Category Archives: Social and Culture

በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው የመጀመሪያው ማጣሪያ ጨዋታ በናይጄሪያ አሸናፊነት ተጠናቀቀ

 

bbbየኢትዮጵያ እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድን ለብራዚሉ ዓለም ዋንጫ 2014 ማጣሪያ በአዲስ አበባ ስታዲየም ዛሬ ጥቅምት 3 ቀን 2006 ዓ.ም. ከናይጄሪያ አቻው ጋር ባደረገው ጨዋታ 2 ለ 1 ተሸነፈ፡፡ በውጤቱም ኢትዮጵያ 1፡ 2 ናይጄሪያ በመሆን ተጠናቀቋል፡፡ በጨዋታውም የኢትዮጵያ ብሔራዊ እግር ኳስ ቡድን ከፍተኛ ብልጭ የበላይነቱን ቢያረጋግጥም፤የኢትዮጵያ የፊት አጥቂ ሳላዲን ሰይድ ያገባት ጎል በዳኛው ተሽራለች፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድን የበረኛው ክልል አካባቢ በተፈጠረ የቴክኒክ ችግር ባለቀ ሰዓት ናይጄሪያ ልታሸንፍ ችላለች፡፡

ሁለቱም ቡድኖች ጎሉን ያስቆጠሩት በሁለተኛ አጋማሽ ሰዓት ሲሆን ለኢትዮጵያ በ56ኛው ደቂቃ የመሪነት ጎሉን በግራ አቅጣጫ ያስቆጠረው በኃይሉ አሰፋ (ቱሳ) ነው፡፡ ናይጄሪያ ደግሞ አንዱን በጨዋታ ስታገባ ሁለተኛውን ጎል ግን በተሰጣት ፍፁም ቅጣት ምት ነበር፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ ስታዲየም በተመልካቾች የብሔራዊ ቡድኑን መለያ በመልበስ እጅግ አሸብርቀው ለሜዳው ደምቀት ሰጥተውታል፡፡ ቀጣዩ የደርሶ መልስ በናይጄሪያ በሚደረገው ጨዋታ ለዓለም ዋንጫ የመጨረሻው ውጤት ይታወቃል፡፡

የአለም ሻምፒዮኖቹ ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ለአለም ኮከብ አትሌትነት እጩ ሆኑ

