በኢትዮጵያ የሚካሄድው መጪው ምርጫ 2007 ዓ.ም. እና ተፅዕኖው
ብስራት ወልደሚካኤል
የፖለቲካ ምርጫ ህዝብ የስልጣኑ ባለቤት መሆኑ የሚረጋገጥበትና ለዚህም ቀጥተኛ ተሳትፎ የሚያደርግበት አንዱ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሂደት አካል ነው፡፡ ሂደቱ የሚከናወነውም ሁለትና ከዛ በላይ በሆኑ ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች በተዘጋጀላቸው እኩል መድረክ ተወዳድረው አማራጫቸውን ለህዝቡ በማቅረብ የመንግስት ስልጣን ውክልና የሚያገኙበት መንገድ ነው፡፡ ኢትዮጵያም የፖለቲካ ምርጫን ከጀመረች የቆየች ቢሆንም፤እስካሁን በህዝቡ ተቀባይነትና መተማመን ላይ የደረሰ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ ውጤት ላይ ለስልጣን የበቃ የመንግስት ስርዓት ለማየት እንዳልተቻለ ይነገራል፡፡
የፖለቲካ ምርጫ ዓላማ፣ጠቀሜታና አስፈላጊነት ዜጎችን የሀገራቸው ስልጣን ባለቤት ከማድረግ ጎን ለጎን ሀገሪቱን የመምራት ዕድል ባጋጠማቸውና በህዝቡ መካከል መተማመን ለመፍጠር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዜጎች በሀገሪቱ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ በሚኖራቸው የነቃ ተሳትፎ የሚደርስባቸውን ግድያ፣ እስር፣ ስቃይ፣ ስደት፣አድሎና መገለልን ለማጥፋትና ለመቀነስ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ያለው እውነታ ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው፡፡ ምክንያቱም የፖለቲካ ስልጣን ምርጫ በቀረበ ቁጥር መብቶቻቸውን የሚጠይቁ ዜጎች ላይ የሚወሰደው ጭካኔ የተሞላበት እምርምጃ ተባብሶ የሚቀጥል በመሆኑ፤በገዥው ስርዓት በሚወሰዱ ወታደራዊ የኃይል እርምጃዎች መቀነስ ሲገባቸው ይበልጥ ተጠናክረው በመቀጠል በርካታ ንፁሃን ዜጎች ይገደላሉ፣ ይታሰራሉ፣ ይሰደዳሉ፡፡ በሚፈጠሩ ስህተቶችም የድርጊቱ ፈፃሚዎችም ሆኑ አዛዦቹ ኃላፊነት ወስደው አያውቁም፤ ሲወስዱም አይታይም፡፡
ምርጫ በቀረበ ቁጥር ሌላው የሚስተዋለው ችግር የፍትህ ስርዓቱ በህዝብ ያለው ተቀባይነትና አመኔታ ጥያቄ ውስጥ መግባቱ ነው፡፡ በተለይም ከገዥው ስርዓት ተቃራኒ ሐሳብ ያነሱት ላይ የሚመሰረተው ክስ፣ የፍርድ ሂደት እጅግ መዘግየትና ፍርዱ ምርጫ ሲመጣ ከመቼውም ቀናት በላቀ ፍርሃት ሲነግስበት ይታያል፡፡ ይሄ በገዥውም፣ በፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆነ በህዝቡ የሚስተዋል አውነታ ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ዋነኛው ምክንያት ተደርጎ የሚወሰደው በስልጣን ላይ ያለው አካል የራስ መተማመን ያለመኖርና የህዝብ አመኔታና ቅቡልነት አለኝ ብሎ ባለማመኑ በሚፈጠር ፍርሃት ነው በሚል ሲተች ይስተዋላል፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ በተለይም ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ ምርጫ ሲቀርብና ሲመጣ ከበጎ ጎን ይልቅ አሉታዊ ተፅዕኖዎቹ ጎልተው ይወጣሉ፡፡
የኢትዮጵያ ምርጫ ታሪክ
ኢትዮጵ ውስጥ የፖለቲካ ምርጫ መካሄድ የጀመረው በ1911 ዓ.ም. ነበር፡፡ ይህም የዘውድ ምክር ቤት በሚል የንጉሱ አማካሪዎች ምርጫ እንጂ የህዝብ የሉዓላዊ ስልጣኑ ባለቤት የሚሆንበት ዴሞክራሲያዊ ምርጫ አልነበረም፡፡ ተመራጮችም የህዝብ ወኪሎች ሳይሆኑ የዘውድ አማካዎች ምክር ቤት አባል ነበሩ፡፡ በመቀጠልም በ1923 ዓ.ም. በሀገሪቱ የተፃፈ የመጀመሪያው ህገ መንግስት በቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ ዘመን መፅደቁን ተከትሎ እኩል ቁጥር ያለው ሁለት ምክር ቤት ምርጫ ተካሂዷል፡፡ ምክር ቤቶቹም የህግ መወሰኛ እና የህግ መምሪያ የሚባሉ ሲሆን፤ አባላቱ የተመረጡት በህዝቡ ቀጥተኛ ተሳትፎ ሳይሆን በንጉሰ ነገስቱና በመኳንንቱ ነበር፡፡ ምክር ቤቶቹም ከ1923-1928 ዓ.ም. የጣሊያን ወረራ ድረስ ሲሰራ ቆይቷል፡፡
