መንግሥት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 አካባቢ 6 ያህል ነዋሪዎች ገድሎ ከ3 ሺህ ያላነሱ ነዋሪዎችን ቤት አፈረሰ
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ሐና ማርያም፣ ፉሪ፣ ቀርሳ፣ ኮንቱማ እና ማንጎ ጨፌ አካባቢ ነዋሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ አንዲት ነፍሰጡር እናት እና አንድ ቄስን ጨምሮ 6 ያህል ሰዎች ሲገደሉ፤ ከ 3 ሺህ ያላነሱ የመኖሪያ ቤቶች በዶዘር እየፈረሰ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ መንግሥት የኃይል ርምጃውን የወሰደው ሐሙስ ሰኔ 23 እና ትናንት አርብ ሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲሆን፤ በአካባቢው ህፃናት፣ ሴቶች እና ነፍሰጡር የሆኑ እናቶችን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መፈናቀላቸው ታውቋል፡፡ በተለይ አንዲት ነፍሰጡር እናት በቤቷ ተኝታ እያለ፤ ቤቷ በዶዘር ሲፈርስ እዛው መገደሏም ተሰምቷል፡፡

የቤቶቻቸውን በክረምት መፍረስና የመንግሥትን የኃይል ርምጃ የተቃወሙና በጉዳዩ ዙሪያ የሌሉትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውም የተገለፀ ሲሆን፤ የአካባቢው ወንዶች እየፈረሱ ባሉ ቤቶች አካባቢ እንዳይገኙ አካባቢው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር መውደቁ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት የአካባቢው ነዋሪዎች ከቤቶቻቸው መፍረስ በተጨማሪ የመንግሥትን ግድያ እና እስር በመፍራት ከአካባቢው መሰደዳቸው ተጠቁሟል፡፡
መንግሥት የነዋሪዎቹን ቤት በክረምቱ የዝናብ ወቅት ጠብቆ ለምን ማፍረስ እንደወሰና እንደጀመረ ባይታወቅም፤ እንዲፈርሱ የተወሰኑ ቤቶችን የማፍረስ ስራው እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡ በአካባቢውም ቤቶቻቸው በዶዘር እንዲረስ የተደረጉባቸው ሰዎች ንበርትም አብሮ ከጥቅም ውጭ እንዲሆን መደረጉን የአካባቢው ሴቶች ይናገራሉ፡፡
ቀደም ሲል ረቡዕ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. መንግሥት ወደ 30 ሺህ የሚጠጋ የነዋሪዎችን ቤት “ህገወጥ ነው፣ መፍረስ አለበት” በሚል መወሰኑን ተከትሎ ቅሬታ በመቅረቡ፣ የአካባቢው ወረዳ 1 አስተዳደር ነዋሪውን በቦታውና በቤቶቹ ጉዳይ እንነጋገር ብሎ ሰብስቦ እያወያየ ሳለ፤ በጎን አፍራሽ ግብረ ኃይልና የፀጥታ ኃይል ልኮ ማፍረስ በመጀመሩ በተፈጠረ አለመግባባት የወረዳው ስራ አስፈፃሚ እና ፖሊሶች መገደላቸውን፣ ከነዋሪዎችም ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች መገደላቸውን እና መቁሰላቸው ይታወሳል፡፡
ከቤቶቹ መፍረስ ጋር በተያያዘ የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ)፤ መንግሥት ከ19 ሺህ ያላነሱ ቤቶችን ማፍረሱን በመጠቆም፤ እየተወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ እንዲያቆምና ቤቶቹን አፍርሶ ነዋሪዎቹን ለጎዳና ህይወት ከመዳረግ ይልቅ መፍትሄ ሊበጅለት እንደሚገባ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ጠይቋል፡፡
የአቶ ሀብታሙ አያሌው ጤና አደጋ ላይ በመውደቁ ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለበት እግድ እንዲነሳ ተጠየቀ
