Category Archives: Social and Culture

የእኔና አየር መንገዳችን ክርክር – የኢ-ፍትሓዊነት ማሳያ?!

በአቤል ዋበላ

Abel-Wabella

ያኔ ይደብረኝ ነበር፡፡ መሥሪያ ቤቱ ይደብረኛል፡፡ አለቆቼ ይደብሩኛል፤ የሚጠገ’ኑት አውሮጵላኖች ሽታ ይደብረኛል፡፡ አቧራ የጠገቡት የጥገና መሳሪያዎቼ ይደብሩኛል፡፡ ለምን ይህንን ስህተት ሠራሁ እያልኩኝ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡ ለምን በኮሌጅ የተማርኩትን የመሀንዲስነት ሙያ ትቼ ስለምን የአውሮጵላን ጥገና ሙያ ውስጥ ገባሁኝ እያልኩኝ ራሴን እጠይቃለው፡፡ ከኮሌጅ እንደወጣሁኝ ሥራ የጀመርኩት በቢሾፍቱ ከተማ ነበር፡፡ በኋላ ደግሞ የተወሰኑ ወራት ጫንጮ የሚገኝ ሲሚንቶ ፋብሪካ ሠርቻለው፡፡ ጥግ ጥግ ከመዞር ገላግሎ አዲስ አበባን እንድከትምባት ዕድሉን ያመቻቸልኝ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው፡፡ያኔ የትውልድ ከተማዬ ውስጥ፣ አዲስ አበባ መሆን እፈልግ ነበር፡፡ አራት ኪሎ ከቤተ መንግሥቱም፣ ከቤተ ክህነቱም መራቅ አልፈልግም ነበር፡፡ ምክንያቴ ደግሞ የማወቅ የመማር ነበር፡፡ ጫንጮ ብርዳማ ናት፡፡ እንደ አየር ንብረቷ የዐሳብ ገበያዋም ለእኔ ፍላጎት የሚያመረቃ አልነበረም፡፡ በወቅቱ በስስት የምትነበበውን አዲስ ነገር ጋዜጣን ለማግኘት እንኳን ወደ መዲናዋ የሚመላለሱ ሹፌሮችን መለማመጥ ግዴታዬ ነበር፡፡

ህወሓት መራሹ ስርዓት እንዳይሆን-እንዳይሆን ካደረጋቸው ነገሮች አንዱ የሀገሪቱ ኢንዱስትሪ ነው፡፡ የዚህ የተሳከረ ፖሊሲ ግንባር ቀደም ሰለባ ከሆኑት መካከል የቴክኖሎጂ ተማሪዎች ይገኙበታል፡፡ የሀገሪቱ ኢንዱስትሪዎች የተማረ የሰው ኃይል ፍላጎት መጠንና ዓይነት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ በገፍ ከሚያስመርቁት ተማሪ ጋር ሊጣጣም ባለመቻሉ በቴክኖሎጂ ምሩቃን እና ቀጣሪዎቻቸው መካከል የተዛባ ግንኙነት በግልጽ ይታያል፡፡ ከተማሪዎች መካከል በኮሌጅ በብዙ ትጋት የቀሰሙትን ወደ ንድፈ ሐሳብ የሚያደላ ትምህርት በተግባር የሚያውሉበት ዕድል የሚያገኙት እጅግ ጥቂቶች ብቻ ናቸው፡፡ አብዛኛው ግን የዕለት እንጀራውን ለማብሰል በተገኘው የሥራ መስክ መሰማራት ዕድል ፈንታው ነው፡፡ አንዳንድ ቀጣሪዎች ይህንን ዕድል ተጠቅመው ለሥራ መደቡ ከሚያስፈልገው በላይ የሰለጠነ (overqualified) ምሩቅን በዝቅተኛ ክፍያ ይቀጥራሉ፡፡ ‘ስለአፈር እና ድንጋይ ምንነት አጥንተው በሲቪል ምህንድስና የተመረቁ ልጆች ኮብል ስቶን ለመጥረብ መርቴሎ ጨበጡ’ ተብሎ በከተማው መነጋገሪያ ከመሆኑ በፊት ብዙ ምሩቃን ከሠለጠኑበት የቴክኖሎጂ ዕውቀት እጅግ በጣም ጥቂቱን ብቻ በሚሻ የሥራ መደብ ተሰማርተው ነበር፡፡ ከነዚህ overqualified የሆኑ ምሩቃንን ባልተገባ መልኩ ከሚቀጥሩ ድርጅቶች መካከል የኢትዮጵያ አየር መንገድ ይገኝበታል፡፡ አየር መንገዱ በርካታ ባለዲግሪዎችን ከቴክኒክና ሙያ ተቋማት ብቻ በሚገኝ ዕውቀት በሚሠሩ የሥራ መደቦች ላይ ቀጥሮ ያሠራ ነበር፡፡ አሁንም ይህ ተቀይሯል ብዬ አልገምትም፡፡
