Category Archives: News

አዲሱ ማስተር ፕላን አሁንም ተቃውሞ ቀስቅሷል

አዲስ አበባን ከሌሎች አጎራባች ከተሞች በመሰረተ ልማት ለማስተሳሰር በሚል በመንግሥት ይፋ ባደረገው አዲሱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ከትናንት ጀምሮ በድጋሚ ተቃውሞ አስነስቷል፡፡

AA new masterplan protesting

በተለይ በምዕራብ ሸዋ አምቦ፣ ጊኒጪ እና ምዕራብ ወለጋ ተቃውሞው ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ በተቃውሞው ከተሰለፉት መካከል በመንግሥት በተወሰደ ርምጃ በምዕራብ ሸዋ ድሬ ኢንጪኒ አካባቢ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች እንዳሉም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በዋናነት ተቃውሞን የቀሰቀሰው አዲሱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችን ያከተተ በመሆኑ እና የዞኑን እና የክልሉን ጥቅም እንዲሁም ገበሬዎችን ያለምንም በቂ ካሳና ቦታ በማፈናቀል ለጎዳና ህይወት ይዳርጋል የሚሉ ሐሳቦች እንደሚገኙበት የተጠቆሙ ሲሆን፤ ይህንን ፕላን ተግባራዊ ለማድረግ ኢህአዴግ የፖለቲካ ድርጅት አባል ከሆነው ከኦህዴድ አመራር አባላት ከመፅደቁ ውጭ ወደ ህዝብ ያልወረደና ለምክክርም እንዳልቀረበ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት የዚህ ማስተር ፕላን ተቋውሞው በ2006 ዓ.ም. በመንግሥት በተወሰደ እርምጃ በርካታ ተማሪዎች እና የተቃውሞ ታዳሚዎች ግድያ ከቆመ በኋላ ድጋሚ ማገርሸቱ ተሰምቷል፡፡

 

AA masterplan protesting

በአንዳንድ ከተሞች የመኪና መንገዶች የተዘጉ ሲሆን፤ በተቃውሞው የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎችም መካተታቸው ታውቋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ከመንግሥት ምንም የተሰጠ ማብራሪያም ሆነ አስተያየት የለም፡፡

የሳውዲ ባለሃብት በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ቅሬታ ማሰማት ጀመሩ

ነብዩ ሲራክ

* “በኢትዮጵያ በደልና ዘረፋ ተፈጸመብን !” ባለሃብቱ!
* ” ቅሬታ ውንጀላው መሰረት ቢስ ነው ” የኢትዮጵያ ዲፕሎማት

ታዋቂው የሳውዲ ጋዜጣ አረብ ኒውስ ‪#‎Arabnews‬ የኢትዮጵያ መንግስት አንዳንድ ባለ ኃላፊዎች መሬታቸውን እየተቀሙ በደልና ዘረፋ እየተፈጸመባቸው መሆኑን ሞሀመድ አልሸህሪ የተባሉ ሳውዲ ባለ ሃብት አስታውቀዋል። እኒሁ ባለሃብቶችን መርተው ወደ አፍሪካና ወደ ኢትዮጵያ ከአመታት በፊት የዘለቁት ባለ ሃብት Investor በኢንቨስትመንት ፈቃድ ወደ ኢትዮጵያ ያስገቧቸው ንብረቶችን ለመውረስ በእርሳቸውና በጓደኞቻቸው ላይ የወንጀል ክስ አንደተመሰረተባቸው ማስታወቃቸውን አረብ ኒውስ ዘግቧል ። ቅሬታ አቅራቢው ሳውዲ ባለሃብት ሞሃመድ አልሸህሪ ለአረብ ኒውስ ጋዜጣ እንዳስታወቁት ሙስናው የከፋ እየሆነ መምጣቱን በመጠቆም ሳውዲ ባለሃብቶች በማመሳሰል ( Forgery) ወንጀል ሳይቀር ተወንጅለው ለስራ ያስገቧቸውን እቃዎች መመለስ እንዳልቻሉ አስረድተዋል።

