ቤት እያዘዋወሩ ያሰሩት አቶ ዘካርያስ ከሶስት አመት ክርክር በኋላ ፍርድ ቤት ነፃ ይለዋል። “እስካሁን ያሰረኝን ሳላውቅ። ሶስት አመት ተንገላታሁ። አሁን ነፃ ተብያለሁ። ፍቱኝ” የሚል ጥያቄ ያቀርባል። “አዎ! በዚህ ነፃ ተብለሃል። ግን ተጠይቆብሃል ተብሎ ፍች ሲጠብቅ በይግባኝ እስር ቤት ሆኖ ለ2 ዓመት በክርክር ያሳልፋል። ከ5 ዓመት እስር በኋላ ነፃ ይወጣል። “አሁን ነፃ ወጥቻለሁ ፍቱኝ!” የሚል ጥያቄ ያቀርባል። “አዎ በዚህ ክስ ነፃ ተብለሃል!ግን ሌላ የ17 ዓመት ፍርድ አለብህ!” ይባላል። 

አቶ ዘካርያስም “ማን ከሶኝ? መቼስ ክስ ደረሰኝ? በየትኛው ፍርድቤት ቀርቤ ተከራክሬ ነው የተፈረደብኝ? የፈረደብኝ ፍርድ ቤት ውሰዱኝ!” የሚል ጥያቄ ያቀርብና ፍርድ ይወስዱታል። ፍርድ ቀርቦ “17 ዓመት የተፈረደብኝ በምን ወንጀል ነው? ክስ አልደረሰኝ። የመሳሰለውን ጥያቄ ያቀርባል። ዳኛው “እኛ አልፈረድንም። የምናውቀው ነጻ መውጣትህን ነው።” ይለዋል። “ታዲያ ማነው 17 ዓመት የፈረደብኝ ማነው? እኔ ተከራክሬ ነፃ ወጥቻለሁ መፍቻ ፃፉል!! የሚል ጥያቄ ለዳኛ አቅርበ። ዳኛው “ያንተ ጉዳይ አስቸጋሪ ነው። መፍቻ አልፅፍም” የሚል መልስ ይሰጠዋል። ዘካርያስ ከዳኛ ጋር ሰጣ ገባ ይጀመራል። ዳኛው ለዘካርያስ መፍቻ ከመጻፍ ይልቅ 6 ዓመት ቅጣት ጨምሮ በድምሩ የ24 ዓመት ፍርድ ተፈርዶበት ወደ ቃሊቲ እስር ቤት በልዩ ቅጣት ኮንቴነር ቤት ወደሚባለው ጨለማ ቤት ይወረወራል።

ዘካርያስ ጉዳዩን የሚከታተሉለት ጠበቆች ቢያቆምም በስውሩ እጅ የሱን ጉዳይ እንዲተው በማስፈራራት 8 ጠበቆች አባረውበታል። በዚህ ሁኔታም ሆኖ ዘካርያስ ተስፋ ሳይቆርጥ ለፍትህ ሚኒስትር አቤቱታ ያቀርባል። ፍትህ ሚኒስቴር በዚህ የመዝገብ ቁጥር ዘካርያስ ገ/ፃዲቅ የሚባል ሰው አናውቅም። “በዚህ መዝገብ ቁጥር አማን ከሊፋ የሚባል ሰው ነበር የተከሰተው እሱም በሽምግልና ጉዳዩ በማለቁ መዝገቡ ተዘግቷል” የሚል መልስ ፍትህ ሚኒስትር ለዘካርያስ ገ/ፃዲቅ ደብዳቤ ይልካል። 

ዘካርያስም አቤት የሚልበት ተቋም በማጣቱ ከነሐሴ 14 ቀን 2000 ዓ.ም. ጀምሮ በልዩ ልዩ እስር ቤት ዛሬም ድረስ የመከራ ጊዜውን እየገፋ ይገኛል። በተለይ ቃሊቲ እስር ቤት ከገባበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ሰኔ 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ከሰው ተለይቶ መታሰሩን ገልጿል። ከሰኔ 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ቃሊቲ ዞን 6 ከሰው ተቀላቅሎ ማን እንዳሰረው ማን እንዳሳሰረው ለምን እንደታሰረ ሳያውቅ 11 ዓመታት አስቆጥሯል። የግፍ እስረኛው ምንም እንኳ ከተመሰረተበት ክስ በተደጋጋሚ በፍርድ ቤት ነፃ ቢባልም ይህ እስከተዘገበበት መስከረም 20 ቀን 2011 ዓ ም ቃሊቲ ወህኒ ቤት አልወጣም። ዘካርያስ ገብረፃዲቅ አሁንም ፍትህ ይሻል።