ከወረራው ድል በኋላ በ1935 ዓ.ም እንደገና የህግ መምሪያና የህግ መወሰኛ ምክር ቤቶች ያሉት ፓርላማ ተቋቋመ፡፡ የህግ መወሰኛ ምክር ቤት አባላትም በንጉሠ ነገሥቱ የተመረጡ ሲሆን የህግ መምሪያ አባላት ግን እንደቀድሞው በንጉሡና በባለሟሎቻቸው አማካይነት የተመረጡ መሆናቸው ቀርቶ የአገር የሽማግሌዎች በየወረዳቸው ተሰብሰበው የሚመርጡዋቸው ባላባቶች እንዲሆኑ ተደረገ፡፡ እነዚህ የምርጥ ምርጥ ተወካዮች ከ1935 እስከ 1948 ዓ.ም ድረሰ ሳይለወጡ ለ15 ዓመታት አገልግለዋል፡፡ በመቀጠልም ከ1948 ዓ.ም ጀምሮ ህዝቡ ራሱ ወኪሎቹን በቀጥታ እንዲመርጥ ተፈቀደ፡፡ በዚህም መሰረት ከ1948-1967 ዓ.ም በየአራት ዓመቱ አምስት ተከታታይ ምርጫዎች ተካሂደዋል፡፡ በወቅቱም ምርጫውን የሚያካሂደው የምርጫ ቦርድ የተቋቋመ ሲሆን፤ስራውም ከአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ይሰራ ነበር፡፡
በ1967 ዓ.ም. በሀገሪቱ በወታደራዊ ኮሚቴ “ደርግ” በተካሄደው መፈንቅለ መንግስት ሥልጣኑን ጨበጠ፡፡ በሥራ ላይ የነበረው ፓርላማ ተበትኖ በምትኩ በ1967 ዓ.ም በጥቅምት ወር ከልዩ ልዩ ወታደራዊ ክፍሎችና መሥሪያ ቤቶች የተውጣጡ 6ዐ ሰዎችን ያቀፈ የመማክርት ጉባኤ ተመሠረተ፡፡ ይህ የመማክርት ጉባኤ እስከ 1968 ዓ.ም ድረስ ሲሰራ ቆይቶ ተበተነ፡፡
በኋላም በ1979 ዓ.ም 835 አባላት ያሉት የሥራ ዘመናቸውም አምስት ዓመት የሆኑ ባለ አንድ ሸንጎ ምክር ቤት በምርጫ ተሰየመ፡፡ በወቅቱ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች በሀገሪቱ ቢኖሩም፤ዕጩ ተወዳዳሪ የሚጠቁመውምና የሚያስመርጠው የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ “ኢሠፓ” ነበር፡፡ ኢሠፓ ይከተለው የነበረው የሶሻሊስት ርዕዮት ዓለምን በመሆኑ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ዝግጁነቱም ሆነ ፈቃደኝነቱ አልነበረውም፡፡ ስለሆነም በነበረው ምርጫ ጠቋሚው፣ አስመራጩ እና ተመራጩ ራሱ “ኢሠፓ” ነበር፡፡
በግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ.ም. በትጥቅ ትግል ኢሠፓን በኃይል ከተወገደ በኋላ ወደ ሥልጣን በወጣው ኢህአዴግና አጋሮቹ የሽግግር መንግስት ተመሰረተ፡፡ በሽግግር መንግስቱ በየካቲት 1984 ዓ.ም የወረዳና የቀበሌ ጊዜያዊ አስተዳደር አካላት ምርጫመደረጉን እና ብዙ ሳይቆይ በዚሁ ዓመት በግንቦት ወር 1984 ዓ.ም ሀገር አቀፍ፣ ክልላዊ፣ የዞን እና የወረዳ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ መደረጉን የአሁኑ የምርጫ ቦርድ ድርሳን ያመለከታል፡፡
በወቅቱ የነበረው ምርጫ ኮሚሽን ሥራውን አጠናቆ ሲጨርስ በምትኩ የዛሬው “ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ” በአዋጅ ቁጥር 64/1985 ዓ.ም መሠረት ተቋቋመ ፡፡ በተለይ በህዳር 1987 ዓ.ም. በሀገሪቱ ታሪክ 4ኛ ተደረጎ የሚወሰደው ህገ-መንግስት ከፀደቀ በኋላ ቀደም ሲል በአዋጅ የተቋቋመው “የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ” በህገ መንግሥቱ አንቀፅ 1ዐ2 መሠረት ነፃ፣ ገለልተኛና ፍትሃዊ ምርጫ ለማካሄድ የተቋቋመ ሲቪል ተቋም ነው ቢልም፤ ዛሬም ድረስ ከገዥው ስርዓት በስተቀር በህዝቡም ሆነ በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ነፃና ገለልተኛ አይደለም በሚል ይተቻል፡፡
ቦርዱ ከተሠየመበት ከህዳር 1986 ዓ.ም ጀምሮ ጎልተው የሚታዩ ችግሮች ተከትሎ በተፈጠሩ ቅሬታዎች መፍትሔ ይሆናሉ የተባሉ ሐሳቦችን አካቷል በሚል የምርጫ አዋጁ አምስት ጊዜ ተሻሽሏል፡፡ይሁን እንጂ ችግሩ በተለይም ቦርዱ ነፃና ገለልተኛ አይደለም፣ የገዥው ስርዓት አንዱና ዋነኛው መሳሪያ ነው የሚሉ በርካታ ቅሬታዎች ከማስረጃ ጋር ቢቀርብም፤ ቦርዱ ራሱን ነፃና ገለልተኛ ነኝ በሚል ዛሬም ቀጥሏል፡፡