(አዲስ ሚዲያ) የቀድሞው የአንደነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው የጤናው ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ በመድረሱ ተገቢውን ህክምና ማግኘት አለመቻሉ ታውቋል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ህመሙ ይበልጥ ተባብሶ ራሱን በመሳቱ በአቅራቢያ ወደሚገኘው ዋሸንግተን ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ዕርዳታ ማግኘት ባለመቻሉ ወደ ቤተዛታ ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ርዳታ ባለማግኘቱ ወደ ካዲስኮ ሆስፒታል ተወስዶ በማስታገሻ ሆስፒታል ውስጥ አልጋ ይዞ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡

አቶ ሀብታሙ የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል “ማዕከላዊ”ን ጨምሮ ለ18 ወራት ያህል በታሰረበት ባጋጠመው ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ቢጠይቅም ከመንግሥት በጎ ምላሽ ባለመገኘቱ ከእስር በነፃ ከተለቀቀ በኋላ ህመሙ እንደተባባሰ ተጠቁሟል፡፡
አቶ ሀብታሙ በሀገር ውስጥ ባሉ የተለያዩ የህክምና ተቋማት ተገቢውን የህክምና ክትትል ለማድረግ ቢንቀሳቀስም ህመሙ ካለበት ከፍተኛ ደረጃ አንፃር አቅም ካለው ከሀገር ውጭ ሄዶ ቢታከም የተሻለ እንደሆነ ከዶክተሮቹ በተነገረው መሰረት በውጭ ሀገር ህክምና ማድረግ ቢፈልግም፤ የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሀገር እንዳይወጣ በጣለው እግድ መሰረት ተገቢውን ህክምና ባለማግኘቱ ማክሰኞ ራሱን መቆጣጠር የማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱ ታውቋል፡፡ በአቃቤ ህግ ይግባኝ ምክንያት ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለው የፍርድ ቤት እግድ እንዲነሳ አቶ ሀብታሙ በጠበቃቸው አቶ አምሃ መኮንን አማካኝነት ፍርድ ቤቱን ቢጠይቅም እስካሁን ምላሽ እንዳልተገኘ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ኢትዮጵያውያን በማኀበራዊ ሚዲያ እና አምንስቲ ኢንተርናሽናል አቶ ሀብታሙ ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለበት እግድ እንዲነሳ እና ተጊቢውን የህክምና ዕርዳታ እንዲያገኝ ሊፈቀድ ይገባል ሲሉ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን፤ የማኀበራዊ ሚዲያ ዘመቻው እስከነገ እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ ይህ እስከ ተዘገበበት ድረስ አቶ ሀብታሙ ራሱን ስቶ በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ በካዲስኮ ሆስፒታል ተኝቶ እስኪነቃ በሚል ከሚሰጠው ማስታገሻ በስተቀር ምንም ዓይነት መደበኛ የህክምና ዕርዳታ እንዳልጀመረ ታውቋል፡፡
በአዲስ አበባ በመንግሥት እና በህዝብ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የአዲስ አበባ ፖሊሶች ተገደሉ!