ለመንግሥት ሀላፊዎች 

ላለፉት 27 ዓመታት ልክ እንደ ዘካርያስ ገብረፃዲቅ በግፍ የታሰሩ በርካታ ዜጎች በማንነታቸው እና በአገዛዙ ሰዎች ቀጭን ትዕዛዝ በርካታ ዜጎች በግፍ ታስረው እንደሚገኙ የታወቀ ነው። በአሁኑ ሰዓት የመንግስትነት ስልጣን የጨበጣችሁ ሰዎች በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ እስር ቤቶች ላይ ፍተሻ በማድረግ ያለ አግባብ የታሰሩ ሰዎች ነፃ እንዲወጡ ታደርጉ ዘንድ ጥሪየን አቀርባለሁ።
ለሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች 

ዘካርያስ ገብረፃዲቅ እና እንደሱ በግፍ የታሰሩ ወገኖችን ጉዳይ በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ እስር ቤት የተወረወሩ ወገኖችን ጉዳዩ በማጣራት ከግፍ እስር ነጻ እንዲወጡ ጥረት እንድታደርጉ ጥሪ አስተላልፋሁ።

የነኦቦ በቀለ ገርባ መግለጫና አዲስ አበባ 

አቻምየለህ ታምሩ

ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንደጻፍነው አዲስ አበባ ፊንፊኔ አይደለችም። ፊንፊኔ ወይንም ፍልውሃ አዲስ አበባ ውስጥ ዛሬም ድረስ የምትገኝ አንድ ትንሽ መንደር እንጂ በሁለንተናዊ መልኩ ሰፊና ግዙፍ ከሆነችዋ አዲስ አበባ ጋር አንድ አይደለችም። እነኦቦ በቀለ ገርባ በዛሬው መግለጫቸው አዲስ አበባን ፊንፊኔ አድርገው ለማቅረብ ቢኖክሩም ያቀረቧቸውን መንደሮች ስም ዝርዝር ለሰማ ግን እነ ኦቦ በቀለ አዲስ አበባ ማለት ፊንፊኔ ማለት እንዳልሆነ ሳይታወቃቸው ነግረውናል። 

Addis Ababa municipality office
ፎቶ፡ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር

እነ ኦቦ በቀለ የአዲስ አበባን ጉዳይ በተመለከተው ባወጡት በዛሬው መግለጫቸው፤ 
«ዛሬ ፊንፊፌ ከተማ የምትገኝበት ስፍራ የኤካ፣ የጉለሌና የገላን የኦሮሞ ጎሳዎች የዕምነት፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማዕከል እንደነበረች ማንም የሚክደው አይደለም። ነገር ግን እነዚህ ጎሳዎች የመኖሪያ፣ የእርሻና የግጦሽ መሬታቸውን በኃይል ተነጥቀው እንዲጠፉ ተደርገዋል» ሲሉ ተናግረዋል። 

እነ ኦቦ በቀለ ገርባ ይህንን የውሸት ታሪክ የተማሩት ከኦነግ የፕሮፓጋንዳ ጸሐፊዎች ነው። ኦቦ በቀለ እንደ ዩኒቨርሲቲ መምህር ይህ የኦነግ ፕሮፓጋንዳ እውነት ስለመሆኑ መጽሐፍትን አገላብጠው ወይንም ምርምር ሰርተው አላጣሩትም። ጥናትና ምርምር ሳያካሂዱ ተረት እየደገሙ ትውልድ ሊያሳስቱበት ይችላሉ ይሆናል፤ የአገራችንን ታሪክ ላነበብንና ለመረመርን ሰዎች ግን ይህ የነ ኦቦ በቀለ ገርባ የውሸት ታሪክ አታውቁም ደንቆሮ ናችሁ ብሎ ከመስደብ አይተናነስምና ዝም ብለን ልናየው አንሻም። ስለሆነም የመረመርነውን ዶሴ ልንመዝ ተገደናል። ዶሴው ሲወጣ እነ ኦቦ በቀለ ገርባ የሚነግሩን የፈጠራ ታሪክ ቅቡልነት እስከምን ድረስ እንደሆነ እንደሚከተለው ይታያል።

የዐፄ ዳዊት ከተማ በረራ በግራኝ ወረራ ከወደመች ከሁለት መቶ አመታት በኋላ ሸዋን ጎብኝተው ታሪክ ጽፈው ካለፉ የውጭ አገር ሰዎች መካከል ጀርመናዊው ቄስ Johann Ludwig Krapf ቀዳሚው ነው። ቄስ Johann Krapf እ.ኤ.አ. በ1840ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ሸዋን የጎበኘ ሲሆን ከንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ጋር በተለያዩ ዘመቻዎች አብሮ በመጓዝ የተለያዩ የሸዋን አካባቢዎች ጎብኝቷል። Krapf እ.ኤ.አ. በ1840 ዓ.ም. ከንጉሡ ጋር በእግሩ ረግጦ ካለፈባቸው የሸዋ አካባቢዎች መካከል የዛሬው የአዲስ አበባ አካባቢ አንዱ ነው። Krapf ይህን የአዲስ አበባ አካባቢ በ1840ዎቹ ከጎበኘ በኋላ እ.አ.አ. በ1860 ዓ.ም. ከጀርመን ወደ እንግሊዝኛ ተተርጉሞ በታተመው «Travels, researches, and missionary labours, during an eighteen years’ residence in Eastern Africa» መጽሐፉ ገጽ 25 ላይ ዛሬ አዲስ አበባ በተባለው አካባቢ እነ ማን ይኖሩበት እንደነበር እንዲህ ብሏል፤
«The first campaign which I thus made in January and February 1840 led me into the territories of the tribes of the Abeju, Woberi, Gelan, Dembichu, Finfini, and of the Mulofalada, Metta Robi, Wogidi, Metta and Kuttai, all Gallas» 
ይህ የ Krapf ጽሑፍ ወደ አማርኛ ሲመለስ፤ «በጥር እና የካቲት 1833 ዓ.ም. የጀመርነው የመጀመሪያው ዘመቻ የአብቹ፣ የገላን፣ የወበሪ፣ የደምብቹ፣ የፊንፊኔ፣ የሞሎፋላዳ፣ የሜታ ሮቢ፣ የወግዲ፣ የቤኤና የጉታይ ኦሮሞ ጎሳዎች በሚኖሩበት ወሰደኝን» እንደማለት ነው። 

