Category Archives: Social and Culture

ፍርድ ቤቱ ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጣ

በጌታቸው ሺፈራው

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእስር ላይ የምትገኘው ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጥቷል። በእነ ደቻሳ ሞሲሳ የክስ መዝገብ 4 ተከሳሽ ጫልቱ ታከለ “እናንተ ኢህአዴግ ናችሁ፣ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አልጠብቅም” ብላ ተናግራለች በሚል በችሎት መድፈር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።
Chaltu Takele
ፎቶ፡- ጫልቱ ታከለ

ህዳር 28 ቀን 2010 ዓም እነ ደቻሳ ሞሲሳ ተከላከሉ የሚል ብይን በተሰጠባቸው ወቅት 3ኛ ተከሳሽ የሆነችው ጫልቱ በሰነድ ማስረጃነት የቀረበባት የደህንነት ሪፖርት ወደ ኤርትራ ስለመሄድ የጠቀሰው ነገር ሳይኖር ብይን ላይ ወደ ኤርትራ ልትሄድ እንደነበር ተጠቅሶ ተከላከይ መባሏ እንዳሳዘናት ገልፃለች።
ጫልቱ ታከለ በወቅቱ “ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አንጠብቅም። ወደፊትም ፍትህ እንደማናገኝ ነው የምናስበው።” ብላ በመናገሯ በችሎት መድፈር ጥፋተኛ ተብላ በአዳር ዛሬ ህዳር 29 ቀን 2010ዓ.ም. የ500 ብር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።

ጫልቱ ታከለ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ክስ ተፈርዶባት ፍርዷን ጨርሳ እንደወጣች ተገልጿል።

የፖለቲካ እስረኞች በኢትዮጵያ እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትን አስመልክቶ የድረሱልን ጥሪ አቀረቡ

በመቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ ላይ ያሉ 38ቱ ተከሳሾች አቤቱታ

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን(ኢሰመኮ) ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!
Masresha Setie
ፎቶ፡- ማስረሻ ሰጤ

~ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የተሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።

~አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።

እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተከሰን በነበርንበት ክስ የዋስትና መብተችንን ተከልክለን እንደማንኛውም እስረኛ ክሳችንን በቀጠሮ እየተከታተልን ሳለን ነሃሴ 28/ 2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ውስጥ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ ምክንያት “ሊያመልጡ ሞክረዋል!” በሚል ሰበብ፣ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥያቄ የሚጠይቁ ወንድሞቻችን (ጓደኞቻችንን) እኛ ፊት በጥይት ገድለው እሳት ውስጥ ጨምረው አቃጥለዋቸዋል።

እንዲህ ያለ አረመኔያዊ ድርጊት ከፈፀሙ በኋላ ገና ለገና ይህንን እውነት ያጋልጡብናል ብለው በመስጋት እኛን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት በመውሰድ ለ3ወራት ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ በማፈን፣ ለምርመራ በሚል ሰበብ በዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ በሚመራው ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሰማዕታት ሙዝዬም ውስጥ ሀውልት የተሰራለት የ”ቶርች” ገረፋ ተፈፅሞብናል።

በካቴና ታስረን፣ ተሰቅለን ተገርፈናል። ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። በኤሌክትሪክ ሾክ ተደርገናል። በሚስማር ውስጥ እግራችንና ጀርባችን ተበሳስቷል። ጭንቅላታችንን በሰደፍ ፈንክተውናል። የተወሰንን ታራሚዎች ተለይተን ብልታችን ላይ ሁለት ሊትር ሀይላንድ ውሃ ተንጠልጥሎብናል። ሌሎችም ተዘርዝረው የማያልቁ ብዙ በደሎች ተፈፅመውብናል።

ይህ የደረሰብን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ታህሳስ 14/2009 ዓ•ም ለፍርድ ቤት በማሳየትና በማስረዳት ፎቶ መነሳት አለብን ብንልም ፍርድ ቤቱ ጥያቄያችን ሊቀበለን አልቻለም። ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ስንመለስ ደግሞ “ፍርድ ቤት ሄዳችሁ ብትለፈልፉ ምንም አታመጡም!” በማለት እስከ መጋቢት 12/2009 ዓ•ም ድረሰ ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ውስጥ ከተው የቤተሰብ ግንኙነት ከልክለውን በፀሀይ ብርሃን እጦት መልካችን ቢጫ እስኪሆንና አይናችን ብርሃን ማየት እስኪያቅተው ድረስ ተቆልፎብን ተሰቃይተናል።

እንደዚህ አይነት ግፍ የተፈፀመብን በወቅቱ የነበሩ በጣት የሚቆጠሩ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችን ከተጠያቂነት ለማዳን በጣም ደካማ አስተሳሰብ ያላቸው የመንግስት ኃላፊዎች እኛን የፖለቲካ መልስ ለማድረግ የወሰኑት ውሳኔ ነው። ህሊናቸውን ሸጠው በእኛ በንፁሃን ላይ እንዲህ አይነት ስቃይ የፈፀሙብን፣ ያስፈፀሙብን እንዲሁም ሀሳት የተቀነባበረ ክሰ የከሰሱን።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት የኮምሽኑ መርማሪዎች ከ10 ወራት ቆይታ በኋላም ቢሆን በአይናቸው ያዩትን እውነት በዝርዝር በሪፖርት ለፍርድ ቤት አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱም ሰብአዊ መብት ኮምሽን ሪፖርት ላይ ብይን ለመስጠት ለህዳር 29/ 2010 ዓ•ም ቀጠሮ ይዟል።

#የኢትዮጵያሰብአዊመብትኮምሽን ስላቀረበው ሪፖርት ያለን አስተያየት:_
1) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን (ኢሰመኮ) የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ሙሉ ለሙሉ አላካተተም።

2)የኢሰመኮ ኢ _ሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ በማለት ቁርጥ ያለ ሪፖርት ማቅረብ ሲገባው እና የኮምሽን መስርያ ቤቱ ጉዳዩን ተከታትሎ በዜጎች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት ያደረሱ አካላት በሕግ ማስቀጣት ሲገባው ምክረ ሀሳብ በማለት የተለሳለሰ የፍራቻ የሚመስል ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል። መስርያ ቤቱ እውነቱን እያወቀ እንዲህ ያለ ሪፖርት በማቅረቡ ምን ያህል የደህንነት ቢሮ ተፅዕኖ እንዳለበት እና በራስ መተማመን የጎደለው መስርያ ቤት መሆኑን የሚያሳይ ነው።

3) ኢሰመኮ በእኛ ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙ አካላትን እንዲመረምር ወይም እንዲያጣራ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽንና ለህክምና ቡድን አባላት በመፃፉ ቅር ተሰኝተናል። ምክንያቱም ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ነው። ውሻ ነከሰን ብለን ለጅብ እንድንናገር መደረግ የለበትም።

4) ኢሰመኮ በዚህ መልክም (በጥቂቱም) ቢሆን የተፈፀመብንን ግፍ በሪፖርት በማቅረቡ ምስጋና እናቀርባለን። ምክንያቱም ምን ያህል ተገደን ለፖሊስ ቃል እንደሰጠንና ለዶክመንተሪ ፊልማቸው በቪዲዮ እንደተቀረፅን የሚያሳይ ነው። በፍርድ ቤቱም በ27(2) ቃላችን ውድቅ እንዲደረግ የሚጠቅመን የሰነድ ማድረጃ በመሆኑ ነው።

#የህዝብተወካዮች ምክር ቤት እና የፌደራል ማረሚ ያ ቤቶች ላይ ያለን አስተያየት:-
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ነን፣ ለምርመራ ነው የመጣነው ብለው በግልና በጋራ አናግረው መርምረው ምንም አይነት መፍትሄ አልሰጡንም። ምንም አይነት ሪፖርትም አላቅረቡም። በዚህም በጣም ቅር ተሰኝተናል። እንዲህ ነው እንጅ የህዝብ ተወካይ መሆን፤
1) የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር እውነቱን እያወቀ፣ እኛ እንድንከሰስ በማቀነባበር፣ በህግ ጥላ ስር እያለን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን ያ ሁሉ ኢሰብአዊ ድርጊት እንዲፈፀምብን ማድረጉ፣
~ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ያሉ እስረኞችን በማስፈራራትና በማባበል ወደ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት በመውሰድ በእኛ ላይ እንዲመሰክሩብን በማድረጉ፣
~መርማሪዎች ነን ከሚሉ አካላት ጋር በመተባበር እኛን በመደብደብና በማስደብደብ ጨለማ ቤት አስገብቶ፣ ቤተሰብ ግንኙነት ከልክሎ በማሰቃየት በተፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት ቅር ተሰኝተናል።

2) በዚህ ኢትዮጵያዊነት በጎደለው በዘራችንና በሀይማኖታችን ተመርጠን፣ በሀሰት ተከሰን ለአመታት እንዲህ ያለ ስቃይ እንድንሰቃይ መደረጋችን ታሪክ የማይሽረው ጠባሳ በልባችን ላይ ጥላችሁብናል። የሞቱት ጓደኞቻችን! ገዳይ እናንተ! በሀሰት ተከሰን የምንሰቃየው እኛ! ፈጣሪን አትፈሩም? ግፍ አይደለም? ነገ በልጆቻችሁ አይደርስም? ከትግራይ ተወላጆች ውጭ ሌላው ዘር ጠላት ነው? ያሳዝናል!

3) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከትግሬ ውጭ ሌላ አመራር የለም። አንድም የተማረ ወይም የበሰለ አስተዳደር የለም። ተናዳጅ፣ ተቆጭ፣ መሃይሞች ብቻ ናቸው። አብዛኛዎቹ ታጋይ የነበሩና በዘረኝነት ያበዱ ከትግሬ ውጭ ሌላው ዘር ሰው የማይመስላቸው ያልሰለጡ ናቸው። ይህ ደግሞ ለጭካኔና አረሜኔያዊ ተግባር ለመፈፀም አግዟቸዋል። ለዚህ ነው ፍርድ ቤት ሄደን ስንናገር የምንደበደበው። ጨለማ ቤት የምንገባው ማገናዘብ በማይችሉ አመራሮች ስለምንመራ ነው።

ቂሊንጦ ማረፊያ የሆኑት ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አሰፋ ኪዳነ ቃጠሎው ሲደርስ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ነበርኩ ብለው ተጠርጣሪዎች በቆይታቸው ምንም ጉዳት አልደረሰባቸውም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። ሰብአዊ መብት ኮምሽን መርማሪዎች የደረሰብንን ጉዳት እያወቀ! በምን አይነት ሰዎች እጅ ተይዘን እንዳለን ማሳያ ነው።

#በ19ኛወንጀልችሎት ዳኞች ላይ ያለን ቅሬታ

ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ቀጠሮ የተያዘ ቢሆንም ሌሎች መዝገቦችን በተደራቢ በመስራት በጠዋቱ ፕሮግራም ላይ ዳኞች ከ4 ሰዓት በፊት ባለመግባት ጉዳያችን ተጓትቶብናል።

ይህ ሳያንስ ቀሪ የዐቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በሚል ነሃዴ 12/2009 ዓም፣ ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3 /2010 ዓም ድረስ የግማሽ አመት ቀጠሮ ተቀጥሮብናል። በዚህም ቅር ተሰኝተናል። “የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል” የሚለውን መርህ የጣሰ ተግባር ነው።

2) በፍርድ ቤቱ ውስጥ ለሟች ቤተሰቦች፣ ለእኛ ቤተሰቦችና የእኛን ጉዳይ መከታታል እና መታዘብ ለሚፈልጉ የትኛውም ወገኖች በችሎት ውስጥ በቂ የመቀመጫ ወንበር አለመኖር፣ የችሎት መጥበብ፣ በምስክር አሰጣጥ ወቅት ዳኞች ገለልተኛ አለመሆን ቅር አሰኝቶናል።

#ለኢትዮጵያሕዝብና #ለዓለምአቀፍ ማህበረሰብ የምናቀርበው የድረሱልን ጥሪ!
1) ይህ ክስ ባለቤት አለው። ክሱ ለባለቤቶቹ ይሰጥ! ክሱ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችና ፖሊሶች ነው።
2) ኢትዮጵያ ውስጥ እውነት መንግስትና ሕግ ካለ በእኛ ላይ የቀረበው ክስ ሊቋረጥ ይገባዋል። የምናውቀው ብዙ ሚስጥር አለን። ከፍተኛ የመንግስት አካላት መጥተው ሊነጋግሩን ይገባል።
3) የብሔራዊ ደህንነት ስብሰባ ላይ በቴሌቪዝን ያየነው ዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ ኃይሉ የተባለው የማዕከላዊ መርማሪ ፖሊስ የሚመራው ቡድን ለፈፀመብንና ላስፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት በህግ ይጠየቅልን።

4) ኢሰመኮ ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!

5) ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ የሚያሰማቸውን የሀሰት ምስክሮችና የሀሰት ሁኔታ እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።

6) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ቃጠሎ ምክንያት ከእኛ ከ38ቱ ተከሳሾች ውጭ 121 ተጠርጣሪዎች በዚሁ ወንጀል ከ20 እስከ 25 ተከፋፍለው በሌላ መዝገብ መከሰሳቸው ይተወቃል። ከእነሱ ውስጥ አርማዬ ዋቄ በማረሚያ ቤት ፖሊሶች ተደብድቦ የተገደለ በመሆኑ ጉዳዩ በሕግ ተይዞ እየተመረመረ ይገኛል። ሌሎቻችን ሰውነታችን በድብደባ በልዞ፣ ዝለን፣ ከነገ ዛሬ ገደሉን እያለን ስጋት ላይ ስለሆንን ይህ ግፍ እንዲቆም እንጠይቃለን።

#ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን
#ጀኔባ

እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተጠርጥረን በታሰርንበት ክስ የዋስትና መብታችን ተከልክለን ክሳችን በመከታተል ላይ እያለን ነሃሴ 28/2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በደረሰበት የእሳት ቃጠሎ ሊያመልጡ ሞክረዋል በሚል ምክንያት በእስር ቤት ውስጥ የመብት ጥያቄ ይጠይቁ የነበሩ በርካታ ወንድሞቻችን ተነጥለው በማረሚያ ቤተ ፖሊሶች በጥይት እኛ ፊት ተገድለውብናል። ይህ ሳያንሳቸው ራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን እኛ ለምርመራ በሚል ሰበብ ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን በዘራችን ብቻ ተመርጠን የአማራ፣ የኦሮሞና የጉራጌ ተወላጆች ብቻ ከፍተኛ የሆነ ኢሰብአዊ ድርጊት ተፈፅሞብናል።

ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የየሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።

አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። ይህን ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጥቅምት 20/2010 መርምሬ አረጋግጫለሁ ባለው ሪፖርት ላይ በመጠኑም ቢሆን ተፈፀመብንን ኢ ሰብአዊ ድርጊት አቅርቧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።

1)አሁንም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከፍተኛ የሆነ ድብደባ፣ ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰብን ስለሆነ፣ አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ ነው። በዚሁ በቃጠሎ ምክንያት በሌላ መዝገብ ከተከሰሱ ወንድሞቻችን ውስጥ አርማዬ ዋቄ የተባለ ተከሳሽ በማረሚያ ቤት ፖሊስ ተደብድቦ ተገድሎ ቤተሰቦቹ በክስ ላይ ይገኛሉ
2) ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ በሀሰት ያሰለጠናቸውን ምሰረክሮች ያሰማ ሲሆን ቀሪ ምስክሮችን ለማሰማት በሚል ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ተቀጥረናል። እስካሁንም ፍርድ ቤት ቀርበው የመሰከሩ ምስክሮች በተፅዕኖ ስር ሆነው ዐቃቤ ሕግ ባሰለጠናቸው መሰረት የመሰከሩ ናቸው። ቀሪ ምስክሮችም እንደ ቀድሞ ምስክሮች የታሰሩና በተፅዕኖ ስር ሆነው የሚመሰክሩ ናቸው። አንዳንድ በዋስት እና በነፃ የተፈቱ ምስክሮችን በዐቃቤ ሕግና ፖሊስ “እኛ በምንላችሁ መሰረት ነው የምትመሰክሩት” እየተባሉ ፣”ይህን ካደረጋችሁ ከቀድሞ ክሳችሁ ነፃ ትባላላችሁ” እያሉ በመደለል እንዲሁም፣ የተለያየ ማስፈራሪያና ዛቻ እየደረሰባቸው እንደሆነ አረጋግጠናል። ይህንን በተፅዕኖና ምስክሮችን በማስገደድ የሚደረግ አመሰካከር እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።

3) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ባቀረበው ሪፖርት መሰረት በእኛ በተከሳሾች ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ግፊት እንድታደርጉልን እንጠይቃለን። ነገር ግን ኢሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን በመሆኑ በሌላ ገለልተኛ ወገን ምርመራው እንዲካሄድ እንጠይቃለን።

4) ኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ ኤምባሲዎች ይህንን በሀገራችን እየተፈፀመብን ያለውን ኢሰብአዊ ድርጊት እንድትቃወሙልንና አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ በመሆኑ የድረሱልን ጥሪ እናቀርባለን።
5) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ምርመራ አረጋግጫለሁ ብሎ ባቀረበው ሪፖርት ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ማድረግ ሲገባው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን የወንጀል ምርመራ ክፍልና የህክምና ባለሙያዎች አስፈላጊ ምርመራ በማድረግ ውጤቱን ለሚመለከተው አካል አስተላልፈው የተደረሰበትን ድምዳሜ ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን እንዲያቀርቡ ምክረ ሀሰብ ቀርቧል በማለት ያቀረበው ሪፖርት ላይ በጣም ቅር ተሰኝተናል።

ምክንያቱም በሕግ ሊጠየቁ የሚገባቸው አካላት በሕግ ሊጠየቁ ይገበል ማለት ሲገባው፣ ጉዳዩን ተከታትሎ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ሲገባው በጣም ተለሳልሶ የፍራቻ የሚመስል መደምደሚያ ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል።

#ግልባጭ:_
#ለአፍሪካ ህብረት
#ለአሜሪካ፣ ለብሪታኒያ፣ ስውይድን፣ ካናዳ፣ ኖርዎይ ኤምባሲዎች
#ለማህበራዊ ሚዲያ፣ ለራዲዮ ጣቢያዎች፣ ኢቢሲና ሌሎች ሚዲያዎች ይድረስልን
#ወደእንግሊዝኛና አረብኝ ተተርጉሙ ለዓለም ህዝብ ይድረስልን

አነጋጋሪዉ የክልል ፍርድ ቤቶች ስልጣን በፌደራል ጉዳዮች ላይ!

በቃሉ ፈረደ

“የአማራ ክልል ዳኞች እና ዓቃቢያነ ህጎች ድምፅ” ገፅ ላይ የተወሰደ ጠቃሚ ትንታኔ

አሁን አሁን የክልል ፍርድ ቤቶች በፌደራል ጉዳይ ላይ ያላቸዉን የዉክልና ስልጣን አስመልከቶ አዲስ የክርክር ምዕራፍ እየተነሳ ይመስላል፡፡ እስካሁን ይህ ጉዳይ አነጋጋሪ ሳይሆን ቢቆይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትበሚታዩ ጉዳዮች በተለይም ከሽብረተኝነት ክስ ጋር በተገናኘ ጉዳዩ ተደገጋግሞ እየተነሳ ይገኛል፡፡ ከተነሱ ጉዳዮች ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ፤
ወንጀል ችሎት ከተወሰኑት ዉስጥ፡-
1ኛ. የወልቃይት ሕዝብ አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ አባላት ድርጊቱን ፈፀምን የተባለዉ በአማራ ክልል ዉስጥ ስለሆነ በክልሉ በሚገኙ ፍርድ ቤት ጉዳያችን ሊታይ ይገባል በማለት መቃወሚያ አቅርበዉ መቃወሚያቸዉ ዉድቅ
ተደርጓል፡፡
– –
2ኛ. የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ ጨምሮ 22 ተከሳሾች የተከሰስንበት ወንጀል ተፈፀመ የተባለዉ በኦሮሚያ ክልል በመሆኑ ጉዳያችን ሊታይ የሚገባዉ በኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ነዉ በማለት የፍርድ ቤቱ ስልጣን ላይ መቃወሚያ አንስተዉ ነበር፡፡ ችሎቱም ሃምሌ 19-2008 ዓ.ም በሰጠዉ ብይን የፀረ-ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 31 የሽብር ክሶችን የማየት ስልጣን የፌደራል ፍርድ ቤት መሆኑን በመጥቀስ መቃወሚያቸዉን ዉድቅ
አድርጎታል፡፡
– –
3ኛ. በተመሳሳይ በእነ ብርሃኑ ሙሉ እና ነጋ የኔዉ መዝገብ ክስ የቀረበባቸዉ ተከሳሾች ወንጀሉን ፈፀምን የተባለዉ በአማራ ክልል በመሆኑ በወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ 99 እና 100 መሰረት ክሱ ሊታይ የሚገባዉ ድርጊቱ ተፈጸመበት በተባለ ቦታ ሊሆን ይገባል የሚል መቃወሚያ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ፍርድ ቤቶች በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ-ሥርዓት ህጉ ስልጣን የተሰጣቸዉ አገሪቱ በአሃዳዊ ሥርዓት ሥር በነበረችበት ጊዜ ስለሆነ አሁን ላለዉ ፌደራላዊ ሥርዓት ተፈጻሚነት የለዉም፤ በሕገ መንግስቱ አንቀፅ 78 በፌደራል ጉዳይ ለክልል ፍርድ ቤቶች ተሰጥቶ የነበረዉ የዉክልና ስልጣን የሚቆየዉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፌደራል ፍርድ ቤቶችን በክልሎች እስኪያቋቁም በመሆኑና በአዋጅ ቁጥር 322/95 መሰረት በአፋር፣ደቡብ ሕዝቦች፣ ሶማሌ፣ ቤኒሻንጉልና ጋምቤላ ክልሎች ስለተቋቋሙ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤትም የዉክልና ስልጣኑን ስላጣ የተከሳሾች መቃወሚያ ተቀባይነት የለዉም በማለት ጥቅምት 23-2010 ዓ.ም በዋለዉ ችሎት በአብላጫ ወስኗል፡፡
– –
እነዚህ እና ሌሎች ተመሳሳይ ዉሳኔዎች በሕግ ባለሙያዎች መካከል አወያይ መሆን ጀምረዋል፡፡ ጉዳዩን ከቀረበበት አዉድ መመልከቱ አስፈላጊ ቢሆንም ሕጉና መርሁ ምን እንደሚል ከስሩ በመመልከት እኛም የድርሻችን እንበል፡፡