የአለም ኮከብ እጩዎቹ ጥሩነሽ፣ መሐምድ እና መሰረት

athlets
የአለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር ባለሞያዎች ቡድን እ.አ.አ በ2013 ዓ.ም የአትሌቲክስ ውድድር አመት አትሌቶች በሩጫ፣ ውርወራ እና ዝላይ ውድድሮች ያስመዘገቧቸውን ውጤቶች እና ሌሎች መስፈርቶችን ከግምት ውስጥ በማስገባት ባደረገው የኮከብ አትሌቶች እጩዎች ምርጫ ኢትዮጵያዊያኖቹ የረጅም ርቀት ሩጫ ድንቆች ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰረት ደፋር፣ እንዲሁም የወቅቱ የ800 ሜትር ሩጫ ኮከብ መሀመድ አማንን ጨምሮ በወንዶች 10፣ በሴቶች 10 አትሌቶችን እጩ አድርጎ አቅርቧል።
በሞስኮ አስተናጋጅነት በተካሄደው 14ኛው የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 10 ሺህ ሜትሩን 30፡43.35 በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ በአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ በርቀቱ ሶስተኛዋ በአጠቃላይ ደግሞ አምስተኛዋ የሆነው የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘችው ጥሩነሽ ዲባባ በ10 ሺህ ሜትር ርቀት ባደረገቻቸው 11 ተከታታይ ውድድሮች አንድም ውድድር አለመሸነፏ እና በ2013 ዓ.ም በተለያዩ ርቀቶች ባደረገቻቸው ውድድሮች ጠንካራ ተፎካካሪነቷን በተደጋጋሚ ለማሳየት መቻሏ ለእጩነት አብቅቷታል።
የ 2007 ዓ.ም የአለም ኮከብ መሰረት
ሌላዋ ለአለም ኮከብነቱ እጩ የሆነችው ኢትዮጵያዊ አትሌት መሰረት ደፋር በሞስኮው የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ማጣሪያውን በቀላሉ ካለፈች በኋላ በፍጻሜው ውድድር ወቅት በተለመደው አስደናቂ የአጨራረስ ብቃቷ በመታጀብ 5 ሺህ ሜትሩን 14:50.19 በሆነ ጊዜ አጠናቃ ለሁለተኛ ጊዜ በርቀቱ የአለም ሻምፒዮን ከመሆኗ በተጨማሪ አመቱ ጥንካራ ተፎካካሪዋ ጥሩነሽ ዲባባን በዳይመንድ ሊግ ያሸነፈችበት እና በተደጋጋሚ አስደናቂ ብቃቷን ያሳየችበት ሆኖ ነው የተጠናቀቀው።
እ.አ.አ በ 2007 ዓ.ም መሰረት ደፋር እጅግ በጣም ውጤታማ አመትን በማሳለፏ በአለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (IAAF) የአመቱ ኮከብ ሴት አትሌት ተብላ በመመረጥ ይሄንን ክብር ያገኘች በታሪክ ሁለተኛዋ ሴት አፍሪካዊት አትሌት ለመሆን ከመቻሏ በተጨማሪ ሶስተኛዋ ኢትዮጵያዊትም ለመሆን መቻሏ ይታወሳል። ከመሰረት በፊት ታላላቆቹ ሀይሌ ገብረስላሴ (1998 ዓ.ም) እና ቀነኒሳ በቀለ (2004 እና 2005 ዓ.ም) የአመቱ የአለም ኮከብ አትሌቶች ተብለው ተሸልመዋል።
በወንዶቹ በኩል ለኮከብ አትሌትነት ዘንድሮ እጩ ሆነው ከቀረቡት አስር አትሌቶች መካከል ብቸኛው ኢትዮጵያዊ መሀመድ አማን 2013 ዓ.ም እጅግ በጣም ስኬታማው አመት ነበር። በሞስኮው 14ኛው የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በድንቅ የአጨራረስ ብቃት 800 ሜትሩን በአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ ሶስተኛው ፈጣን ሰአት ሆኖ በተመዘገበ 1:43.31 በሆነ ጊዜ አጠናቆ ለኢትዮጵያ በታላላቅ ሻምፒዮናዎች ከ5 ሺህ ሜትር በታች በሆነ ውድድር የወርቅ ሜዳሊያ ያስገኘ በታሪክ የመጀመሪያው አትሌት የሆነው መሀመድ አማን በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮን በመሆን በፍጹም የበላይነት ነበር የዘንድሮውን የውድድር አመት ያጠናቀቀው።
እ.አ.አ ከጥቅምት 1 ቀን 2013 ጀምሮ እስከ ፊታችን ጥቅምት 27 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ *የአለም አትሌቲክስ ቤተሰብ* በኢሜል መልእክቶች በሚያደርገው የድምጽ አሰጣጥ ሂደት ከፍተኛ ድምጽ የሚያገኙ ሶስት ወንድ እና ሶስት ሴት አትሌቶች ወደፍጻሜው የሚያልፉ ሲሆን፣ ከዛ በኋላ የአለም አቀፉ አትሌቲክ ፋውንዴሽን ምክርቤት የአለም ኮከብ በመሆን የሚያሸንፉት ወንድ እና ሴት አትሌቶችን መርጦ አሸናፊዎቹ እ.አ.አ ህዳር 16 ቀን 2013 ዓ.ም ሞናኮ ውስጥ በሚካሄድ ስነ-ስርአት በይፋ ይታወቃሉ።
የዘንድሮውን የአለም ኮከብ አትሌትነት ክብር ጃማይካዊያኖቹ የአጭር ርቀት ውድድር ኮከቦች ዩሴን ቦልት እና ሼሊ-አን ፍሬዘር-ፕራይስ ይወስዱታል ተብሎ ይጠበቃል።
ዩሴን ቦልት እና አሜሪካዊቷ አሊሰን ፊልክስ የ2012 ዓ.ም የወንዶች እና ሴቶች የአለም ኮከብ አትሌቶች ተብለው መመረጣቸው ይታወሳል።
ምንጭ፡- ፍስሃ ተገኝ “ቶታል 433 “ ስፖርት