ይህ የKrapf ምስክርነት የሚነግረን ፊንፊኔ፣ የካ፣ ጉለሌና ገላን የተባሉት ቦታዎች በየራሳቸው የኦሮሞ ጎሳዎች የሚኖሩባቸው መንደሮች እንደሆኑ እንጂ እነ በቀለ ገርባ ሊነግሩን እንደፈለጉት ፊንፊኔ የካ፣ ጉለሌና ገላን የተባሉ የኦሮሞ ጎሳዎች የመኖሪያ፣ የእርሻና የግጦሽ መሬት እንደነበረች አይደለም። በሌላ አነጋገር ፊንፊኔ ልክ እንደ የካ፣ ገላንና ጉለሌ ራሷን የቻለች መንደር፤ የየካ፣ የገላንና የጉለሌ ጎሳዎች አካል ያልሆነ የራሷ ጎሳ ይኖርባት የነበረች እንጂ የየካ፣ የጉለሌና የገላን ጎሳዎች የመኖሪያ፣ የእርሻና የግጦሽ ቦታ አልነበችም። ለዚህም ነበር አዲስ አበባ ማለት ፊንፊኔ ማለት አይደለም ስንል የከረምነው። አዲስ አበባ ፊንፊኔ/ፍል ውሃ ፣ ገላን፣ የካ፣ ጉለሌ፣ አቧሬ፣ ግንፍሌ፣ ወዘተ የሚባሉ መንደሮችን በውስጧ የያዘች ከተማ ናት እንጂ በፊንፊኔ ልክ ተሰፍታ በፍል ውሃ ልክ የታጠረች አንድ ትንሽ መንደር አይደለችም። በKrapf ምስክርነት መሠረት አዲስ አበባን ፊንፊኔ ብሎ መጥራት አዲስ አባን ገላን ብሎ እንደመጥራት፤ ከጉለሌ ጋር እኩል እንደማድረግና ከየካ ጋር እንደማስተካከል ነው። ለዚያም ነው አዲስ አበባን ፊንፊኔ ብሎ መጥራቱ ምንም አይነት የታሪክ ተጨባጭነት የማይኖረው። 

Krapf አዲስ አበባን አካባቢ በጎበኘበት ወቅት በአካባቢው ፊንፊኔ፣ የካ፣ ጉለሌና ገላን የሚባሉ መንደሮች እንደነበሩ ብቻ ጠቅሶ አያበቃም። በፊንፊኔ፣ በየካ፣ በጉለሌና በገላ የሚኖሩት የኦሮሞ ጎሳዎች የቱለማ ኦሮሞዎች እንደሆኑ ይነግረንና እነዚህ ኦሮሞዎች ወደነዚህ ቦታዎች መቼ እንደሰፈሩም ጭምር በገጽ 234 ላይ እንዲህ ሲል ጽፏል፤ 
<>
ይህ ታሪክ ባጭሩ ወደ አማርኛ ሲመለስ፤ «የቱለማ፣ የከረዩና የሜጫ ኦሮሞዎች የጉራጌና የሸዋን አካባቢዎች ኗሪዎች ግራኝ ሲያፈናቅላቸው ኦሮሞዎች ወረሩና ለምለሙን ምድር የራሳቸው አደረጉት» እንደ ማለት ነው። 

ለዚህም ነበር ከዚህኛው ጽሑፍ ቀደም ሲል በጻፍሁትና ለጸጋዬ አራርሳ በሰጠሁት ምላሽ ላይ የዐፄ ዳዊትንና የዐፄ ልብነ ድንግልን ልጆች ያያታቸው ዋና ከተማ ለነበረችው የቀድሞዋ በረራ የኋላዋ እንጦጦና የዛሬዋ አዲስ አበባ ዙሪያ መጤና የዋና ከተማችን እንግዳ አድርጎ ማቅረቡ ነውረኛነት ነው ያልሁት። በግራኝ ወረራ ምክንያት የሞቱና ከርስታቸው የተፈናቀሉትን ለአዲስ አበባ እንግዳና መጤ አድርጎ በማቅረብ ኋላ የመጣውን ኦሮሞን ብቸኛ የአዲስ አበባ ባለቤት አድርጎ ለማቅረብ መሞከር ነውረኛነትን ከማሳየት ባለፈ ታሪካዊ እውነታውን አይለውጠውም።

