Author Archive: Dagumedia

የማያዳምጥና የማያነብ መንግስት እድሜው ስንት ነው?

ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ

bedlu“መንገዱ በዚህ ወር ይጠናቀቃል፤ ባቡሩ በዚህ ወር ስራ ይጀምራል” ይሉናል፡፡ መንገዱ ወዴት ያደርሳል? ባቡሩ ወዴት ይወስዳል? ልጆቻችን ወጥተው የማይገቡበት መንገድ፣ የማይሳፈሩበት ባቡር ምን ያደርጋል? መንገዱ ሲሰፋ፣ መጓጓዣው ሲበረክት የልጆቻችን ፍርሀት፣ የእኛ የወላጆች ጭንቀት ከመበርከቱ በቀር ትርፉ ምንድነው?

ቁሳዊ ልማት ብቻውን ማህበረሰባዊ እድገት አያመጣም፤ ቀውስ ካልሆነ በቀር፡፡ የማህበረሰብህን . . . የነገ ወራሽህን. . የወጣቱን አስተሳሰብና አሰራር ሳታለማ (ሳትለውጥ) ታክሲ ብታመጣ፣ ወንዝ ውሀ ስትቀዳ፣ ጫካ እንጨት ስትለቅም ትደፈር የነበረችውን ልጃገረድ፣ ታክሲ ውስጥ ታስደፍራታለህ፤ ነገም ባቡር ውስጥ (ዛሬ በህንድ ሀገር ባቡር ማለት ብዙ የማያስከፍል ፔንሲዮን ነው)፡፡ እኛ ሀገር ብዙ መንገድ ብዙ ወንጀል፣ ሰፊ ኢንቨስትመንት ሰፊ ዝርፊያ፣ ትልቅ ባለስልጣን ትልቅ ዘራፊ ከማለት የተለየ ፍቺ የሚኖረው መቼ ነው?

“ልማታዊ መንግስት ነን፣ ኒዎ ሊብራሊዝምን እንቃወማለን” ይሉናል፡፡ በልማት ስም ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብታችንን አንጠፍጥፈው ወሰዱት፡፡ ይበጃል ያልነውን ስንጽፍና ስንናገር ጸረ ልማት ይሉናል፡፡ ደፈር ብለን መብታችንን ከጠየቅን አሸባሪ ይሉናል፡፡ በየእስር ቤቱ ያጉሩናል፤ ድንበር አሻግረው ያሰድዱናል፡፡ መብታችንንና የመናገር ነጻነታችን ልማታዊ ላሉት መንግስት ጭዳ አደረጉት፡፡

“ልማታዊ አይደላችሁም! ኒዎ ሊብራል ናችሁ አንላቸዋለን፡፡ የምትኖሩበት ቤት፣ የምትነዱት መኪና፣ ልጆቻችሁ የሚማሩበት ትምህርት ቤት (ሀገር)፣ የምትገበያዩበት ሱፐር ማርኬት፣ የምትዝናኑበት ሪዞሪት. . . የልማታዊነት ሳይሆን የኒዎ ሊብራሎች መገለጫ ነው፡፡” እንላቸዋለን፡፡

“ዝም በሉ! የምንላችሁን አሜን ብላችሁ ተቀበሉ” ይሉናል፡፡ ማተሚያ ቤቱ የእነሱ ነው፤ ራዲዮና ኢቲቪው የእነሱ ነው፤ አዋጅና መመሪያ የሚጥልብን ፓርላማ የእነሱ ነው፡፡ አዋጅ ጣሳችሁ፣ አሸበራችሁ፣ እራለ የሚይዘን ፖሊስ የእነሱ ነው፤ ከፖሊሶቹ ተቀብሎ የሚፈርድብን ፍርድ ቤት የነሱ ነው፡፡ ያለ ወንጀሉ ተከስሶ የሚፈረድበት ዜጋ እሱ ራሱ የራሱ አይደለም፡፡ ራሳችንም የእነሱ ነን፡፡ የእኛ የሆነው ተስፋችን ብቻ ነው! ለሀገራችንና ለወገናችን ያለንን ብሩህ ተስፋ ምንም ሊያስረው አይችልም፡፡ የኔ ተስፋ ልጆቼ ውስጥ፣ ያልተወለደው የልጆቼ ልጆች . . . . . ውስጥ አለ፡፡ ተስፋ የሚታሰረው፣ የሚሞተው እርኩስ፣ ለሀገርና ለወገን የማይበጅ ሲሆን ብቻ ነው፡፡

ዛሬ አትጻፉ ተብለናል፡፡ አትናገሩ ተብለናል፡፡ አንጽፍም፡፡ አንናገርም፡፡ ከተማው ጭር ብሏል፡፡ ሀገሩ ጭር ብሏል፡፡ መንግስትም ጭርታው ተስማምቶታል፡፡ እኛ ግን አንጽፍም እንጂ እንነበባለን፤ አንናገርም እንጂ እንደመጣለን፡፡ የማያነበንና የማያዳምጠን የኢህአዴግ መንግስት ብቻ ነው፡፡ አንድ መንግስት ህዝቡን ሳያዳምጥና ሳያነብ ምን ያህል እድሜ ይኖራል? እንጃ! . . . . . አንድ ቀን መንግስት ህዝብን ማንበብ፣ ህዝብን ማዳመጥ ግዴታው ይሆናል፡፡ አቤት ታዲያ ያኔ የሚያነበው መአት! የሚያዳምጠው ቁጣ! ያኔ ማንም መንግስትን መሆን አይመኝም፡፡ እውነቴን እኮ ነው፣ አሁን 1983 ዛሬ ቢሆን ደርግን መሆን የሚመኝ አለ?