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ፉሪ ሐና ማርያም ቀርሳ ኮንቱማ እና ማንጎ ሰፈር በሚባል ስፍራ ትናንት ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በነዋሪውና በከተማ አስተዳደሩ መካከል በተፈጠረ ግጭት ከ4 ያላነሱ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ 1 አፍራሽ ግብረ ኃይል እና 1 የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች ገለፃ ከሆነ፤ ከነዋሪዎችም በርካታ ሰዎች በፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መቁሰላቸውን እና የህክምና እርዳታም እንዳያገኙ መደረጋቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በተፈጠረው ግጭት የሟቾች ቁጥር ከተጠቀሰው በላይ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡ መንግሥት በበኩሉ ዛሬ በተፈጠረው ግጭት ሁለት ፖሊስ እና የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን አስታውቋል፡፡

የግጭቱ ዋነኛ ምክንያት መንግሥት በአካባቢው ያሉ 30 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ከመንግሥት እውቅና ውጭ በህገ ወጥ መንገድ ቤት ሰርተው እየኖሩ ያሉ ሰዎች ቤታቸውን አፍርሰው ከአካባቢው መነሳት አለባቸው የሚል ውሳኔን ተከትሎ፤መንግሥትም ቤቶቹን ለማፍረስ የቤት አፍራሽ ግብረ ኃይል፣ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ አራት ሲቪለ የለበሱ ማንነታቸው ያልታወቁ ሰዎች፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ የመብራት ኃይል ሰራተኞች እና ሁለት የአካባው የወረዳ አመራር ወደስፍራው ልኮ እንደነበር ታውቋል፡፡
የቤታቸውን መፍረስ በመቃወም የአካባቢው ሴቶችና ህፃናት ወደ አዲስ አበባ ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ቅሬታ ለማቅረብ ቢሄዱም ሰሚ ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ሐና ማርያም አካባቢ የሚገኘው የወረዳው አስተዳደር የአካባቢውን ነዋሪ በቤት መፍረሱ ጉዳይ ኑና እንነጋገር በሚል ከጠራ በኋላ፤ በጎን ወደነዋሪዎቹ አካባቢ አፍራሽ ግብረ ኃይል መላኩ ነዋሪውን ይበልጥ እንዳበሳጨውና ለህይወት መጥፋት ዋናው መንስኤ እንደሆነ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
ቤቶቻቸው በኃይል እንዲፈርስ ከተደሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ምንም ዓይነት ካሳ እና ምትክ ቤትም ሆነ ቦታ በመንግሥት እንዳልተሰጣቸው የጠገለፀ ሲሆን፤ እንዲፈርሱ በተወሰነው የመንደሩ ነዋሪዎች በርካታ አዛውንት፣ ህፃናት፣ ነፍሰጡር እናቶች እንደሚገኙ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ወቅቱ ከፍተኛ ዝናብ የሚዘንብበት ክረምት በመሆኑ፤ ነዋሪዎች ቤቶቻቸው ያለምንም ምትክ ቤትና ካሳ ቤቶቻቸው የሚፈርሱ ከሆነ ህፃናትና ነፍሰጡር እናቶችን ጨምሮ ሁሉም ለጎዳና ህይወት እንደሚዳረጉ እየተናገሩ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ከመንግሥት በኩል ስለምትክ ቤትና ቦታም ሆነ ካሳን በሚመለከት እስካሁን የተባለ ነገር የለም፡፡ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በአካባቢው አሁንም ውጥረት እንደነገሰ ነው፡፡