በተለይ በዘመነ ኢህአዴግ የስልጣን ዘመን የተቋቋመው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በስምና በስልት ካልሆነ በግብር ከቀደሙት ብዙም የተለየ አይደለም በሚል ቢተችም፤ በሀገሪቱ የነበረውን የምርጫ ታሪክ ወደ ጎን በመተው፤ ራሱን ቀዳሚ በማድረግ 1ኛው ምርጫ ብሎ የሚጀምረው በግንቦት1987 የተደረገውን ነው፡፡ በመቀጠልም 2ኛው በግንቦት 1992፣3ኛው በግንቦት 1997፣ 4ኛው በግንቦት 2002ዓ.ም. ብሎ 5ኛውን የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለማካሄድ በሂደት ላይ ይገኛል፡፡ ቦርዱ አከናወንኳቸው በሚላቸው ያለፉት አራቱም ምርጫዎች አስፈፃሚዎች፣ የህዝብ ታዛቢዎችና የቦርዱ አባላት ከአባልነት ጀምሮ ለገዥው ስርዓት ወገንተኝነት ስላለ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ አልነበረም በሚል ወቀሳ የቀረበበት ሲሆን፤በተለይ በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓ.ም. የተካሄደው ምርጫ ግን ያልተጠበቁ በርካታ ክስተቶችን አስተናግዷል፡፡ ከነበሩ ክስተቶች መካከልም ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ያልተጠበቀ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገባቸው፣ በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ከምርጫ ውጤት ጋር በተያያዘ በንፁሃን ሲቭሎች ላይ የተፈፀመው ግድያና እስራት እንዲሁም ስደት የማይረሳ ክፉ ትዝታን ጥሎ አልፏል፡፡
ቦርዱ በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓ.ም. የነበረውን የምርጫ ውጤት ይፋ ማድረጉን ተከትሎ በምርጫ ቦረድ፣በገዥው ፓርቲ ኢህአዴግና በዋነኞቹ ተፎካካሪ በነበሩት ቅንጅት እና ህብረት ከፍተኛ ቅራኔ ተፈጠረ፡፡ በዚህም አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ከፍተኛ ተቃውሞች ሲሰሙ፤በተለይም በአዲስ አበባ በመንግስት የመከላከያና ፖሊስ አባላት ህፃናትን ጨምሮ ከ160 በላይ ንፁሃን ዜጎች መገደላቸውን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ በወቅቱ የአሁኑ ምርጫ ቦርድ ይፋ ባደረገው የመጨረሻ ውጤት መሰረት ከ547 የህዝብ ተወካዮች (ፓርላማ) መቀመጫዎች መካከል ኢህአዴግ 327፣ ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች 174 (ቅንጅት 109፣ ህብረት 52፣ ኦፌዴን 11)፣ የኢህአዴግ አጋር ፓርቲዎች የሚባሉት 45 እና 1 የግል ተወዳዳሪዎች መቀመጫ ማግኘታቸውን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡ በወቅቱ በምዕራብ ወለጋ ደምቢዶሎ የግል ተወዳዳሪ ሆነው ያሸነፉት ደግሞ የቀድሞ የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ነበሩ፡፡
በግንቦት 2002 ዓ.ም. የተካሄደው ምርጫ ደግሞ ተስፋ ሲጣልበት የነበረው የዴሞክራሲ ስርዓት በአንድ ፓርቲ ቁጥጥር ስር መውደቁ ራሱ ገዥው ኢህአዴግንም እጅግ ያስደነገጠ ነበር፡፡ ይህም ገዥው ስርዓት በሚከተለው አሰራር ከቢሮ ጀምሮ የመንግስትን ንብረት ከህግ አግባብ ውጭ በይፋ ከመጠቀም አልፎ ከራሱ ውጭ መገናኛ ብዙኃን ጉልህ ሚና እንዳይኖራቸው ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ በገዥው ፓርቲ ጥብቅ ቁጥጥርና መልካም ፈቃድ ካልሆነ ተፎካካሪዎች አማራጭ ፖሊሲዎቻቸውንም ሆነ የአደባባይ የፖለቲካ ምክክርና ክርክር እንደ 1997 ዓ.ም. እንዳያደርጉ በርካታ የእጅ አዙር አሉታዊ ገደቦች የተጣሉ ተጣሉ፡፡ ከነዚህም መካከል በቴሌቪዥን መስኮት ለህዝቡ ፊትለፊት የሚደረግ ክርክር ቀርቶ በስቱዲዮ ተቀርፆና ተቀንሶ እንዲተላለፍ ተደረገ፡፡ በዚህም መሰረት በዓለም ላይ በመድበለ የፖለቲካ ፓርቲ ስርዓት ታይቶ የማይታወቅ በግንቦት 2002 ዓ.ም.በተደረገው ምርጫ ከ547 የፓርላማ መቀመጫ ኢህአዴግና አጋር ፓርቲዎቹ 545 መቀመጫ ድምፅ ሲያገኙ፣ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል 1 ተወዳዳሪ ከአዲስ አበባ የአንድነት/መድረክ ተወካይ አቶ ግርማ ሰይፉ ፣ ከደቡብ ክልል ልዩ ቦታው ከፋ ቦንጋ በሚባል አካባቢ ዶ/ር አሸብር ወልደጊዮርጊስ የሚባሉ 1 የግል ተወዳዳሪ ሆነው ብቻ ማሸነፋቸውን ቦርዱ ይፋ አደረገ፡፡ ከዛ ውጭ ያለውን 99.6 በመቶ የሚሆነው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ በአንድ ፓርቲ ሐሳብና ድምፅ ውክልና ተዋጠ፡፡