Teddy Afro chosen for World Cup 2014 Official Singer for Africa

tedyIn the grand tradition of music for the 2014 FIFA World Cup, the most Ethiopian young popular singer Tewodros Kassahun (Teddy Afro ) has been chosen to represent the world’s most popular sports competition. Teddy Afro’s Song will be featured as the official song for the 2014 World Cup for Africa.
According to the source Teddy afro was selected by Coca Cola to represent Africa for the 2014 FIFA World Cup song. It seems like Teddy Afro took Ethiopia to world cup already.
Teddy Afro’s finished Song and Video Clip that was shot in Kenya will be available world wide very soon.

ነፍስህን በገነት ያኑራት

ብስራት ወ/ሚካኤል

eyob

ብዙ ተስፋ ጥለን በህይወት ልናይህ
የጀመርከው አልቆ በለዛ አንደበትህ
ልናደምጠው ነበር አዲሱን ስራህን
ተስፋ ሆኖ ባይቀር ምኞት ቢሰምርልን
ይሁና…ምን ይደረጋል ከቁጭት በቀር
የሚወዱትን ማጣት እየጓጉ ማረር
በቃ እውን ሆነ ማለት ነው?
ዳግም ከድምፁ ውጭ በመድረክ ላናየው
ኦ…አንተ ሞት ለካ እንዲህ ጨካኝ ነህ
ተወዳጁ ኢዮቤን እንዲህ ትለያለህ
አሁን ምን ይባላል…አጣንህ በህይወት
በቃ ኢዮቤዬ… ነፍስህን ፈጣሪ በገነት ያኑራት
(ለድምፃዊ ኢዮብ መኮንን ነሐሴ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.)

ወጣቱ ወዴት እየተመራ ነው?