#የክልል ፍርድ ቤቶች በፌደራል ጉዳይ ያለቸዉ ስልጣን የሕግ ማዕቀፍ
– –
ፍርድ ቤቶች በሕግ ያላቸዉ የመዳኘት ስልጣን አንድም ከሕገ መንግስት ወይም ሕግ አዉጭዉ በሚያወጣቸዉ ሕጎች ሊወሰን ይችላል፡፡ በአገራችን የፌደራሉ ሆነ የክልሉ ፍርድ ቤቶች በኢፌዲሪ ሕገ መንግስት አንቀፅ 78(2) እዉቅና ተሰጥቷቸዉ የተቋቋሙ ናቸዉ፡፡ የክልል ፍርድ ቤቶችም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እስካልተቋቋመ ድረስ የፌደራል ጉዳዮች ስልጣን በግልፅ እንደተሰጣቸዉ በግልፅ ተቀምጧል፡፡
– – –
#የፌደራል ፍርድ ቤቶች በክልሎች ለምን ይቋቋማሉ?
– –
የፌደራል ሥርዓት የሚከተሉ አብዛኞቹ አገሮች የፌደራልና የክልል ፍርድ ቤቶችን በማቋቋም የሁለትዮሽ የፍርድ ቤት አወቃቀር ስርዓት ይከተላሉ፡፡ በክልሎችም የፌደራልን ጉዳይ የሚመለከቱ ፍርድ ቤቶች የሚሰረቱበትን ስርዓት አብረዉ ይዘረጋሉ፡፡ ጥያቄዉ የሚሆነዉ በክልሎች ለምን የፌደራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋም አስፈለገ የሚለዉ ነዉ፡፡
በመስኩ ያጠኑ ልሒቃኖች የፌደራሉን ፍርድ ቤት በክልል እንዲያቋቋም የሚያደርገዉ ትልቁ ገፊ ምክንያት ስጋት ነዉ ይላሉ፡፡ ትልቁ ስጋትም ክልሎች የፌደራሉን ጉዳይ ወይም ፖሊሲ እንደራሳቸዉ አድርገዉ ላያስፈጽሙት ይችላሉ የሚለዉ እንደሆነ ይገልጹና፤ ይሄ ጥርጣሬ ደግሞ የክልል ፍርድ ቤቶች አቅም ላይ ሙሉ እምነት ካለመኖርም ይመነጫል ይላሉ፡፡ በተጨማሪም የፌደራሉን ህግ ከክልል ክልል በተለያዬ ሁኔታ ሊተረጎም ስለሚችል ወጥነት ያለዉ የሕግ አተረጓጎም እንዳይኖር ሊያደርግ ስለሚችል የፌደራል ፍርድ ቤቶች በክልል መቋቋማቸዉ አጠያያቂ እንዳልሆነ ይገልፃሉ፡፡
– –
የፌደራል ፍርድ ቤቱን ከማደረጃት ዉክልና መስጠት ተመራጭ የሆነዉም በክልሎች የፌደራል ፍርድ ቤት ለማቋቋም ከወጪ እና ከሰዉ ሃይል አንጻርም አስቸጋሪ ስለሚያደርገዉ እንደሆነ በጉዳዩ ላይ ጥናት ደረጉ አካሎች ይገልፃሉ፡፡ለሁሉም ክልሎች የፌደራል መጀመሪያ ደረጃ እና ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይቋቋም ቢባል ተቋሙ ከሚፈልገዉ የሰዉ ሃይል ጀምሮ ሰፊ እና የረጅም ጊዜ ስራ የሚጠይቅ በመሆኑ በዉክልና እያሰሩ ስርዓቱን በሂደት መገንባት የሕግ አዉጭዉ
ገፊ ምክንያት እንደሚሆን መገንዘብ ይቻላል፡፡
– –
#የክልል ፍርድ ቤቶች ያላቸዉ የዉክልና ስልጣን አይነኬነት!
– –
የሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 78(2) አማርኛዉ ድንጋጌ በግልፅ እንዳስቀመጠዉ የፌደራል ፍርድ ቤቶች በክልል እስካልተቋቋሙ ድረስ በፌደራል ጉዳይ የክልል ፍርድ ቤቶች ስልጣን እንዳላቸዉ ነዉ፡፡ የክልል ፍርድ ቤቶች በፌደራል ጉዳይ ያላቸዉን ስልጣን የሚያጡት በክልሉ ፌደራል ፍርድ ቤት ሲቋቋም ብቻ ነዉ፡፡ በዚህ ድንጋጌ መርሁ የፌደራል ጉዳይ በክልል ፍርድ ቤቶች በዉክልና እንደሚታይ ሲሆን በልዩ ሁኔታ አስፈላጊ ሆኖ እስካልተገኘ ድረስ የክልል ፍርድ ቤቶች የፀና ስልጣን የሚኖራቸዉ ይሆናል፡፡ አሁን በቅርብ እየታዬ ባለዉ ሁኔታ የፌደራል ፍርድ ቤቶች የክልል ፍርድ ቤቶች በፌደራል ጉዳይ በሕገ መንግስቱ የተሰጣቸዉን የመዳኘት ስልጣን እየተቀበሉት አይመስልም፡፡
– –
ለክልል ፍርድ ቤቶች ዉክልናዉን የሰጠዉ ሕገ መንግስት እንጅ የፌደራሉ ፍርድ ቤት አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት የፌደራሉ ፍርድ ቤት የእኔን ጉዳይ ለማየት የተወከልክና በፈለግሁት ጊዜ ጉዳዬን ማየት እችላለሁ ለማለት የሕግ መሰረት የለዉም፡፡ ምክንያቱም ይህ ዉክልና ተራ ከዉል የሚመጣ ዉክልና ሳይሆን ከሕግ የሚመነጭ ዉክልና ነዉ፡፡ በሕግ የተሰጠ ዉክልና ደግሞ ሊነሳ የሚገባዉ አንድም ሕጉን በማሻሻል አልያም በሕጉ የተቀመጠዉ ሁኔታ ሲሟላ ነዉ፡፡ ክልሎች በፌደራል ጉዳይ ያላቸዉን ስልጣንም በፌደራል ፍርድ ቤቶች ስልጣን ሊነጠቁ አይችሉም፡፡ ስልጣናቸዉ ሊወሰድባቸዉ የሚችለዉ ወይ የዉክልና ስልጣን የሰጣቸዉን የሕገ መንግስት ድንጋጌ በማሻሻል ወይም በሕገ መንግስት የተቀመጠዉን ሁኔታ የፌደራል ፍርድ ቤቶች በክልሎች ሲቋቋሙ ብቻ ነዉ፡፡

