በአዲስ አበባ ከ 8 ዓመታት በኋላ ታላቅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ
ሰማያዊ ፓርቲ ግንቦት 25 ቀን 2005ዓ.ም. በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ከ1997ዓ.ም. ምርጫ 8 ዓመት በኋላ ታላቅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ፡፡ ፓርቲው በዋነናነት አንግቦ የተነሳው 4 ጥያቄዎችን ሲሆን እነኚህም ሙያዊ ግዴታቸውን በመወጣታቸው ብቻ የታሰሩ ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች እንዲፈቱ፣ የኃይማኖት ነፃነት ይከበር በሚል ጥያቄ በማንሳታቸው ብቻ የታሰሩ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች እንዲፈቱ፣ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ከሚኖሩበት ቦታ እንዲፈናቀሉ የተደረጉ ዜጎች ካሳ ተከፍሏቸው በነበሩበት ቀዬ እንዲኖሩና የድርጊቱ ፈፃሚዎች ለህግ እንዲቀርቡ ፣ ኢህአዴግ በሚከተለው የተሳሳተ ፖሊሲ ምክንያት ሙስና እና ስራ አጥነት እንዲሁም ብልሹ አሰራሮች በአስቸኳይ እንዲታረሙ የሚሉ ጥያቄዎች ናቸው፡፡
ሰላማዊ ሰልፉም ከፓርቲው ጽህፈት ቤት ግንፍሌ መነሻ በማድረግ አራት ኪሎ የድል ሐውልት፣ ፒያሳ ከዚያም ቸርችል ጎዳና በማድረግ ወደ መዳረሻው ዋናው ፖስታ ቤት ፊትለፊት በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ የወዳጅነት አደባባይ በሺህዎች የሚቀጠሩ ሰዎች በተገኙበት ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል፡፡ በሰልፉም ላይ በርካታ መፈክሮች የቀረቡ ሲሆን ከነኚህም መካከል ያለ ነፃ ፕሬስ ዴሞክራሲ የለም፣ ኢቴቪ ሌባ፣ ኢህአዴግ ሌባ፣አንለያይም፣ አንድ ነን(ሙስሊምና ክርስቲያን)፣ አሸባሪ አይደለንም፣ የታሰሩ ይፈቱ፣ ህገመንግስቱን የሚፃረሩ አፋኝ አዋጆች በአስቸኳይ ይሰረዙ፣…የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በርካታ ሙስሊሞችን ጨምሮ የሰማያዊ፣ የአንድነት፣ የመኢአድና የመደኢዴፓ እንዲሁም የመድረክ ወጣቶች በብዛት መገኘታቸውን ለማየት ተችሏል፡፡ በመጨረሻም በሰልፉ መዳረሻ በነበረው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም፣ አቶ አለሙ ጎቤቦ(የጋዜጠኛ ርዕዮት አባት) እና የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሰልፈኞቹ በሰላማዊና በኢትዮጵያዊ ጨዋነት በማካሄዳቸው አመስግነው በተለይ ኢንጅነር ይልቃል በንግስት አራቱንም ጥያቄ በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ ካልመለሰ በድጋሚ ለተቃውሞ ሰልፍ እንደሚወጡ በመግለፅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ በተሳካ ሁኔታ ከቀኑ በ 8፡00 ሰዓት ተጠናቋል፡፡
በሰልፉ ወቅትምየታሰሩ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፣ጋዜጠኞች እስክንድር ነጋ፣ውብሸት ታዬ እና ርዕዮት አለሙ፤ ከፖለቲከኞች አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን፣ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ኦልባና ሌሊሳ በተጨማሪ ከቢኒሻንጉል ጉሙዝ የተፈናቀሉ የአማርኛ ተናገሪ ኢትዮጵያዊያን ፎቶ በትልቁ ተዘጋጅቶ ይታይ ነበር፡፡