ሌላው እነ በቀለ ገርባ በመግለጫቸው ያነሱት አስቂኝ ነገር ስለ የካ፣ ጉለሌና ገላን ኦሮሞዎች በኃይል ተነቅለው እንዲጠፉ ተደርገዋል የሚለው የመነቸከ ተረት ተረት ነው። አዲስ አበባ እንደገና ስትመሰረት የተመሰረተችው ገላን፣ የካና ጉለሌ ላይ አይደለም። አዲስ አበባ እንደገና የተቆረቆረችው ፍል ውሃ አካባቢ የተገኘውን በግራኝ ዘመን የፈረሰ የማርያም ቤተ ክርስቲያን መሠረት አድርጎ የተሰራውን የንጉሠ ነገሥቱን ቤተ መንግሥት [የዳግማዊ ምኒልክን ቤተ መንግሥት] ማዕከል በማድረግ ነው። ከዚህ መሠረትና አንድ ሺህ ከማይሞሉ ቤቶች ተነስታ ዛሬ አዲስ አበባ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የግል ይዞታ የሆኑ ቤቶችን በማቀፍ በሁለንተናዊ መልኩ የሰፋችና የገዘፈች አለማቀፍ ከተማ ሆናለች። 

እነ ኦቦ በቀለ አዲስ አበባ ስትቆረቆር የገላን፣ የካና የጉለሌ ጎሳዎች በኃይል ተነቅለው ነው ያሉት የፈጠራ ታሪክ ነው። እንኳን ያኔ ዛሬም የባለርስቶቹ ዘሮች ከልዩ ልዩ ኢትዮጵያውያን ጋር ተዋልደውና በዝተው ባያቶቻቸው ርስት ላይና በተለያዩ የአዲስ አበባ ክፍሎች ይኖራሉ። ከአዲስ አበቤው ጋር ተዋልደው፣ እንደ ሌላው ራሳቸውን አቅልጠው አዲስ አበቤ ስለሆኑ ዛሬ ላይ ከብት የሚያስግጡና እርሻ የሚያርሱ ግን አይደሉም። ከብት ማጋጥንና እርሻ ማረስን እንደ ሥራ ምርጫ እንኳን የዛሬዎቹ ልጆቻቸው የያኔዎቹ አያቶቻቸውም ትተውት ከተሜ ሆነው ነበር ይኖሩ የነበረው። 

ለዚህ አንድ ምሳሌ የጉለሌውን ባላባት የደጃዝማች አበቤ ቱፋ አባት ቱፋ ሙናን መጥቀስ ይቻላል። የልጃቸው የአበቤ ቱፋ ቤት ዛሬም እዚያው ጉለሌ ውስጥ ይገኛል። እነ ኦቦ በቀለ እንደተነቀሉ የሚነግሩን አበቤ ቱፋና መሰል የጉለሌው ባላባቶች ከነራስ ጎበና ጋር አገር ያቀኑ ናቸው። ኦነጋውያን ግን መሬቱን እንጂ ሰዎቹን ስለማይፈልጓቸው እነዚህ አገር አቅኝዎች «ጎበናዎች» እያሉ በማሸማቀቅ ሲያሳድዷቸው ነው የኖሩት። 