Ethio farmer

ከስድስት አመት በፊት ጀምሮ በእርሻ ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ ሳውዲ ባለሃብቶች በመንግስት የተገባላቸው ቃል በተግባር ባለመፈጸሙ 50 % እጅ ያህሉ ከኢትዮጵያ ለቀው መውጣታቸውን እኒሁ ቅሬታ አቅራቢ ሳውዲ ባለ ሃብት ተናግረዋል ። ” በደረሰባቸው በደል ተማረው ሀገሪቱን ለቀዋል !” ስላሏቸው ባለሃብቶች ሲያስረዱም የቻሉት ሸጠው መውጣታቸውን አልደበቁም። መሸጥ ያልቻሉትና ያልቻሉት እቃቸውን ትተው የወጡት ግን ተመልሰው እቃቸውን ቢጠይቁ ” በማናውቀው ወንጀል እንያዛለን !” በሚል ስጋት ባለ ሃብቶች ኢትዮጵያ ላይ ወረታቸውን በትነው መቅረታቸውን ሞሃመድ አልሸህሪ ለአረብ ኒውስ አስታውቀዋል ።
ከዚህ ቀደም ተሰምቶ የማይታወቀውን የሳውዲ ባለ ሃብቶች ቅሬታና ብሶት ለታዋቂው የሳውዲ ጋዜጣ ለአረብ ኒውስ በአደባባይ ያጋለጡት ባለሃብቱ ሞሃመድ አልሻህሪ ቅሬታቸውን ለሁለቱም ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ቢያቀርቡም እስካሁን ምነም አይነት ምልሽ እንዳላገኙ ጠቁመዋል !
ይህ በእንዲህ እንዳለ የዜናውን ማስፈንጠሪያ Link በፊስ ቡክ የፊት ገጼ ላይ እንደለጠፍኩ ” እንዴት ይህን ያልተጨበጠ አደገኛ መረጃ ሊንክ Link ይዘህ ትለጥፋለህ? ” በማለት የጅዳ ቆንስል ዲፕሎማት ቆንስል ሸሪፍ በስልክ ቅሬታቸውን ግልጸውልኛል ። ለሚሊዮኖች በአለም ዙሪያ የተሰራጨውን መረጃ ማስተላለፌን በአግራሞት የተመለከቱትና በጅዳ ቆንስል የኢኮኖሚ ኋላፊ አቶ ሸሪፍ ኼሪ በዜናው ዙሪያ ዘርዘር ባለ መልኩ አነጋግረውኛል ። እኔም ያቀረብኩት መረጃ ከአረብ ኒውስ ማግኘቴን ደግሜ በማስረዳት ማሰተባበያ ማቅረብ እንጅ የወጣውን መረጃ አታሰራጩ ፣ አለያም አትለጥፉ ማለት እንደ ሚከብድ አሳውቄቸዋለሁ !
ቆንስል ሸሪፍ በመጨረሻም ” አረብ ኒውስ ጋዜ ለ ያወጣው መረጃ የተዛባ በመሆኑ አስፈላጊው ሁሉ እርምጃ ይወሰዳል ” በማለት “ፍጹም መሰረተ ቢስ ነው ! ” ላሉትን የተሰራጨ መረጃ ምላሽ ለመስጠት በሪያድ የኢትዮጵያ ኢንባሲ በኩል አስፈላጊ ዝግጅት በመደረግ ላይ መሆኑን ገልጸውልኛል !
ቸር ያሰማን !

እነ ሀብታሙ አያሌው ለጥቅምት 22 ተቀጠሩ

᎐ማረሚያ ቤት እነ ሀብታሙን አላቀረባቸውም

Politicians
የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ እንዲሰናበቱ የተበየነላቸው የአንድነት፣ የሰማያዊ እና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ላይ አቃቤ ህግ ይግባኝ ጠይቆ ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት አምስት ተከሳሾች ለጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ቢጠበቅም ማረሚያ ቤት ሳያቀርባቸው በሌሉበት ቀጠሮ የተሰጣቸው የፓርቲዎች አመራሮቹ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና አብሯቸው ይግባኝ የተጠየቀበት አብርሃም ሰለሞን ናቸው፡፡
የቂሊንጦ እና የቃሊቲ ማረሚያ ቤቶች እነ ሀብታሙን ፍርድ ቤት ያላቀረቡበትን ምክንያት ፍርድ ቤቱ ሲጠይቅ፣ “ቃሊቲ በፕላዝማ ይታያል ስለተባለ አላመጣናቸውም፤ ከአይ.ሲ.ቲ ጋር ተነጋግረው ነው ያስቀሯቸው” የሚል መልስ ተሰጥቷል፡፡ ማረሚያ ቤቱ እነ ሀብታሙን ብቻ ሳይሆን በሌላ መዝገብ በተለያዩ ወንጀሎች ስር የተጠቀሱ ተከሳሾችንም አለማቅረቡ ታውቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በበኩሉ የቃሊቲ ማረሚያ ቤትን መልስ ካደመጠ በኋላ፣ “ይሄ ቪዲዮ ኮንፈረንስ የሚባል ነገር የሚሆን አይደለም፤ አቅርቧቸው ብለን አዝዘን ነበር፤ እኛ ነን የምናዝዛችሁ ወይስ ማን ነው? አሁንም ቀጣይ ቀጠሮ ላይ አቅርቧቸው” ሲል በእነ ሀብታሙ መዝገብም በሌሎች መዝገቦችም ላይ ዛሬ ላልቀረቡ ተከሳሾች ተመሳሳይ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም እነ ሀብታሙ አያሌው ሰኞ ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም የተጠየቀባቸው ይግባኝ ያስቀርባል ወይስ አያስቀርብም የሚለውን ብይን ቀርበው ለመስማት ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ

ሰበር ዜና ፡- ፈቃድ የሌላቸው የኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራሞች በቤተ ክርስቲያን ስም እንዳይጠቀሙ ተወሰነ፤ የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት ይጀመራል

• የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ እና ዕውቅና የሌላቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል
• በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ መሠረት፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
የብዙኃን መገናኛ ቦርድ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው
• በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ላይ የቀረቡ ማስረጃዎች የበለጠ ተጠናክረው አጀንዳው በልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ተወስኗል
EOTC Synod 2008
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ከማእከል የተሰጠ ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም፣ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ(EBS) የቴሌቭዥን ጣቢያ፣ “ሃይማኖታዊ ትምህርት” የሚያስተላልፉ ፕሮግራሞች፣ የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ ወሰነ፡፡

ምልአተ ጉባኤው በዛሬ፣ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ስድስተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው ያሳለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲኾን፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቭዥን በደብዳቤ እንዲያውቁት ይደረግ ዘንድ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
በውሳኔው÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በስም የተጠቀሱ ሲኾን በፕሮግራሞቹ አዘጋጅነት የሚታወቁት በተለይ የ“ታዖሎጎስ” ግንባር ቀደም ምንደኞች፣ ፕሮግራማቸው“ራሱን የቻለ የሚዲያ ተቋም” እንጂ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ይኹን ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በይፋ በሰጡት መግለጫ ማረጋገጣቸው ይታወሳል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ከዚኹ ጋር በማያያዝ፤ በሊቃውንት ጉባኤ ሳይመረመሩ እና በማእከል ሳይፈቀዱ በግለሰቦች እየተዘጋጁ የቤተ ክርስቲያንን ስም ይዘው ስለሚወጡ የስብከት፣ የመዝሙር እና የመጻሕፍት ኅትመቶች እንዲኹም የአዳራሽ ጉባኤያት እና ስብሰባዎች ከተወያየ በኋላ ቀደም ሲል ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች በማጽናት ተመሳሳይ ትእዛዝ መስጠቱ ታውቋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ስብከተ ወንጌል እና ሚዲያን በተመለከተ” በተራ ቁጥር ሦስት በያዘው አጀንዳ፤ ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊነቱን ጠብቆ የራስዋን ድምፅ ለዓለም የምታሰማበት እና ስብከተ ወንጌልን የምታስፋፋበት የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት እንዲጀመርም ወስኗል፡፡