 

በርካታ የአንድነት ፓርቲ አባላትና አመራሮች በቃሊቲ እስር ቤት ታግተው መለቀቃቸው ተገለፀ

የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃምን ጨምሮ ከ40 ያላነሱ  የፓርቲው አባላት ቃሊቲ እስር ቤት መታገታቸው ተገለፀ፡፡

አንድነት ፓርቲ  ለአንድ ሳምንት የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” በሚል መሪ ቃል ከህዳር 14 ጀምሮ እያካሄደ ያለው የማህበራዊ ሚዲያ ንቅናቄ አካል የሆነውን የህሊና እስረኞችን የመጎብኘት መርሀ-ግብር ለመሳተፍ አመራሮቹና አባላቱ ወደ ቃሊቲ እስር አቅንተው ነበር፡፡  የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም  እና የፓርቲው የአዲስ አበባ ሰብሳቢ አቶ ነገሰ ተፈረደኝን  ጨምሮ ከ40 ያላነሱ የአንድነት ፓርቲ አባላት ለግዜው ባልታወቀ ምክንያት  በእስር ቤቱ ግዜያዊ ማቆያ እንዲገቡ መደረጋቸውን  የፍኖተ ነፃነት ዘገባ አመልክቷል፡፡

kalitiበተለይ እገታውን በተመለከተ የአንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ አስራት አብርሃም ተናገሩት እንደታለው ከሆነው ‹‹እነእስክንድርንና አንዷለምን መጠየቅ አትችሉም ተባልን፡፡ ከዚያም ‹‹ለምን?›› ብለን ስንጠይቅ በዋናው በር በኩል ኃላፊውን አነጋግሩ የሚል መልስ ተሠጠን፡፡ እኛም ይህንን አምነን ሄድን፡፡ ነገር ግን በተባለው በር ስንደርስ በቁጥጥር ሥር ውላችኋል ብለውን መታወቂያችንን ከመዘገቡ በኋላ በአንድ ክፍል ውስጥ ለጊዜው ታገተው እንደነበር ሚኒሊክ ሳልሳዊ ዘግቧል፡፡ በመጨረሻም በኮንቴይነር ውስጥ ታግተው የነበሩት እስረኛ ጠያቂዎች ከበድ ያለ ፍተሻ ተደርጎላቸው ከቃሊቲ ግቢ እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን፤ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ወጣት ትዕግስት ካሳዬ የተባለች የአዲስ አበባ የፓርቲው አመራር ግን ከእገታው እንዳልተለቀቀች ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

እስረኞችን ሊጠይቁ የሄዱ የአንድነት አባላት በዛሬው እለት በአከባቢው የጠበቃቸው የደህንነት ቡድን በእያንዳንዱ ላይ ፍተሻ በማድረግ በኪሳቸው የነበረውን የአንድነት ፓርቲ ወረቀት እንዲሁም አንዲት ሴት የአንድነት አባል ፎት ልትነሳ መሞከር በሚል በተፈጠረ ሰበብ እንዲሁም በአባላቶቹ እጅ የተገኙት የፍኖተ ነፃነት እትሞች መቀማታቸው ተጠቁሟል፡፡ ይህ የተፈፀመው በቶዮታ ነጭ ዲኤክስ መኪና ተጭነው የመጡት የደህንነት አባላት እስረኛ ሊጠይቁ የሄዱትን በቁጥጥር ስር ካዋሉ በኋላ ስም ዝርዝራቸውን መዝግበው በመውሰድ እንዲፈቱ ትእዛዝ ሰጥተው ደህንነቶቹ መመለሳቸውን እና ከአንዲት አባል በስተቀር ሌሎች መለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡

 

 

አመክሮና በቀለ ገርባ

Zelalem Kibret

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) ምክትል ሊቀመንበርና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ መድረክ ስራ አስፈፃሚ የነበሩት “ህጋዊ የፖለቲካ ፓርቲን ሽፋን በማድረግ  የአሸባሪ ቡድን የሆነው ኦነግ አባል ሆነዋል” በሚል ክስ ተመስርቶባቸው የ8 ዓመት እሥር የተበየነባቸው ሲሆን፤ ይግባኝ ጠይቀው እስሩ ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ተደርጎላቸዋል፡፡

bekele-gerbaከ3 ዓመት ከ7 ወር የእስር ጊዜ ውስጥም 3ቱን ዓመት በመጨረሳቸው በአመክሮ ይፈቱ ዘንድ ለማረሚያ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ማረሚያ ቤቱም ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው›  በማለት እስከአሁን ሊፈታቸው አልቻለም፡፡ ይህም ብዙ ጥያቄዎችን አስነስቷል፡፡

አንዳንድ ህጋዊ ሁኔታዎች ስለጉዳዩ፡

አመክሮ ምንደር ነው?
ሌላውን ትርጉም ትተን የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ‹በተወሰነ ጊዜ በአመክሮ መፈታት› በሚለው ክፍል በተለይም በአንቀፅ 202 እንደደነገገው፡
“ተቀጭው ከተወሰነበት የእስራት ጊዜ ከሶስት እጅ ሁለቱን እጅ ወይም ፍርዱ የእድሜ ልክ እስራት ሲሆን ሀያ ዓመት በፈፀመ ጊዜ አግባብ ባለው አካል ወይም በጥፋተኛው አሳሳቢነት ጥፋተኛውን ከቅጣቱ ነፃ ያወጣዋል፡፡” ይህም ማለት አመክሮ 2/3ኛውን የቅጣት ጊዜውን የጨረሰ ታራሚ ከእስር የሚፈታበት አሰራር ነው፡፡

አመክሮ ለማግኝት ምን መስፈርት ማሟላት ያስፈልጋል?

የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ከላይ በጠቀስነው አንቀፅ 202 ላይ አመክሮ ለማግኝት አንድ እስረኛ ማሟላት የሚያስፈልገውን መስፈርቶች ይዘረዝራል፡፡ ይህም፡

– ‹ታራሚው በስራ ጠባዩ የተረጋገጠ መሻሻል አሳይቶ እንደሆነ…›

– ‹ካሳ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበት ከነበረና ካሳውን መክፈሉ የተረጋገጠ እንደሆነ…›

– ‹አመሉና ጠባዩ መልካም አኗኗር ለመኖር የሚያስችለውና በአመክሮ መፈታቱ መልካም ውጤት ሊያስገኝ ይችላል ተብሎ የታመነ እንደሆነ..›

ነው ብሎ ይደነግጋል፡፡

ማረሚያ ቤት ወይስ ፍርድ ቤት?

ታራሚን በአመክሮ የመልቀቅ የመጨረሻው ስልጣን የፍርድ ቤት፡፡ ነገር ግን ጉዳዩን ማረሚያ ቤቱ በራሱ ተነሳሽነት ወይም በታራሚው አሳሳቢነት ለፍርድ ቤት ሲያቀርብ ነው ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጠው፡፡ እዚህ ላይ ማረሚያ ቤቱ ትልቁን ስልጣን ይዞ እናገኛለን፡፡ ማረሚያ ቤቱ ለፍርድ ቤት ማቅረብ ካልፈለገ ሊተወው የሚችልበት አግባብ አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ማረሚያ ቤቱ በሕግ ስር ያለ አካል እንደመሆኑ መጠን በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 202 ላይ የተቀመጡ መስፈርቶችን ላሟላ ታራሚ አመክሮ ሊከለክል አይችልም – የታራሚው መብት ነውና!

በቀለ ገርባስ?

አቶ በቀለ ገርባ ከተፈረደባቸው የአምስት ዓመት እስር ውስጥ 2/3ኛውን ወይም 3 ዓመት የሚሆነውን ጨርሰው የአመክሮ ጥያቄያቸው በማረሚያ ቤቱ በኩል ለፍርድ ቤት እንዲቀርብላቸው ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ  ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የሚል መልስ እንደሰጣቸው ተሰምቷል፡፡
1ኛ. አመክሮ መስጠት የማረሚያ ቤት መብት ሳይሆን ግዴታም ጭምር ነው፡፡ መስፈርቱን ያሟላ ታራሚ አመክሮ የማግኝት መብት ያለው መሆኑ በሌላ በኩል አመክሮ ሰጭውን አካል ላይ ግዴታ ይጥላልና፡፡
2ኛ ሌላው አቶ በቀለ ገርባ መስፈርቱን አሟልተዋል ወይስ አላሟሉም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ 2/3ኛውን የእስር ጊዜ መጨረስ የሚለውን Objective መስፈርት እንዳሟሉ ግልፅ ሲሆን፡፡ ችግሩ የተፈጠረው Subjective መስፈርቱ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ይህም ማለት በእስር ወቅት መልካም ፀባይ አሳይተዋል ወይስ አላሳዩም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ አንድ ታራሚ በእስር ወቅት ለመልካም ፀባይ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮችን ካሳየ የቅጣት ማስጠንቀቂያ ከመፃፍ እስከ ብቻውን ማሰር (Solitary Confinement) ድረስ ያሉ እርምጃዎች በማረሚያ ቤቱ ሊወሰዱበት ይችላሉ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ ከፀባያቸው ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ቅጣት ያልተወሰደባቸው ከመሆኑም ሌላ መልካም ፀባይ እንዳሳዩ ከማረሚያ ቤቱ እንደተነገራቸው ራሳቸው ገልፀዋል፡፡ በቀለ ገርባ ምም መስፈር አሟልተዋል ማለት ነው፡፡ ታዲያ ምን ይሆን አቶ በቀለን በአመክሮ ከመፈታት ያገዳቸው?

አንዳንድ ነገሮች

ባለው አካሄድ አብዛኛው ታራሚዎች በአመክሮ ይፈታል፡፡ ከሌባ እስከ ሙሰኛ፡፡ High Profile በሆኑ ክሶች የተከሰሱ ሰዎች ሳይቀሩ በአመክሮ ሲፈቱ እንደነበር እናስታውሳለን ለምሳሌ ቴዲ አፍሮ 24 ወራት ተፈርዶበት 16 ወራትን ጨርሶ በአመክሮ ተፈቷል፡፡ አቶ አሰፋ አብርሃ 9 ዓመት ተፈርዶባቸው ሰባት ዓመታት ታስረው ከብዙ ውዝግብ በኋላ በአመክሮ ተፈተዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅንጅት ክስ ስር ተከሰው የነበሩት አቶ ዳንኤል በቀለና አቶ ነፃነት ደምሴ 30 ወራት የተፈረደባቸው ሲሆን 20 ወራትን በእስር አሳልፈው አመክሮ ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ ‹ፍርዳችሁን ጨርሳችሁ ውጡ› በሚል ምክንያት አመክሮ ከልክሏቸው ነበር፡፡

እንግዲህ አቶ በቀለ ገርባ በሕጉ የተቀመጠውን መስፈርት አሟልተው እያለ በአመክሮ የመፈታት መብታቸው አልተከበረም ወይም ማረሚያ ቤቱ ግዴታውን ሊወጣ አልፈለገም!

ምክንያት: በጉልበተኞች የምትተዳደር ሀገር ዜጋ ስለሆኑ!

ልዩ ማስታወሻ፡-ይህ ባለፈው ጥር  16 ቀን 2006 ዓ.ም. የዞን 9 ብሎገርና የአምቦ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ዘለዓለም ክብረት ከመታሰሩ በፊት የፃፈው ቢሆንም፤በአሁን ሰዓት እሱ ራሱ በግፍ እስር አቃቂ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ይገኛል፡፡

#‎FreeBekeleGerba

የነፃነቴ ዋጋ ነብሴ ነው!!

ግርማ ሰይፉ ማሩ
girma seifuመረጃ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ጠቃሚ ነው ብሎ መንገር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው፡፡ የተሟላ መረጃ የሰውን ልጅ ሙሉ ያደርገዋል፡፡ መረጃን አጣሞ ማቅረብ ደግሞ የሰውን ልጅ ውሳኔ ለማጣመም ካልሆነ በስተቀር ግቡ ምን ሊሆን እንደሚችል አይገባኝም፡፡ በሰሞኑ ሰው በላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጥርሱም በጥፍሩም ዘመቻ የጀመረው እኔ ላይ ነው፡፡ ዓላማው ግልፅ ነው፡፡ በነፃነት የማሰብ መብቴን ለድርድር እንዳቀርብ ነው፡፡ ለነፃነቴ ያለኝን ዋጋ የማያውቁ ሰዎችን ይህንን ለማድረግ ቢሞክር ካላቸው የመረጃ እጥረት ወይም ማወቅ ባለመፈለጋቸው ነው፡፡ አንዳንድ ቅን ሰዎች ሰህተት እንደሰራው አድርገው ይቅርታ እንድጠይቅ፤ ይቅርም እንድባል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በቅን ልቦና ላደረጋችሁት ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡

ነገር ግን በሰጠሁት አስተያየት ያልተስማማ ሰው በሃሰብ ልዮነት መለያየት እያለ ይቅርታ ጠይቄ፤ ይቅርታም ተደርጎልኝ ወደ እነሱ ሃሳብ እንድገበ መፈለጉ ምን ዓይነት ከፍተኛ ችግር ያለበት አስተሳሰብ እንደሆነ የተረዱት አይመሰለኝም፡፡ ይህ ደግሞ በጣም አስገራሚ የሚሆነው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ደጋፊ፣ ለግለሰብ ነፃነት እንቆማለን የሚሉ ወገኖች መሆናቸው ነው፡፡ ለሃሳብ ነፃነት የማይቆም እንዴት አድርጎ ለመድበላ ፓርቲ ስርዓት ግንባታና የግለሰብ ነፃነት እንደሚያከብር አይገባኝም፡፡

ጫጫታ ወደ ፈጠረው አጃንዳ ስገባ፡፡ አንድነት ፓርቲ የምርጫ ግብረ ሀይል ማቋቋሙን ለህዝብ በይፋ ለማሳወቅ እና በቀጣይ ሳምንት ስለሚያደርገው የህሊና እስረኞች ስለሚታሰብበት ፕሮግራም መግለጫ በሰጠንበት ወቅት በፍፁም ጠቃሚ ያልሆነ የተቃዋሚ ጎራውን በተለይ በሀገር ውስጥ ለምንገኝ ሰዎች የማይጠቅም (በኢቲቪ ቢቀርብ የማይገርም) ጥያቄ ቀረበ፡፡ ጥያቄው በእስር ላይ የሚገኙ የቀድሞ አንድነት አባል የነበሩ ታሳሪ ስም ጠርቶ በአንድነት አቋም እኝህ ሰው የህሊና እስረኛ ናቸው ብላችሁ ታምናላችሁ ወይ? የሚል ነበር፡፡ የሰጠሁት መልስ የማንንም ታሳሪ ስም ማንሳት ሳያስፈልግ የአንድነት ፓርቲ አባል ሆኖ የሌላ ፓርቲ አባል መሆን ትክክል እንዳልሆነ፣ ከአንድነት ጋር በትግል ስትራቴጂ ከማይመሳሰሉት ጋር ብቻ ሳይሆን በትግል ከሚመሳሰሉትም ጋር ቢሆን የተሻለ ወደሚለው መጠቃለል እንጂ ሁለት ቦታ መሆን ትክክል እንዳልሆነ አስረድቻለሁ፡፡ በማስከተልም “በፀረ ሽብር” ህግ መንግሰት እየከሰሰ የሚያስራቸው ሰዎች አንዳንዶቹ በወንጀል ህግ ሊያስጠይቅ የሚችል ሰህተት አልሰሩም የሚል ድምዳሜ እንደሌለኝ አሰረግጬ ተናግሬያለሁ፡፡ ለምሳሌ በፈንጂ ስው የገደለ ሰው በወንጀለኛ ህግ መጠየቅ እና መቀጣት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ እምቴ አሁን ፅኑ ነው፡፡ የ “ፀረ ሽብር” የሚባለውን ህግ በይፋ አሸባሪ ህግ ነው፡፡

ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች አሸባሪ እየተባሉ የሚታሰሩ ያሉት የአራት ኪሎን ወንበር ስለሚያሸብሩ ነው የሚል አቋሜን ከብዙዎቹ ተችዎቼ በላይ እና ከማንም በማያንስ መልኩ ሃሳቤን በነፃነት አራምጃለሁ፡፡ ይህን ሳራምድ ማንንም ለማስደስት ሳይሆን አምኜበት ነው፡፡ አንድነት የ “ፀረ ሽብር” የሚባለው ህግ እንዲሰረዝ የተገበረውን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ዘመቻ በቁርጠኝነት ከመሩት አንዱ ስሆን፤ በተለይ በደሴ ከተማ የተደረገውን የሚሊዮኖች ድምፅ ዘመቻ በቦታው ተገኝቼ የመራሁት እኔ ነኝ፡፡ ይህን ሁሉ የምዘበዝበው በዚህ ህግ ላይ ያለኝን ግልፅ አቋም በድጋሚ ለማረጋገጥ ነው፡፡

በእኔ በኩል የአቋም ለውጥ ሳይኖር እሳት ጭረው ቤንዝን እያርከፈከፉ ያሉት ግለሰቦችና ቡድኖች ለምን ተፈጠሩ? የሚለው ነው፡፡ በእኔ እምነት የአንድነት በምርጫው የመሳተፍ ውሳኔ በትግል ስልታቸው ላይ የሚፈጥረው ጫና ስለሚያስጨንቃቸው ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ምርጫ መሳተፍ ትክክል አይደለም ብሎ መሟገት ሲያቅታቸው የፈጠሯት ስልት ነች፡፡ አንድነት ምርጫ መሳተፍ ሲወስን በምንም መመዘኛ የመወዳደሪያው ሜዳ ምቹ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶ አይደለም፡፡ የፖለተካ ምዕዳሩ ጠበበ ብቻ ሳይሆን ዝግ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶዋል፡፡ ልዩነቱ ማስከፈቻ መንገዱ ምን ይሁን የሚለው ነው፡፡ በህዝብ ድምፅ የተዘጋው የፖለተኪ በር ይከፈታል ነው አንድነት ያለው፡፡ በዚህ ውሳኔ የማይስማማ ሊኖር እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህ ደረጃ ወርዶ ግን በጥርስና በጥፍር ለመናከስና ለመቧጨር መሞከር ግን ያስተዛዝባል፡፡

የግል ሰሜቴን ለመግለፅ እሰከ ዛሬ ድረስ ለሚቀርብልኝ ሙገሳና የማጀገኛ ቃለቶችን ተመርኩዥ ልቤ አላበጠም፡፡ አንድ ቀን ያለአግባብ ከፍ አድርገው ከሰቀሉ ቦታ ላይ አውርዶ የሚከሰክስ ማህበረሰብ አባል መሆኔን አውቃለሁ፡፡ ያለ አግባብ በእራሳቸው ስሜት ሊወስዱኝ የፈለጉት ከፍታ ላይ ስለአልሄድኩኝ አሁን ሊያወርዱኝ አይችሉም፡፡ እደግመዋለሁ ለነፃነቴ የምሰጠውን ዋጋ የማያውቁ ሰዎች ምንም ሊሞክሩ ቢችሉም ነፃነቴን ለኢህአዴግ አሳልፌ አልሰጥም ስል በተቃዋሚ ጎራ ለተሰለፈ አሳልፌ እሰጣለሁ ማለት አይደለም፡፡ ለነፃነቴ የመደብኩት ዋጋ ነብሴን ነው፡፡ ስም፣ ዝና፣ ክብር፣ ገንዘብ፣ ወዘተ እንዳይመስላችሁ!!!!! ነብሴን ነው፡፡

ለብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ አቀባበል ተደረገ፤ ፍቅረ ንዋይን በማሸነፍ ከሊቀ ጳጳሱ ጋራ በመመካከር እንዲሠሩ ማሳሰቢያ ተሰጠ

  • ‹‹የቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት የአገር ነው፤ ቤተ ክርስቲያንን ልናስቀድም ይገባል›› ፓትርያርኩ  
  • ‹‹ገንዘብን አሸንፉት፤ መቃብርን አትርሱት›› /ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ
  • ‹‹ሕዋሳት ድርሻ አላቸው፤ ሕዋሳቱ ካልታዘዙ ግን ችግር ይፈጠራል›› /አቡነ ቀሌምንጦስ
  • ‹‹ሀገረ ስብከቱን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ አለበት›› //ሥራ አስኪያጁ
  • ‹‹ያልምዶት እንጂ እንኳን ደስ ያለዎት አንልዎትም›› /አስተያየት ሰጭ የደብር አለቃ
  • ‹‹ንግግር ከማብዛት ይልቅ ወደፊት በየሥራችን ብንመዘን›› /ሌላው የደብር አለቃ

abune kelemintos

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፤ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እና የከምባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ

ቅዱስ ሲኖዶስ በወርኃ ጥቅምት የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባው፣ የከንባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው እንዲሠሩ መድቧቸዋል፡፡ በምደባ ውሳኔው መሠረት ኅዳር ፱ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በሀገረ ስብከቱ የስብሰባ አዳራሽ በተከናወነ መርሐ ግብር ለብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

 

‹‹የመጣነው ሥራቸውን በቡራኬ ለማስጀመር ነው፤ብፁዕነታቸው ደግ አባትና ጠንቃቃ መነኵሴ በመኾናቸው ይህን ከተማ ያስተካክሉታል ብለን እናምናለን፤ ኹላችኁም ትተባበሯቸዋላችኹ፤ ኹሉም መሪውን ይከተላልና፡፡››/ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/

ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋራ ስምንት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሀገረ ስብከቱ እና የሰባቱም ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች፣ ከ160 በላይ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ምክትል ሊቃነ መናብርትና ጸሐፊዎች የተገኙበት ይኸው የአቀባበል መርሐ ግብር፣‹‹ለብፁዕነታቸው በተደራቢነት የተሰጠውን ሥራ በቡራኬ ለማስጀመር››የተዘጋጀ መኾኑን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ተናግረዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ደግ አባትና ጠንቃቃ መነኵሴ መኾናቸው እንደሚታወቅ የጠቀሱት ቅዱስነታቸው፣ ‹‹ትልቅና ጥንቃቄ የሚፈልግ ከተማ›› ያሉትን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እንደሚያስተካክሉት እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡

ችግሮች ሲፈጠሩ ከሐሜትና መነቃቀፍ ይልቅ ግራና ቀኝ አስፍቶ በማየት እየተወያዩ መሥራት ቅድስትና ልዕልት ለኾነችው ቤተ ክርስቲያናችን እንደሚበጅ ቅዱስነታቸው አመልክተው÷ ‹‹የቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት የአገር ሓላፊነት በመኾኑ ከኹሉም በፊት ቤተ ክርስቲያንን ልናስቀድም ይገባል፤ የተሠየምነው ቅድስናዋንና ሕጓን ጠብቀን ለመኖር ነው፤›› በማለት አስገንዘበዋል፡፡ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የተቸገሩ የገጠር አብያተ ክርስቲያንን ለመርዳት ቅርበት እንዳላቸውና ሊኖራቸውም እንደሚገባ በመግለጽ ስለ አስተዋፅኦዋቸው አመስግነዋቸዋል፤ ‹‹አዲስ አበባ ሰላም ከኾነች ኹሉም ሰላም ይኾናል›› ያሉት አቡነ ማትያስ የአህጉረ ስብከት ኹሉ ማእከል በኾነው አዲስ አበባ ለሰላም፣ ለልማትና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ሊቀ ጳጳሱን በመደገፍና ከሊቀ ጳጳሱ ጋራ በመመካከር መሥራት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል – ‹‹ኹላችኁም ትተባበሯቸዋላችኹ፤ ኹሉም መሪውን ይከተላልና፡፡››abune matiyas

‹ለኹለት ጌቶች መገዛት አይገባም፤ ገንዘብን ወድዳችኹ አይታችኁታል፤ እስኪ ደግሞ ንቃችኹ እዩት›› /የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ/

ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና መመሪያ ቀደም ብሎ የመርሐ ግብሩን ትምህርት የሰጡት የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ወይ ለእግዚአብሔር ወይ ለገንዘብ እንጂ ለኹለት ጌታ መገዛት እንደማይችል የጠቀሱት ብፁዕነታቸው÷ ገንዘብን ንቀው ለእግዚአብሔር የተገዙ አባቶች ግን ማትረፋቸውን በዋቢነት አስረድተዋል፡፡ እነቅዱስ እንጦንስን እነጻድቁ ገብረ ክርስቶስን ለምኑልን፤ አማልዱን ብለን የምንጸልየውም ገንዘብን ንቀው ለእግዚአብሔር ስለተገዙ ነው፡፡ ‹‹ገንዘብን አሸንፉት፤ መቃብርን አትርሱት፤ ሰው ገንዘብ ቆጥሮ ሥልጣንም አግኝቶ ትቶት ይሔዳልና፤››ሲሉም በአጽንዖት መክረዋል፡፡

የዓለም መናኸርያ፣ የአፍሪቃ መዲና፣ የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት አዲስ አበባ÷ ትንሽ ጉድፍ ጎልቶ የሚታይባት በመኾኑ አመራሯ ጥንቃቄን እንደሚጠይቅ በ፳፻፫ ዓ.ም. በንቡረ እድ አባ ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ ዋና ሥራ አስኪያጅነት ሀገረ ስብከቱን በሊቀ ጳጳስነት የመሩት ብፁዕነታቸው ተናግረዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የተጣለባቸው አደራ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩን እንዲረዱ እና አዲስ አበባን እንዲያስተካክሉ መኾኑን ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ አስታውቀዋል፡፡ አዲስ አበባ ብዙ ችግሮች ቢኖሩባትም ሕግ ፈጻሚዎች መኾን እንዳለብን በአጽንዖት ያመለከቱት ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ አበክረው እንዳሳሰቡት፣ እያንዳንዱ የራሱን ጉድፍ ካጸዳ አዲስ አበባ በአንድ ቀን ልትጸዳ ትችላለች፤ ኹሉም የየራሱን ድርሻ ከተወጣና በቅንነት ከሠራ ልትስተካከል ትችላለች፡፡

abune kewestosብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በቀድሞው የሸዋ ሀገረ ስብከት መዋቅር በአዲስ አበባ በስብከተ ወንጌል ለብዙ ጊዜ ሲያገለግሉ እንደነበር ብፁዕነታቸው አስታውሰዋል፡፡ በደብረ ሊባኖስ ገዳም በጸባቴነት፣ በደብረ ከርቤ ደብረ ጽጌ ማርያም እና በደብረ ብርሃን ሥላሴም በእልቅና ባገለገሉበት ወቅትም በርካታ ነገሮችን በማስተካከላቸው አኹን ፓትርያርኩን እንዲረዱ ሲመደቡ ፈተናውን ለመወጣት እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል፡፡ ለዚኽም ‹‹እርሳቸው ፓትርያርኩን ሲረዱ እኛ [የሀ/ስብከቱ፣ የክፍላተ ከተማና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን አገልጋዮችና ሠራተኞች] ደግሞ ብፁዕነታቸውን መርዳት ይጠበቅብናል›› ብለዋል፡፡

‹‹በአሉባልታና በሐሰት አሸናፊ ለመኾን አይቻልም፤ ሀገረ ስብከቱን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ አለበት›› /የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን/

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ከጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው የተመደቡበትን የሹመት ደብዳቤ በንባብ ያሰሙት የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን የሀ/ስብከቱንና የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ሓላፊዎችንና ሠራተኞችን በመወከል ባሰሙት ንግግር÷ ‹‹እኛ የቅዱስ ሲኖዶሱን ትእዛዝ እናከብራለን፤ በዚኹም መሠረት ብፁዕ አባታችንን ተቀብለናቸዋል›› ብለዋል፡፡

እንደ ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ አዲስ አበባ መልካም ነገሮች የሞሉባትን ያኽል ውስብስብ ነገሮችም አሉባት፤ የውስብስቡ ቋጠሮ ሊፈታና ሊስተካከል የሚችለውም ኹሉም የድርሻውን ሲወጣ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በአሉባልታና በሐሰት አሸናፊ ለመኾን እንደሚሯሯጡ ያስታወቁት ሊቀ አእላፍ ቄስ በላይ፣ በሀ/ስብከቱ ነገሮችን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ እንዳለበት ከመግለጻቸውም ባሻገር ‹‹በክርስትና አሸናፊነት ሰላምና ቸርነት ማድረግ ነው፤ በጎውን ብናደርግ መልካሙን ብንሠራ መልካም ስም ማትረፍ እንችላለን፤›› ብለዋል፡፡ ለዚኽም ‹‹የብፁዕነታቸውን መመሪያ ሕግ በሚፈቅደው መሠረት ለማስፈጸምና በትእዛዙ መሠረት ለመጓዝ ቃል እንገባለን፤›› በማለት ንግግራቸውን አጠቃልለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከተገኙት ከአምስት መቶ ያላነሱ የገዳማትና አድባራት ተወካዮች መካከል የአራት አድባራት አስተዳዳሪዎች በሰጡት አስተያየት፣ ከብፁዕነታቸው መመሪያ እየተቀበሉ በመታዘዝና በመመካከር ተግተው ለመሥራትና የድርሻቸውን ለመወጣት ዝግጁ መኾናቸውን አስታውቀዋል፡፡

‹‹እንኳን ደስ ያለዎት ሳይኾን ያጽናዎት፤ ያልምዶት ማለት እፈልጋለኹ›› ያሉት የደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ፀጋይ ግደይ፣ በሀገረ ስብከቱ አገልግሎታቸው ብዙ ሊቃነ ጳጳሳትና ሥራ አስኪያጆች ተመድበው ማለፋቸውን ገልጸው ‹‹ብፁዕ አባታችን ረዥም ጊዜ እንዲቆዩ እኛ ሰላማውያን መኾን ይገባናል፤ ምእመናን ከእኛ መልካም ነገር ይሻሉ፤ እኛም በጎና መልካም እንኹን›› ብለዋል፡፡ አዲስ አባቶች ተመድበው በመጡ ቁጥር የተወሰኑ ግለሰቦች ከሌላው ጎልተው የሚታዩበትና ለሌሎች ትኩረት የሚነፈገበት ኹኔታ መታረም እንደሚገባው ያሳሰቡትም ‹‹ትንሽ አለቃ፣ ትልቅ አለቃ የለም፤ ኹላችንም የቅዱስ ፓትርያርኩ እንደራሴዎች ነን፤ በቅዱስ ሲኖዶስ ነው የተሠየምነው›› በማለት ነው፡፡

‹‹ችግሮች እንዲወገዱ እኛም ጥረት እናደርጋለን›› ያሉት የታዕካ ነገሥት በኣታ ለማርያም ገዳም ሊቀ ሊቃውንት፣ ሀገረ ስብከቱም ለጉዳዮች አፋጣኝ መፍትሔ መስጠት እንዳለበት፣ ጉዳዮች በተገቢና በተቀላጠፈ አሠራር ከታዩ የነበረው የመልካም አስተዳደር ችግር እንደሚፈታተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡ የቀበና ምሥራቀ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ÷ የመናገር/የአነጋገር ችግር እንደሌለና የሔደውን መውቀስ የመጣውን ማወደስ ልማድ መኾኑን ተችተው፣ ‹‹ንግግር ከማብዛት ይልቅ ወደፊት በየሥራችን ብንመዘን፤ ይህን ብፁዕነትዎ በሒደት ይለዩት፤ አኹን ግን ብፁዕነታቸውን ተቀብለናልና በዚኹ ብናበቃ›› ሲሉ የአስተያየቱ ክፍለ ጊዜ ተጠቃሎ ወደ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቃለ ምዕዳንና መመሪያ ሽግግር ተደርጓል፡፡