የጉለሌው ባላባት ደጃዝማች አበቤ ቱፋ እነ በቀለ ገርባ እንዳሉን እንኳን ከቦታቸው ሊጠፉና ሊነቀሉ ይቅርና አበቤ ቱፋ ካለፉ ከዘመናት በኋላ የተፈጠረው ድምጻዊ ካሳ ተሰማ፤
እነ አበቤ ቱፋ እንደገሩት ፈረስ፣
ወርዶፋ ጨንገሬ እንደገራው ፈረስ፣
ጡቷ ደንገላሳ ይላል መለስ ቀለስ፤
ብሎ ዘፍኖላቸው ከጉለሌ አልፎ ዝናቸውን በመላ አዲስ አበባና በመላ ኢትዮጵያ ተክሎላቸዋል። ደጃች አበቤ ጽኑ ክርስቲያን ነበሩ። ሱሉልታ ውስጥ የሚገኙ የጥንት ቤተ ክርስቲያኖችን ያሰሩት እሳቸው ናቸው። ከፍ ሲል እንዳመለከትሁት ቅርሳቸው ግን ከሱሉልታ ቤተ ክርስቲያኖች አልፎ ዛሬም ድረስ ጉለሌ በሚገኘው ግቢያቸው ውስጥ ልጆቻቸውና የልጅ ልጆቻቸው ወልደው ተዋልደው አዲስ አበቤ ሆነው ይኖሩበታል። 
ወርዶፋ ጨንገሬም ሌላው አዲስ አበባ ውስጥ ፈረስ የሚያስጋልብ ርስት የነበራቸው የአካባቢው ባላባት ነበሩ። አበሻን የናቀን አንድ ትቢተኛ ፈረንጅ በጦርና ጋሻ ፍልሚያ ተዋግተው ድል ካደረጉ በኋላ በዐፄ ምኒልክ ፊት ቀርበው፤ 
ዘራፍ አካኪ ዘራፍ፣ 
ከጥንት እስከ ዛሬ፣ 
ጀግና ላልነጠፈባት ሀገሬ፣
ዛሬም አሸንፏል ወርዶፋ ጨንገሬ፤ 
ዘራፍ ዘራፍ አካኪ ዘራፍ.. . 
እያሉ ፎክረው ለሰሩት የጀግንነት ተግባራቸው ንጉሠ-ነገሥቱ ካመሰገኗቸው በኋላ የሚፈልጉትን ቢጠይቁ እንደሚደረግላቸው ቃል ገብተውላቸው ጃን ሜዳ አካባቢ ያለውን ሰፈር ሰፈር ልባቸው የፈቀደውን ያህል በፈረሳቸው ጋልበው ጠይቀው የተሰጣቸው ባላባት ናቸው። የሳቸው ዘሮችም ዛሬም እዚያው ይኖራሉ። 
የሱሉልታ ገዢ የነበሩት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አጎትና የልዑል ራስ መኮነን ወንድም ደጃዝማች ኃይሌ ጉዲሳም ዛሬ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሚገኝበት የቀድሞው ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ባለ ርስት ናቸው። የደጃች ኃይሌ አባት ኦቦ ጉዲሳ ቦጃ የአካባቢው ታዋቂ ዳኛ ነበሩ። ይህንን የሚያውቁት የሱሉልታ ኦሮሞዎች ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ዲኔግዴ ገዢ ተደርገው ቢሾሙላቸው «የጌታችንን ልጅ ይሹሙልን» ብለው ለዳግማዊ ምኒልክ አቤት በማለታቸው አባ መላን አንስተው ደጃች ኃይሌ ጉዲሳን ገዢ አድርገው ሾመውላቸዋል። የፊንፊኔውን የደጃች ኃይሌ ርስት ወራሽ የሆኑት የወንድማቸው ልጅ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ናቸው። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ደግሞ የግል ርስታቸው በሆነው ቦታ ላይ ከአባታቸው በርስትነት ያገኝትን በመጨመር ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥትን አሰርተው የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በማድረግ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በርስትነት ማስረከባቸውን ባለፈው ከጻፍነው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ታሪክ ጋር ባያያዝነው በንጉሠ ነገሥቱ በራሳቸው የተፈረመ የንብረት ማስረከቢያ ዶሴ ላይ አሳይተናል። 

እንግዲህ! ፊንፊኔ፣ የካ፣ ጉለሌና ገላን እዚያው አዲስ አበባ ውስጥ ያሉ የተለያዩ መንደሮች እንጂ አዲስ አበባና ፊንፌኔ አንድ አለመሆናቸውን፤ የየካ፣ ጉለሌና ገላን ጎሳዎች ልጆችም ዛሬም ድረስ አዲስ አበቤ ሆነው ከቅድሚያ አያቶቻቸው ከወረሱት ርስት መካከል ከፊሉን ሸጠው፤ አብዛኛውን ደግሞ እን ኦነግ በዋናነት ባወጡት የደርግ የከተማና ትርፍ ቤት ደርግ ተወርሶባቸው፤ በተረፈው ርስታቸው ላይ ግን አሁንም ድረስ ስም የሚያስጠሩ ልጆች በቦታው ላይ የሚገኙ መሆናቸውን ጉለሌ በሚገኘው የባላባቱ የአበቤ ቱፋ ቤት በመሄድ ዘሮቻቸውን አግኝቶ «በኃይል ተነጥቀው እንዲጠፉ ተደርገዋል» የሚለውን የኦነግ ተረት የፈጠራ ወሬነት ማረጋገጥ ይቻላል። 

በመጨረሻ «ሕገ መንግሥት» ለተባለው የወያኔ ፕሮግራም ጠበቃ ሆነን ካልቆምን ሞተን እንገኛለን ላሉን ለነ ኦቦ በቀለ ሁለት ጥያቄዎች ማቅረብ እፈልጋለሁ። እንደሚታወቀው «ሕገ መንግሥት» ተብዮው ሲረቀቅ አማራ አልተሳተፈበትም። አክብሩ እያላችሁን ያላችሁት እኛ ያልተሳተፍንበትን የቅሚያ ደንብ ነው። እኛ አማሮች «ሕገ መንግሥት» የተባለውን ከማንፈልገባቸው በርካታ ምክንያቶች አንዱ እኛ ተወክለንበት የተዘጋጀ ባለመሆኑ ስለማይመለከተን ነው። እኔ ግን እንደ አንድ አማራ ወንድሜ የምለው የኦሮሞ ሕዝብም ሆነ ማናቸውም ኢትዮጵያዊ ሳይሳተፍ በተረቀቀና በጸደቀ ሕገ መንግሥት ተገዛ ብዬ የምጠይቅበት ህሊና የለኝም! ኦሮሞን ባልተሳተፈበት ሕገ መንግሥት እንዲገዛና ሕጉን እንዲያከብር መጠየቅ በአፓርታይድ ሕግ፤ በቅኝ ግዛት ደንብ ተገዛ ብሎ እንደመፍረስ ያለ ደመኛነት ነው። አማራንም በተመሳሳይ መልኩ ባልተሳተፈበትና ባላጸደቀው ሕገ መንግሥት ተገዛ ብሎ መግለጫ እስከማውጣት ድረስ የሚያደርስ ስብዕና በሰው ቁስል እንጨት ስደድበት ከማለት የተለየ ነውረኛነት አይደለም!
 