እኔም አዲስ አበባ መሆንን አጥብቄ ፈለግሁኝ፡፡ማስታወቂያ ሲወጣ ጠብቄ አመለከትኩኝ፡፡ አየር መንገዱም ወግ ወጉን ይችልበታል፡፡ የጽሑፍ፣ የቃልና የህክምና የመሳሰሉ ፈተናዎችን አሳልፎ የአውሮጵላን ጥገና ማሰልጠኛ ትምህርት ቤቱን እንድቀላቀል ፈቀደልኝ፡፡ በትምህርት ቤቱ የሚሰጠውን የዐሥራ አንድ ወራት ሥልጠና ተከታትዬ አየር መንገዱን ለሰባት ዓመታት እንዳገለግል ይህን ባልፈጽም ግን ከሰባ ሺሕ በጥቂቱ ከፍ የሚል የኢትዮጵያ ብር ለመክፈል ተስማምቼ ፈረምኩኝ፡፡ ሥልጠናው ተጀመረ፡፡ ሁሉም ነገር የዓይን አዋጅ፤ ጽዱው የትምህርት ቤቱ ግቢ፣ የደንብ ልብስ ለብሰው አጀብ ሠርተው የሚጓዙ ተማሪዎች፣ ቆነጃጅቱ እጩ የበረራ አስተናጋጆች . . . ምኑ ይወራል ሁሉም ነገር አዲስ ሆነብኝ፡፡ ስለትምህርት ቤቱና አየር መንገዱ ገለጻ ተደረገልን፡፡ ዎርልድ ክላስ ኩባንያ እንደተቀላቀልን ተደሰኮረልን፡፡ ጀብድ የሚወደው ልቤ የምር ነገር የተገኘ መስሎት ቋመጠ፡፡ ትምህርት/ሥልጠና ተጀመረ፡፡
Deserve
በሥልጠናው የመጀመሪያ ሁለት ሳምንታት የተማርነው አንድ ክብደት ያለውን ነገር ከመሬት ከፍ በማድረግ አየር ላይ ማንቀሳቀስና መቆጣጠር እንዴት እንደሚቻል የሚያስረዳው የኤሮዳይናሚክስ (aerodynamics) ትምህርት ነበር፡፡ በጣም የሚያስደስትና የሰው ልጅን አእምሮ ምጥቀት እንድናደንቅ የሚያስገድድ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ የወሰድናቸው ትምህርቶች ግን የኔን ቀልብ የሚስቡ ሆነው አልተገኙም፡፡ በአብዛኛው ከጥገና ጋር የተያያዙ መሰረታዊ ዕወቀቶችን የሚያስጨብጡ ተደጋጋሚና ውስብስብነት የሌላቸው ነበሩ፡፡ ይህ ደግሞ አስቸጋሪ የምህንድስና ችግሮችን ከነመፍትሔዎቻቸው ለቃረመ አእምሮ እዚህ ግባ የሚባል አልነበረም፡፡ ከእኔ ጋር አቪየሽን ትምህርት ቤት ከነበሩ ሀያ አምስት ተማሪዎች መካከል ካልተዘነጋኝ ሀያ ሶስቱ በሀገሪቱ ውስጥ ከሚገኙ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በምህንድስና የተመረቁ በመሆናቸው ስለጥገናው ትምህርት ያላቸው ግንዛቤ ከኔ ብዙም የሚርቅ አልነበረም፡፡ ከአንዳንድ እድሜያቸው ከገፋ መምህራን በስተቀር መምህራኑ የኛን ሥነ ልቦና ስለሚረዱ ብዙም አላስጨነቁንም፡፡ እኛም ጥሩ ታዛቢዎች ነበርን፡፡ ዳግም ሥራ ፍለጋ መውጣትን በመስጋት የትምህርት ቤቱ መምህራንና አስተዳደርን ላለማስቆጣት ተጠንቅቄ በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ባልገኝም ትምህሩቱን አጠናቅቄ በአውሮጵላን ስትራክቸር ጥገና ክፍል ተመድብኩኝ፡፡
ወደሥራ ገበታ ስሄድ በሁለት ጉዳዮች ላይ የራሴን ግምት ወስጄ ነበር፡፡ ከመጀመሪያውና ልክ ከሆነው ግምቴ ልጀምር፡፡ ከልጅነት ጀምሮ መጽሐፍ ከማንበብና ኳስ ከመጫወት በዘለለ የአካልና የአእምሮ ቅልጥፍናን በሚጠይቁ ሥራዎች ደካማ ነበርኩኝ፡፡ እናታችንን በመርዳት የቤት ወስጥ ሥራዎች የሚያከናውኑት ታላላቅ እህቶቼ ነበሩ፡፡ አሁን ሳስበው በሚያሳፍረኝ ሁኔታ ያኔ ግቢያችን የቧንቧ ውሃ በሌለበት ጊዜ ከቦኖ ውሃ በባሊ ሲቀዱ እንኳ አላግዛቸውም ነበር፡፡ ስለዚህ ይህ የአውሮጵላን ጥገና ባለሙያነት አካላዊ ብቃትና ዲሲፕሊን እንዲኖረኝ ያደርገኛል ብዬ አስብ ነበር፡፡ ይህ ግምቴ ልክ ነበር፡፡ በብዙ መልኩ ተለውጫለው፡፡ በትዕግስት መካኒካል ችግሮችን የመፍታት ክህሎት አዳብሪያለሁ፡፡ ምን አልባት አንድ ባለሙያ የሆነ ሰው አሁን ነገሮች የምሠራበት አኳኋን ላይጥመው ይችላል፡፡ እኔ ግን የነበርኩበትን አውቃለውና በአሁኑ ቅልጥፍናዬ ደስተኛ ነኝ፡፡