ብስራት ወ/ሚካኤል

ልማት ትርጓሜው እጅግ ሰፊ ቢሆንም ጥቅል ሐሳቡ ግን ለሰው ልጆችም ሆነ የተፈጥሮ ሚዛንን በመጠበቅ በማኀበረሰቡ ዘንድ ይሁንታን ያስገኘ ለኑሮ ተስማሚ ሁኔታን በመፍጠር ውጤታማ የሆነ ተጨባጭ እውነታን ያዘለ ክንውን ነው፡፡ ይህም ሰብዓዊና ቁሳዊ ይባላል፡፡ ይህን በተመለከተ በተለይ ሰብዓዊ ልማት የሚባለው ቁሳዊ የሚባለውን ልማት ሊያመጣ የሚችል የሰው ልጆች የባህሪ አስተሳሰብ አዎንታዊ ለውጥ ነው፡፡ ይህ ለውጥ የማኀበረሰቡን በጎ አሴቶችን አጠናክሮ በመቀጠል አሉታዊ የሚባሉትን በማረምና አዳዲስ አዎንታዊ ለውጦችን ከልማዳዊ አኗኗር ጋር በማስማማት በስልጣኔ ቀላልና ምቹ ሁኔታን መፍጠር ነው፡፡ ያኔ ቁሳዊ ልማቱን በሚፈለገው ደረጃ ማምጣት ይቻላል፡፡ የዚህ ልማት ውጤታማ ተግባርና የስልጣኔ ዝመና ሽግግር ትልቁን ሚና የሚጫወተው ወጣቱ ሲሆን ለዚህም አበረታች የሞራል ስንቅ ያስፈልጋል፡፡
በተለይ በኢትዮጵያ ከሀገሪቱ አብላጫው የህዝብ ቁጥር ልቆ የሚታየው ወጣቱ ነው፡፡ የዛን ያህል ደግሞ ከምርታማነት ይልቅ ጥገኛ እንዲሆን የተፈረደበት ይመስላል፡፡ በተለይ በአሁን ወቅት በኢትዮጵያ የራሱን ዕድል በራሱ መወሰን ተስኖት ሌሎች የሚመርጡለትን፣ የመረጡለትን በመጠበቅ ጊዜውን ሲያባክን ይታያል፡፡ ይህ ማለት ግን አኩሪ ተግባር እየፈፀሙ ያሉ ወጣቶች ጭራሽ የሉም ማለት አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ከለው ቁጥር አንፃር ሲታይ አብዛኛው ወጣት በብዙ ነገሮች ጥገኛ እንዲሆን በመገደዱ እራሱን እንዳይመለከት ጋርዶታል፡፡
ድሮ ድሮ እንኳን ስለራሱ፣ ስለሀገሩ ከዛም አለፍ ሲል ስለሌሎች ይጨነቅ የነበረው ወጣት ዛሬ ስለራሱ በራሱ መወሰን ተስኖት የተመረጠለት ካልተስማማው የመጨረሻ ምርጫውን ስደት ሲያደርግ ይስተዋላል፡፡ በዚህም መሐል ህጋዊና ህገወጥ የሚል ስያሜ ይሰጠዋል፡፡ ይሁን እንጂ ለስደት የዳረገውን ምክንያት ግን ደፍሮ የሚገልፅ አካል አልተገኘም፡፡ እንግዲህ እንዲህ የተፈረደበትን ወጣት ሀገር እያሳጡት ሀገር ተረካቢ እየተባለ ይቀለድበታል፡፡
ወጣትነት እጅግ ፈተና የበዛበት የተፈጥሮ የእድሜ ሂደት አካል ቢሆንም በርካታ ውጤታማ ስራዎችን ለመስራት ግን ከየትኛውም የዕድሜ ክልል የተሻለ ነው፡፡ የመኖሪያም ሆነ የመዋያ ምርጫው በሌሎች መልካም ፈቃድ ላይ ብቻ የተወሰነ በመሆኑ በተለይ በኢትዮጵያ ያለው ክስተት ወጣቶች ሆን ተብሎ ምርታማ እንዳይሆኑ የሚሰራ ይመስላል፡፡ ለዚህም ማረጋገጫ ይሆነን ዘንድ ጥቂቶቹን እንይ፡፡
የወጣት ማዕከላት