የሆነው ሆኖ ነገሮችን እንዳሉ እንውሰድና ሕገ መንግሥት የተባለውን የወያኔ ፕሮግራም ካላከበራችሁ በሕልውናችን እንደመጣችሁ እንቆጥረዋለን ያሉንን እነ ኦቦ በቀለ ገርባን የሚከተሉትን ሁለት ጥያቄዎች መጠየቅ ወደድሁ፤ አንደኛ፡ በዶክተር ነጋሶ ፊት አውራሪነት ተዘጋጅቶ የጸደቀው ሕገ መንግሥት አንቀጽ 49(1) ላይ «የፌዴራሉ መንግሥት ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባ ነው» ይላል። ሆኖም ግን መግለጫ ያወጡት አምስቱም የኦሮሞ የፖለቲካ ፓርቲዎች ርዕሰ ከተማችንን አዲስ አበባ ብለው ጠርተው አያውቁም። ጤና ይስጥልኝ እነ ኦቦ በቀለ?! የፌዴራል መንግሥቱን ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባ ብሎ አለመጥራት ካላካበርነውና ካላስከበርነው ሞተን እንገኛለን የምትሉትን ሕገ መንግሥት መጣስ አይደለም? ነው ይህ ሕገ መንግሥት እንድናከበር የተፈረደብን እኛ ብቻ ነን? 

ሁለተኛ፡ ካላከበርነውና ካላስከበርነው ሞተን እንገኛለን የምትሉት የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ አንቀጽ 49(5) «አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሐል ትገኛለች» ይላል እንጂ «የኦሮምያ ክልል» አካል ናት አይልም። ይህ ከሆነ እናንተ መግለጫ ያወጣችሁት አምስቱ የኦሮሞ ፓርቲዎች «ፊንፊኔ ትናንትም፣ ዛሬም፣ ወደፊትም የኦሮምያ አካልና የኦሮሞ ሕዝብ መኖሪያ ናት» ያላችሁት የሕገ መንግሥት ጥሰት ነው። እናንተ ራሳችሁ ካላከበርነውና ካላስከበርነው የምትሉትን ሕገ መንግሥት አናት እያፈረሳችሁ ሌላውን በአፍራሽነት የመክሰስ የሞራል ልዕልና እንዴት ሊኖራችሁ ይችላል? እስቲ መልሱልን? ሲል እቻምየለህ ይጠይቃል።

ለሁለት ተከፍሎ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሶኖዶስወደ ቀድሞ አንድነቱ ተመለሰ

(ዳጉሚድያ)በመንግሥት ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ምክንያት ላለፉት 27 ዓመታት ለሁለት ተከፍሎ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወደቀድሞ አንድነቱ ተመለሰ። ከዚህ ቀደም መቀመጫውን “የሀገር ቤቱ እና በስደት ያለው ” በሚል በብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ የሚመራው በስደት አሜሪካ ፤ በብፁዕ አቡነ ማትያስ የሚመራ በሀገር ቤት ተከፍሎ የነበረው ሲኖዶስ ሐሙስ ታህሣሥ 19 ቀን 2010 ዓ ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በተገኙበት እርቀሰላም በመፈፀም ወደ ቀድሞ አንድነት መመለሱን የዕርቀ ስላሙ ኮሚቴ በይፋ አስታውቋል።

እርቀሰላሙ ከተፈፀመበት ዕለት ጀምሮ “በስደት ያለው ህጋዊው እና በሀገር ቤት ሲኖዶስ” የሚመራው መባሉ ቀርቶ ቤተክርስቲያኗ ከ27 ዓመታት በፊት እንደነበረው ወደ ቀድሞ አድነት በመመለስ በአንዲት “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሚል አንድ ስም እንደሚጠራ፥ በመላው ዓለም ያሉ የቤተክርስቲያኗ አስተዳደርም በአንድ ጥላ ስር ብቻ እንዲሆን የእርቀሰላሙ ኮሚቴ ሊቃነጳጳሳቱ በይፋ አስታውቀዋል።