ሁለተኛው ግምቴ የሥራው ከባቢ ባለሙያነት የሚበከበርበትና ከስልጠናው ደግሞ የተሻለ ሳቢ ይሆናል የሚል ግምት ነበረኝ፡፡ ይህ ግምቴ ፈጽሞ ከእውነታው እጅግ የራቀ ነበር፡፡ በአለቆችና የበታች ሠራተኞች መሐል ያለው ግንኙነት ያለሁት ያ ስመ ገናናው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው ወይስ ሌላ ቦታ ያሰኛል፡፡ ይህን ጤናማ ያልሆነ የሥራ ግንኙነት ተከትሎ ሠራተኛውም በሥራው የሚለግም፣ አለቆቹን ሲያይ ብቻ ሠራተኛ ለመምሰል የሚሞክር ሀሜተኛና ብሶት የሚያበዛ ነው፡፡ አለቆቹም ከበታች ሠራተኛ የተሻለ ስብዕና ስለሌላቸው ጎበዝ ሠራተኛን ሳይሆን ወሬ የሚያቀብልን የሚወዱ፣ በጥቅማጥቅም እየደለሉ የራሳቸውን አንጃ የሚያደራጁ፣ ሰራተኛ የተመቸው ሲመስላቸው የሚከፋቸው፣ ትልቅ የሚመስሉ ነገር ግን የህጻናት ተግባር ሲፈጽሙ የሚገኙ ናቸው፡፡ በእርግጥ ይህ ገለጻ የማይመለከታቸው ጥቂት ደህና ሰዎችን እንዳያሰከፋብኝ እሰጋለሁ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሰዎች በዚያ ስፍራ ጥሩ ለመሆን ሲሞክሩ ከእኔ በላይ ችግር ገጥሟቸዋል ብዬ ስለማምን መግለጽ የፈለግኹትን ዐሳብ ይርረዱኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለው፡፡ በዚህ በተበከለ የሥራ ከባቢ ከሠለጠኑበት የሙያ ዘርፍ ያነሰ ብዙ የአእምሮ ጉልበት የማይጠይቅ ሥራን መከወን ከባድና ስለ አስቸጋሪነቱ የሥነ ልቦና ባለሙያዎች የሚስማቡበት ነው፡፡ ይህ ሁኔታ አብዮተኛው ልቤን ምቾት ሊሰጠው አልቻለም፡፡ ይህን ቅሬታዬን በአንድ በዲፓርትመንት ደረጃ በተደረገ ስብሰባ ላይ አነሳኹት፡፡በዚያ ቀን በአለቆቼ ጥርስ ውስጥ ገባሁኝ፡፡ በቅንነት መሥሪያ ቤቱን ሀገራችንን የምናገለግልበት፣ ለብዙ ዓመት በሥራ ላይ ከነበሩ አንጋፋ ሠራተኞች ልምድ የምንቀስምበትና የምንማርበት፣ እኛም የምንጠቀምበት ምቹ ስፍራ እናድርገው ባልኩኝ ጠላት አፈራኹኝ፡፡ ከዚያ እኔም ደበረኝ ከአየር መንገዱም ጋር ሆድና ጀርባ ሆንን፡፡ አየር መንገድ ትቼ የምወጣበትን ቀን መናፈቅ ጀመርኩኝ፡፡
በዚህ በደበረኝ ወቅት ነበር አየር መንገዱ ሥራ ላይ ለሚገኙ ሠራተኞቹ ከዘመኑ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ ጋር በየጊዜው እንዲተዋወቁ (Recurrent) ሲል ያዘጋጀውን ሥልጠና እንድወስድ የታዘዝኩት፡፡ አለቆቼ ለእኔ አስበው ሳይሆን የፎርማሊቲ ጉዳይ ሆኖባቸው ይህንን ሥልጠና እንድከታተል ፈቀዱ፡፡ እኔም ከዚያ ከማልወደው የሥራ አከባቢ ገለል ማለትን ፈልጌ ስለነበር በደስታ ወደ ሥልጠናው አመራኹኝ፡፡ በሥልጠናው ከዚህ በፊት እንዳሠለጠኑኝ መምህራን ከዚህ በፊት የማውቀውን ነገር በተሰላቸ መንገድ የሚደግም ሰው አልገጠመኝም፡፡ ሰውየው ዓለም ዐቀፍ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ በሚገባ የተረዳ ነው፡፡ በዚህ ውድድር በበዛበት መድረክ አየር መንገዱ ውጤታማ እንዲሆን እያንዳንዱ ሠራተኛ በተመደበበት የሥራ መደብ ምን እንደሚጠበቅበት በመተንተን ያስረዳል፡፡ የኢንዱስትሪውን ፓለቲካ፣ የተቆጣጣሪ ድርጅቶችን ጸባይ፣ እንደ አይካዎ ያሉ አለም አቀፍ የአቪዬሽን ማኅበራት ፍላጎቶች፣ አየር መንገዱ ያሉበትን ተግዳሮቶች፣ ኢንዱስትሪው በዘመኑ የደረሰበትን ዕውቀት በከፍታ(experts with excellence)የሚያውቁ ሠራተኞች እንዴት ለአየር መንገዱ ጉልበት እንደሚሆኑ ነገር ግን አየር መንገዳችን የነጠረ (refine) ዕውቀት ያላቸው ባለሙያዎች እጥረት እንዳለበት ተጨባጭ በሆነ መልኩ አስረዳን፡፡ ያን ጊዜ ከእንቅልፌ እንደመባነን አልኩኝ፡፡ ተዳፍኖ የነበረውን ሀገሬን በባለሙያነት የማገልገል ስሜቴን ቆሰቆሰው፡፡ ወደቢሮው ሄጄ ላመሰግነው ብቋምጥም አየር መንገዱን ከተቀላቀልኩኝ ጀምሮ ያዳበርኩት የባይተዋርነት ስሜት ቀፍድዶ ያዘኝ፡፡ ለራሴ ግን ያለሁበትን ሁኔታ ለመቀየር ቃል ገባኹኝ፡፡