መጪው ምርጫ 2007 ዓ.ም. እና ሰብዓዊ መብቶች
ከዛሬ 10 ዓመት በፊት በሀገሪቱ አንፃራዊ ሐሳብን የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት ሙከራ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ 1997 ዓ.ም. ተከትሎ በተወሰዱ ስልታዊ እርምጃዎች 101 የነበሩ የህትመት መገናኛ ብዙኃን በ2007 ዓ.ም. ከ90 ሚሊዮን በላይ ለሆነ ህዝብ ያሉት ጋዜጦችና መፅሔቶች በአጠቃላ ከ25 አይበልጡም፡፡ ከነዚህም 16 ያህሉ በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማኀበራዊ ላይ ትኩረት አድርገው ይሰሩ ከነበሩት ውስጥ 8ቱ መንግስት በመሰረተው ክስና ስልታዊ እርምጃ ከአንባቢው ውጭ ሆነዋል፡፡ የብሮድካስ ሚዲያ በተለይ ከጥቂት መዝናኛ ላይ ትኩረት ከሚያደርጉ ኤፍ ኤም ጣቢያዎችና ንብረትነታቸው የገዥው ፓርቲና የመንግስት ከሆኑት ውጭ አጭርና መካከለኛ የሬዲዮ ሞገድ ስርጭት ጣቢያ እስካሁን አልተፈቀደም፡፡ የቴሌቪዥን ጣቢያ ደግሞ እስካሁን ከመንግስት ቁጥጥር ውጭ የሆነ አንድም የግል የቴሌቪዥን ጣቢያ የለም፡፡ ይህም ምርጫ 1997 ዓ.ም. ለነበረው ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ትልቅ ሚና የነበራቸው በመሆኑ ገዥው ስርዓት እንዲቀጥሉ ባለመፈለጉ የተወሰዱ እርምጃዎች ተደርገው ሊወሰዱ ይችላሉ፡፡በተለይ ከምርጫ 1997 ዓ.መ. በፊት አዲስ ብሮድ ካስቲንግ ካምፓኒ የሚባል የሬዲዮ ጣቢያ የስራ ፈቃድ ወስዶ ለስርጭት የሚያስፈልጉ መሳሪያዎችን ቢያስገባም፤ኩባንያው ስርጭት ሳይጀምር ከምርጫ በኋላ መሳሪያዎቹ እንዲወረሱና ፈቃዱም እንዲሰረዝ ተደርጓል፡፡ ይሄም አንዱ ያለፈው ምርጫ አሉታዊ ተፅዕኖ ውጤት ነው፡፡
የነበሩት የጋዜጦችና የመፅሔቶች መጠን በእጅጉ መቀነስ ዋነኛው ምክንያት ያ የ1997 ዓ.ም. ምርጫ መሆኑ እሙን ነው፡፡ ያ እንዳይቀጥል የተለያዩ አዋጆች ተከታትለው የወጡ ሲሆን፤በዋነኝነትም የፕሬስ ነፃነት አዋጅ፣ የብሮድካስት ማቋቋሚያ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ፣ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኀበራት አዋጆች ይጠቀሳሉ፡፡ አዋጆቹም በቀጥታና በተዘዋዋሪ የፕሬስ ነፃነት እና ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት፣ የፕሬስ ነፃነትና የሲቪክ ተቋማትን መጎልበት አሽመድምደውታል፡፡ በተለይ በአሁን ሰዓት በሀገሪቱ ነፃ ፕሬስ መመስረትና ነፃና ገለልተኛ የሲቪክ ተቋም (የሙያ ማኀበርም ሆነ የብዙኃን ማኀባር) ማቋቋም የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል ማለት ይቻላል፡፡ ይህም የምርጫ ውጤትን ተከትሎ የተወሰደ እርምጃ ሲሆን፣ ለዚህም እርምጃ ህጋዊነት ለማላበስ ተቋማቱ ከገዥው ስርዓት ቁጥጥር እና ፍላጎት ውጭ እንዳይሆኑ የሚያስችል አዋጅ ከመደንገግ በተጨማሪ መዋቅር ዘርግቶ ተቋም እስከመመስረት ተደርሷል፡፡ የዚህም ውጤት ደግሞ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲጣሱ ሰፊ እድል መፍጠሩ ቢታወቅም፤ በመንግስት በኩል ግን እስካሁን የተወሰደ እርምት የለም፡፡
በተለይ በ2001 ዓ.ም. የወጣው የፀረ-ሽብርተንነት አዋጅ የሀገሪቱን እና ህዝቧን ደህንነት ለመጠበቅ በሚል የወጣ አዋጅ ነው ቢባልም፤ በተግባር እየታየ ያለው ግን የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም አዋጁ ህገ መንግስቱን ጨምሮ በርካታ የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን የሚጥሱ አንቀፆች ያሉበት በመሆኑ ሐሳባቸውን በነፃነት ለመግለፅ የሞከሩና በህዝቡ ከፍተኛ ተቀባይነት ያላቸው ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች የአዋጁ ሰለባ ሆነዋል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ አዋጁን ተከትሎ 17 ጋዜጠኞችና ብሎገሮች እንዲሁም ከ200 