ባለፈው ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በተመሳሳይ መልኩ በቦሌ ልፍለከ ከተማ ወረዳ 12 ልዩ ስሙ ወረገኑ በሚባል ስፍራ 20 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ያሉበትን ቤት፤ መንግሥት ህገወጥ ነው በሚል ለማፍረስ በመንቀሳቀሱ በተፈጠረ አለመግባባት የሰው ህይወት መጥፋት የአካል ጉዳት ማስከተሉ አይዘነጋም፡፡
የግዕዝ ጉባዔ በጅማ ዩኒቨርስቲ “ዓይን ቅንድብን ያየበት” ተካሄደ
በሔኖክ ያሬድ
የቡናዋ ገበታ ጅማ ከተማ መሰንበቻውን በጅማ ዩኒቨርሲቲ አማካይነት ጥንታዊውን የኢትዮጵያ ቋንቋ ግእዝን የተመለከተ አገር አቀፍ ጉባኤ አስተናግዳ ነበር፡፡

“የግእዝ ቋንቋ ሀብት ለሀገራዊ ዕድገት ያለው ፋይዳ” በሚል መሪ ቃል የተካሄደው ሦስተኛው ጉባኤ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቋንቋና የጋራ ባህል እሴቶች ልማት ዳይሬክቶሬት፣ ከብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባህል ማዕከልና ከጅማ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ነው፡፡ በጉባኤው አሥር ወረቀቶች ቀርበውበታል፡፡
“ግእዝን የኢትዮጵያውያን የጋራ ታሪክና ባህል የተጻፈበት መሆኑ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ብሔረሰቦች ሊቃውንት በጋራ ያሳደጉትና ያበለጸጉት ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ነው፤” የሚሉት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዶ/ር ሥርግው ገላው እንደማሳያነት ያቀረቡት ቀደምት የኦሮሞ ሊቃውንት ድርሻን በማሳየት ነበር፡፡
እንደ አፄ ሱስንዮስ ታሪክ ጸሐፊ አዛዥ ጢኖ (አለቃ ተክለሥላሴ)፣ እንደ ዝነኛው የቅኔና መጻሕፍት መምህር አለቃ ገብረሥላሴ ክንፉ፣ እንደ ንጉሥ ተክለሃይማኖት ታሪክ ጸሐፊ አለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ፣ እንደ ዝነኛው የቅኔና መጻሕፍት መምህር መምህር ጥበቡ ገሜና ሌሎችም በርካታ የኦሮሞ ሊቃውንት ለግእዝ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ዕድገት ያደረጉትን አስተዋጽኦ ዶ/ር ሥርግው አስታውሰዋል፡፡
አዛዥ ጢኖ የጻፉት የአፄ ሱስንዮስ (1597-1625) ዜና መዋዕል ከዚያ በፊትም ሆነ ከዚያ በኋላ ከተጻፉት ዜና መዋዕሎች በብዛትም (የአፄ ሠርፀ ድንግልን ሳይጨምር) ሆነ በጥራት ከሁሉም የተሻለ ነው ብለውታል አጥኚው፡፡
ዶ/ር ሥርግው በማሳያነት ያቀረቡት ሌላው ሊቅ አለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ ከታሪክ ጸሐፊነታቸው በተጨማሪ በሠዓሊነትም ይታወቃሉ፡፡ በ1860 ዓ.ም. አካባቢ ወለጋ ኩታይ [ጉድሩ] ውስጥ የተወለዱት አለቃ ተክለኢየሱስ የጎጃም ንጉሥ ተክለሃይማኖት ታሪክ ከመጻፋቸውም ሌላ በ1961 ዓ.ም. የልዑል ራስ ተፈሪ መኰንን የአውሮፓ ጉብኝትና የዚህ ጉብኝት ተሳታፊ በነበሩት በራስ ኃይሉ አለመኖር ምክንያት በደብረ ማርቆስ ከተማ የተፈጠረውን ግርግር አካትተው የጻፉት ይጠቀሳል፡፡
የግእዝ ቋንቋ በአፍ መፍቻነት ያገለግል በነበረበት ጊዜ እንደማንኛውም ቋንቋ ባህላዊ ዘፈን ሲዘፈንበት የቆየ መሆኑን ያመለከቱት ሌላው ጥናት አቅራቢ የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲው ዶ/ር ሙሉቀን አንዱዓለም ናቸው፡፡ ‹‹ማሕሌተ ገንቦ›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናታቸው እንዳመለከቱት፣ ማሕሌተ ገንቦ የሚባለው የግእዝ ዘፈን ከጥንት ጀምሮ ሲዘፈን የመጣ የዘፈን ዓይነት ነው፡፡ ሰይህ ዓይነት ዘፈን የሚዘፈነው በአሁኑ ሰዓት በቤተ ክህነት ሰዎች ሲሆን ዘፈኑ የሚከናወንባቸው ዐውዶችም የተለያዩ ናቸው፡፡ በዋናነት ሠርግን፣ ማኅበርን፣ የዓመት በዓልን፣ ክርስትናን፣ በአጠቃላይ ካህናቱ በሚጠሩባቸው የደስታ ድግሶች ሁሉ ይከናወናሉ፡፡
