‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› ማለት ሊቀር ነውን?

ዲ/ን ዳንኤል ክብረት
ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርኩን እንደራሴ ሹመት በተመለከተ ለመወያት የያዘው አጀንዳ የመንግሥት ተወካይ ባለበት እንዲታይ መወሰኑን ዛሬ ጠዋት ሰማን፡፡ ከብጹዐን ጳጳሳት በቀር ካህናትና ቆሞሳት እንኳን የማይገቡበት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አማኝ ይሁን ኢአማኒ፣ ሙስሊም ይሁን ክርስቲያን የማይታወቅ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝበት መጋበዙ የደረስንበትን የውርደት ደረጃ የሚያሳየን ነው፡፡
በአንድ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ወሳኝ አካል መሆኑን ስናስበው፤ በሌላ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የሚደረገው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ነው፤ ውሳኔውም በሐዋርያት ሥራ እንደተገለጠው ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› የሚባልበት ነው(የሐዋ. 15፣29) የሚለውን ስናየው ‹የመንግሥት ተወካይ ይኑርልን› የሚለውን ውሳኔ ኢሃይማኖታዊ ነው ያሰኘዋል፡፡ ለአንድ የሲኖዶስ ጉባኤ የመንፈስ ቅዱስ መገኘት አልበቃው ብሎ ነው የመንግሥትን ተወካይ የሚጋብዘው? ‹ሱባኤ ይዘን፣ ጸሎት አድርገን፤ አንድ ገዳም ወርደን፣ ከእግዚአብሔር ጋር መክረን› አይደለም ይሉን አባቶቻችን፡፡ ‹የመንግሥትን ተወካይ ጋብዘን› ነው ያሉን፡፡ እንዲያውም ቀኖናው የሊቀ ጳጳሳቱ(ፓትርያርኩ) ጉዳይ ሲታይ ‹በመቀመጫቸው መካከል አንድ ወንበር አስቀምጠው፣ ቅዱስ ወንጌሉን በዚያ ላይ አኑረው፣ ሊቀ ጳጳሳቱ በፊታቸው ተቀምጦ፣ አንድነት ተነሥተው በሩን ዘግተው ይጸልዩ፤ የተሰበሰቡበትንም ጉዳይ በሥውር(በኅቡእ) ይመርምሩ› ነው የሚለው(ፍ.ነ. ዐ.168)፡፡ እንዴት ተደርጎ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የሚታየው? አግዚአብሔር ያየናል የሚለው ጠፍቶ ታዛቢ ቢያስፈልግ እንኳን የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ለታዛቢነት አይበቁም? ቅዱስ ጳውሎስ ‹በወንድሞች መካከል ሽማግሌ ሊሆን የሚችል አንድ አስተዋይ ሰው በእናንተ ዘንድ አይገኝምን?› (1ኛቆሮ. 6፣5) ያለው ለዚህ ጊዜ አይሆነንም?
በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝ መጋበዙ በአንድ በኩል የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዕልና የሚነካ በሌላ በኩልም ሕገ መንግሥቱን የሚጥስ፤ በመጨረሻም ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚያፈርስ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያለ ማንም ጣልቃ ገብነትና ታዛቢነት የራስዋን ጉዳዮች በራስዋ ሕግጋት፣ ቀኖናና ሥርዓት መሠረት የመወሰን መብት አላት፡፡ አባቶቻችን ከንጉሥ ሐርቤ ዘመን ጀምረው ከግብጽ ሲኖዶስ ጋር ሲሟገቱ የኖሩት ይህን ሉዐላዊነት ለቤተ ክርስቲያናቸው ለማስገኘት ነው፡፡ ጳጳሳትን ለማግኘት የግብጽ ሡልጣኖች መለማመጥ፣ የግብጽንም ፓትርያርኮች መለመን ሰልችቷቸው፡፡ ከግብጽ ቀድማ ክርስትናና የተቀበለች ሀገር፣ የራስዋን ጉዳይ ለመወሰን አለመቻሏ አስደናቂ ስለሆነባቸው፡፡ ከቤተ ክርስቲያንዋ ታላቅነትና ከሀገሪቱ ክብር ጋር ስላልተመጣጠነላቸው፡፡
ዛሬ ያ ሁሉ ተረስቶ መንግሥትን በገዛ ፈቃዳቸው ‹አንተ በመካከላችን ካልተገኘህ አንሰበሰብም› የሚሉ አባቶች መጡ፡፡ ቀደምት አበው ‹አንተ ከኛ ጋር ሁን› የሚሉት ፈጣሪያቸው ነበር፡፡ ዘመን ተቀየረ፡፡ በቀደመው ጊዜ ‹መንግሥት ለምን በጉዳያችን ውስጥ ይገባል?› ነበር ክርክሩ፡፡ ‹አሁን መንግሥት ከሌለ ይህንን አጀንዳ አናይም› የሚባልበት ዘመን ላይ ደረስን፡፡ የፓትርያርክ እንደራሴ ጉዳይ የሃይማኖት ጉዳይ ነው፡፡ እንደራሴውም የሚፈጽመው ሃይማኖታዊ ጉዳዮችን ነው፡፡ የሥልጣን ክልሉም በቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን ክልል ነው፡፡ ታድያ ለምንድን ነው መንግሥት ያስፈለገው? ይህንን ጥያቄ ፓትርያርኩ ጠይቀውት ይሆናል፡፡ እንደመከራከሪያ ቢያቀርቡት አይገርምም፤ ቢያሳዝንም፡፡ የምልዐተ ጉባኤው መቀበል ግን ሕመም ነው፡፡
መንግሥትስ ቢሆን ምን ብሎ ነው ተወካይ የሚልከው? ምናልባት ‹ጠሩኝ፣ ሄድኩ› ካላለ በቀር፡፡ ሕገ መንግሥታችን መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ እንደማይገባ በግልጽ እየደነገገ እንዴት አድርጎ ነው በቀኖናዊ ስብሰባ ላይ የሚገኘው? ውሳኔውንስ ከየትኞቹ የቀኖና መጻሕፍት ጋር ሊያገናዝብ ነው? በጉባኤው የሚኖረውስ ሚና ምን ሊሆን ነው? ምን ዓይነት ወኪልስ ነው የሚወክለው? በየትኛው ሥልጣንና ሕግ ነው የሚገኘው? የዚህ ዓይነቱ አሠራርስ መጨረሻው ምን ይሆናል? በጉባኤው ላይ የሚተላለፈው ውሳኔ የማን ውሳኔ ነው? ‹የእኛና መንፈስ ቅዱስ› ወይስ ‹የእኛና የመንግሥት›? መንግሥትም ጉዳዩን ሊያስብበት ይገባል፤ ‹ሲጠሩት አቤት› ሳይሆን ‹ሲጠሩት ለምን?› መሆን አለበት፡፡
የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ኤጲስ ቆጶስ በዚህ ዓለም መኳንንት ርዳታ አንዳይቆም ያዝዛል፡፡ በእምነቱና በእግዚአብሔር ቃል ብቻ እንዲጸና፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ 176፤ረስጠብ 21) በዲድስቅልያም ላይ ‹ከቤተ ክርስቲያን ሹሞች በቀር ሕዝባዊ አይፍረድ› ይላል (ዐንቀጽ 71)፡፡ ታድያ በምን ሕግ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤውን የሚያደርገው?
ዛሬ እንደዋዛ የሚከፈተው በር ነገ እንዝጋህ ቢሉት አስቸጋሪ ነው፡፡ አንድ አባት የመንግሥት ተወካይ ይገኝልኝ ባለ ቁጥር የሚፈቀድ ከሆነ፤ ነገ ደግሞ ወንድሜ ባለበት፤ እናቴ ባለችበት፤ ሐኪሜ ባለበት፣ ፖሊስ በተገኘበት ይሄ አጀንዳ ይታይ የሚል ነገር መስማታችን አይቀሬ ነው፡፡ ጋባዡም፤ ተጋባዡም ቆመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ መቼም እንደዘንድሮ የእንጦንስና ጳውሊ ራእይ በተግባር የታየበት ዘመን የለም፡፡
ሀገር አቀፉ የ12ኛ ክፍል ዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ተደረገ
(አዲስ ሚዲያ) ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሐሙስ ግንቦት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የነበረው ሀገር አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግቢያ የሆነው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተቋረጠ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር መገለጫውን በድረ-ገፁ እንዳስታወቀው ከሆነ፤ ብሔራዊ ፈተናው እንዲቋረጥ የተደረገበት ምክንያት ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ኮድ 14 የእንግሊዘኛ ፈተና በመውጣቱ ነው፡፡ ሚኒስተሩን አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በመስሪያ ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ሌሎች ፈተናዎች ላለመውጣታቸው ምንም ዓይነት ማረጋገጫ ባለመኖሩ ሁሉም ፈተናዎች እንዲቋረጡ መደረጉን በመጠቆም፤ ተማሪዎችን እና ወላጆቻቸውን ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡

ይሁን እንጂ እንዲቋረጥ የተደረገው የዚህ ዓመት የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ሌላ ፈተና በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚዘጋጅ ከመግለፅ ውጭ፤ መቼ ሊሰጥ እንደተወሰነ የተገለፀ ነገር የለም፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የፈተናውን መቋረጥ አስመልክቶ ዛሬ አራት ኪሎ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤ ፈተናው ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ለምን እና እንዴት ወጥቶ ሊሰራጭ እንደቻለ እና ለተፈጠረው ችግር ማን ኃላፊነት መውሰድ እንዳለበት ከመግለፅ ተቆጥቧል፡፡
ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ እንግሊዘኛ ኮድ 14 ከመፈተኛው ቀን አስቀድሞ ወጥቷል ቢሉም፤ በተመሳሳይ ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. የሂሳብ ትምህርት የተፈጥሮ ሳይንስ እና ማኀበራዊ ሳይንስ የሂሳብ ትምህርት ፈተናም በተመሳሳይ መልኩ ከነ መልሶቻቸው በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨታቸው ታውቋል፡፡ የአዲስ ሚዲያ ምንጮች ከሆነ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጀመር የነበረው ሁሉም የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተናዎች ግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም.በተለይ በኦሮሚያ ክልል ለወራት ትምህርታቸው የተስተጓጎለባቸው ተማሪዎችን ታሳቢ ሳያደርግ የፈተናውን መሰጠት በሚቃወሙና ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ከመፈተኛው ቀናት አስቀድሞ ፈተናውን አዘጋጅቶ ከሚያሰራጨው ትምህርት ሚኒስቴር፤ ሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ ቢሮ እንደወጣ ጠቁመዋል፡፡

በተመሳሳይም ባለፈው ሳምንት የተሰጠው የ10ኛ ክፍል ፈተናም እንደ 12ኛ ክፍሉ ባይሆንም አስቀድሞ መውጣቱና በተወሰነ መልኩ መሰራጨቱ ቢገለፅም፤ እንደ 12ኛ ክፍል ፈተና በማኀበራዊ ሚዲያ ባለመሰራጨቱ እና በገለልተኛ አካል ይፋ ባይገለፅም፤ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ግን የ10ኛ ክፍል ፈተናም ወጥቶ መሰራጨቱን አስተባብለዋል፡፡ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ከዛሬው መግለጫና የወጣው ፈተናው በማኀበራዊ ሚዲያ ከመሰራጨቱ በፊት ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን በኢቢሲ ዜና እወጃ “ፈተናው ተሰርቆ ወጥቷል የሚባለው መረጃ ሐሰት ነው፤ ስለዚህ ተማሪዎች ለዛሬው ፈተና ተረጋግተው እንዲዘጋጁ” የሚል ማሳሰቢያ መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡
ለፈተናው ቀድሞ መውጣትና በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨት ዋነኛ ምክንያት፤ ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለ5 ተከታታይ ወራት የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን አዲሱ የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ተቃውሞ በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ ክልል የወሰደውን የኃይል እርምጃ ተከትሎ በተፈጠረ አለመረጋጋት ፈተናው እንዲራዘም የቀረበው የተማሪዎቹና የወላጆቻቸው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ የተወሰደ የአፀፋ እርምጃ እንደሆነ ፈተናውን ካሰራጩት አካላት ለማወቅ ተችሏል፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ወጥቶ የተሰራጨበትም ሆነ ፈተናው በሀገር አቀፍ ደረጃ ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ሲደረግ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የሽብርተኝነት ክስ ተመሰረተበት
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው ክስ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡
በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የዕንቁ መፅሔት አምደኛ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ፣ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መስራች አባልና የጊዜያዊ አስተባባሪው አመራር እንዲሁም አዲስ ሚዲያ ተባባሪ እና በራሱ የማኀበራዊ ገፅ ብሎገር እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- EHRP.
የብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ሃላፊ አቶ ኢሳይያስ ወልደ ጊዮርጊስ ከስልጣናቸው ተባረሩ
ባሌቤታቸውም ከስራቸው የተነሱ ሲሆን፡ ሁለቱም በጸጥታ ሃይሎች ክትትል ውስጥ ይገኛሉ። በአቶ ኢሳይያስ ምትክ በደርግ ዘመን የደርግ ደህንነት የነበሩት ሃደራ አበራ ተክተዋቸዋል።

ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ቅርብ የነበሩት አቶ ኢሳይያስ ወልደጊዮርጊስ መባረራቸውን ተከትሎ በሌሎች ሃላፊዎችም ሆነ ሰራተኞች ላይ ስለተወሰደ ርምጃ የታወቀ ነገር የለም።
ወ/ሮ አዜብ መስፍን ግን የአቶ ኢሳይያስን ስንብት ተከትሎ ባለፈው ቅዳሜ አሜሪካ ገብተዋል፡ ዋሺንግተን ዳላስ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ካሜራ ዕይታ ውስጥ የገቡት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ከአንድ ልጃቸው ጋር ሰለመጡብት ምክንያት በውል የታወቀ ነገር የለም።
ምንጭ፡- ኢሳት
በቦሌ ወረገኑ በሕገወጥ ግንባታ ምክንያት ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ጉዳት ደረሰ
ታምሩ ጽጌ
‹‹መንግሥት ያለምንም ርህራሔ በክረምት ጐዳና ላይ በተነን›› ቤት የፈረሰባቸው ነዋሪዎች
‹‹መንግሥት ዜጎቹን በማክበር ሕገወጥ ተግባራትን ይከላከላል›› የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

በአዲስ አበባ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ቦሌ ቡልቡላ ወረገኑ በመባል በሚታወቀውና በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች እንደሚገኙበት በተገለጸው ሥፍራ፣ ከሕገወጥ ግንባታ ጋር በተገናኘ ረቡዕ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ተጠቆመ፡፡
በአካባቢው ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ ያለምሪት ቤት የሠሩ ቁጥራቸው በርካታ (ከ20 ሺሕ በላይ መሆናቸውን ይገልጻሉ) የሚሆኑ ነዋሪዎች የሚገኙ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 12 አስተዳደር የገነባቸው ቤቶች ሕገወጥ መሆናቸውን በመግለጽ በተደጋጋሚ እንዲያፈርሱ ቢነግራቸውም፣ ‹‹ወዴት እንሂድ? በድህነት አቅማችን የሠራነውን ቤት ግምት ወጥቶለትና ካርታ ተሠርቶለት ሕጋዊ እንሁን፤›› በማለት ሲከራከሩ መክረማቸውን ነዋሪዎቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
በአስተዳደሩና በነዋሪዎቹ መካከል መግባባት ሳይፈጠር ቆይቶ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች የታጀበው የወረዳው አፍራሽ ግብረ ኃይል ወደ ነዋሪዎቹ መንደር በመሄዱ፣ ከነዋሪዎቹ ተቃውሞ እንደገጠመው ተገልጿል፡፡
ነዋሪዎች አንድ ላይ በመሆን በድህነት ያቋቋሙት ጎጆ መፍረስ እንደሌለበት በመግለጽ ለመከላከል ባደረጉት እንቅስቃሴ፣ ከፀጥታ አስከባሪዎች ጋር ወደ ከረረ ግጭት በመግባታቸው ሁለቱም ወገኖች መጐዳዳታቸውን የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በወቅቱ በርካታ ጥይት የተተኮሰ በመሆኑ ቁጥራቸው ያልተገለጹ ሰዎች እንደሞቱ የተነገረ ቢሆንም፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ግን አንድም የሞተ ሰው እንደሌለ አስታውቋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አሰግድ ጌታቸው እንደተናገሩት፣ በሕገወጥ መንገድ የተገነቡ 1,040 ቤቶች አሉ፡፡ ሕገወጥ በመሆናቸው እንዲፈርሱ ተደርጓል፡፡ ቤቶቹ ሲፈርሱ በአካባቢው ግርግር ለመፍጠር የሞከሩ የነበሩ ቢሆንም፣ ነገር ግን አንድም ሰው የሞተ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡
የአካባቢው ነዋሪዎችም በወቅቱ አስለቃሽ ጭስ በመርጨት የነበረውን ግርግር ለመበተን ጥረት ሲደረግ ማየታቸውን፣ የጥይት ድምፅ እንደነበርና በርከት ያሉ አምቡላንሶች ሲመላለሱ በማየታቸው፣ የሞተ ሰው ሊኖር እንደሚችል ከመገመት ባለፈ የሞተ ሰው አለማየታቸውን ተናግረዋል፡፡
ነዋሪዎቹ ጨምረው እንዳስረዱት፣ ወረዳው ሰብስቧቸው በአካባቢው ረጅም ዓመታት ለቆዩ አርሶ አደሮች ምትክ ቦታና ካሳ እንደሚሰጥ ገልጾ፣ ሌሎች ነዋሪዎች ግን በቅርቡ የመጡና በሕገወጥ መንገድ የገነቡ በመሆናቸው እንዲያፈርሱ አስጠንቅቆ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ክረምት እየገባ በመሆኑና በድህነት የቀለሷትን ጎጆ አፍርሰው የት እንደሚሄዱ ግራ በመጋባታቸው፣ መንግሥትን ለመለመን በመዘጋጀት ላይ እያሉ ባላሰቡት ቀን መጥቶ ከነንብረታቸው በግሬደር እንዳረሰባቸው ተናግረዋል፡፡
‹‹እኛ ኃይል የለንም፣ ኃይል የእግዚአብሔር ነው፣ ዜጎቹን የመንከባከብና የማስተዳደር ኃላፊነትና ግዴታ ያለበት መንግሥት በጎዳና ላይ ከበተነን እኛ ኢትዮጵያውያን ነን?›› በማለት ጠይቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የተፈጸመባቸውን በደል አይቶ ብይን እንዲሰጣቸውም ጠይቀዋል፡፡
በአካባቢው የሚገኙ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውንና ልጆቻቸውም ትምህርት ማቆማቸውን ጠቁመው፣ ‹‹የትምህርት ዘመኑ እስኪጠናቀቅና መጪው ክረምት እስከሚወጣ ቢታገሱን ምን ችግር ነበረው?›› በማለትም የተፈጠረባቸውን ሐዘን ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ1988 ዓ.ም. እስከ 1997 ዓ.ም. ግንቦት ወር ድረስ፣ በሕገወጥ መንገድ ቤት ለሠሩ ሰነድ አልባ ቦታዎች ካርታ ሠርቶ በመስጠት ሕጋዊ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ከግንቦት ወር 1997 ዓ.ም. ወዲህ የተያዙ ሕገወጥ ግንባታዎች ግን ሕገወጥ ይዞታዎች መሆናቸውን በማስታወቅ፣ ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑንም አስተዳደሩ ይናገራል፡፡
በቦሌ ወረዳ 12 ወረገኑ በሚባለው አካባቢ ስለተሠሩት ቤቶች የአስተዳደሩ መሬት ልማት ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ኃይሌ እንደገለጹት፣ ግንባታዎቹ ከ2004 ዓ.ም. ወዲህ የተገነቡና ሕገወጥ ይዞታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም አስተዳደሩ በሕገወጥ ይዞታዎች ላይ የማያወላውል ዕርምጃ እንደሚወስድ ተናግረው፣ በወረገኑ የተወሰደው ዕርምጃም ከዚህ የተለየ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