ቀደም ባለው የደረግ ስርዓት ግልፅና ቀጥተኛ ሶሻሊስት የነበረ ቢሆንም ወጣቱን በእስፖርትና በሌሎች የኪነ ጥበብ ዘርፎች ለማጎልበት ይረዳ ዘንድ በርካታ የተለያዩ የወጣት ማዕከላት ነበሩ፤ አሁን በነበሩ ቀረ እንጂ፡፡ በወቅቱ በተለያዩ ከተሞች ከስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳ እስከ ሙዚቃና ቴአያትር (ድራማ መለማመጃ) በየከተማ ቀበሌው ይገኝ ነበር፡፡ለወጣቶቹ ታስቦ በተሰሩት ሜዳዎችና አዳራሾች ወጣቱ በአግባቡ ይጠቀምበት የነበረ ቢሆንም ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ነፃ የሐሳብ መንሸራሸርን በተመለከተ ግን ከስርዓቱ ውጭ እንደማይፈቀድ በግልፅ ስለሚታወቅ ጎጅ ቢሆንም ብዙም የሚገርም አይደለም፡፡
ዛሬ ደግሞ በአንፃሩ የነበሩ ሜዳዎች ዳግም ባናያቸውም በወጣቱ መዝናኛ ሰም የኢህአዴግ ካድሬ መመልመያ ሆነው አርፈዋል፡፡ የወጣት ማዕከል ተብሎ በተሰሩ አዳራሾች ምንም ከቀድሞ የተለየ ነገር የለም፡፡ ምክንቱም ዛሬም በአዳራቹ ስለ ኢህአዴግ ጥሩነት ለማውራትና የርካሽ ባዶ ፖለቲካ መጠቀሚያ ከመሆን ውጭ ወጣቱ ነፃ የሆነና ያመነበትን ርዕስ አንስቶ መወያየት አይችልም፡፡ ይህ የሆነው ግን በህግ ሳይሆን ከመጋረጃ በስተጀርባ ባልተፃፈው ትዕዛዝ ነው፡፡
በተለይ በአዲስ አበባ በርካታ የቀበሌ አዳራሾች ቢገነቡም እየሰጡት ያለው አገልግሎት ግን ሁሉንም ወጣት ሊያካትት በሚችል የተለያዩ ሐሳቦች ሊንሸራሸሩ በሚያስችል ሁኔታ ሳይሆን በኢህአዴግ ጥላ ለተሰበሰቡት ብቻ ነው፡፡ እንዲህም ቢሆን የሚሰጡት አገልግሎት ቢበዛ ቤተመፅሐፍ፣ ጂም እና የገላ መታጠቢያ አገልግሎት ነው፡፡ በዚህም የወጣቱ ፍላጎት በሁሉም የአዲስ አበባ ከተማም ይሁን በሀገር አቀፍ ምርጫው ሁሉን ያሳተፈ የወጣቱ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ይህ ካልሆነ ደግሞ ወጣቱ በፍላጎቱ በልማት ላይ ተሳታፊ ነው ማለት አይቻልም፡፡ምክንያቱም ቁሳዊ የአዳራሽ ግንባታ የወጣቱን አስተሳሰብ በመቀየር ሰብዓዊ ልማት ማምጣት አልቻለምና፡፡
አስተሳሰብን ያህል ነገር ሁሉም በሌሎች ፍላጎትና ምርጫ ተፈጥሮን በሚሽር መልኩ አንድ እንዲሆን እየተደረገ ባለበት ሁኔታ ሁሉን አቀፍ ተሳትፎዓዊ የተደረገበት አሳታፊ ቁሳዊ ልማትን ማምጣት አይቻልም፡፡ ሰርተናል እየተባለ የሚዘፈንለት ቁሳዊ ልማትም ቢሆን የወጣቱን የመንፈስ ልዕልና ሊገነባ ባልቻለበት ሁኔታ በሀገሪቱ ላይ ሁለንተናዊ እምርታ ለውጥ ማየት ይናፍቃል፡፡ ቀድሞ በየአካባቢው የነበሩ ሜዳዎችም ቢሆኑ አንዳንዶቹ በነበሩበት ቢቀጥሉም አብዛኞቹ ባለመኖራቸው፣ አዳዲስ የመኖሪያ ቤት ግንባታ የተደረገባቸውም ሆነ እየተደረገባቸው ያሉ አካባቢዎች የወጣቶች ስፖርት ማዘውተሪያዎች ባለመታየታቸው ዋቱን ወደ አልባሌ ቦታ እንዲውል እያስገደዱት ይገኛሉ፡፡
ጎጂ የደባል ሱስ ግብዣ
በአሁን ሰዓት ወጣቱ በራሱ ጉዳይ እራሱ እንዲወስን ከማድረግ ይልቅ በደባል ሱስ ጥገኛ እንዲሆን የሺሻና ጫት ግብዣ እየቀረበለት ይገኛል፡፡ ይሄም በፊት እንደ ነውር ይታይባቸው በነበሩ አካባቢዎች ሳይቀር ዛሬ ዛሬ እንደመልካም እየታየ እስከ ዩኒቨርስቲዎች መዝለቁ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ እነኚህን ድርጊቶች የሚያበረታታ የመንግስት አካል ባይኖር ኖሮ መኖሪያ መንደር ድረስ ዘልቀው ባልታዩ ነበር፡፡
ከከፍተኛ የትምህርት ተቋም የተመረቁና የሚመረቁ ወጣቶችም ቢሆኑ ከ15ዓመታት በላይ በእውቀት ግብይት በትምህርት ቢያሳልፉም ዛሬ ግን 15 ቀናት በማይፈጅ ስልጠና ያውም ጥቂቶችን በኮብል ስቶን ድንጋይ ጠረባ ስራ እንዲሰማሩ ይደረጋል፡፡ በርግጥ ማንኛውም ሙያም ሆነ ስራ የሌሎችን ሰዎች መብትና ጥቅም እስካልነካ ድረስ የሚናቅ ባይሆንም ለዘመናት ያካበቱት እውቀት ግን ሜዳ ላይ ሲወድቅ የሀገር ሀብት በከንቱ መባከኑን ማሳየቱ አይቀርም፡፡ በአሁን ወቅትም የያዝነው 2005ዓ.ም.ን ጨምሮ በየዓመቱ ከ 80 ሺህ በላይ የሀገሪቱ ወጣቶች በተለያየ የትምህርት ዘርፍ ቢመረቁም በሙያቸው የሚሰማሩት ግን 10ሺህ እንዳማይሞሉ ይገለፃል፡፡ ይሄ ደግሞ የእውቀት፣የገንዘብና የጉልበት ብክነት መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
በሙያቸው ተደራጅተው የስራ ዕድል እንዳይፈጥሩም ስርዓቱ እና የስነ ህዝብ ፖሊሲው ዜጎችን ሙሉ በሙሉ የመንግስት ኢኮኖሚ ጥገኛ ስላደረገ በሚፈልጉት ሙያ መሰማራት አይችሉም፡፡ ይህንንም ለመቅረፍ የገንዘብ ብድር ቢፈልጉ እንኳ የግድ አብዮታዊ ዴሞክራሲን ተቀብለው በኢትዮጵያዊነት ሳይሆን በኢህአዴግ አባልነት ቅድመ ሁኔታ በየቀበሌ ያሉ ተራ ካድሬዎች ከላይ በሚወርድ መመሪያ መሰረት ለማደራጀት ይሚክራሉ፡፡ ውጤቱ ግን ወጣቱን አምራች ኃይል ከማድረግ ይልቅ የሙያና የኢኮኖሚ ነፃነት ስለሌለው ጥገኛ እንዲሆን አስችለውታል፤እያስቻሉትም ነው፡፡ ይሄ ካልተቀየረ ደግሞ የሀገሪቱ ወጣት ጊዜውን፣እውቀቱንና ጉልበቱን በከንቱ እንዲያባክን ያደርጉታል፡፡
ከላይ ከተጠቀሰው በተጨማሪ በየመንደሩ እየፈሉ ያሉት የአልኮል መጠጥ ቤቶችና ጭፈራ ቤቶች አንዱ የልማት አካል እንጂ የሰብዓዊ ልማትን ወደ ኋላ የሚያስቀር ተደርጎ አልተወሰደም፡፡ በዚህ ምክንያት ወጣቱ ሰርቶ ከመለወጥ ይልቅ የሰራበትንም በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲያውል ምቹ ሁኔታ እንኳ ሲፈጠርለት አይታይም፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ለወጣቱ እጅግ ጠቃሚና አስፈላጊ እንደሆኑ የሚታወቁት የሐሳብ የበላይነት ላይ የሚደረጉ ውይይቶችና ክርክሮች ቦታ ባለመሰጠታቸው እንደ ሚዩዚክ ሜዴይ የመሳሰሉት የንባብን ባህል ለማዳበር የሚረዳው የመፅሐፍ ሐሳብ መወያያ አዳራሽ አጥተው አምስት ኪሎ በሚገኘው በጠባቧ ብሔራዊ ሙዝየም አዳራሽ ማየት ልማት ወዴት ወዴት ያሰኛል፡፡ ባንፃሩ አብዛኛውን ጊዜ የገዥው ኢህአዴግ ካድሬዎች መፈንጫ እየሆነ ያለውና በህዝብ አንጡራ ሃብት የተገነቡት የቀበሌ/የወረዳ አዳራሾች ደግሞ አብዛኛውን ጊዜ ከኢህአዴግ ስራና ካድሬዎች በስተቀር ኸረ የሰው ያለህ እያሉ ይገኛል፡፡ ይህ ሁሉ ታዲያ ለሰብዓዊ ልማት ትኩረት ባለመሰጡ ነገ ሀገር ተረካቢ በሚባለው ወጣት ላይ ይነገድበታል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በፊት የወጣቶች መዝናኛ የነበሩ የስፖርት ሜዳዎችና የመናፈሻ ቦታዎች አንዳንዶቹ የህንፃ ግንባታ ሲሰራባቸው እንደነ ሂልተን አዲስ ሆቴል ፊትለፊት የነበሩ መናፈሻዎች ደግሞ ተከልለው ወጣቶች ዝር እንዳይሉባቸው ተደርገዋል፡፡
ከሌሎች መጠበቅንና መቀበልን መምረጥ
የተሻለ ነገርን በራስ ከመወሰን፤ እንዲሳካም ከመጠየቅ ይልቅ በሌሎች ላይ ጥገኛ በመሆን በሁሉም ነገር የመጠበቅና የመቀበል ብቻ አዝማሚያ በስፋት በወጣቱ ያስተዋላል፡፡ በዚህም የራሱን ጉዳይ ሌሎች እንዲወስኑለት በመፍቀዱ የራሱን ሚና አሳልፎ እየሰጠ ይገኛል፡፡ ስለሆነም ምርጫውን ከመፈለግ ይልቅ የመጣውን ብቻ የመቀበል ጉዳይ በስፋት ይስተዋላል፡፡
አማራጭ ሐሳቦችን ከራስ ጋር አስማምቶ ለመያዝም ሆነ የራስን ምርጫ ለማስተናገድ ይረዳ ዘንድ ነፃ የሆነ የሐሳብ ፍጭት ዕድል በመነፈጉ አሉታዊም ቢሆን ተቀብሎ የራስ ማድረግ እንደ አዋቂነትና ብልህነት እየተወሰደ ይገኛል፡፡ ይሄ ደግሞ የትውልድ የአስተሳሰብ ብክነትንና ምክነትን በማንፀባረቅ ተተኪው ትውልድ ከማለት ይልቅ ጠባቂው ቢባል የሚስማማው ይመስላል ፡፡
ከላይ ለተጠቀሱት ችግሮች ዋነኛ ምክንያት ደግሞ በተለይ በወጣቶች ላይ እየተሰራ ያለው ሰብዓዊ ልማት በቁሳዊ በመሸፈኑ የሚመጣ ኋላቀር እሳቤ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ገዥው ስርዓት የልማትን አስፈላጊነትና ምንነት በቅጡ ካለመረዳት የሚመጣ ደጋማ እሳቤ ሲሆን እራሱ ወጣቱም ቢሆን በእራሱ ላይ አሉታው ድርሻ እንዳለው ሊዘነጋ አይችልም፡፡ ስለዚህ እምርታዊ |የሀገር ዕድገትና ለውጥ ለማምጣትና ሁሉን አቀፍ ገቢራዊ ልማት ለማስመዝገብ ቅድሚያ ሰብዓዊ ልማት መቅደም ይኖርበታል፡፡ ያኔ ቁሳዊ ልማትን በሚፈለገው መጠንና ዓይነት ማምጣት ይቻላል፡፡