የማሕሌተ ገንቦ ዘፈኖች በአሁኑ ሰዓት የሚዘፈኑት ለካህናት ሆነው የሚዘፈኑባቸው ዐውዶችም ሠርግ፣ የዓመት በዓላት፣ ክርስትና፣ ማኅበር ወዘተ. ቢሆኑም ለዚህ ጥናት የቀረቡት የሠርግ ግጥሞች ናቸው፡፡ በማሳያነት ከቀረቡት መካከል የሚከተሉት ይገኙባቸዋል፡፡
‹‹ዝ ጠላ ከመ ወይን ጣእሙ፤ እስኪ ድግሙ ድግሙ እስኪ ድግሙ
ይህ ጠላ ጣዕሙ እንደ ወይን ነው፡፡ እስኪ ድገሙ፤ እስኪ ድገሙ፡፡
እመይቴ ጥሩ ዓይነት እጅሽን ይባርከው መልሶ መልሶ፣
ያደረግሽው ጠላ በማር ተለውሶ፣
ቁርጥማት አይንካው ጥሩዬ እጅሽን፣ ይህንን ጠላና ጠጅ ያረገውን፣
ይህን ጠላና ጠጅ የጠጣችሁ ኹሉ፣
ጥሩ ዓይነት ጥሩ ዓይነት እጡብ ድንቅ በሉ››
እንደ ዶ/ር ሙሉቀን ማብራሪያ፣ ይህም በኢትዮጵያ ባህል የደገሰውን ሲበሉለት፤ የወለደውን ሲስሙለት ባለቤቱ በጣም ደስተኛ ስለሚሆን የማስደሰት ኃይሉ ከፍተኛ ነው፡፡ መልእክቱም የሚጠጣው ጠላ እጅግ ተወዳጅ በሚሆንበት ጊዜ ደጋግመው እንዲጠጡ ጥያቄ የሚያቀርቡበትና ጠላውን የሚያደንቁበት ስንኝ ነው፡፡
ከሴትዮዋ ስም ጋር በማስተባበር ዓይነቱ ጥሩ እንደሆነ አመስጥረውበታል፡፡ ይህ ስንኝ በሐዲስ ዓለማየሁ ፍቅር እስከ መቃብር መጽሐፍም ተጠቅሶ ይገኛል፡፡
‹‹ወይቤላ ንዒ ከመ ንትዋነይ››
የዚህ ስንኝ ትርጉምም፡- ሙሽራው ሙሽሪትን እንጫወት ዘንድ ነዪ አላት፡፡ ለማለት ነው፡፡
ብዙውን ጊዜ የማሕሌተ ገንቦ ግጥሞች ደራሲያቸው ስለማይታወቅና በምሁራን የማይደረሱ የሕዝብ በመሆናቸው እንደ ቅኔ ጠንካራ ሕግ የላቸውም፡፡ በግእዙ ስንኝ ላይ ያለውን ስንመለከት ባለቤቱ (ጠሪውም ተጠሪዋም) በግልጥ አልተቀመጡም፡፡ ሲፈልግ የአማርኛ፣ ሲፈልግ የግእዝ ወይም ደግሞ እያቀላቀለ ግጥሞችን ያስገባል፡ በምሳሌነት የሚከተለውን አጥኚው አሳይተዋል፡- ‹‹ወይቤላ ንዒ ከመ ንትዋነይ፡፡
ተማሪ ተማሪ ተማሪ ቢሉሽ፤
ከጉድጓድ የወጣ ገብስ አይምሰልሽ፤
መደረቢያው ካባ መጠምጠሚያው ሻሽ፤
ወይቤላ ንዒ ከመ ንትዋነይ፡፡
ተማሪውና ሙሽራዋ በሚጋቡበት ጊዜ ሙሽራዋ የቄስ ተማሪ ስታገባ ቅር እንዳይላት በካባ፣ በሻሽ የተንቆጠቆጠ ምሁር እንጂ ከጉድጓድ እንደ ወጣ ገብስ የተናቀ አይደለም ለማለት ነው ሲሉ አጥኚው አብራርተዋል፡፡
በዚህ ጥናት ውስጥ ኅብረተሰቡ አብሮ በግእዝ ይዘፍን እንደነበረ፤ ቋንቋውም እንደማንኛውም ቋንቋ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ብቻ ሳይሆን ለዓለማዊ ዘፈንም አገልግሎት ይሰጥ እንደነበረና የዜማው ሁኔታም ሲታይ የራሱ የሆን ውበት ቢኖረውም ከቅዱስ ያሬድ ዜማ አጠርና ፈጠን ያለ ምት እንዳለውና የኅብረተሰብን የአኗኗር ሁኔታ የሚዳስሱ ማኅበራዊ ግጥሞች በመሆናቸው ማሕሌተ ገንቦ በደምብ ሊጠና ይገባል የሚል ምክር አዘል መልእክት ጥናት አቅራቢው አቅርበዋል፡፡
በሦስተኛው ጉባኤ ከቀረቡት ጥናቶች መካከል የዝዋይ ሐይቅ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ቅርሶችን የዳሰሰ፣ ግእዝ ለአማርኛ የፍልስፍና ቃላት ያደረገው አስተዋጽዖ፣ በግዕዝ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ስለሚገኘው የሥነ ፈለክ ትምህርት፣ እውቀት እንደ ሕንጻ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ሥርዓተ ትምህርት ፍልስፍና እና የግእዝ ግሶች ሥነ ድምፅ የሚተነትን ሶፍትዌር ለመሥራት የተደረገውን ጥረት አመልካች ጥናቶች ይገኙበታል፡፡