እስካሁን ባለዉ ሁኔታም በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ማደረጃ አዋጅ ቁጥር 322/1995 መሰረት ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተቋቋመላቸዉ አፋር፣ ቤንሻንጉል፣ጋምቤላ፣ሶማሌ እና ደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ብቻ ናቸዉ፡፡ በሌሎቹ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ባልተቋቋመባቸዉ የአማራ፣ ኦሮሚያ፣ሐረሪና ትግራይ ክልል የፌደራል ጉዳዮች የክልል የፍርድ ቤቶች እስካሁን የፀና ስልጣን እንዳላቸዉ ነዉ፡፡ በአምስቱ ክልሎች የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት መቋቋምም ከሕግ መርህ ሆነ ከምክንያታዊ መመዘኛ አንጻር ሌሎች ክልሎች ያላቸዉን ስልጣን ሊያሳጣ የሚችል አይደለም፡፡
– –
#የወንጀለኛ መቅጫ ስነ-ስርኣት ህጉ ተፈጻሚነት ወሰን፡-
– –
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በሕገ መንግስቱ የተሰጠዉን የዉክልና ስልጣኑ ተነስቷል በማለት ሲወስን የወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ 99 እና 100 አሁን ባለዉ የፌደራል ስርዓት የፍርድ ቤቶችን ስልጣን ለመወሰን ስልጣን እንደሌለዉ ጠቅሷል፡፡ ይህ የወንጀለኛ መቅጫ ስነ-ስርዓትህ ሕግ አገሪቱ አሃዳዊ የመንግስት ሥርዓት ስርትዳደር በነበረበት ወቅት የወጣ ሕግ ቢሆንም አሁንም ሁሉም የወንጀል ክርክሮች የሚመሩበት ስነ-ስርዓት ሕግ ሆኖ ቀጥሏል፡፡የወንጀል ክስ የሚታይበትን ፍርድ ቤት የሚወስነዉ የሕግ ክፍልም አሁን ባለዉ ሁኔታ እየተሰራበት ያለ ሲሆን ካለዉ የፌደራል ሥርዓት ጋርም የሚጋጭ ነገር የለዉም፡፡
ወንጀል በተፈፀመበት ቦታ ክስ መታየቱም ከየትኛዉም ሕግ ጋር የሚጋጭ አይደለም፡፡ ክልሎች የፌደራልን ጉዳይ እየተመለከቱ የሚገኙት በሕገ-መንግስት ድንጋጌ ተሰጣቸዉ ስልጣን እንጅ በዚህ የስነ-ስርዓት ሕግ አይደለም፡፡ ክልሎች በፌደራል ጉዳዮች ላይ ያልተሻረ እስካሁን የፀና የማየት መብት እስካላቸዉ ድረስ የስነ-ስርዓት ሕጉ ስጋት አይሆንም፡፡
– – –
በአንድ ጉዳይ በስረ-ነገር ደረጃ እኩል ስልጣን ያለቸዉ የፌደራልና የክልል ፍርድ ቤቶች ከየትኛዉ ፍርድ ቤት ክርክሩ ይቅረብ የሚለዉን የሚመልሰዉ ስለ ግዛት ክልል የተቀመጠዉ የስነ-ስርዓት ሕጉ በመሆኑ ካልተሻረ በስተቀር ተፈፃሚ ከመሆን የሚገድበዉ ነገር አይኖርም፡፡ በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጎንደር ክላስተር ምድብ ችሎት እየታዬ የሚገኘዉ የኮሎኔል ደመቀ ጉዳይ ለዚህ ማሳያ ነዉ፡፡ ኮሎኔል ደመቀ በግልጽ ክስ የቀረበበት የፀረ-ሽብርተኛ አዋጅ ቁጥር 652/2001 ተላልፏል በሚል ሲሆን የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክሱን እየተመለከተ ያለዉ የወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ 99 እና 100 መሰረት በማድረግ ነዉ፡፡ ይህ የስነ-ስርዓት ሕግ ድንጋጌም ለኮሎኔል ደመቀ ጉዳይ ሲሆን ተፈፃሚ የሚሆን ለሌሎች ተከሳሾች ሲሆን ደግሞ የሚታለፍ አይደለም፡፡
– – –
#የፀረ -ሽብርተኛ አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀፅ 31 እና ሕገ- መንግስቱ
አንቀጽ 78(2)
– – –
የፌደራል ፍርድ ቤቶች የግዛት ክልል ስልጣን ተቃዉሞ ሲቀርብላቸዉ አብዛኛዉን ጊዜ መቃወሚያዉን ዉድቅ የሚያደርጉት የፀረ-ሽብርተኛ አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 31 በመጥቀስ ነዉ፡፡ በዚህ ድንጋጌ የሽብርተኝነት ወንጀል የፌደራል ከፍተኛ እና ጠቅላይ ፍርድ ቤት ስልጣን እንደሆነ ይናገራል፡፡ በአዋጁ የሽብርተኛነት ጉዳይ የፌደራል ከፍተኛ እና ጠቅላይ ፍርድ ቤት ስልጣን ስለመሆኑ ቢገልፅም በግልፅ የሽብርተኝነት ጉዳይ በክልሉ ባሉ አቻ ፍርድ ቤቶች በዉክልና ሊታይ እንደማይችል ያስቀመጠዉ ገድብ የለም፡፡ ይህ የፀረ-ሽብር አዋጅ ሲተረጎም ሆነ ስለፍርድ ቤት ስልጣን የሚገልጸዉ ድንጋጌ ሊተረጎም እና ሊፈፀምም የሚገባዉ ከሕገ መንግስቱ አንቀፅ 78(2) ጋር በማጣመር ነዉ፡፡ በዚሕ የሕገ መንግስት ድንጋጌም የክልል ፍርድ ቤቶች የፌደራል ፍርድ ቤት ባለ,ልተቋቋመበት ሁኔታ ስልጣን ያላቸዉ ስለመሆኑ ስለሚገልጽ በተመሳሳይ የሽብርተኝነት ወንጀሎችንም ለማየት ስልጣን አላቸዉ፡፡ ፀረ-ሽብርተኛ አዋጁንም በመጥቀስ የሽብረተኝነት ወንጀሎች የሚታዩት በፌደራል ፍርድ ቤቶች ብቻ ነዉ ለማለት አይቻልም፡፡
– –
#በፌደራል ጉዳይ በክልልና ፌደራል ፍርድ ቤቶች መካከል የሚፈጠር የስልጣን ግጭት!
– –
የፌደራል ጉዳዮች ሕግን፣ተከራካሪ ወገንን እና ቦታን መሰረት አድርገዉ ሊመሰረቱ እንደሚችል በፌደራል ፍርድ ቤት ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀፅ 3 ተገልፀዋል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች አንድም ፌደራል ክፍተኛ ፍርድ ቤቱ በተደራጄበት ቦታ (አዲስ አበባ፣ድሬደዋ እንዲሁም የፈደራል ፍርድ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በተደራጄባቸዉ አምስት ክልልሎች) እንዲሁም በሌላ ሁኔታ የፌደራል ፍርድ ቤት ባልተደራጀባቸዉ ግን በዉክልና ጉዳዩን መመልከት በሚችሉ ክልል ፍርድ ቤቶች ሊቀርቡ ይችላሉ፡፡ በጉዳዩ ላይ የፌደራል ፍርድ ቤቶች ጉዳዩ የፌደራል ጉዳይ በመሆኑ ስልጣን ሲኖራቸዉ የዉክልና ስልጣን ያላቸዉ የክልል ፍርድ ቤቶችም ደግሞ ከሕገ-መንግስት የመነጨ ጉዳዩን የመዳኘት ሰልጣን አላቸዉ፡፡ ሁለቱም ፍርድ ቤቶች እኩል በጉዳዩ ላይ ከሕግ የመነጨ ስልጣን ያለቸዉ ከሆነ በስረ-ነገር ስልጣን (material jurisdiction) ደረጃ ተመሳሳይ ወይም እኩል
ስልጣን አላቸዉ ማለት ነዉ፡፡
– –
በአንድ ጉዳይ ላይ በስረ-ነገር ስልጣን ደረጃ እኩል ወይም ተመሳሳይ ስልጣን ያላቸዉ ፍርድ ቤቶች ካሉ ደግሞ ጉዳዩ ሊፈታ የሚችለዉ ወይም ክርክሩ ሊታይ የሚገባዉ የግዛት ክልል ስልጣን (Local jurisdiction) መሰረት ባደረገ መልኩ ነዉ፡፡ የግዛት ክልል ስልጣን የሚባለዉ በወንጀል ጉዳይ ወንጀሉ በተፈፀመበት ወይም የወንጀሉ ዉጤት በተገለጸበት ስፍራ ለመሆኑ እና ጉዳዩ ሊታይ የሚገባዉም በዚህ ስፍራ በሚገኝ ፍርድ ቤት ለመሆኑ ከወ/መ/ስ/ስ/ህ/ ቁጥር 99 እና ከታዮቹ ድንጋጌ መረዳት የሚቻል ነዉ፡፡ በዚሁ በስነ-ሥርዓት ሕግ ቁጥር 107 መሰረት ክሱን የሚያቀርበዉ ዓቃቤ ሕግ ነገሩ የሚታይበትን ፍርድ ቤት ሊመራ እንደሚችል ቢያስቀምጥም የከሳሹ ምርጫ ተቃወሞ ሊቀርብለት አይገባም ማለት አይቻልም፡፡ ተከሳሹ ክስ የቀረበበት ሁኔታ መብቴን ይጎዳል ካለ መቃወሚያ ከማቅረብ የሚያግደዉ ነገር አይኖርም፡፡
– –
#የግዛት ክልል ስልጣን አለመከበር የሚያስከትለዉ ስጋት!
– –
የግዛት ክልል ስልጣን ተቃዉሞ የሚቀርበዉ ጉዳዩ የቀረበለት ፍርድ ቤት በስረ- ነገር ደረጃ ስልጣን ኖሮት በግዛት ክልል ስልጣን ደረጃ ግን ድርጊቱ ከተፈፀመበት ወይም ዉጤቱ ከታወቀበት ቦታ ዉጪ ከሚገኝ ፍርድ ቤት መታየት ሲጀምር ነዉ፡፡ ሕጉ ድርጊቱ ተፈፀመ ወይም ዉጤቱ ታወቀ በተባለበት ቦታ ክስ እንዲቀርብ ሲያስቀምጥ በዋናነት መሰረት ያደረገዉ በጉዳዩ ላይ አፋጣኝ እና ፍትሐዊ ዉሳኔ ከመስጠት አንፃር ነዉ፡፡ የአንድ ክርክር አፋጣኝነት የሚገለፀዉም ክርክሩን በአጭር ጊዜ ከማጠናቀቅ አንፃር ሲሆን ፍትሐዊነቱ የሚገለጸዉ ደግሞ ሁለቱም ወገኖች የመደመጥ፣ማስረጃ የማቅረብ መብታቸዉ በእኩልነት
በመጠበቅ እና የተከሳሾችን ሰብዓዊ መብቶች በማስከበር ነዉ፡፡
– –
#ከተከሳሽ መብት አንፃር፡-
– –
የፍርድ ቤቶች የግዛት ስልጣን ካልተከበረ የተከሳሾች መብት ስጋት ዉስጥ ይወድቃል፡፡በወንጀል ክርክር ሂደት አንድ ክርክር ፍትሐዊ የሚባለዉ ከዉጤቱ ሳይሆን ገና ከሂደቱ ጀምሮ በመሆኑ ተከሳሹ በክርክር ሂደት ከአቆያየቱ ጀምሮ የመደመጥ መብቱን ባስከበረ መልኩ ጠብቆ ከተጓዘ ነዉ፡፡ ፍርድ ቤቶችም በግዛት ስልጣን ላይ ተቃዉሞ ሲነሳ ከተከሳሽ መብት አንፃርም ጉዳዩን ሊያዩት ይገባል፡፡ የወንጀል ክስ የቀረበበት አንድ ተከሳሽ ድርጊቱ ተፈፀመ በተባለበት አካባቢ ነዋሪ ከሆነ እና ክርክሩን በማረፊያ ቤት ሆኖ የሚከታተል ከሆነ በዚያዉ አካባቢ መሆኑ በቅርብ በቤተሰብና በወዳጅ የመጎብኘት ሕገ መንግስታዊ መብቱ ይጠብቅለታል፡፡ በተጨማሪም መከላከያ ማስረጃዉን ለማቅረብ እና እዉነቱን ለማስረዳት ምቹ እና ቀላል ሁኔታም ይፈጠርለታል፡፡