ያላነሱ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ለከፍተኛ ስቃይና እስር ተዳርገዋል፡፡ መገናኛ ብዙኃን እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ይፋ እያወጧቸው ያሉና ይፋ ያልወጡ በየ አካባቢው በሺህዎች የሚቆጠሩ እንደታሰሩ፣ ፍርድ ቤት ያልቀረቡና ስቃይ እየደረሰባቸው ያሉ ዜጎችም ቀላል አይደሉም፡፡ በዚህም የዜጎች ሐሳባቸውን በነፃነት የመግለፅ፣ ሰብዓዊ ክብራቸውና አካላቸው ያለመደፈር መብትን ጨምሮ የዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸው መነፈጉ ይነገራል፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የ1997 ዓ.ም. ምርጫ ተደርጎ ቢወሰድም፤ በግንቦት 16 ቀን ለሚካሄደው መጪው ምርጫ 2007 ዓ.ም. ላይም አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩ አልቀረም፡፡
ተፅዕኖውም ዜጎች ሐሳባቸውን በነፃነት ገልፀው በሚፈልጉት የፖለቲካም ሆነ ማኀበራዊ እንቅስቃሴ እንዳያደርጉና ገዠው ስርዓት በሚያከናውናቸው አሉታዊ ድርጊቶች ላይ ትችት የሚሰነዝሩ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እስር እንደሚጠብቃቸው በመገመት በፍርሃት እንዲቀድቁ ምክንያት መሆኑ ይነገርለታል፡፡ ይህም በሀገሪቱ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ላይ ገዥው ስርዓት ካላዘዘና ካልፈቀደ በስተቀር በፖለቲካው፣ በማኀራዊ እና በኢኮኖሚው ላይ ነፃ ተሳትፎ እንዳይኖር ተጨማሪ አሉታዊ ተፅዕኖ አለው ብለው የሚከራከሩም አልታጡም፡፡
ቀደም ሲል በተወሰዱ እርምጃዎች መጪው ግንቦት 2007 ዓ.ም. ምርጫ ከወዲሁ የፍርሃት ድባብ እንዳጠላበት በርካታ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡ ለአብነትም ከሚያዚያ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በፖለቲካውና ማኀበራዊ ጉዳዮች ላይ ንቁ ተሳትፎ አላቸው ተብለው የሚታመኑ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አክቲቪስቶች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች መታሰራቸውና በርካታ ጋዜጠኞች መሰደዳቸው ሌላው ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በተለይ ገዥው ፓርቲ በስልጣን ላይ ለመቆየት ካለው ጉጉት የተነሳ የሚወስዳቸው እርምጃዎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እየተጣሱና እንዳሉና፤ የምርጫ ውጤቱ ይፋ ይደረጋል ተብሎ በሚጠበቀው ሰኞ ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚችል ይገመታል፡፡ለዚህመ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩ የስርዓት ለውጥ ፍላጎቶች፣ የኑሮ ውድነት፣ በገዠው ስርዓት የሚፈፀሙ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች ጥሰት ውጤቱንም ሆነ ሂደቱን በፍርሃትና በጉጉት እንዲጠበቅ አስችሎታል፡፡
በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶችና በመራጩ ህዝብ በኩል አሁን ያለው ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚዎችም ሆኑ የህዝብ ታዛቢ ተደርገው የሚቀመጡ ሰዎች ነፃናት ገለልተና ሳይሆኑ ለገዥው ስርዓት ወገንተኝነት የሚታይባቸው ናቸው ተብለው ቅሬታ ቢቀርብባቸውም በቦርዱ በኩል ተቀባይነት ሊያገኙ አልቻለም፡፡ እንደ ምርጫ 1997 ዓ.ም. የአውሮፓ ህብረት፣ የአሜሪካና ሌሎች ነፃና ገለልተኛ ናቸው የሚባሉ በርካታ የሲቪክ ተቋማት ከሀገሪቱ እንዲባረሩ በመደረጋቸው ምርጫ 2007 ዓ.