ከአዲስ አበባ ደቡብ ምዕራብ 346 ኪሜ ርቀት ላይ በሚገኘውና ጉባኤውን ባስተናገደው ጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት፣ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ለሜሳ አነጋገር፣ በግእዝ ቋንቋ የተከማቹ የመረጃ ሀብቶች ለአገሪቱም ይሁን ለጠቅላላው የሰው ልጆች በርካታ ጥቅም ያላቸውን ዘርፈ ብዙ ዕውቀቶች ያዘሉ ናቸው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ እነኚህን በርካታ ዕውቀቶች አውጥቶ ለዘመናዊው የኑሮ ሥርዓት ጥቅም ላይ ለማዋልም ይሁን ለቋንቋዎቻችን ዕድገትና ልማት አስተዋጽኦ እንዲያደርግ በሚመለከታቸው የመንግሥትም ይሁን ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገቢው ትኩረት ተሰጥቶት በመዋቅር፣ በአደረጃጀትና በስትራቴጂ የሚሠራ አካል እምብዛም እንደማይታይ የጠቆሙት ፕሮፌሰር ፍቅሬ፣ ከአገሪቱ ይልቅ ምዕራባውያን ከቋንቋውና ቋንቋው ከያዘው መረጃ ተጠቃሚ ለመሆን ለበርካታ ዓመታት በቋንቋው ላይ ጥናት ከማከናወናቸው ባሻገር፣ በዘርፉ በከፍተኛ ደረጃ ተመራማሪዎችንና አማካሪዎችን በማፍራት ራሳቸውን የቻሉ የግእዝ የትምህርት ክፍሎች ከፍተው በመሥራት ላይ ይገኛሉ ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ አያይዘውም፣ የግእዝ ቋንቋ በውስጡ አምቆ የያዛቸውን የሕክምና፣ የምህንድስና፣ የሥነፈለክ፣ የሥነትምህርትና የኪነጥበብ ትሩፋት የሚጣጣሙበት ከመሆኑ በተጨማሪ፣ ለወደፊቱ ለአገር ዕድገት መሠረታዊ የሆኑ ዕውቀቶች እየተመረመሩ ከዘርፉ የሚገኘውን አገራዊ ጥቅም የሚያድግበት እንደሚሆን ተስፋቸው መሆኑን ሳይናገሩ አላለፉም፡፡
በግእዝ ቋንቋ የተጻፉ፣ የሥነ ጽሑፍ ቅርሶችና መረጃዎች የሕክምና ጥበብ ምንጭና የባህላዊ መድኃኒቶች መሠረት የሚጠቁሙ፣ የነገሥታት አስተዳደር፣ የሕጋዊ የዳኝነት ሥርዓት፣ የሕዝቦች የመቻቻልና የመደጋገፍ ጥበብና ሥርዓት፣ እንዲሁም የዘመን አቆጣጠር መነሻና መሠረት ምንጭ መሆኑ ያመለክታሉ ያሉት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ጮሻ፣ ይህም የግእዝ ቋንቋ የሥራ፣ የመግባቢያና የመተዳደሪያ ቋንቋ እንደነበረ ያመለክታል ብለዋል፡፡ የግእዝ ጉባኤ መካሄዱ ትክክለኛ መረጃ በማድረስ ግንዛቤውን ለማሳደግ ያግዛል የሚል እምነት እንዳላቸውም አቶ አብርሃም ተናግረዋል፡፡
ሃቻምና በአክሱም የተጀመረው የግእዝ ጉባኤ፣ አምና ሁለተኛውን ጉባኤ በባሕር ዳር ማከናወኑ ይታወሳል፡፡ በዘንድሮው ጉባኤ ማጠቃለያ በተደረገው ውይይት በሦስቱ ጉባኤዎች ግንዛቤን በመፍጠር ረገድ ትልቅ ሥራ መሠራቱ ተመልክቷል፡፡ የጅማ ዩኒቨርሲቲ የሶሻል ሳይንስና ሂዩማኒቲስ ፋኩልቲ ዲን ዶ/ር ደጀኔ ገመቹ፣ ጉባኤ ከማዘጋጀት ባለፈ ለወደፊት ምን መሠራት እንደሚኖርበት የሚጠቁም ከትምህርት ሚኒስቴር፣ ከሃይማኖት ተቋማትና ከሌሎችም የሚውጣጣ ግብረ ኃይል መቋቋም እንዳለበት ተናግረዋል፡፡
ለየት ያለ ሐሳብ ያነሱት ዶ/ር ሙሉቀን በሦስት ዓመት ውስጥ ብዙ ውጤት ለማየት የመጓጓት ሁኔታ መኖሩን ጠቁመው፣ ነገር ግን ኅብረተሰቡ በደንብ የተረዳው ስላልሆነ ሰፊ የማስገንዘቢያና የቅስቀሳ ሥራ መሠራት አለበት ብለዋል፡፡
‹‹ለተወሰነ ቡድን ከሚሰጥ ሁሉም እንደባለቤት መንቀሳቀስ አለበት፡፡ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ትስስር መፍጠር አለበት፤ ከጅማ ዩኒቨርሲቲ ጋር እንደተካሄደው ዓይነት ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች ከገቡበት ውጤት ሊመጣ ይችላል፡፡ ወደታችም ሁለተኛ ደረጃ መለስተኛና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችም መውረድ አለበት፡፡ ተተኪውን ትውልድ ማስተማር አገር በቀሉን ዕውቀት ለማስተላለፍ ያስችላልና፡፡››