አንድ ሰዉ ከቀዬዉ በራቀ ቁጥር ከቦታዉ ርቀት አንፃር የመረጃ ልዉዉጡ ቀልጣፋና ቀላል ስለማይሆን በተከሰሰበት ጉዳይ ማስረጃ ከማሰባሰብ ጀምሮ የሚኖረዉ ሚና ዝቅተኛ ስለሚሆን ተጎጅ ይሆናል፡፡ አንድ ሰዉ ፍትሕ የማግኘት ሕገ መንግስታዊ መብቱን ሊጠቀምበት የሚችለዉ ምቹ ሁኔታ ሲፈጥረለት ነዉ፡፡ ምቹ ሁኔታ በሌለበት ሁኔታ ከቦታዉ ርቆ ታስሮ እንዲሁም ከሳሹ አካል ካለዉ የመደራረደር አቅም ግዝፈት አንፃርም ግምት ዉስጥ ሳይገባ የግዛት ክልል ስልጣንን መወሰን ፍትሐዊ አይሆንም፡፡

በተደጋጋሚ እንደታዬዉ በተለይም ከሽብር ጉዳይ ጋር በተገናኘ ከአማራ ክልል የሚመጡ ተከሳሾች ድርጊቱ ተፈፀመ ከተባለበት ቦታ እና ከሚኖሩበት አካባቢ ርቀዉ ጉዳያቸዉ ስለሚታይ መከላከያ ማስረጃ ማቅረብ ሳይችሉ በመቅረታቸዉ ጥፋተኛ የተባሉበት ሁኔታ አለ፡፡ ከሚኖሩበት አካባቢም በመራቃቸዉ ለቅጣት ማቅለያ ማስረጃ ሊሆን የሚችላቸዉን ማስረጃ ባለማቅረባቸዉ ፍትሐዊነት እንዲጓደል ሆኗል፡፡
– –
#የፌደራል ስርዓቱን እና የክልሎች ሕልዉና ፡-
– –
የግዛት ክልል ስልጣን መቃወሚያ ሲወሰን የተከሳሾችን መብትና ፍላጎት ብቻ ሳይሆን አገሪቱ የቆመችበትን የፌደራል ስርዓት በጠበቀ መልኩ ሊሆን ይገባዋል፡፡ በሕገ መንግስቱ እያንዳንዱ ክልል በህግ የተሰጠዉን ስልጣን ከሕግ ዉጪ ማንኛዉም የፌደራል መንግስት ሆነ የመንግስት አካል ሊጥስበት እንደማይገባ የሕግ ድጋፍ አለዉ፡፡ የክልል ፍርድ ቤቶችም በግልፅ በሕግ የተሰጣቸዉን ስልጣን ሊነጠቁ የሚገባ አይደለም፡፡ የግዛት ክልል ስልጣን እያለዉ ስልጣኑን ተጠቅሞ እንዳያይ የሚያደርግ አሰራር ካለ በተዘዋዋሪ የክልሎችን ራስ ገዝነት እና ስልጣን መንጠቅ ወይም ስልጣናቸዉን ማምከን ይሆናል፡፡ የፌደራል ፍርድ ቤቶች የግዛት ክልል ስልጣን ተቃዉሞ ሲነሳባቸዉ ክልሎች ያላቸዉን ስልጣን ስራ ላይ እንዲያዉሉ ጉዳዩ ድርጊቱ ተፈፀመ በተባለበት አቻ ፍርድ ቤት እንዲቀርብ መደረግ ይኖርበቸዋል እንጅ ከሕገ-መንግስት ለክልል ፍርድ ቤቶች የተሰጠዉን መብት በአንድ ብይን ሊነጥቁ አይገባም፡፡ የክልል ፍርድ ቤቶች በሕገ መንግስቱ የተሰጣቸዉን የዳኝነት ስልጣን እንዳይጠቀሙ የሚደረግ ከሆነም የፌደራል ሥርዓቱ በራሱ አደጋ ዉስጥ ይወድቃል፡፡
– –
#ከገለልተኛነት እና ያለተፅዕኖ ከመዳኘት መርህ አንፃር፡-
– –
ፍርድ ቤቶች በቅድሚያ ሊያተርፉት የሚገባ የሕዝብ አመኔታ ሊሆን ይገባል። እንደዜጋ በፍርድ ቤቶች ተዳኝቼ ፍትሕ አገኛለሁ የሚል የሕበረተሰብ ክፍል መፍጠር ካልተቻለ የፍትሕ ስርዓቱ በራሱ ለዜጎች ስጋት ይሆናል፡፡ ፍርድ ቤቶችም ከፍትሕ ተቋምነት የአንድ ቡድን ፍላጎት ማስፈፀሚያ መሳሪያ ይሆናሉ፡፡ ለዚህም ነዉ ፍርድ ቤቶች የሚሰጧቸዉ ዉሳኔዎች ገለልተኝነታቸዉን ባስጠበቀ ሊሆን የሚገባዉ፡፡
– –
ክልሎች የፌደራል ጉዳይን እንደራሳቸዉ አድርገዉ ላያስፈጽሙ ይችላሉ የሚለዉ ስጋት የፌደራልን ጉዳይ በክልል የሚመለከት የፌደራል ፍርድ ቤት ለማቋቋም ገፊ ምክንያት እንደሆነ አይተናል፡፡ የፌደራል መንግስቱም ከፖለቲካ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችም በክልሎች እንዲታዩበት የማይፈልገዉም ለዚህ ይመስላል፡፡ በተደጋጋሚ እንደታዘብነዉ ከፖለቲካ ጉዳዮች ጋር በተየያዙ የሚታዩ ጉዳዮች ክልሎች የዉክልና ስልጣናቸዉን ተጠቅመዉ እንዲመለከቱ ከማድረግ ይልቅ ጉዳዮችን ከክልል ፍርድ ቤቶች ስር የማራቅ ስራ ተለምዷል፡፡ ይህ የተለምዶ አሰራር የተከሳሹን መብት በፅኑ የሚጎዳ እና የክልሎችን ሕጋዊ ስልጣን የሚወስድ ከመሆኑ በተጨማሪ የገለልተኛነት ጥያቄ እንዲነሳ የሚያደርግ ነዉ፤እያስነሳም ነዉ፡፡ የፌደራል ፍርድ ቤቶችም ከጉዳዩ የተለዬ ጥቅም እንዳላቸዉ በሚያስመስል መልኩ በግልጽ የተሰጠዉን የክልሎች የግዛት ስልጣን አለማክበር ደረጃም ደርሰዋል፡፡ ይህ ደግሞ ተከሳሾች በፌደራል ፍርድ ቤቱ ላይ ያላቸዉን እምነት እንዲሸረሽረዉም አድርጓል፡፡
– –
በተለዬ መልኩ የሽብርተኛ ወንጀል ተከሳሾች የፌደራሉ ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ እየደረሰባቸዉ ስላለዉ የመብት ጥሰት፣ቶርቸር እና ያለመደመጥ መብታቸዉን እያስከበረዉ እንዳልሆነ ከመግለጽ እና በችሎትም ዳኞችንም ሃይለ ቃል እስከ መናገር ፍትሕ እናገኛለንም ብለዉ ከማያምኑበት ደረጃ ደርሰዋል፡፡ በተደጋጋሚም እነዚህ ተከሳሾች ከምንንኖርበት እና ድርጊቱ ተፈጸመ ከተባለበት ክልል በሚገኝ ፍርድ ቤት ጉዳያችን ሊታይ ይገባል በማለት የፍርድ ቤት የግዛት ስልጣን ጥያቄ ሲያነሱ የነበሩ ናቸዉ፡፡ አሁን ግን የፍርድ ቤቶችን የግዛት ክልል ስልጣን ጉዳይ ወደ ገለልተኛ እና ያለተፅዕኖ ከመዳኘት መብት ጋር ተገናኝቶ ከፍ ብሎ እተነሳ ነዉ፡፡ ጉዳዩም የግዛት ስልጣን ብቻ ሳይሆን ክሱን ወደ ሌላ ፍርድ ቤት የማዛወር (change of venue) መልክ እንዲይዝም እያደረገዉ ይመስላል፡፡ የዚህም መነሻ የክልል ፍርድ ቤቶች ስልጣን በፌደራል ፍርድ ቤቶች መነጠቅ ያመጠዉ መዘዝ ነዉ፡፡
– –
#እንደመዉጫ!