ም. እንደማይታዘቡ መረጃዎች የጠቀሙ ሲሆን፤ ከዓለም አቀፍ ተቋማት የአፍሪካ ህብረት ይገኛል ተብሎ ይገመታል፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት ምርጫው ከወዲሁ የፍርሃት ድባብ ያጠላበት እንዲሆን አስችሎታል፡፡ ምናልባትም የፍርሃት ድባቡ ወደ እውነት የሚቀየር ከሆነና መንግስት ካለበት ውስጣዊና ውጫዊ ችግር በማንኛውም መንገድ ራሱን በስልጣን ለማቆየት ካለው ፍላጎት አንፃር እንደ ከዚህ ቀደሙ የኃይል እርምጃን የሚጠቀም ከሆነ፤ በሀገሪቱም ሆነ በአፍሪካ ቀንድ ሌላ ከፍተኛ የፖለቲካና ማኀበራዊ ቀውስ ሊያስከትል ይችላል፡፡ በተለይም ምርጫውን አስመልክቶና ተከትሎ ሰብዓዊና ዴሞክራሲም መብቶች መጣስ በቀጠናወም ላይም የፖለቲካ አለመረጋጋት በመፍጠር በማኀበራዊና በኢኮኖሚው ዘርፍ ላይም አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚኖረው አያጠያይቅም፡፡ ስለሆነም መጪው ምርጫ ከሰብዓዊና ዴሞክራሲዊ መብት አንፃር ከአዎንታዊ ጎኑ ይልቅ አሉታዊ ተፅዕኖው ሊወጣ ይችላል በሚል ከሀገሪቱ ዜጎች በተጨማሪ የዓለም አቀፍ ትኩረት እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡
እነ አብርሃ ደስታ ለታህሳስ 15 ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተሰጣቸው
∙ተከሳሾቹ የክስ መቃወሚያ አቅርበዋል
በዘለዓለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችን ጨምሮ 10ሩም ተከሳሾች ለታህሳስ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ዛሬ ታህሳስ 9 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛው ወንጀል ምድብ ችሎት የቀረቡት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና አቶ አብርሃ ደስታ እንዲሁም አንደኛ ተከሳሽን ጨምሮ ስድስት ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የክስ መቃወሚያቸውን ይዘው ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡
ሆኖም ግን 7ተኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን የሰጠው የተከሳሽነት ቃል ከክሱ ጋር ተያይዞ ለጠበቃው አለመቅረቡን ተከትሎ ጠበቃው የክስ መቃወሚያ ለማዘጋጀት ባለመቻላቸው የተከሳሽ ቃልን የያዘውን ዶክሜንት ከጽ/ቤት ወስደው መቃወሚያቸውን እንዲያስገቡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን የክስ መቃወሚያ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ ባሉበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሊጎበኟቸው የሚሄዱ ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው ወደ እስር ቤቱ ሲገቡ በተለየ መዝገብ እንዲመዘገቡ እየተደረጉ መሆናቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ተከሳሾች ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው በተለየ መዝገብ በመመዝገባቸው ከሌላው በተለየ ማሸማቀቅ እየተፈጸመባቸው ነው፡፡
ይህን በተመለከተ ለማረሚያ ቤቱ አቤት ቢሉም ሊሻሻል አለመቻሉን ተከሳሾቹ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ለማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም አቤቱታቸውን ተቀብሎ በቀጣይ ቀጠሮ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ስለጉዳዩ ቀርቦ እንዲያስረዳ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡-ነገረ-ኢትዮጵያ
ድምፃዊ ቴዲ አፍሮ ከሃገር እንዳይወጣ ታገደ
በአውሮፓና በተለያዩ መካከለኛው ምስራቅ ሀገራት በርካታ የሙዚቃ ኮንሰርቶቹን ለማቅረብ ወደ ባህር ማዶ ሊጓዝ የነበረው ታዋቂው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ከሀገር እንዳይወጣ መታገዱ ተገለፀ። ቴዲ አፍሮ የሙዚቃ ኮንሰርቱን በፊንላንድ ሄልሲንኪ በነገው ዕለት ማቅረብ ይጀምራል ተብሎ ተጠብቆ ነበር፡፡ ለዚህም የሙዚቃ ባንዱ አባላትና ማናጀሩ ዘካርያስ ጌታቸው እዛው ፊላንድ ቢገቡም፤ ቴዲ ከሃገር እንዳይወጣ በደህንነቶች በመታገዱ ምክንያት የነገው የፊንላንድ ኮንሰርት መሰረዙን አዘጋጆቹ ከፊንላንድ ሄልሲንኪ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታው ቀዋል።