ለቤተ ክርስቲያንየቴሌቭዥን አገልግሎት ስርጭት የሚያስፈልገውና በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አስተባባሪነት የተጠናው በጀት ባለፈው ዓመት ግንቦት በምልአተ ጉባኤው የጸደቀ ሲኾን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር እንደተመለከተው፤ በዚኽ ዓመት በጀቱ በአፋጣኝ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበውን ጥያቄ በመቀበል የፋይናንስ ምንጮቹን ወስኖ ለነገ የሚያቀርብ ሦስት አባላት ያሉት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት(ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ) ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤ ተሠይሟል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ባለፈው ዓመት ግንቦት ባጸደቀው የሚዲያዎች (የሬዲዮ እና የቴሌቭዥን አገልግሎት) ሥርጭት ደንብ መሠረት፤ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራ ዘጠኝ አባላት ያሉት የብዙኃን መገናኛ የሥራ አመራር ቦርድ የተቋቋመ ሲኾን ተግባሩን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ለ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ የቀረበው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ሪፖርት ያስረዳል፡፡

በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልን ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በአጽናፈ ዓለም ለማስፋፋት እና ለማጠናከር ስለሚያስፈልጓት ሚዲያዎች፣ በመምሪያው አስተባባሪነት በብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎች የተካሔደውን ጥናት መሠረት አድርጎ መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ/ማኑዋል ተዘጋጅቷል፡፡

በተያያዘ ዜና፣“የቤተ ክርስቲያኗን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ማየት” በሚል ዐቢይ አጀንዳ ሥር በፊደል ተራ ቁጥር 4/መ፣ “የተሐድሶ እንቅስቃሴን በተመለከተ”፤ የተዘጋጀው ሰነድ በተጨማሪ ማስረጃዎች ተስፋፍቶ እና ተጠናክሮ ራሱን በቻለ ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል፡፡

የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፤ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ግንባር ቀደም መሪዎች በሚሰጣቸው ተልእኮ እና ድጋፍ በቤተ ክርስቲያናችን የአስተዳደር እና የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በመስረግ የኑፋቄውን አስተሳሰብ እና ድርጊት የሚያራምዱ የ66 አካላት እና ግለሰቦች የሰነድ፣ የምስል እና የድምፅ ማስረጃዎች ከኃምሳ ገጾች ማብራሪያ ጋር ተደግፎ ተዘጋጅቷል፡፡

ከቤተ ክርስቲያናችን ዐውደ ምሕረት እና የአስተዳደር መዋቅር ባሻገር፣ የኑፋቄው ግንባር ቀደም መሪዎች እና ምንደኞቻቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን(መንፈሳዊ ኮሌጆች እና የካህናት ማሠልጠኛዎች) ውስጥ በተለያየ ሽፋን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ከፍተኛ ትኩረት እንዲደረግበት ምልአተ ጉባኤው ኮሚቴውን አሳስቧል፡፡

በመካከለኛው ምሥራቅ አህጉረ ስብከት፣ ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ሳያውቁት ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በተቋቋመው የኑፋቄው መናኸርያ “ዱባይ ሚካኤል” እና “ቤርያ ቲኦሎጂካል ኢንስቲትዩት” በሚል መሪዎቹ የመሠረቱት ሕገ ወጥ ተቋም በከፍተኛ ደረጃ ያነጋገረ ሲኾን በምልአተ ጉባኤው ጥናት ተካቶ እንዲቀርብ መወሰኑ ተጠቁሟል፡፡