በዓለም አቀፍ ደረጃ ግእዝን የሚመለከቱ እስከ አሥር የሚደርሱ ጆርናሎች በየዓመቱ እንደሚወጡ ያመለከቱት በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከፍተኛ የቋንቋ ባለሙያና የጉባኤው አስተባባሪ አቶ ዓለማየሁ ጌታቸው ናቸው፡፡ ግእዝን የመመርመር አስፈላጊነትና ጠቀሜታ እንዲህ አመላከቱት፡፡
‹‹የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ግእዝን ለምን አተኩሮ ያጠናል? እኛስ ለምንድን ነው የማናጠናው? ጥያቄ መሆን ያበት ይኼ ነው፡፡ የተሻለ ሥራ ለመሥራት ዕውቀት እናምጣ ካልን ከሩቅ ከባሕር ማዶ ከምናመጣቸው ዕውቀቶች ይልቅ፣ ከባህላችን ጋር ተሰናስለው የተፈጠሩ በግእዝ የተጻፉ ሀብቶች አሉን፡፡ እነዚህን ጥንታዊ ዕውቀቶች ፈልፍለን አውጥተን፣ ለዛሬው ኑሮ ሥርዓታችን የመጠቀምና ያለመጠቀም ምርጫ ነው፡፡ ይጠቅመናል ካልን እንመርምረው፣ እንፈትሸው እናውጣው፣ አይጠቅመንም ካልን እንተወው፣ ስለዚህ መጥቀም አለመጥቀሙን ለማወቅ በመስኩ ለተሰማራን የግንዛቤ ሥራ ያስፈልጋል፡፡››
አንዱ ጉባኤተኛም በሦስቱ ዓመታት በአክሱም፣ በባሕርዳርና በጅማ የተካሄዱትን ሦስቱን የግእዝ አዝመራ ጉባኤዎች አያይዘው፣ ‹‹ዓይን ቅንድብን ያየበት›› መድረክ ነው ሲሉ አወድሰውታል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ
ፓርላማው የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ኮሚሽን ምክር ቤት አባላትን ሹመት አፀደቀ
• ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሰብሳቢ ሆነዋል
ዮሐንስ አንበርብር

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለሕዝብና ቤት ቆጠራ ኮሚሽን ምክር ቤት አባልነት ያቀረቧቸውን 23 ዕጩዎች ሹመት አፀደቀ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 103 ንዑስ አንቀጽ ሁለት እንዲሁም በሕዝብና ቤት ቆጠራ ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 449/97 መሠረት ዕጩ የማቅረብ ሥልጠናቸውን ተጠቅመው ነው ለምክር ቤቱ ዕጩ ተሿሚዎችን ያቀረቡት፡፡
በኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 449 አንቀጽ ስድስት መሠረት የኮሚሽኑ አባላት ለሕዝብ ቆጠራ ጉዳይ አግባብነት ካላቸው የፌዴራል ሚኒስቴር ሚኒስትሮች፣ ከምርጫ ቦርድ፣ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት፣ ከዘጠኙ ክልሎች፣ ከአዲስ አበባና ድሬዳዋ መስተዳድሮች የተውጣጡ ይሆናሉ፡፡
በዚህ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሐረር ክልል ርዕሰ መስተዳድር በስተቀር ሁሉም ክልሎችና የከተማ መስተዳድሮች በምክትል ርዕሰ መስተዳድሮችና በምክትል ከንቲባዎቻቸው የኮሚሽኑ አባል እንዲሆኑ በዕጩነት አቅርበዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሕዝብና ቤት ቆጣራ ጉዳይ አግባብነት ካላቸው የፌዴራል ሚኒስቴር ሚኒስትሮች፣ ከፌዴሬሽን ምክር ቤትና ከምርጫ ቦርድ በሚለው የኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ መሠረት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ለኮሚሽኑ ምክር ቤት ሰብሳቢነት አጭተዋል፡፡