ከጥቂት ወራት በፊት ለቴዲ አፍሮ የበርካታ ወራት እስር በመንግስት በምክንያትነት የተገለፀችው ቢ ኤም ደብልዩ የቤት አውቶሞቢል ከገቢዎችና ጉሙሩክ ቀረጥ ጋር በተያያዘ ክፍያ ሳይፈፀም ወደ ሶስተኛ ወገን በሽያጭ አስተላልፏል በሚል ክስ ተመስርቶበት በዋስ ከተለቀቀ በኋላ ወደ አሜሪካ ሊሄድ ሲል እንዲሁ በደህነንቶች ተይዞ በቦሌ ኤርፖርት ሲጉላላ ከቆየ በኋላ የተለመደ የኮንሰርት ስራውን ቀጥሎ ወደ ሀገሩ መመለሱ አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ ህዳር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. አርቲስቱ ከሀገር እንዳይወጣ ፓስፖርቱ በደህንነቶች ለጉዞ ዝግጅት ላይ እያለ ድንገት መነጠቁን እና ይህ እስከተዘገበበት ድረስም የጉዞ ሰነዱ እንዳልተመለሰለት መረጃዎች አመልክተዋል። ድምፃዊ ቴዲ አፍሮ ለምን ከሃገር እንዳይወጣ እንደታገደ እስካሁን የተገለፀ ነገር የለም:።
በሄል ሲንኪ ፊላንድ የቴዲ አፍሮን ኮንሰርት ለመታደም ትኬቱን የገዙ በርካታ ታዳሚዎች በጉጉት ይጠባበቁ የነበረ ሲሆን፤ከአቅም በላይ በተፈጠረ ችግር ኮንሰርቱን በዕለቱ ማቅረብ ስለማይቻል መሰረዙን አዘጋጁ ቲ-ፕሮሞሽን ከሄልሲንኪ ፊንላንድ አስታውቋል ። ይሁን እንጂ አዘጋጆች ኮንሰርቱ በመሰረዙ ምክንያት ትኬቱን የገዙ ሰዎች ገንዘባቸው ክፍያ በፈፀሙበት መንገድ እንደሚመለስላቸው እና በቅርቡም የታሰበው ኮንሰርት እንደሚካሄድ በመጠቆም፤ ችግሩ የተፈጠረው ከአርቲስቱና ከአዘጋጆቹ አቅም በላይ በሆነ ችግር በመሆኑ አዘጋጁ ይቅርታ ጠይቋል፡፡ ለኮንሰርቱ መሰረዝ የሆነው ችግር እንደተፈታም የሙዚቃ ድግሱ እንደሚቀጥል ተጠቁሟል፡፡
አመክሮና በቀለ ገርባ
የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) ምክትል ሊቀመንበርና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ መድረክ ስራ አስፈፃሚ የነበሩት “ህጋዊ የፖለቲካ ፓርቲን ሽፋን በማድረግ የአሸባሪ ቡድን የሆነው ኦነግ አባል ሆነዋል” በሚል ክስ ተመስርቶባቸው የ8 ዓመት እሥር የተበየነባቸው ሲሆን፤ ይግባኝ ጠይቀው እስሩ ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ተደርጎላቸዋል፡፡
ከ3 ዓመት ከ7 ወር የእስር ጊዜ ውስጥም 3ቱን ዓመት በመጨረሳቸው በአመክሮ ይፈቱ ዘንድ ለማረሚያ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ማረሚያ ቤቱም ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› በማለት እስከአሁን ሊፈታቸው አልቻለም፡፡ ይህም ብዙ ጥያቄዎችን አስነስቷል፡፡
አንዳንድ ህጋዊ ሁኔታዎች ስለጉዳዩ፡
አመክሮ ምንደር ነው?
ሌላውን ትርጉም ትተን የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ‹በተወሰነ ጊዜ በአመክሮ መፈታት› በሚለው ክፍል በተለይም በአንቀፅ 202 እንደደነገገው፡
“ተቀጭው ከተወሰነበት የእስራት ጊዜ ከሶስት እጅ ሁለቱን እጅ ወይም ፍርዱ የእድሜ ልክ እስራት ሲሆን ሀያ ዓመት በፈፀመ ጊዜ አግባብ ባለው አካል ወይም በጥፋተኛው አሳሳቢነት ጥፋተኛውን ከቅጣቱ ነፃ ያወጣዋል፡፡” ይህም ማለት አመክሮ 2/3ኛውን የቅጣት ጊዜውን የጨረሰ ታራሚ ከእስር የሚፈታበት አሰራር ነው፡፡
አመክሮ ለማግኝት ምን መስፈርት ማሟላት ያስፈልጋል?
የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ከላይ በጠቀስነው አንቀፅ 202 ላይ አመክሮ ለማግኝት አንድ እስረኛ ማሟላት የሚያስፈልገውን መስፈርቶች ይዘረዝራል፡፡ ይህም፡
– ‹ታራሚው በስራ ጠባዩ የተረጋገጠ መሻሻል አሳይቶ እንደሆነ…›
– ‹ካሳ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበት ከነበረና ካሳውን መክፈሉ የተረጋገጠ እንደሆነ…›
– ‹አመሉና ጠባዩ መልካም አኗኗር ለመኖር የሚያስችለውና በአመክሮ መፈታቱ መልካም ውጤት ሊያስገኝ ይችላል ተብሎ የታመነ እንደሆነ..›
ነው ብሎ ይደነግጋል፡፡
ማረሚያ ቤት ወይስ ፍርድ ቤት?