በብፁዓነ ሊቃነ ጳጳሳቱ የተፈፀመው የእርቀ ሰላሙ ስምምነት እና አፈፃፀምም ዝርዝር ሁኔታውም ከዚህ እንደሚከተለው ተገልጿል።

4th-pat-his-holiness-abune-merqorewos-6th-pat-his-holiness-abune-mathias
ፎቶ፡ ከግራ ወደ ቀኝ ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ እና ብፁዕ አቡነ ማትያስ

-አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ በአንድ የቅዱስ ሲኖዶስ አመራር ትመራለች፤
-4ኛው ፓትርያርክ በጸሎት እና በቡራኬ፣ 6ኛው ፓትርያርክ በአስተዳደር ሥራ፤
-የኹለቱም ስም፣ቤተ ክርስቲያን ባለችበት ዓለም ሁሉ ዘወትር በጸሎት ይነሣል፤
-ሰማዕቱ አቡነ ቴዎፍሎስ ለሞት ከተላለፉበት ጀምሮ የቀኖና ጥሰት ተፈጽሟል፤
-ቅ/ሲኖዶስ፣ የቤተ ክርስቲያንን ክብር ባለማስጠበቁ ልጆቿን ይቅርታ ይጠይቃል፤
†††

-ጥሰቱን ለመከላከልና ሉዓላዊነቷን ለማስጠበቅ፣ቅዱስ ሲኖዶስ ደንብ ያዘጋጃል፤
-በኹለቱም ሲኖዶስ የተላለፈው ቃለ ውግዘት፣ በጋራ ምልዓተ ጉባኤ ይፈታል፤
-ከልዩነት በኋላ የተሾሙ ቅቡል ናቸው፤አጠራራቸው እንደ ቅደመ ተከተላቸው፤
-ለውጭ ቤተ ክርስቲያን፣የየሀገሩን ሕገ መንግሥት ያገናዘበ መመሪያ ይወጣል፤
-የስምምነቱን ተግባራዊነትና የአንድነቱን ፍጹምነት ልኡካን አባቶች ይከታተላሉ፤

Reconcilation Archbishop members
የእርቀሰላም ኮሚቴ አባላት የሆኑት ሊቃነጳጳሳት

ስለ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ መርቆሬዎስ

በሀገራችን ኢትዮጵያ በ1983 ዓ.ም. በተፈጠረው የመንግሥት ለውጥ የተነሣ አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ለሁለት ተከፍላ በሁለት ፓትርያርኮች የሚመሩ አንድ ሲኖዶስ ለሁለት ሲኖዶሶች መፈጠራቸው ግልጽ ነው። በዚህም የተነሣ አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከሁለት ዐሥርት ዓመታት በላይ በስደት ዓለም መቆየታቸው ይታወቃል። ስለኾነም የሁለቱን ቅዱሳን ፓትርያርኮች ቀጣይ ኹኔታ በተመለከተ በሁለቱም ቅዱስ ሲኖዶሶች የተወከሉት የሰላም ልኡካን ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሰላም በአደረጉት የጋራ ስብሰባ በሰፊው ከተወያዩ በኋላ እንደሚከተለው በአንድ ድምፅ ወስነዋል።

ሀ/ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ በፓትያርክነት ክብርና ደረጃ ወደ ቅድስት አገር ኢትዮጵያ እንዲመለሱ/እንዲገቡ፤

ለ/ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ወደ አገር ቤት ኢትዮጵያ ሲመለሱ በክብር የሚያርፉበትን የመኖሪያ ቦታ በተመለከተ ደረጃውን የጠበቀ በመንበረ ፓትርያርክ ግቢ ውስጥ ቦታ ተዘጋጅቶና የሚያስፈልጋቸው ሁሉ ተሟልቶ በክብር እንዲቀመጡ፤

ሐ/ የሥራ አፈጻጸምን በተመለከተ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ጸሎት እና ቡራኬ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፤

1.1/ ስለ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤

ሀ/ በሕገ ቤተ ክርቲያን መሠረት የአስተዳደር ሥራውን በመሥራት ቅድስት ቤተ ክርስቲንን እንዲመሩ፤

ለ/ ጸሎት እና ቡራኬ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፤
1.2/ የሁለቱም ቅዱሳን ፓትርያርክ አባቶቻችን ስም በቅደም ተከተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአለችበት ዓለም ሁሉ ዘወትር በጸሎት እንዲነሣ፤

1.3/ ሁለቱ ቅዱሳን ፓትርያርኮች በሕይወተ ሥጋ እስከ አሉ ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በእኩልነት የአባትነት ክብራቸውን ጠብቃ እንድትይዝ፤

1.4/ይህ ስምምነት ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ፣ የአገር ቤትና የውጭ አገር ሲኖዶስ የሚለው ስም ቀርቶ አንዲት ቤተ ክርስቲያንና አንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ እንዲኾን፤