የምህንድስና ክፍል ክፍት የሥራ ቦታ ሲያወጣ ተወዳድሬ ለማለፍ በቦሌም በባሌም መንገድ ጥረት አደረግኹኝ፡፡ ዕድል ዘግይታም ቢሆን ከእኔ ጋር ሆነች፡፡ አስፈላጊውን ፈተና እና ቃለ መጠይቅ በማለፌ በአየር መንገዱ የአውሮጵላን ጥገና እና ዕድሳት ክፍል የጥገና መሳሪያዎች አስተዳደር እና ምህንድስና ክፍል በመሀንዲስት እንዳገለግል ተመደብኩኝ፡፡ በአጋጣሚ የቅርብ አለቃዬም የሚሠራውን የሚያውቅ፣ ትጉሕና የሚመራው ክፍል የሚጠበቅበትን ሚና በአግባቡ የተረዳ ነበር፡፡በርካታ ሥራዎችን ለመከወን ዕቅድ ያዝን፡፡ እኔም ለመጀመሪያ ጊዜ ቢሮዬ ይናፍቀኝ ጀመር፡፡ ጠዋት ቀድሞ መግባት፣ ማታ ደግሞ አርፍዶ መውጣት እና በእረፍት ቀኔም ወደቢሮ መሄድ ልማዴ ሆነ፡፡ የተወሰኑ ወራት ደስ ብሎኝ ሠራሁ፡፡ አለቃዬም ስገምት በሥራችን ከሞላ ጎደል ደስተኛ የነበረ ይመስለኛል፡፡
በዕለተ ዓርብ ሚያዝያ 17/2006 ዓ.ም. ከ ቀኑ 10፡30 አከባቢ ነው፡፡ የተለመደ ሥራዬን ለማከናወን ኮምፒዩተሬ ላይ አፍጥጫለው፡፡ የመሥሪያ ቤቱ ደኅንነት ከሁለት የማላውቃቸው ሰዎች ጋር ወደቢሮ ገብተው “አቤል ዋበላ . . . አንዴ ውጭ ፈልገንህ ነው” ሲሉ ጠሩኝ፡፡ ሕገ-መንግሥቱን እና ሕገ-መንገሥታዊ ስርዓቱን በኃይል ለማፍረስ በመሞከር ተጠርጥሬ በፌደራል ፓሊስ ቁጥጥር ስር መዋሌ ነው፡፡ ዞን ዘጠኝ ላይ ከሚጽፉ አምስት ጦማሪዎች እና ሌሎች ሦስት ጋዜጠኞች ጋር በአባሪነት የፌደራል ወንጀል ምርመራ ዘርፍ (ማዕከላዊ) ገባን፡፡ በሂደት ፓሊስ ጥርጣሬውን ወደ ሽብር አሳደገው፡፡ ጭራሽ ይግረማችሁ ብሎ በፌደራል ዐቃቤ ሕግ ታግዞ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ክስ መሠረተ፡፡ ክሱ እንኳን ለዳኞቹ እና ለእኛ ለተከሳሾቹ አይደለም ለራሱ ለዐቃቢ ሕጉም የሚገባ ስላልሆነ በጠበቆቻችን አማካኝነት የክስ መቃወሚያችንን አቀረብን፡፡ ዳኞቹ ፈራ ተባ እያሉ የተወሰነ ነጥቦች ብቻ እንዲያስተካከል አድርገው አሻሽል ያሉት ነጥብ ሳይሻሻል ክሱ እንዲቀጥል ወሰኑ፡፡ እኛም በፀረ-ሽብር አዋጁ አንቀጽ ፫/፪ “የኅብረተሰቡን ወይም የኅብረተሰቡን ክፍል ደኅንነት ወይም ጤና ለከፍተኛ አደጋ” ለማጋለጥ “በመሞከር፣ በማሴር፣ በማነሳሳት” በሚል ተከሰን ፍርዳችንን መጠባበቅ ያዝን፡፡ ከዚያም ዐቃቤ ህግም አስቂኝ የሆነውን የሰውና የሰነድ ማስረጃውን አቀረበ፡፡ ይህ ሂደት አንድ ዓመት ከስድስት ወር ገደማ ፈጅቶ ጥቅምት 05/2008 ዓ.ም. መከላከል ሳያስፈልገን በነጻ ተለቀቅን፡፡
ከፍርድ ቤት በቀጥታ ለአየር መንገዱ የተጻፈ በነጻ መለቀቄን የሚገልጽ ማስረጃ ጥቅምት 10/2008 ዓ.ም. ተቀብዬ ድርጅቱ በነጻ መሰናበቴን ተመልክቶ ወደ ሥራ እንዲመልሰኝ ጥቅምት 15/2008 ዓ.ም. አመለከትኩኝ፡፡ ውሳኔ ላይ አልደረስንም በሚል ሲያመላልሱኝ ከቆዩ በኋላ ሕዳር 16/2007 ዓ.ም. ከዓመት በፊት በኖቨምበር 4/2015(ጥቅምት 25/2007 ዓ.ም.) የተጻፈ ከሥራ መታገዴን የሚገልጽ የስንብት ደብዳቤ ሰጡኝ፡፡ ደብዳቤው የሥራ ውሌ እንዲቋረጥ ምክንያት የሆነው ለስድስት እና ከዚያ በላይ ለተከታታይ ወራት በእስር ምክንያት ከሥራ ገበታዬ መቅረት መሆኑን ጠቅሶ ይህ ከሆነ ደግሞ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እና የኢ.አ.መ. መሠረታዊ የሠራተኞች ማኅበር 10ኛ የኅብረት ስምምነት አባሪ 1 ክፍል አንድ ተ.ቁ 6(111) እና የአሠሪ እና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377(2003) አንቀጽ 27(1)(ተ) አንድ ላይ በመሆን የሥራ ቅጥር ውል ወዲያው እንዲቋረጥ ያደርጋል ይላል፡፡
በሕግ ከኅብረት ሥምምነቶች በላይ ተቀባይነት ያለው የአሠሪ እና ሠራተኛ አዋጅ አንቀጽ ፳፯ ያለማስጠንቀቂያ የሥራ ውል ስለማቋረጥ በቁጥር (፩) “በኅብረት ስምምነት ካልተጠቀሰ በሌላ አኳኋን ካልተወሰነ በስተቀር የሥራ ውልን ያለማስጠንቀቂያ ማቋረጥ የሚቻለው በሚከተሉት ሁኔታዎች ብቻ ነው፡፡” ይልና ከፊደል ተራ ሀ-ቀ ከእስራት ጋር ያልተያያዙ የሥራ ውልን የሚያቋርጡ ሕገ-ወጥ ድርጊቶችን ይዘረዝራል፡፡ በፊደል ተራ (በ) ደግሞ “በሠራተኛው ላይ ፴ ቀናት ለሚበልጥ ጊዜ የእስራት ፍርድ ተወስኖበት ከሥራ ሲቀር” ይላል፡፡ እኔ በሕግ አንድም ቀን እንድታሰር ‹የጥፋተኝነት ብይን› ስላልተላለፈብኝ አይመለከተኝም፡፡ በድርጅቱ የተጠቀሰው በፊደል ተራ (ተ) “ያለማስጠንቀቂያ የሥራ ውል ለማቋረጥ ያስችላሉ ተብለው በኅብረት ስምምነት የተወሰኑ ሌሎች ጥፋቶች መፈጸም” የሚለው ነው፡፡ በዚህ መሠረት አዋጁ ሥልጣኑን ለኅብረት ስምምነቱ ስለሚሰጥ ያንን መመልከቱ አስፈላጊ ነው፡፡
የኅብረት ስምምነቱ አባሪ 1 ክፍል አንድ “ያለማስጠንቀቂያ ከሥራ የሚያሰናብቱ ከፍተኛ የሥነ-ስርዓት ግድፈቶች/ጥፋቶች እና የሥነ-ስርዓት እርምጃዎች” ይልና ከ ተ.ቁ 1-30 ያሉ ከወሲብ ትንኮሳ አንስቶ በድርጅቱ ቅጽር ግቢ ውስጥ ጠብና አምባጓሮ እስከመጫር የሚደርሱ የጥፋት ዓይነቶችን ይዘረዝራል፡፡እኔን የሚመለከተው 6(111) “ወንጀል ፈጽሞ የ6 ወር እስራት ወይም ከዚያ በላይ እስራት ተፈርዶበት በፍርዱ መሠረት የሚታሰር መሆኑ ሲታወቅ ወይም በማንኛውም ምክንያት ሳይፈረድበት 6 ወር ወይም ከዚያ በላይ ታስሮ የቆየ ” የሚለው ነው፡፡ እዚህ ጋር ነው እንግዲህ ሕገ-መንግሥታዊ መብቴ የተጣሰው፡፡ አዋጁ ለኅብረት ስምምነቱ ሥልጣን ቢሰጥም አሠሪዎች የሠራተኛ ማኅበራትን እየጠመዘዙ የዜጎችን ሕገ-መንግሥታዊ መብት በሚጥስ መልኩ የፈለጉትን ነገር በኅብረት ስምምነት እያሰፈሩ ሠራተኛውን እንዲድበሉ አይፈቅድም፡፡ የኅብረት ስምምነቱ ሕገ-መንግሥቱንና ሌሎች የሀገሪቱን ሕጎች የማይጥስ፣ በመንፈሱ ፍትሓዊ ሊሆን ይገባዋል፡፡ በሕገ-መንግሥቱ በግልጽ አንድ ሰው በፍርድ ቤት እስካልተወሰነበት ድረስ እንደ ነጻ ሰው እንደሚቆጠር በአንቀጽ 20 ላይ ሰፍሯል፡፡ በመጠ’ርጠሬ ምክንያት ብቻ የሥራ ውሌን ማቋረጥ ሕገ-መንግሥታዊ ታዛዥነትን ያፈረሰ ነው፡፡ ‹በማንኛውም ምክንያት ሳይፈረድበት 6 ወር እና ከዚያ በላይ የቆየ› የሚለው የሀገራችንን የፍርድ ቤቶች ‹ፍትሕን ከሰጡ አዘግይተው የመስጠት› ተጨባጭ ሁኔታ ያላገናዘበ ነው፡፡
ይህንን የመብት ጥሰት ከሕግ ባለሙያው አመሐ መኮንን ጋር ተማክሬ ሕዳር 24/2008 ዓ.ም. በፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ደረጃ ፍ/ቤት ቦሌ ምድብ ሥራ ክርክር ችሎት ወደ ሥር እንድመለስ ወይም ድርጅቱ ወደሥራ የምልመለስበት በቂ ምክንያት አለ ሚባል ከሆነ ከሕግ ውጭ ለተቋረጠው የሥራ ውል በሕጉ መሠረት አስፈላጊውን ክፍያ እንዲፈጽም በመጠየቅ ክስ መስርቻለሁ፡፡ ይህን ክሴን ተከትሎ መሥሪያ ቤቱ በደረሰው መጥሪያ መሠረት በታኅሣሥ 22/2008 ዓ.ም. የጽሑፍ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በዚህ መልሱም የሌባ ዓይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ እንዲሉ ድርጅቱ ስህተቱን ለማረም ዝግጁነት እንደሌለው አሳይቷል፡፡ የሚገርመው በማይመለከተው ጉዳይ ላይ በመግባት የፌደራል ዐቃቤ ሕግ በእኔ እና ጓደኞቼ በጠቅላይ ፍርድ ቤት የጠየቀውን ይግባኝ በማንሳት ከሳሽ ገና ለገና ተከሳሽ በድጋሚ ሊታሰር ይችላል በሚል ወደ ሥራ ልመልሰው ልገደድ አይገባኝም ብሏል፡፡ ሰሚት የሚገኘው ፍርድ ቤትም ክርክሩን ለመስማት ለየካቲት 24/2008 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 ቀጠሮ ይዟል፡፡

ጉዳዩ በዚህ ቢያበቃ መልካም ነበር፡፡ ድርጅቱ በሕገ-ወጥ መንገድ የሥራ ውሌን አቋርጦ ሳለ ድርጅቱ የሚሰጠውን ሥልጠና ስወስድ ቃል የገባኹት የሰባት ዓመት አገልግሎት በግሌ ያልተወጣኹኝ በማስመሰል ሰባ ሺ የኢትዮጵያ ብር ከነወለዱ እንድከፍለው ለፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የካ ምድብ ችሎት ክስ መስርቶብኛል፡፡ ይህ የሚያሳየው ድርጅቱ ምን ያህል ኢ-ፍትሓዊነት ቀለባቸው በሆኑ ሰዎች እንደሚመራ ነው፡፡ ከሥራ ለምን ቀረው? በእስራት ምክንያት እስራቱ የማን ስህተት ነው? የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እንዳረጋገጠው የፖሊስ ሐሰተኛ ክስ ነው:: የሥራ ውሌን ማን አቋረጠው? የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሥራ ገበታ ለምን ቀረህ በማለት በመጨረሻም የገባኸውን ቃል አልፈጸምክም በሚል የከሰሰኝ ራሱ አየር መንገድ ሆኖ አዙሪት ውስጥ ገብቼያለሁ፡፡ ከዚህ ቀደም የልደታውን፣ የአራዳውን፣ የስድስት ኪሎውን ፍርድ ቤት ነበር የማውቀው አሁን ደግሞ የካ ፍርድ ቤት በታህሳስ 26/2008 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 እንድቀርብ ታዝዣለው፡፡ የምቆመው ብቻዬን ከመሰላቸው ተሳስተዋል፡፡ የምቆመው እንደ አየር መንገዱ ከሕግ በላይ በሆኑ አሠሪዎች በደል ከደረሰባቸው ሠራተኞች ጋር ነው፡፡ የምቆመው ኢ-ፍትሓዊነት በሀገራችን እንዲወገድ ከሚፈልጉ ኢትዮጵያውያን ጋር ነው፡፡ ከዚህ በፊት አየር መንገዱ ብዙ ሠራተኞችን በድሎ በዝምታ እንደታለፈው(የጽሑፉ ዓላማ ይሄ አይደለም እንጂ ስለበደሉ ብዙ ማለት ይቻላል) ከእኔ ዝምታን ቢፈልግ አያገኛትም፡፡ ከእስር እንደወጣኹኝ አንዳንድ ወዳጆቼን ሥራ እንዴት ነው ብዬ ጠይቄ ነበር የብዙዎቹ ምላሽ “ቀንበሩ ከበዷል” የሚል ነው፡፡ ይህንን መሰል ዘመናዊ ባርነቶች እንዲወገዱ ምኞቴ ነው፡፡ እኔ ግን ፍትሕ ባላገኝ እንኳን ለታሪክ ተመዝግቦ እንዲቀመጥ ስል ይህን እናገራለሁ፡፡

ለሱዳን ሊሰጥ ነው ስለተባለው መሬት

(ምክር-ለበስ አስተያ)
ፍቅሬ ቶሎሳ ጅግሳ (ፒ ኤች ዲ)
(የሁማኒቲስ ፕሮፌሰር)

Dr. Fikre Tolosa

መንግሥት ለሱዳን ሊሰጣቸው ነው የተባሉት አሁን በጎንደር አና በቤንሻንጉል አካባቢ የሜገኙት የእነ ኦሜድላና ጋምቤላ መሬቶች በአውነት የማን ናቸው? ያለጥርጥር የኢትዮጵያ ናቸው። ለምን እንደዚህ እንዳልኩ ዝቅ ብዬ አስረዳለሁ። መሬቶቹ በታሪክ የሱዳን ነበሩና ለሱዳን ይሰጡ የሚሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት መሬቶቹን ለሱዳን ለመስጠት የሚያቀርቡት ምክንያት “በ በሱዳን የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ጊዜ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካይ የሆነ አንድ ሻለቃ የወሰን ምልክቱን የተከለው እዛ አካባቢ ነው፤ቀድሞ አፄ ምንይልክ በዚህ ተስማምተው፥ በሁዋላ ደግሞ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግም ይህን አፅድቀውታል፤” የሚል ነው። በሌላ አነጋገር፥ በታሪካዊ ምክንያት ነው። እዚህ ላይ አንድ አስቂኝ ታሪክ ታወሰኝ። አንድ እንግሊዛዊ ከሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር ተሻግሮ የዱር እንስሳና አውሬ ለማደን በሚል ፈሊጥ ሲዘዋወር ለስለላ ነው ብለው በጠረጠሩት የሃገሬው ተወላጆች ተገሎ እዛው ተቀበረ። ታዲያ ይህን ሰበብ አድርጎ አንድ እንግሊዛዊ መኮንን (ምናልባትም እላይ የተጠቀስው እብድ ሻለቃ) ያ አካባቢ በሞላ ለእንግሊዝ መንግሥት ሊሰጥ ይገባል፤አለ። በምን ሂሳብ ተብሎ በአባ መላ (ፊታውራሪሃብተጊዮርጊስ ዲነግዴ) ተጠየቀ። አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ፤ሲል መለሰ። አባ መላም ከትከት ብለው ስቀው፥እሺ ደግ ነው፤አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ ይሄን ሁሉ መሬት ለናንተ እንሰጣችሁአለን። የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ ልዑል ዓለማየሁ ለንደን ውስጥ ሞቶ እዛው ለንደን (ዌስትሚኒስትር አቢ) ስለተቀበረ እኛ ደግሞ ለንደንን እንረከባችሁአለን። በዚህ ከተስማማህ ውል መፈራረም እንችላለን፤ብለው አሾፉበት። ከዛ ቦታ በቅፅበት ዳብዛው ጠፋ።

Ethio Sudan

ስለታሪክ ካወሳን ዘንድ፥ ይሄ ዛሬ ሱዳን የተባለው ምድር ሁሉ ቢያንስ ለ 4000 ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ ግዛት ነበር።ጥንት የሚታወቀው ኑብያ ተብሎ ነበር። ኖባ በተሰኘው የኩሽ ዘር ስም።መናገሻውም መርዌ ነበር። የዛሬ 2900 ዓመት ግን ሱዳን ይባል ጀመር። ይህ ስም የወረደው ከአፄ አክሱማይት እናት ከንግሥት ሳዶንያ ነው። እሱ በህፃንነቱ የግብፅ ፈርኦን ሆኖ እስከሚያድግ ድረስ እስዋ በ 350,000 የአማራ ሰራዊት ታጅባ ዙፋኑን እየጠበቀች በሱ ስም ግብፅን፥ ሊብያን እና የዛሬውን ሱዳን ታስተዳድር ነበር። በዚህ ምክንያት፥ ከሳሃራ በርሃ በታች የአለው ምድር በሞላ ሳዶንያ ተባለ። ቀስ በቀስ ደግሞ ሱዳን። እንዳውም ኑብያ ውስጥ የነበረው መርዌ ለዛ አካባቢ እንደ ዋና ከተማ ሆኖ ያገለግል ነበር። ቢያንስ 14 የኢትዮጵያ ሴቶች ህንደኬ በሚል ማእረግ በንግሥትነት በተከታታይ ዛሬ ሱዳን፤ ግብፅና ሊብያ የሚባሉትን ሃገሮች ለ 1000 ዐመት ያህል ገዝተዋል። ለመጨረሻ ጊዜ የኑብያ ንጉሥ የነበሩት በ 16ኛው ክፍለ ዘመን የኖሩት አፄ ፋሲል ነበሩ። ከኑብያ ብቻ ሳይሆን ከስናር (ከካርቱምብዙያልራቀ ስፍራ) ድረስ የወርቅ ግብር ይመጣላቸው ስለነበር አዝማሪ አንዲህ ሲል የሱዳን ገዥነታቸውን አረጋግጦላቸው ነበር፤-
ጎንደር ቢያጉረመርም ፋሲል ፈረስህ
ኑብያና ስናር ወርቁን ጫኑልህ፥
ሳሩን ተጠየፈ የፋሲል ፈረሱ፥
ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለሱ።
