የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጥፋተኛ መሆኑን አመነ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምንያህል ተሾመ ሰኔ 1 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን ጋር በተደረገው ጨዋታ መሰለፉ ስህተት እንደሆነ አመነ፡፡ ፌዴሬሽኑ ብሄራዊ ቡድኑ ከደቡብ አፍሪካ አቻው ጋር ከመጫወቱ በፊት ችግር ስለመፈጠሩ ከፊፋ ደብዳቤ ደርሶት እንደነበርም ገልጿል፡፡
የፌዴሬሽኑ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ለችግሩ ተጠያቂ ያላቸውን ግለሰቦች ዝርዝርም ይፋ አድርጓል፡፡ በዚህ መሰረት የብሄራዊ ቡድኑ ቡድን መሪ አቶ ብርሀኑ ከበደ ፣ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ፣ ረዳት አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ፣ የቡድኑ ተጨዋች ምንያህል ተሾመ እና የፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት ኃላፊዎች ጥፋተኛ ተብለዋል።
ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በጥፋተኞቹ ላይ በቅርቡ ተገቢውን ቅጣት በመውሰድ የቅጣት ውሳኔውን ለህዝብ ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
ፌዴሬሽኑ በተፈጠረው ችግር ከፍተኛ ሀዘን እንደተሰማው ገልፆ መላውን የኢትዮጵያ ህዝብ ይቅርታ ጠይቋል፡፡
የቡድኑ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በተፈጠረው ስህተት የተሰማቸውን ሀዘን ገልፀው ፥ ከማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር ለሚካሄደው ጨዋታ ከወዲሁ መዘጋጀት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ጨዋታውም አሸንፈን ወደ አለም ዋንጫ እንደምንሳተፍ እርግጠኛ ነኝ ብለዋል ፡፡
በፊፋ ህግ መሰረት ተገቢ ያልሆነ ተጨዋችን ማሰለፍ በጨዋታው የተገኘውን ነጥብ እና ተጨማሪ የገንዘብ ቅጣት እንደሚያስጥል ይታወቃል፡፡