ተስማምቶና ተግባብቶ፣ ምስጢር ጠብቆና ምስጢራውያን ኾኖ መሥራት የብፁዕነታቸው ንግግር ዋነኛ ትኩረት ነው፡፡ ‹‹ኹሉን ማድረግ የሚችል አምላክ ይህችን ጊዜ ስለሰጠን እናመሰግነዋለን›› በማለት ንግግራቸውን የጀመሩት ብፁዕነታቸው፣ ‹‹ወደ ታላቁ ከተማ ተመድቤ ስመጣ ቅዱስ ፓትርያርኩን እንድረዳ ነው፤›› ካሉ በኋላ ዓላማቸው ሰላምን ማስፈንና ቤተ ክርስቲያንን ማስፋፋት እንደኾነ አስታውቀዋል፤ ኹላችንም የቤተ ክርስቲያን እንደራሴዎች ስለኾን ሕጉን ጠብቀን መጓዝ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አክለውም ‹‹ኹሉም የአካላችን ሕዋሳት ልዩ ልዩና የየራሳቸው ድርሻ አላቸው፤ ሕዋሳቱ አልታዘዝም ካሉ ግን ችግር ይፈጠራል፤ ተግባብተን ተደማምጠን መሥራት አለብን፤ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ምስጢር ነው፤ ምስጢር ጠብቀንና ምስጢራውያን ኾነን ልንጓዝ ይገባል፤ ሥራ በምንሠራበት ወቅት መሰናክል፣ መውደቅና መነሣት ይኖራል፤ ይህንንም በመተባበርና በመከባበር ማረም ይገባል፤ ከቅዱስ አባታችን መመሪያ እየተቀበልን እንሠራለን፤››ብለዋል፡፡

ወደፊት በሥራ መተያየትና መመዘን እንደሚገባ በቀበና መሥራቀ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የተሰጠውን አስተያየት የተጋሩት ብፁዕነታቸው፣ ንግግራቸውን የቋጩት ለተሰብሳቢው ኹሉ መነጋገርያ ኾኖ በዋለው ተከታዩ ቃል ነበር – ‹‹የቅድሙ ተናጋሪ እንዳሉት ለወደፊቱ በሥራ መተያየት ያስፈልጋል፤ የሥራ መርሐ ግብር እናወጣለን፤ ኹሉንም በየድርሻውና በየደረጃው እናስተናግዳለን፤ በሥራው ሰዓት በቢሮ እንድትስተናገዱ እንጂ ወደ መኖርያዬ እንድትመጡብኝ አልፈልግም፡፡››

ከሰባት መቶ ያላነሱ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት እና የገዳማትና አድባራት የአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች በተገኙበት በዚኹ የአቀባበል መርሐ ግብር÷ ለሰባቱ ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች የአስተያየት መስጫ መርሐ ግብር አለመያዙ ቅሬታ አሥነስቷል፡፡ በአንዳንድ ተሳታፊዎች ዘንድም ሀገረ ስብከቱ ለክፍለ ከተማ የሥልጣን መዋቅር ነፍጎታል ለሚሉት ትኩረት ቀጣይ ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል፡፡

ለሀገረ ስብከቱ የገዘፈና የተመሰቃቀለ የመልካም አስተዳደር ዕጦት እንደ አንድ መንሥኤ የተወሰደው፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች በቃለ ዐዋዲው የተደነገገው ሥልጣን ተከፍሎ አለመሰጠትና ሥራቸውን አለመሥራታቸው እንደነበር ያስታወሱት ሓላፊዎቹ፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች ሥራቸውን ለመሥራት የሚያስችል ችግር ፈቺ አደረጃጀት ቢዘረጋም በአፈጻጸም/በተግባር ደረጃቸው ተጠብቆ የሥራ ድርሻቸውን የሚያከናወኑበት ሥልጣን አላቸው ለማለት አዳጋች እንደኾነ ገልጸዋል፡፡ ከሀገረ ስብከቱ ጋራ ሽሚያ በሚመስል አኳኋን የሠራተኛ ምደባ፣ ዝውውርና ዕድገት እንዲኹም ሌሎች መንፈሳዊና ልማታዊ ተግባራት ባለመናበብ ሲፈጸሙ የነበረበትን ኹኔታ በመገምገም፣ በሀገረ ስብከቱ እና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች መካከል ግልጽ የሥራ ክፍፍል የሚያስቀምጥ ጊዜያዊ መመሪያ በጋራ ስምምነት ተዘጋጅቶ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ይኹንታና የአፈጻጸም አቅጣጫ የሰጠበትና የብዙኃኑን ካህናትና ምእመናን ተቀባይነት ያረጋገጠው የመዋቅር የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት በሥራ ላይ እስኪውል ድረስ በሀገረ ስብከቱና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶቹ የተስማሙበት ይኸው ጊዜያዊ መመሪያእንዲሠራበት ተደጋጋሚ ውሳኔ ቢተላለፍም ባለመተግበሩ በአኹኑ ወቅት በክፍላተ ከተማ /ቤቶቹ ተሟሙቶ ለሚታየው የአሠራር ኹኔታበመንሥኤነት ተቀምጧል፡፡

ኹሉንም በየድርሻውና በየደረጃው በማስተናገድ ሰላምን ለማስፈንና ቤተ ክርስቲያንን ለማስፋፋት ቃል የገቡት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ÷ በሀገረ ስብከቱ እና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች መካከል ተፈጥሮ ለቆየው የአሠራር ክፍተት ተገቢውን ትኩረት ከመስጠት ባሻገር ለችግሩ ዘለቄታዊ መፍትሔ ለሚያስገኘውና ወደ ትግበራ ምዕራፍ መሸጋገር ሲገባው በእጅጉ የዘገየውን የመዋቅር የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት አፈጻጸም በመምራት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን የተቋማዊ ለውጥ አርኣያ እንደሚያደርጉት ተስፋ አለን፡፡ የኾኑ ግለሰብ ሓላፊዎች ከቦታ ወደ ቦታ መዘዋወር ብቻ ሳይኾን በጥናት የተደገፈውና የብዙኃኑን ተቀባይነት ያረጋገጠው የተቋማዊ ለውጥ እንደሚያስፈልግ ተጠቁሟል፡፡

ምንጭ ፡-ሐራ ተዋህዶ