የፌደራል ፍርድ ቤቶች በአዋጅ ያልተቋቋመባቸዉ ክልሎች በግልጽ ከሕግ የመነጨ የፌደራል ጉዳይን የማየት ስልጣን አላቸዉ፡፡ ስልጣናቸዉንም የሚያጡት በክልሉ የፌደራል ፍርድ ቤት በአዋጅ ከተቋቋመ ወይም ስልጣን የሰጣቸዉ የሕገ መንግስት ድንጋጌ ከተሻሻለ ብቻ ነዉ፡፡ የፍርድ ቤቶች የግዛት
ስልጣን ጥያቄ ዉጤቱ ትክክለኛ ፍትሕ እንዳይሰጥ ከማድረግ አልፎ የክልሎችን ስልጣን በመጋፋት ለፌደራል ስርዓቱ አደጋ የሚሆን እና ገለልተኛ ያልሆነ የፍትሕ ስርዓት እንዳይኖር የሚያደረግ ነዉ፡፡ ለዚህም የፌደራል ፍርድ ቤቶች የክልል ፍርድ ቤቶች እኩል የስረ-ነገር ስልጣን ያላቸዉንና በግዛት ክልል ደረጃ ክልሎች ቀዳሚ ስልጣን ያላቸዉን ጉዳይ ሊመለከቱ አይገባም፡፡ ክልሎች በሕግ የተሰጣቸዉ ስልጣን ፀንቶ ባለበት ሁኔታ ከስልጣናቸዉ ማግለል አንድምታዉ ለአንድ ወገን መሳሪያ ከመሆን ያለፈ ዓላማ አለዉ ለማለት የሚቻል ስላልሆነ እና ተከሳሾችም በቅርብ ማስረጃ አቅርበዉ የተፋጠነ እና ፍትሐዊ የሆነ ዉሳኔ እንዳያገኙ ምክንያት ስለሚሆን ጉዳዩ መፍትሔ የሚያሻዉ ነዉ፡፡ ፍርድ ቤቶች ሕግና መርህን ካለማክበር ተመልሰዉ ቀልብ ካልገዙ የቁልቁለቱን መንገድ ፈጣን ያደረግዋል ፤ ከዛሬ ነገ ይሻል ይሆናል የምንለዉ የፍትሕ ሥርዓትም አይኖርም፡፡

የፍርድ ቤት ችሎት ትዝብት

ጌታቸው ሺፈራው

“በዚህ ፍትህ በሌለበት ሀገር እንደኛ መሆን መታደል ነው። ዳኛ መሆን ከባድ ነው።……ቢገባችሁ የምንታገለው ለእናንተም ነው!” ቴዎድሮስ አስፋው

“መሳርያ ይዛችሁ የመጣችሁት ስርዓት ለማስከበር ነው። ” መሃል ዳኛው ለማረሚያ ቤቱ ፖሊስ አዛዥ

“የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል ያላችሁን ራሳችሁ ናችሁ” ፍሬው ተክሌ

Tewodros, et la.
ፎቶው (ከግራ ወደ ቀኝ) የኤርሚያስ ፀጋዬ፣ የፍሬው ተክሌ፣ የዳንኤል ተስፋዬ እና የቴዎድሮስ አስፋው ነው።)

ህዳር 8 ቀን 2010 ዓ.ም. በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ትንሳኤ በሪሶ የክስ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው 9 ተከሳሾች ይከላከሉ አይከላከሉ የሚል ብይን ለመስማት ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር። ተከሳሾቹ በተደጋጋሚ ለብይን የተቀጠሩ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ዳኛ ባለመሟላቱ ብይኑ እንዳልተሰራ በመግለፅ ለታህሳስ 6/2010 ዓም የአንድ ወር ቀጠሮ ሰጥቷል።

ከተከሳሾቹ መካከል ያለ ጠበቃ የሚከራከሩት ዳንኤል ተስፋዬ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ፍሬው ተክሌና ቴዎድሮስ አስፋው ፍርድ ቤቱ ስለሰጠው ቀጠሮ እና በማረሚያ ቤቱ ስለሚፈፀም የሕግ ጥሰት አስተያየት ለመስጠት እጃቸውን ቢያወጡም ፍርድ ቤቱ አልተቀበላቸውም።

ፍርድ ቤቱ ” ከአቅማችን በላይ ነው” ብሎ እንዳይናገሩ ሲከለክል ቴዎድሮስ አስፋው ” የታሰርነው የመናገር መብታችን ለማስከበር ስንታገል ነው። አሁንም ፍርድ ቤቱ የመናገር መብታችን ሲከለክል ዝም አንልም” ብሏል። ቴዎድሮስ ይህን ሲናገር መሃል ዳኛው “ምን ልታመጣ?” ብለዋል።

ቴዎድሮስ አስፋው ” በዚህ ፍትህ በሌለበት ሀገር እንደኛ (ተከሳሽ) መሆን መታደል ነው። ዳኛ መሆን ከባድ ነው። የታሰርነው የመናገር መብታችን ለማስከበር ነው። ወደፊትም እንታገላለን። ቢገባችሁ የምንታገለው ለእናንተም ነው!” ብሏል።

ከቴዎድሮስ አስፋው በተጨማሪ ፍሬው ተክሌም ቂሊንጦ እስር ቤት ለፍርድ ቤት ለማቅረብ በፅሁፍ ያቀረበውን አቤቱታ ይዞ እንዳይመጣ እንደከለከለው ገልፆ በቀጠሮውና እስር ቤት በሚፈፅመው በደል ላይ አስተያየት መከልከላቸው አግባብ እንዳልሆነ ገልፆአል። ፍሬው ተክሌ አክሎም “የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል ያላችሁን ራሳችሁ ናችሁ” ብሏል።

ቴዎድሮስ አስፋው፣ ፍሬው ተክሌ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬና ዳንኤል ተስፋዬ በችሎት ቅሬታቸውን ባቀረቡበት ወቅት ፍርድ ቤቱ ፖሊስ ከችሎት እንዲያስወጣቸው ትዕዛዝ ሰጥቶ፣ በፖሊስ ከችሎት እንዲወጡ ተደርገዋል። አራቱ ወጣቶች በፖሊስ ከችሎት እንዲወጡ ሲደረጉም ቅሬታቸውን ሲናገሩ ተደምጠዋል። መሃል ዳኛው የማረሚያ ቤት ፖሊስ አዛዡን አስጠርተው ” እኛ አልተመቸንም ስንል እንደፈለጉ መጮህ የለባቸውም። መሳርያ ይዛችሁ የመጣችሁት ስርዓት ለማስከበር ነው። ” ብለዋል።

ችሎት እየተከታተሉ የነበሩት የተከሳሽ ቤተሰቦችም ቅሬታቸውን የገለፁ ሲሆን የፍሬው ተክሌ እናት “እግዚያብሄር ይፍረድ!” ብለው ከችሎት ሲወጡ በችሎት ተጠርተው ማስጠንቀቆያ ተሰጥቷቸዋል።
በእነ ትንሳኤ በሪሶ የክስ መዝገብ ስር የተከሰሱት
1. ትንሳኤ በሪሶ
2. ዳንኤል ተስፋዬ
3. ግሩም አስቀናው
4. ቴዎድሮስ አስፋው
5. ፍሬው ተክሌ
6. ኤርሚያስ ፀጋዬ
7. አሰጋ አሰፋ
8. ጌታቸው ይርጋ
9. ሽቴ ሙሉ እና ክሳቸው የተቋረጠላቸው ሀይሌ ማሞ ናቸው፡፡

ወይዘሪት ንግስት ይርጋ በክሷ ምክንያት በደል እየደረሰባት እንደሆነ ተገለፀ

ጌታቸው ሺፈራው

የ”ሽብር” ክስ የተመሰረተባት ንግስት ይርጋ በክሷ ምክንያት ማረሚያ ቤት ውስጥ በደል እየደረሰባት መሆኑን ጠበቃዋ ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል። ንግስት ይርጋ በቤተሰብ ጥየቃ ገደብ እየተደረገባት መሆኑን ለፍርድ ቤት አቤቱታ ባቀረበችው መሰረት ፍርድ ቤቱ ምንም ገደብ ሳይደረግባት እንድትጠየቅ ቢወስንም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ሳያከብር ቀርቷል።

ፍርድ ቤቱ ትዕዛዙን ለምን እንዳላከበረ በችሎት እንዲያስረዳ ትዕዛዝ ቢልክም ማረሚያ ቤቱ በሁለት ቀጠሮች ቀርቦ አላስረዳም። የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ለ3ኛ ጊዜ በሰጠው ትዕዛዝ ዛሬ ህዳር 1 ቀን 2010 ዓ.ም.ሁለት ኃላፊዎች ቀርበዋል።

የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የፍትህ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አስቻለው መኮንን የማረሚያ ቤቱን እና የታራሚውን ደህንነት ለማስጠበቅ ሲባል ንግስት ተለይታ እንደምትጠየቅ፣ እንዲሁም ሁሉን እስረኛ በተመሳሳይ ሰዓት ማስተናገድ ስለማይቻል የንግስት ጥየቃ ሰዓት ከሌሎች እስረኞች የተለየ መሆኑን እና ባስመዘገበችው የቤተሰብ አባላት እየተጠየቀች መሆኑን አስረድተዋል።

ንግስት ይርጋ በበኩሏ ወደ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ስትገባ የሚጠይቋትን አስመዝግቢ መባሏንና ከተመዘገቡት ውጭ ያሉና 720 ኪሎ ሜትር ርቀት ድረስ ሊጠይቋት የሚመጡ ዘመድና ወዳጆቿ አልተመዘገባችሁም እየተባሉ እንደሚመለሱ ለፍርድ ቤቱ ገልፃለች። ጉዳዩን ለፍርድ ቤት በአቤቱታ አቅርባ ገደብ እንዳይደረግባት ብይን ቢሰጥም ማረሚያ ቤቱ ትዕዛዝን አለማክበሩን አስታውሳለች። ማረሚያ ቤቱ ለምን የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ እንደማያከብር በጠየቀችበት ወቅትም የሴቶች ጥበቃ እና ማረፊያ አስተዳደር ኃላፊ ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አለም ጥላሁን “ይህን ትዕዛዝ የሰጠው ዳኛ ማን ነው? ማወቅ እፈልጋለሁ።” እንዳሏትና እኚህ ኃላፊ ችሎት ውስጥ እንደሚገኙ ለፍርድ ቤቱ አስረድታለች።

ሆኖም ፍርድ ቤቱ ችሎት ውስጥ የነበሩትን ኃለፊ ለምን ይህን እንዳሉ መልስ እንዲሰጡ ሳይጠይቃቸው ቀርቷል። ማረሚያ ቤቱ ለፍርድ ቤቱ በፅሁፍ በሰጠው መልስ ላይ የፈረሙት የሴቶች ጥበቃና ማረፊያ አስተዳደር ጥበቃና ደኅንነት ስራ ዘርፍ ኃላፊ ለተ እግዜር ገ/ መድኅን ናቸው። ሆኖም ትዕዛዙን ለፍርድ ቤት ያደረሱትና በቃል መልስ የሰጡት የለተ እግዜር ኃላፊ ናቸው የተባሉት ዋና ሱፐር አለም ናቸው።
ማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ከሰጡት መልስ በተቃራኒ ገደብ እየተደረገባት መሆኑን ንግስት ለፍርድ ቤቱ ገልፃለች። በሀገራችን ባህል የታመመ እና የታሰረ ሰው ማንም እንደሚጠይቀው ያስታወሰችው ንግስት ይርጋ ጠያቂዎቿ መታወቂያ እስከያዙ እና ጠያቂና እሷን የሚቆጣጠሩ ፖሊሶች እስካሉ ድረስ በማንኛውም ሰው መጠየቅ መብቷ እንደሆነ ገልፃለች።

“ማንኛውም የተከሰሰ ሰው ነፃ ሆኖ የመገመት መብት አለው” ያሉት ጠበቃ ሄኖክ አክሉሉ በበኩላቸው፣ ማረሚያ ቤቱ ንግስት ይርጋን በክሷ ምክንያት በደል እየፈፀመባት እንደሚገኝ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል። የፌደራል ማረሚያ ቤቱ ተወካይ ከገለፁት በተቃራኒ ሌሎች እስረኞች ከ3 ሰዓት እስከ 6 ሰዓት ሲጠየቁ ንግስት ይርጋ ከ6 እስከ 7 ሰዓት ባለው አንድ ሰዓት ብቻ እንደምትጠየቅ ገልፀውም ማረሚያ ቤቱ የሚያደርሰውን አድሎ አስረድተዋል። ካስመዘገብሽው ውጭ አትጠየቂም የሚለው የማረሚያ ቤቱ አሰራርም ህገ መንግስታዊ እንዳልሆነ ገልፀዋል።

የንግስት ይርጋ ሌላኛው ጠበቃ አቶ አለልኝ ምህረቱ ፍርድ ቤቱ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት መልስ እንዲሰጥ ትዕዛዝ ቢሰጥም፣ መልስ ለመስጠት የመጡት የእስረኞችን የዕለት ተዕለት ጉዳይ የማይከታተሉ የፌደራል ማረሚያ ቤት ኃላፊ መሆናቸው ጉዳዩን በደንብ እንደማያውቁት ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል። የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ባስመዘገበቻቸው ዘመድና ጓደኛ እየተጠየቀች ነው ያለ ሲሆን አቶ አለልኝ በበኩላቸው ህገ መንግስቱ የቅርብ ዘመድ እና ጓደኛ ሲል ወሰን እንደሌለው፣ ከዚህ መለስ ተብሎ ሊገደብ እንደማይገባ አብራርተዋል።
በንግስት አቤቱታ ጉዳይ ቀጠሮ የተሰጠው ማረሚያ ቤቱ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ለምን እንዳላከበረ ቀርቦ እንዲያስረዳ ለማዳመጥ የነበር ቢሆንም ዛሬም የሁለቱን ክርክር አዳምጦ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

በዚህም መሰረት ንግስት ይርጋ በህገ መንግስቱ አንቀፅ 21 መሰረት ገደብ ሳይደረግባት እንድትጠየቅ ትዕዛዝ ሰጥቷል። የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ንግስት ይርጋ የማይገባ ጭቅጭቅ ማድረጓን ባይገልፁም ፍርድ ቤቱ ” ተከሳሽም የማይገባ ጭቅጭቅ ውስጥ ላለመግባት ጥንቃቄ ያድርጉ፣ ህጉን ለይተው አውቀው ይጠቀሙ” ብሏዋል። ከችሎት ውጭ ያነጋገርኳቸው የንግስት ጠበቆች ንግስት መሰል ባህሪ አሳይታለች ባልተባለበት ፍርድ ቤቱ ያልተነሳ ነገር ላይ ለተከሳሽ ትዕዛዝ መስጠቱ ተገቢ አይደለም ብለዋል። በሌላ በኩል ንግስት ይርጋ ጥርሷን ታማ መድሃኒት ቢታዘዝላትም መድሃኒቱ በታዘዘላት ሰዓት እየተሰጣት እንዳልሆነ አቤቱታ አቅርባለች።

የማረሚያ ቤቱን መልስ ከመስማት በተጨማሪ እነ ንግስት ይከላከሉ ወይስ አይከላከሉ በሚለው ላይ ብይን ለመስጠት ተቀጥረው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ “መዝገቡ ተመርምሯል።ጊዜ አግኝተን ማጠቃለል አልቻልንም” ብሎ ለህዳር 5/2010ዓ•ም ለብይን ሌላ ቀጠሮ ሰጥቷል።

%d bloggers like this: