የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት) ለመጪዎቹ 3 ዓመታት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳን ተክ በመተካት ፓርቲውን በሊቀመንበርነት የሚመራ 3 ዕጩዎች የምረጡኝ ቅስቀሳ መቀጠላቸው ተገለፀ፡፡ ፓርቲው በተለይም የፓርቲውን ዓላማና ግብ በአጭር ጊዜ ከማሳካት አንፃር ትግሉን ይመራል፣ መጪውን 2007 ዓ.ም. ምርጫንም በድል ለማጠናቀቅ ይረዳ በሚል ከወዲሁ ድንገተኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመጥራት አዲስ የፓርቲውን ሊቀመንበር እና የብሔራዊ ምክር ቤት አባላትን ሊያስመርጥ ነው፡፡ ለዚህም መጪዎቹን ዓመታት አንድነት ይመራል በሚል በዕጩነት የቀረቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ኬሚካል ኢንጂነሩ ረዳት ፕሮፌሰር ግዛቸው ሽፈራው፣ በፓርላማ ብቸኛው የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካይ እና የልማት አማካሪ አቶ ግርማ ሰይፉ እና መንግስታዊ ያልሆነ በአፍሪካ የንግድ ግብይት ጥናት ድርጅት ባለሙያ የሆኑት አቶ ተክሌ በቀለ ናቸው፡፡
ኢንጂነር ግዛቸው በሙያቸው በኬሚካል ምህንድስና ማስተርስ ድግሪ ያላቸው ሲሆን፤ በፖለቲካ ህይወታቸው በመኢአድ እና በኋላም በቅንጅት ፤አሁን ደግሞ በአንድነት/መድረክ ከተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበርነት ጀምሮ አሁን ደግሞ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል በመሆን ልምድ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ አቶ ግርማ ሰይፉ ደግሞ በኢኮኖሚ ፖሊሲ ትንተና የማስተርስ ድግሪ ያላቸው ሲሆን፤ በፖለቲካ ህይወታቸው በቀድሞ ኢዴሊ በኋላም በቅንጅት፤ አሁን ደግሞ የአንድነት/መድረክ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር እና ስራ አስፈፃሚ እና የብሔራዊ ምክር ቤት አባል በመሆን ልምድ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡
ሶስተኛው እጩ ደግሞ የአንድነት ፓርቲ የጀርባ አጥንት በመሆን ሰፊ ስራ እየሰሩ ያሉት አቶ ተክሌ በቀለ በሙያቸው በማኀበራዊ ግብይት የማስተርስ ድግሪ ያላቸው ሲሆን፤ በፖለቲካ ህይወታቸው በቀድሞ ኢዴፓ በኋላም በቅንጅት አሁን ደግሞ በአንድነት/መድረክ ከሰሜን ቀጠና አደራጅነት ጀምሮ በአሁን ወቅት የማዕከላዊው ፋይናንስ ሃላፊ እና ስራ አስፈፃሚ አባል እንዲሁም የብሔራዊ ምክር ቤት አባል በመሆን ሰፊ የፖለቲካ ልምድ እንዳላቸው መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
ፓርቲው በያዝነው የፊታችን ታህሳስ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ በሚያካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ የፓርቲውን ሊቀመንበር ጨምሮ በፓርቲው ከፍተኛ ስልጣን ላለው ብሔራዊ ምክር ቤት አባላትን እንደሚያስመርጥ ይታወቃል፡፡ በተለይ ዕጩ ሊቀመንበሮቹ በአሁን ወቅት በይፋ የምረጡኝ ቅስቀሳ መጀመራቸውን የፓርቲው ልሳን ያስታወቀ ሲሆን፤ በመካከላቸው ያለው ፉክክርም እጅግ ፈታኝ እና አጓጊ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