2. ስለ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት

ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት የተነሳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፈተና ላይ ወድቃለች። ይህም ይታወቅ ዘንድ ሁለተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ተላልፈው ለሞት ከተሰጡበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት እንደ ተፈጸመ በልኡካኑ ታምኖበታል። ስለኾነም ለአለፉት ዘመናት የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መብትና ክብር በመጠበቅና በማስጠበቅ በውጭም ኾነ በውስጥ በአገር ቤት የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ ሓላፊነቱን መወጣት ባለመቻሉና ከጊዜው ጋራ አብሮ በመሔዱ፣ ስለተፈጸመው ጥፋትና ለዘመናት በቤተ ክርስቲያኒቱ መለያየት የተነሣ በጥልቅ ኃዘን ልባችው የተሰበረውን የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ልጆች ያለፉትንም ኾነ ዛሬ ላይ ያሉትን በጋራ ይቅርታ እንዲጠይቅ የልኡካኑ ጉባዔ በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ወስኖአል።

ስለኾነም ከሁለቱም ሲኖዶስ መዋሐድ በኋላ ያለፈው የቀኖና ጥሰት ስሕተት ለወደፊቱ እንዳይደገም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሉዓላዊነት ተጠብቆና ጸንቶ እንዲኖር ለማድረግ ሕገ ቤተ ክርስቲያንንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት ያደረገ ደንብ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ እንዲዘጋጅ የልኡካኑ ጉባዔ በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ወስኖአል።

3. ስለ ነባር ሊቃነ ጳጳሳት

ከልዩነት በፊት የተሾሙ ነባር ሊቃነ ጳጳሳትን በተመለከተ በሁለቱ ሲኖዶስ የተላለፈው ቃለ ውግዘት በጋራ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተፈቶ ስማቸውና ክብራቸው ተጠብቆ በውጭ ሀገርም ሆነ በሀገር ቤት በሀገረ ስብከት እንዲመደቡና እንዲያገለግሉ ጉባኤው በአንድ ድምፅ ተስማምቶአል።

4. ከልዩነት በኋላ ስለተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት፤ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት

ከልዩነት በኋላ በሁለቱም ወገኖች የተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳትን፤ ጳጳሳትንና ኤጲስ ቆጶሳትን በተመለከተ፦ ስማቸውን እንደያዙ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቀበላቸውና በውጭ ዓለምም ኾነ በሀገር ቤት በሀገረ ስብከት ተመድበው እንዲያገለግሉ ጉባዔው በአንድ ድምፅ ተስማምቶአል። ስም አጠራራቸውንም አስመልክቶ እንደ ሹመት ቅደም ተከተላቸው ቀዳማይ፣ ካልዓይ፣ ሣልሳይ… ወዘተ እየተባሉ እንዲጠሩ ጉባዔው በአንድ ድምፅ ወስኖአል።

5. ስለ ቃለ ውግዘት

በተፈጠረው ችግር ምክንያት በሁለቱም ሲኖዶስ ቃለ ውግዘት እንደ ተላለፈ ይታወቃል። ስለሆነም ከዚህ ስምምነት በኋላ ቃለ ውግዘቱ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ እንዲነሣ የሰላም ልዑካኑ በአንድ ድምፅ ወስኖአል።

6. በውጭ ዓለም በስደት የምትገኘውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓላማ ያገናዘበ መዋቅራዊ አስተዳደርን ስለማዘጋጀት

እንደሚታወቀው በዘመናችን በየትኛውም ዓለም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ በአሉበት ሁሉ ተስፋፍታ ትገኛለች። ይኹን እንጂ በውጭ ዓለም የምትገኝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከእናት ቤተ ክርስቲያን ጋራ አንድነቷን፤ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንንና ክብሯን ጠብቃ መኖር እንዳለባት ጉባዔው አምኖበታል።

ስለኾነም የየሀገሩን ሕገ መንግሥት መሠረት ያደረገ የቃለ ዐዋዲውና የሕገ ቤተ ክርስቲያን ገዥነት የሚረጋገጥበት መመሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያዘጋጅ ልኡካኑ በአንድ ድምፅ ወስኗል። እንዲሁም በውጭ ዓለም የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንና በመዋቅራዊ አስተዳደር መሠረት ከአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ በመቀበል በአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ እንድትመራም ወስኖአል።

በተጨማሪም በሁለቱ ሲኖዶስ መካከል የተደረገውን የዕርቀ ሰላም ስምምነት ተግባራዊ ለማድረግና የሁለቱንም ሲኖዶስ መዋሐድ ፍጹም ለማድረግ እንዲሁም በስደት የሚገኙ ብፁዓን አባቶች ወደ እናት አገራቸው ተመልሰው፥ የቀደመውን ሰላምና አንድነት አጽንተው፥ ሁሉም በአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚተዳደሩበትን ቅድመ ኹኔታ የሁለቱም ቅዱስ ሲኖዶስ ተወካይ ልኡካን እንዲያዘጋጁና እንዲከታተሉ የሁለቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ተወካይ ልኡክ በአንድ ድምፅ ወስኗል።

ሐምሌ 19 ቀን 2010 ዓ.ም.

ዋሽንግተን ዲሲ

%d bloggers like this: