Category Archives: Social and Culture

77 ቢሊዮን ብር የሚያንቀሳቅሰው ስኳር ኮርፖሬሽን የገጠመው ፈተና

‹‹ለስኳር ኮርፖሬሽን መውደቅ ሜቴክ ትልቅ ድርሻ አለው› ‹‹የስኳር ኮርፖሬሽን የቀድሞ አመራሮች መጠየቅ አለባቸው››

MP, Sugar projects failures

የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች

በዮሐንስ አንበርብር

በ2003 ዓ.ም. በተካሄደው የመጀመርያ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ትልቅ ትኩረት ከተሰጣቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል የስኳር ልማት አንደኛው ነው፡፡ አገሪቱ ለስኳር ልማት ያላትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም አሥር ግዙፍና አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎችን በመገንባት በዓመት 4.07 ሚሊዮን በላይ ስኳር በማምረትና ለውጭ ገበያ በማቅረብ፣ በ2007 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ 1.2 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት በዕቅድ ተይዞ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ይህ ዕቅድ በጣም የተለጠጠ መሆኑ በስተመጨረሻ ሲታወቅ፣ ሰባት ፋብሪካዎችን በመጀመርያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ማጠናቀቅ ተብሎ እንዲከለስ ተደርጓል፡፡

እነዚህ አዳዲስና ግዙፍ ፕሮጀክቶች በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገነቡት ኩራዝ አንድ፣ ኩራዝ ሁለት፣ ኩራዝ ሦስት፣ በለስ አንድ፣ በለስ ሁለት፣ ከሰም፣ ወልቃይት፣ አርጆ፣ ደዴሳና ተንዳሆ ናቸው፡፡

መንግሥት ፕሮጀክቶቹን አጠናቆ ስኳር ለውጭ ገበያ በማቅረብ በሚገኝ የውጭ ምንዛሪ ዕዳ መክፈል እንደሚችል በማሳመን ለስኳር ፋብሪካዎቹ መገንቢያ ከተለያዩ አበዳሪዎች ሁለት ቢሊዮን ዶላር ተበድሯል፡፡ ከአገር ውስጥ ባንኮችም ከፍተኛ ብድር አግኝቷል፡፡ በአጠቃላይ የስኳር ልማቱን የሚመራው የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን 77 ቢሊዮን ብር በላይ እያንቀሳቀሰ የሚገኝ ቢሆንም፣ አንድም ፋብሪካ እስካሁን ተጠናቆ ወደ ሥራ አልገባም፡፡ በሌሎች አገሮች አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ ግፋ ቢል አንድ ዓመት የሚፈጅ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ግን አንድ ዓመት ከስድስት ወራት (18 ወራት) አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ አቅዶ የውል ስምምነቶችን ቢያደርግም፣ አንድ ፋብሪካ ሥራ ሳይጀምር ስድስተኛ ዓመት ላይ ተደርሷል፡፡

የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የሥራ ኃላፊዎች በ2008 የበጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለማቅረብ ባለፈው ሰኞ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተገኝተዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ከተሾሙ የወራት ዕድሜን ያስቆጠሩት አቶ እንዳወቅ አብቴና ሌሎች ምክትል ሥራ አስፈጻሚዎች ያቀረቡት ሪፖርት ‹‹ተስፋ በመቁረጥና እያመመን ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት ግንባታው የተጀመረው ተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ በኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ስኳር ማምረት ቢጀምርም ጥራቱ የተጓደለ የእንፋሎት አቅርቦት፣ የፋብሪካውን ፊልተር በቆሻሻ በመዝጋቱና በተርባይን ላይ ጉዳት በማድረሱ እንዲቆም መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ጥገና ከተደረገ በኋላ በአገሪቱ በተከሰተው ድርቅ ለፋብሪካውና ለመስኖ የሚሆን የውኃ አቅርቦት ችግር ወደ ምርት እንዳይገባ እንዳደረገው ጠቁመዋል፡፡
የተንዳሆ ቁጥር ሁለት ፋብሪካ ግንባታም ገና 27 በመቶ ላይ ይገኛል፡፡ ኩራዝ አንድ የተባለው ፋብሪካ ኮንትራት ውል የተገባው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ የውል ማሻሻያ ሰኔ 2004 ዓ.ም. ላይ እንደተደረገ አቶ እንዳወቅ አስረድተዋል፡፡

በዚህ መሠረት ግንባታውን የሚያከናውነው አገር በቀሉ የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ፕሮጀክቱን በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. አጠናቆ ማስረከብ ይጠበቅበት ነበር፡፡
ፕሮጀክቱ በመጋቢት ወር 2008 ዓ.ም. ላይ የደረሰበት ደረጃ 83 በመቶ ሲሆን፣ ሜቴክ ግን 97 በመቶ ክፍያ እንደተፈጸመለት አቶ እንዳወቅ ተናግረዋል፡፡ ኩራዝ ሁለት የተባለውን ፋብሪካ ለማስገንበት ውል የተፈረመው እ.ኤ.አ. በሐምሌ ወር 2014 ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 58 በመቶ መድረሱን ይጠቅሳሉ፡፡ በውሉ መሠረት በመጪው ሐምሌ ወር ፕሮጀክቱ መጠናቀቅ የነበረበት ቢሆንም መዘግየቱን አስታውቀዋል፡፡ የፕሮጀክቱ ኮንትራክተር የፕሮጀክቱ ማጠናቀቂያ ጊዜ እንዲራዘምለት ጠይቆ እስከ መጪው ኅዳር ወር እንዲያጠናቅቅ መመርያ እንደተሰጠው አብራርተዋል፡፡

ኩራዝ ሦስት ግንባታው የተጀመረው እ.ኤ.አ. በፌብሯሪ 2015 ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 25 በመቶ ደርሷል፡፡ ይህም ቢሆን መሆን ከነበረበት ወደ ኋላ የቀረ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ኩራዝ አምስት ስኳር ፋብሪካን ለማስጀመር ከቻይና ኩባንያ ጋር ውል የተፈጸመ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ለመግባት ኩባንያው ዝግጅት ላይ መሆኑን አቶ እንዳወቅ ይገልጻሉ፡፡ በለስ አንድ ስኳር ፕሮጀክት ወደ ሥራ የገባው በየካቲት 2003 ዓ.ም. ነው፡፡ በሰኔ ወር 2004 ዓ.ም. የውል ማሻሻያ መደረጉንና በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. ኮንትራክተሩ ሜቴክ አጠናቆ ማስረከብ የነበረበት ቢሆንም፣ የፕሮጀክቱ አፈጻጸም በአሁኑ ወቅት ገና 60 በመቶ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ኮንትራክተሩ ግን 94 በመቶ የሚሆነውን ክፍያ መቀበሉን ገልጸዋል፡፡

በለስ ሦስት ፋብሪካን ለመገንባት ውል የተፈጸመው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ መጠናቀቅ የሚገባው በ2005 መጋቢት ላይ እንደነበረ ያስረዳሉ፡፡ ይሁን እንጂ ፕሮጀክቱ ገና 23 በመቶ ሲሆን፣ ኮንትራክተሩ ሜቴክ ግን 94 በመቶ ክፍያ እንደተከፈለው ያስረዳሉ፡፡

የከሰም ስኳር ፋብሪካ አፈጻጸም 96 በመቶ መድረሱን ነገር ግን ገና ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ እንዳልገባ አክለዋል፡፡ ወልቃይት ስኳር ፋብሪካም ግንባታው እንዳልተጀመረና በቅርቡ ግንባታው እንደሚጀመር ገልጸዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን ገንብቶና ምርት ኤክስፖርት በማድረግ ዕዳውን የመክፈል ኃላፊነት የተሰጠው ቢሆንም፣ ኤክስፖርት ማድረግ ይቅርና የአገሪቱን የስኳር ፍላጎት ማሟላት አለመቻሉን ገልጸዋል፡፡
ግንባታዎቹን ለማከናወን 77 ቢሊዮን ብር የውጭና የአገር ውስጥ ብድር የተበደረ በመሆኑ፣ አንድም ፋብሪካ ወደ ምርት ባልገባበት በአሁኑ ወቅት 13 ቢሊዮን ብር ዕዳ ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ የመክፈል ኃላፊነት ከፊቱ ተጋርጧል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ይገዙና የኮሚቴው አባላት የኮርፖሬሽኑ ችግር ምን እንደሆነ፣ ሥራው ባልተሠራበት ሁኔታ ከ90 በመቶ በላይ ገንዘብ ለምን እንደተከፈለ ማብራሪያ ጠይቀዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ የኢንቨስትመንትና ልማት ዘርፍ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ አብርሃም ደምሴ በሰጡት አስተያየት፣ የአሥሩም አዳዲስ ፋብሪካዎች ኮንትራት የተሰጠው ለአገር በቀሉ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) መሆኑን አስታውሰው፣ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን መገንባት እንዳልቻለ ገልጸዋል፡፡ ይህ ቢሆንም የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን አመራሮች ከሜቴክ ጋር የነበራቸው ግንኙነት በቢዝነስ ኮንትራት ሕግ የማይመራ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

‹‹አሥሩም ፋብሪካዎች በዚህ ኮንትራክተር እንዲሠሩ ነበር የተወሰነው፡፡ በኋላ ላይ የመፈጸም አቅሙ እየታየ ፕሮጀክቶቹ እየተነጠቁ አሁን እጁ ላይ ሦስት ፋብሪካዎች ናቸው የቀሩት፤›› ብለዋል፡፡
ከዚህ ኮንትራክተር (ሜቴክ) ተነጥቀው ፋይናንስ ተገኝቶላቸው ወደ ሥራ ከገቡት መካከል ከሰም ሥራ ለመጀመር ዝግጅት ላይ ሲሆን፣ ሌሎቹ ደግሞ እስከ ኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ይደርሳሉ ብለዋል፡፡ በሜቴክ እጅ የሚገኙት ግን መቼ እንደሚጠናቀቁ እንኳን ለማወቅ አስቸጋሪ እንደሆነባቸውና ከድርጅቱ ጋር ልቅ የሆነው ግንኙነት በውል ያልታሰረ በመሆኑ ዕርምጃ እንኳን ለመውሰድ እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡
ሜቴክ በእጁ የሚገኙትን ሦስት ፋብሪካዎች በተለይም ኩራዝ አንድ ፋብሪካን በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ለማጠናቀቅ ገንዘብ እንደሚያስፈልገው ገልጾ፣ በልዩ ሁኔታ ስኳር ኮርፖሬሽን የአገር ውስጥ ብድር እንዲያገኝ ተደርጎ ሊከፈለው መቻሉን አቶ አብርሃም አስረድተዋል፡፡

‹‹ይሁን እንጂ ይህ ፋብሪካ እስካሁን አልተጠናቀቀም፡፡ እኛ ግን ዕዳ የመክፈል አደጋ ከፊታችን ተጋርጧል፤›› ብለዋል፡፡ ፋብሪካዎቹ ባለመድረሳቸው ምክንያት አጠቃላይ የስኳር ኮርፖሬሽን ወጪ እየናረ መሆኑን የሚገልጹት የሥራ ኃላፊው፣ የሸንኮራ አገዳው ቢደርስም አገዳውን ከማስወገድ ሌላ አማራጭ አለመገኘቱን ገልጸዋል፡፡

‹‹ኩራዝ ላይ 870 ሔክታር አገዳ ለማስወገድ ተቃርበናል፡፡ 300 ሺሕ ሔክታር የሸንኮራ አገዳ በለስ ላይ አስወግደናል፡፡ ይህንን ለማስወገድ በሔክታር 50 ሺሕ ብር እያወጣን ነው፤›› በማለት በምሬት ተናግረዋል፡፡
‹‹በዚህ ኮንትራክተር ላይ እንደ ማንኛውም ኩባንያ ቅጣት መጣል እንደማንችል ሁላችሁም ታውቃላችሁ፡፡ የሚያስጠይቅ ነገር ካለ ባለቤቱ ተለይቶ መጠየቅ ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡
ሌላው የኮርፖሬሽኑ አመራርም የሜቴክ ችግር በመገንባት ላይ ባሉት ፋብሪካዎች ላይ ብቻ አለመሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ በማምረት ላይ ለሚገኙ ፋብሪካዎች መለዋወጫ የሚያቀርበው ሜቴክ መሆኑን በመጥቀስ፣ መለዋወጫ ባለማቅረቡ ምክንያት ፋብሪካዎች ለበርካታ ቀናት ምርት እንደማያመርቱ ገልጸዋል፡፡
‹‹የማይችሉትን ሁሉ እንችላለን እያሉ አገርን ዋጋ እያስከፈሉ ነው፡፡ ምክንያቱም ነባሮቹ ፋብሪካዎች ያለ ችግር ቢሠሩ ቢያንስ በውጭ ምንዛሪ ስኳር አናስገባም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ መለዋወጫ ከሜቴክ የመግዛት ግዴታ ለአገሪቱ አዋጭ አለመሆኑን፣ ምክንያቱ ደግሞ ሜቴክ ራሱ ከውጭ ከሚገባው በላይ እየሸጠ መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡ ‹‹ለምሳሌ ሮለር ከውጭ ስንገዛ ከ200 ሺሕ ብር አይበልጥም፡፡ ሜቴክ ግን 600 ሺሕ ብር ነው የሚሸጥልን፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እንቢ ብለን እንኳን እንዳንታገል አመራሮች ያሸማቅቁናል፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው ከሌሎች አካላት ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለብቻ በሌላ መድረክ እንደሚያይ አስታውቆ አሁንም የኪራይ ሰብሳቢነት ችግር በኮርፖሬሽኑ ውስጥ መኖሩን በመጥቀስ ፋብሪካዎች ኦዲት እንዲደረጉ አዟል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

በአዲስ አበባ ሰሚት አካባቢ ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ

በአዲስ አበባ ከተማ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ።

Addis Ababa Poor construction

የአዲስ አበባ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ እንደገለጹት፥ የህንፃ መደርመስ አደጋው ዛሬ ማለዳ 12 ሰአት ላይ ነው በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሰሚት አካባቢ የተከሰተው።

ባለ 5 ፎቅ ህንፃው ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀ ቢሆንም ከታችኛው ወለል ላይ ሁለት ባንኮች አገልግሎት መስጠት ጀምረው እንደነበርም አቶ ንጋቱ ጠቁመዋል።
የመደርመስ አደጋው በስራ ሰዓት ቢደርስ በሰው ላይ ከባድ አደጋ ሊያደርስ ይችል እንደነበርም ነው ባለሙያው ያነሱት።
የባንኮቹ የጥበቃ ሰራተኞች ህንፃው ከመድርመሱ በፊት ከባድ ድምፅ በመስማታቸው ከአደጋው ሊያመልጡ ችለዋል።

ምንጭ፡-ፋናቢሲ

የአዋሽ ወንዝ ሊሞላ ስለሚችል የአካባቢው ወረዳዎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማሳሰቢያ ተሰጠ

በዚህ ሳምንት ውስጥ እንደሚጥል በተተነበየ ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ አማካይነት የአዋሽ ወንዝ ሞልቶ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል፣ ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ፡፡

Awash river

ኮሚሽኑ ለሪፖርተር የላከው የቅድመ ማስጠንቀቂያ መልዕክት እንደሚገልጸው፣ ከሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ በስተቀር በአብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እስከ ሚያዝያ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጥል እንደሚችል፣ ከብሔራዊ የሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲ መረጃ ማግኘቱን ይጠቁማል፡፡

ከአዋሽ ተፋሰስ ባለሥልጣን በተገኘው ሌላ መረጃ መሠረትም የአዋሽ ወንዝ በቀጣዩ ሳምንት ሊሞላ ስለሚችል፣ ከዚህ ጋር ተያይዞ ጐርፍ በተፋሰሱ ባሉ አካባቢዎች ሊከሰት እንደሚችል መረጃዎች የሚያመለክቱ መሆኑን፣ በኮሚሽኑ የቅድሚያ ማስጠንቀቂያና ምላሽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሉነህ ወልደ ማርያም ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም በበቾ ወረዳ፣ በዓለም ጤና ወረዳ (ሁምቡሌና ጐሮ አካባቢዎች)፣ በስሬ ወረዳ፣ በወንጂ በተለይም በቆቃ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በመርቲ ወረዳ፣ በመተሃራ (ፈንታሌ)፣ በአሚባራ፣ በዱለቻ፣ በገላአሎ፣ በገዋኔ፣ በተንዳሆ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በአሳይታና በአፋምቦ ወረዳዎች የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጐርፍ ሊከሰትባቸው ስለሚችል ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኮሚሽኑ አሳስቧል፡፡

የተጠቀሱት አካባቢዎች የመስተዳደር አካላትም በአካባቢዎቹ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ከወንዙ በማራቅ ከጉዳት መጠበቅ እንዲችሉ የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉም አሳስቧል፡፡

ባለፈው መጋቢት ወር መጨረሻ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተከሰተው የጐርፍ አደጋ ከ20 ሰዎች በላይ መሞታቸው ይታወሳል፡፡

ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በ2008 ዓ.ም. የመጀመሪያ ወራት እንደ አዲስ የተቋቋመና በሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን የመከላከልና የቅድመ ማስጠንቀቅ ሥራ የማከናወን ኃላፊነት የተጣለበት ተቋም ሲሆን፣ ተጠሪነቱም በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

ሜዲትራኒያን ባህር ላይ በሰጠመችው ጀልባ አደጋ ምክንያት ከሞቱት መካከል ኢትዮጵያውያንም ይገኙበታል

(አዲስ ሚዲያ) ትናንት እሁድ ሚያዝያ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት 400 ያህል ስደተኞችን ጭና ከግብፅ ወደ ጣሊያን ስታመራ የነበረች ጀልባ ሜዴትራንያን ባህር ላይ በመስጠሟ በርካታ ሰዎች መሞታቸው ተገለፀ ፡፡

Meditreanian sea Boat sinks

በጀልባዋ ሲጓዙ የነበሩት አብዛኛው ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያውያን ሲሆኑ የተወሰኑ ኤርትራውያን ስደተኞች እንደሚገኙበት እየተነገረ ሲሆን፤ የሶማሊያ መንግሥት በበኩሉ 200 ያህል ዜጎቹ በአደጋው መሞታቸውን አስታውቋል፡፡ ከሞቱት መካከል ኢትዮጵያውያን እናት እና ልጅን ጨምሮ በርካታ ወጣቶችም በአደጋው ህይወታቸው እንዳለፈ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በጀልባው ላይ ሲጓዙ ከነበሩት መካከል ከ200 ያላነሱት ኢትዮጵያውያን እንደነበሩም ተጠቁሟል፡፡

በተለይ በጉዞ ላይ እያሉ የአደጋው ሰለባ የሆኑት ከህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እየተደረገ ባለው ህዝባዊ ተቃውሞ መንግሥት እየወሰደ ያለውን ወታደራዊ የኃይል እርምጃ በመፍራት አብዛኛው ከባሌ፣ከሐረር እና ድሬዳዋ አካባቢ የተሰደዱ ኢትዮጵያውን እንደሆኑ ቤተሰቦቻቸውን ዋቢ በማድረግ የኢሳት ዘግቧል፡፡

የጀልባዋን መስጠም ተከትሎ በአቅራቢያ የደረሱት ዓለም አቀፍ የነፍስ አድን ሰራተኞች ከ27 ያላነሱ የአደጋው ሰለባ ሰዎችን ህይወት ማትረፍ መቻላቸው የተገለፀ ሲሆን፤ ከሞቱት መካከልም የተወሰኑ አስከሬኖችን አውጥተዋል፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን በአጠቃላይ ምን ያህል ሰዎች እንደሞቱ እና ምን ያህሉ እንደተረፉ የተሰጠ ዝርዝር መረጃ የለም፡፡

በጋምቤላ ከደቡብ ሱዳን በመጡ ታጣቂዎች 170 ያህል ኢትዮጵያውያን ተገደሉ

(አዲስ ሚዲያ)ትናንት አርብ ሚያዚያ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ ከሰዓት በኋላም የቀጠለው በሺህዎች የሚቆጠሩና የታጠቁ ደቡብ ሱዳን ቡማ ግዛት ወታደራዊ የደንብ ልብስ የለበሱ የሙርሌ ማኀበረሰብ አባላት ወደ ኢትዮጵያ ድንበር ዘልቀው በመግባት በጋምቤላ የሚገኙ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ ቢያንስ 170 ኢትዮጵያውያን የኑዌር ማኀበረሰብ አባላትን መግደላቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ዋቢ በማድረግ ሱዳን ትሪቡን ዘግቧል፡፡

Murle South Sudan

ታጣቂዎቹ በብዛት የኔዌር ኢትዮጵያውያን በሚኖሩበት በጋምቤላ ክልል ዞን 3 ጂካው እና ኒኔኛንግ ወረዳ የካጃክ አስር የኑዌር መንደር በመሄድ ጥቃት ማድረሳቸው የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ የግድያ ሰለባው የሆኑት በዋናነት ህፃናት እና ሴቶች መሆናቸውንም ከጥቃቱ የተረፉ እማኞች ተናግረዋል፡፡ በጥቃቱም በርካታ ዜጎች መቆሰላቸውና እስካሁን ቁጥራቸው ያልተገለፀ በርካታ ህፃናትም ታግተው መወሰዳቸው ተጠቁሟል፡፡