በተመሳሳይ ኹኔታ ጉባኤውን ያነጋገረው፣ በመንበረ ፓትርያርኩ የውጭ ጉዳይ መምሪያ በሓላፊነት የተቀመጡት መልአከ ሰላም አባ ቃለ ጽድቅ የተባሉ ግለሰብ፣ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቁ አንጻር ያላቸው ሃይማኖታዊ አቋም እና ሥነ ምግባራዊ ኹኔታ ነበር፡፡ የግለሰቡ አመጣጥ እና አመዳደብም ከፓትርያርኩ ልዩ ጸሐፊ ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ጋር ባላቸው የጥቅም ግንኙነት እንደኾነ መጠቆሙ ደግሞ ችግሩ ከግለሰቡም በላይ ልዩ ጽ/ቤቱ እንደ መዋቅር ያለበትን አስከፊ ደረጃ እና አሳሳቢነቱን ለምልአተ ጉባኤው አለብቧል፡፡
ከዚኽ ውስብስብነቱና ከሚያስፈልገው ጠንካራ ቅንጅት አኳያ፤ አጀንዳው ራሱን በቻለ አስቸኳይ እና ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሲወስን ጊዜው በመጪው ወርኃ ጥር ላይ ሊኾን እንደሚችል ከወዲኹ የተጠቆመ ቢኾንም በኮሚቴው ውጤታማ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚመሠረት ነው፣ በብዙኃን የምልአተ ጉባኤው አባላት ዘንድ መግባባት የተደረሰበት፡፡

በሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት መሠረት፤ አስቸኳይ እና ድንገተኛ ጉዳይ ሲያጋጥም ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም ቋሚ ሲኖዶሱ ወይም የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ በሚያደርጉት ጥሪ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሊካሔድ ይችላል፤ ከዐራቱ እጅ ሦስቱ እጅ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት ስብሰባም ምልዓተ ጉባኤ ይኾናል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ በማናቸውም ስብሰባ ላይ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍም፣ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ከኾነ በሙሉ ድምፅ ያልፋል፤ በሃይማኖት እና በቀኖና ጉዳይም ድምፀ ተዓቅቦ ማድረግ አይቻልም፡፡

ምንጭ፡- ሐራ ዘተዋሕዶ

በእስር ላይ የሚገኙት መምህር ግርማ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄም ወድቅ ተደረገ

ጥላሁን ካሳ
ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት መምህር ግርማ ወንድሙ ዛሬ ጥቅምት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፖሊስ መርማሪ ቡድን ዛሬ ግለሰቡን በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት አቅርቧቸዋል።

መምህር ግርማ ወንድሙ

መምህር ግርማ ወንድሙ

ፖሊስ ግለሰቡ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ቀሪ የምርመራ ስራ ስላሉብኝ ተጨማሪ 14 ቀን ይፈቀድልኝ ብሏል።
ተጠርጣሪው በራሳቸውና በጠበቃቸው በኩል ፖሊስ የጠየቀውን ተጨማሪ ጊዜ በመቃወም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል።
የፖሊስ የምርመራ ቡድን በበኩሉ እሳቸው ቢለቀቁ ሌሎች ተፈላጊዎችን እና የተለያዩ ሰነዶችን ስለሚያሸሹብን ጥያቄያቸው ውድቅ ይሁን ብሏል።
ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ አብዛኛውን የምርመራ ስራ ያካሄደ በመሆኑ ለቀሪ የምርመራ ስራዎቹ ይረዳል በማለት ከጠየቀው የ14 ቀን ጊዜ ውስጥ 7 ቀን ብቻ ፈቅዷል።
ውጤቱን ለመጠባበቅም ለጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
የወንጀሉ ዝርዝር
ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ.ም ነው ብሏል።
በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው።
እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።
እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል።
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ800 ሺህ ብር ይሸጡታል።
ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው የሚለው የምርመራ መዝገቡ።
ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው።
ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።
የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው።
ተጠርጣሪው እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።
ጠበቃቸውም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል አይደለም፤ ፖሊስም የሚጠበቁ ምርመራዎቹን አጠናቋል፤ ደንበኛዬ የዋስትና መብታቸው ይከበርልኝ በማለት ጠይውቋል።
ይሁን እንጂ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጓል።
ምንጭ፡- ሬዲዮ ፋና (ኤፍቢሲ)