የተቀሩት የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበው፣ የፌዴራልና የአርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትሩ አቶ ካሳ ተክለብርሃን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ ሚኒስትር አቶ ከበደ ጫኔ፣ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን አቶ ይናገር ደሴ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ያለው አባተ (ብአዴን) ሲሆኑ፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትሩ አቶ አብዱላዚዝ መሐመድ፣ የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ ወርቅነህ ገበየሁ (ኦሕዴድ)፣ የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ (ደኢሕዴን)፣ የመንግሥት ጉዳዮች ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ (ሕወሓት) በዕጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነጋ ዱፊሳና የማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ቢራቱ ይገዙ (በጸሐፊነት) በአባልነት ቀርበዋል፡፡
በቀረቡ ዕጩዎች ዙሪያ የመከሩት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የባለፈው የሕዝብና ቤት ቆጠራ ላይ በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ የሕዝብ ብዛት ላይ ተፈጥሮ የነበረው ከፍተኛ ስህተት እንዳይደገም አሳስበዋል፡፡
የምክር ቤቱ ሴት ተወካዮች በበኩላቸው ከቀረቡት የኮሚሽኑ ዕጩዎች ውስጥ አንድ ሴት ብቻ በዕጩነት መቅረባቸው አስቆጥቷቸዋል፡፡
‹‹የሴቶች ስብጥር በዚህ ሹመት ላይ መታየት አለበት፡፡ መንግሥት በዚህ ላይ ቁርጠኝነቱን ማሳየት ሲገባው የታየው ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ይህ የድርጅታችን ባህል አይደለም፤›› ሲሉ አንድ ሴት ተወካይ ተከራክረዋል፡፡
የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትሩ አቶ አስመላሽ ወልደሥላሴ በሰጡት ምላሽ፣ መንግሥት ከስህተቱ የመማር ልምድ ስላለው በባለፈው ቆጠራ የተከሰተው ችግር እንደማይደገም፣ የሴቶች ስብጥርን በተመለከተ የመንግሥት ቁርጠኝነት እንደሚታወቅና በዚህኛው ላይ አንድ ብቻ መወከላቸው ዕጩ ምልመላው የተካሄደው አዋጁን መሠረት ያደረገ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡
የአቶ አስመላሽ መልስ ለምክር ቤቱ ሴት አባላት አጥጋቢ አልነበረም፡፡ የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባዔ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ ‹‹ሴት ብሆንም በዚህ መድረክ ላይ አቋም መያዝ አልችልም፡፡ በተጨማሪም አዋጁን ማሻሻል የሚጠይቅ በመሆኑ ወደ ድምፅ ብንሄድ፤›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በዚህ መሠረት የኮሚሽን አባላቱ ሹመት በአንድ ተቃውሞ፣ በዘጠኝ ድምፅ ተአቅቦ ፀድቋል፡፡
ሦስተኛው ብሔራዊ የሕዝብና ቤት ቆጠራ በኅዳር ወር 2010 ዓ.ም. ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