እንደእማኞች ገለፃ ከሆነ፤ በጥቃቱ ወቅት በአካባቢው የሚኖሩ ዜጎች ለጋምቤላ ክልላዊ መንግሥትና በአካባቢው በቅርብ ርቀት ለሚገኙ የፌደራል መንግሥት ፌደራል ፖሊስና መከላከያ የድረሱልን ጥሪ ቢያደርጉም ምላሽ እንዳላገኙ እና ጠዋት የጀመረው ጥቃትም እስከ ከሰዓት ድረስ መዝለቁን ያልተለመደ እንደነበርና በወቅቱ መንግሥት ምላሽ ባለመስጠቱም የብዙ ሰዎች ህይወት መጥፋቱም እንዳሳዘናቸው በተለይ ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡

“በእጃችን ራሳችንን የምንከላከልበት እንኳ በቂ መሳሪያ ባለመኖሩና የመንግሥትን ምላሽ በማጣታችን ለአካባቢው የሚገኙ ነዋሪዎች የድረሱልን ጥሪ በማሰማታችንና ትብብር ስላደረጉልን ታጣቂዎቹ እያደረሱ ያሉትን አደጋ ለመቀነስ ችለናል:: በዚህም ከደቡብ ሱዳን ታጣቂዎችም ከ51 ያላነሱ ሰዎችን ገድለናል፣ የተወሰኑ የተዘረፉ ከብቶቻችንን አስመልሰናል፤ ነገር ግን የታገቱ ህፃናት ልጆቻችንን እና የተዘረፉ ከብቶቻችንን ማስመለስ አልቻልንም “ ብለዋ፤ሌላኛው በህይወት የተረፉ አንድ አባት፡፡

ስማቸውን እንዲገለፅ ያልፈለጉና ከጥቃቱ የተረፉ ግለሰብ እንደተናገሩት ከሆነ፤ የደቡብ ሱዳን ታጣቂዎች ከዚህ በፊትም በተደጋጋሚ ሰርገው በመግባት ጥቃት ያደርሱ እንደነበር ያስታወሱት ነዋሪዎቹ፤ የትናንትናው ግን በወታደራዊ የደንብ ልብስ በብዛት ታጥቀው ገብተው የዚህ ዓይነት የከፋ ጉዳት ሲያደርሱ የመጀመሪያቸው እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ በትናንትናው ግድያም 170 ኢትዮጵያውያን እና 51 የደቡብ ሱዳን ታጣቂዎችን ጨምሮ ወደ 221 ሰዎች መገደላቸው ታውቋል፡፡

በስልጣን ላይ ያለው የኢህአዴግ መንግሥት በበኩሉ በስሩ ባሉ ፋናቢሲ እና ኢቢሲ በመሳሰሉ መገናኛ ብዙኃን እንዳስታወቀው ከሆነ፤ በጋምቤላ ከደቡብ ሱዳን መንግሥትም ሆነ ከመንግሥት ተቃዋሚ ታጣቂዎች ምንም ንክኪ የሌላቸው “ወንበዴዎች” 140 ኢትዮጵያውያን መገደላቸውን እና ከጥቃት አድራሽ ደቡብ ሱዳናውያን ደግሞ 60 ያህል ሰዎች መገደላቸውን ቢያስታውቅም፤ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ በጉዳዩ ዙሪያ ዝርዝር መረጃም ሆነ የሰጠው መግለጫ የለም፡፡

ታጣቂዎቹ  ከደቡብ ሱዳን ድረስ ድንበር ጥሰው በመግባት ለምን ኢትዮጵያውያንን እንገደሉ፣ ህፃናቱን እንዳገቱና ከብቶቻቸውን እንደዘረፉ የተገለፀ ነገር የለም፡፡

በያዝነው 2008 ዓ.ም. ባለፉት ወራት በተለያየ ጊዜ በዚሁ በጋምቤላ ክልል የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል እርምጃ በርካታ ዜጎች መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ የትናንቱ ግድያ የጠፈፀመው ግን ከደቡብ ሱዳን በመጡ ታጣቂዎች እንደነበርና ይህንንም ከተገደሉ ሰዎች ማረጋገጥ እንደተቻለ ተጠቁሟል፡፡