ታራሚን በአመክሮ የመልቀቅ የመጨረሻው ስልጣን የፍርድ ቤት፡፡ ነገር ግን ጉዳዩን ማረሚያ ቤቱ በራሱ ተነሳሽነት ወይም በታራሚው አሳሳቢነት ለፍርድ ቤት ሲያቀርብ ነው ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጠው፡፡ እዚህ ላይ ማረሚያ ቤቱ ትልቁን ስልጣን ይዞ እናገኛለን፡፡ ማረሚያ ቤቱ ለፍርድ ቤት ማቅረብ ካልፈለገ ሊተወው የሚችልበት አግባብ አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ማረሚያ ቤቱ በሕግ ስር ያለ አካል እንደመሆኑ መጠን በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 202 ላይ የተቀመጡ መስፈርቶችን ላሟላ ታራሚ አመክሮ ሊከለክል አይችልም – የታራሚው መብት ነውና!
በቀለ ገርባስ?
አቶ በቀለ ገርባ ከተፈረደባቸው የአምስት ዓመት እስር ውስጥ 2/3ኛውን ወይም 3 ዓመት የሚሆነውን ጨርሰው የአመክሮ ጥያቄያቸው በማረሚያ ቤቱ በኩል ለፍርድ ቤት እንዲቀርብላቸው ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የሚል መልስ እንደሰጣቸው ተሰምቷል፡፡
1ኛ. አመክሮ መስጠት የማረሚያ ቤት መብት ሳይሆን ግዴታም ጭምር ነው፡፡ መስፈርቱን ያሟላ ታራሚ አመክሮ የማግኝት መብት ያለው መሆኑ በሌላ በኩል አመክሮ ሰጭውን አካል ላይ ግዴታ ይጥላልና፡፡
2ኛ ሌላው አቶ በቀለ ገርባ መስፈርቱን አሟልተዋል ወይስ አላሟሉም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ 2/3ኛውን የእስር ጊዜ መጨረስ የሚለውን Objective መስፈርት እንዳሟሉ ግልፅ ሲሆን፡፡ ችግሩ የተፈጠረው Subjective መስፈርቱ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ይህም ማለት በእስር ወቅት መልካም ፀባይ አሳይተዋል ወይስ አላሳዩም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ አንድ ታራሚ በእስር ወቅት ለመልካም ፀባይ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮችን ካሳየ የቅጣት ማስጠንቀቂያ ከመፃፍ እስከ ብቻውን ማሰር (Solitary Confinement) ድረስ ያሉ እርምጃዎች በማረሚያ ቤቱ ሊወሰዱበት ይችላሉ፡፡
አቶ በቀለ ገርባ ከፀባያቸው ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ቅጣት ያልተወሰደባቸው ከመሆኑም ሌላ መልካም ፀባይ እንዳሳዩ ከማረሚያ ቤቱ እንደተነገራቸው ራሳቸው ገልፀዋል፡፡ በቀለ ገርባ ምም መስፈር አሟልተዋል ማለት ነው፡፡ ታዲያ ምን ይሆን አቶ በቀለን በአመክሮ ከመፈታት ያገዳቸው?
አንዳንድ ነገሮች…
ባለው አካሄድ አብዛኛው ታራሚዎች በአመክሮ ይፈታል፡፡ ከሌባ እስከ ሙሰኛ፡፡ High Profile በሆኑ ክሶች የተከሰሱ ሰዎች ሳይቀሩ በአመክሮ ሲፈቱ እንደነበር እናስታውሳለን ለምሳሌ ቴዲ አፍሮ 24 ወራት ተፈርዶበት 16 ወራትን ጨርሶ በአመክሮ ተፈቷል፡፡ አቶ አሰፋ አብርሃ 9 ዓመት ተፈርዶባቸው ሰባት ዓመታት ታስረው ከብዙ ውዝግብ በኋላ በአመክሮ ተፈተዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅንጅት ክስ ስር ተከሰው የነበሩት አቶ ዳንኤል በቀለና አቶ ነፃነት ደምሴ 30 ወራት የተፈረደባቸው ሲሆን 20 ወራትን በእስር አሳልፈው አመክሮ ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ ‹ፍርዳችሁን ጨርሳችሁ ውጡ› በሚል ምክንያት አመክሮ ከልክሏቸው ነበር፡፡
እንግዲህ አቶ በቀለ ገርባ በሕጉ የተቀመጠውን መስፈርት አሟልተው እያለ በአመክሮ የመፈታት መብታቸው አልተከበረም ወይም ማረሚያ ቤቱ ግዴታውን ሊወጣ አልፈለገም!
ምክንያት: በጉልበተኞች የምትተዳደር ሀገር ዜጋ ስለሆኑ!
ልዩ ማስታወሻ፡-ይህ ባለፈው ጥር 16 ቀን 2006 ዓ.ም. የዞን 9 ብሎገርና የአምቦ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ዘለዓለም ክብረት ከመታሰሩ በፊት የፃፈው ቢሆንም፤በአሁን ሰዓት እሱ ራሱ በግፍ እስር አቃቂ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ይገኛል፡፡
#FreeBekeleGerba