“ገፈራ” ማለት የፈረስ ምግብ ነው። ዛሬ ፉርሽካ የምንለው ዐይነት። እንግዲህ ይህ ግጥም፥ ሱዳን አስከ የዛሬ 500 ዐመት የኢትዮጵያ ግዛት አንደነበረች ይመሰክራል። በሁዋላ በዘመነ መሳፍንት አና ከዛ ትንሽ ቀደም ብሎ ኢትዮጵያ አየተዳከመች ስትሄድ ቱርኮች ያዝዋት። ቱርኮች ተዳክመው ለእንግሊዝ ለቀቁላት። እንግዲህ ከእጅ የወጣ ሃገር በታሪክ ሰነድ ወይም ማረጋገጫ የሚመለስ ቢሆን ኖሮ፥ መላው ሱዳን ለኢትዮጵያ በተመለሰ ነበረ። ከላይ አንደ ተረዳነው ሱዳን የኢትዮጵያ እንጂ ኢትዮጵያ የሱዳን ሆና አታውቅም። ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን የኢትዮጵያን መሬት የጠየቀችው? እስዋ አፍዋን ምን ቁርጥ አርጉዋት ጠየቀችና? እስዋ በራስዋ ተነሳስታ ደፍራ መሬት አለኝ አላለችም። አሁን በአመራር ላይ የአሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ደርግን በሚዋጉበት ሰዐት ሱዳን ለዋለችላቸው ውለታ ወሮታውን ሊመልሱላትና አሁንም ተቀዋሚዎቻቸውን እንዳታስተናግድ የሚከፍሉዋት ዋጋ መሆኑ ነው። ወዲህም መሬቱ ያለው በአማራ፥በቤንሻንጉል፥ በጋምቤላና በአሮሞ ክልሎች ስለሆነ የእኛን ምድር ስለማይመለከት ችግር የለውም ዐይነት ነው። ብሄራዊ ስሜት የሚባል ነገር ስለሌለ። መሬት በነፃ እንካ ከተባለ ማን ይጠላል? ስለዚህ ሱዳኖቹ እየፈነጠዙ ሊወስዱ አኮብኩበዋል።

አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት 1600 ኪሎሜትር ለም መሬት ለሱዳን ይገባታል ብሎ ጠበቃ የቆመላት እላይ የተጠቀሰው ቅኝ-ገዢ መኮንን በቸከለው ድንበራዊ ችካል ክሆነና በእንግሊዝ ቅኝ ገዥነት አገር ቅርጫ አንዲሆን ከተፈቀደ፥ እንዲሁም እንግሊዝ ያቀናው መሬት ሁሉ ለሱዳን ይቸር ዘንድ ከተፈረደ፥ የቀድሞው የአንግሊዝ ቅኝ ግዛቶች የነበሩት እነ ዩጋንዳና ሱዳን፥ ካስፈለገም እነ ናይጀሪያ ሁሉ ለሱዳን መሰጠት ይገባቸዋል ማለት ነዋ!!! የሆነ ሆኖ፥ ያ ሆፈፌ ቅዥተኛ እንግሊዝ ምኞታዊ ህልም አልሞ የፈለገውን ያህል የወሰን ድንጋይ ቢተክልና አፄ ምኒልክም አልተስማሙም እንጂ ቢስማሙለትና መሬት ቆርሰው ቢሸልሙትም አንኩዋን ያ ውል የሞተ ነው። ለምን ቢባል፥ ሱዳንን ዐለምና የተባበሩት መንግሥታትም ያወቃትና በታሪኩዋ ለመጀመሪያ ጊዜ ራስዋን ችላ የራስዋን ባንዲራ ያውለበለብችበት ዳር ድንበር አሁን የአለው ነውና። እኤአ በ 1953 ዐመተ ምህረት እንግሊዝ ግዛቴ ይሄ ብቻ ነውና ያንቺም ግዛትሽ ይሄው ነው ብሎ በዐስር ጣቱ ፈርሞ የተወላት መሬት ነው። እሱውም ከመከፈልዋ በፊት የነበረው የቆዳ ስፋቱ 2,505,813 ስኩዌር ኪሎሜትር የሆነው ነው። ከመከፈልዋ በፊት ሱዳን በቆዳ ስፋት ከአፍሪካ አንደኛ ነበረች። አሁን ሶስተኛ ነች። አሁንም ከኢትዮጵያ ትልቃለች ማለት ነው። የያዘችው ይበቃት ነበር።

የኢትዮጵያን መሬት ለግሰናት በደቡብ ሱዳን የተወሰደባትን መሬት እንተካላት ካልተባለ በቀር። ሰጭና ነሽው አንግሊዝ ከተደረገና የእንግሊዝ መንግሥት ለክቶ፥ “አበጥሮ”፤ “አንጥሮ” ሁሉን አጣርቶ ራሱ በመጨረሻ ያረጋገጠው የሱዳን ምድር እላይ የተጠቀሰው ስፋት ከሆነ በምን ሂሳብ ነው አንግሊዝም ሆነ የተባበሩት መንግሥታት የማያውቁትን የኢትዮጵያን መሬት በ ህቡዕ ለሱዳን የሚለገሳት? አይገባትም አንጂ በ እርግጥ ሱዳን ይገባኛል የምትለው መሬት ከአላት ወደ ተባበሩት መንግሥታት ሄዳ ነው አንጂ አቤቱታዋን የምታቀርበው በስርቆሽ በር ነው እንዴ መሬት ቆርሳ የምትሮጠው? ወይንስ መሬቱን ከቦጨቀች በሁዋላ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ቀርባ መርቁልኝ ልትል ይሆን? እስዋ ግን ወደ እዛ እስካሁን ያልሄደችው እኤአ በ 1953 እንግሊዝ ካስረከባት በቀር ሌላ መሬት ስለማይገባት “ወይጅ ወዲያ አትቀልጅ!” ይሉኛል፤ ብላ ፈርታ ነው። አለዛ ሱዳን ነፃ ከወጣች ጀምሮ መሪዎችዋ ከ ኢብራሂም አቡድ ጀምሮ እስከነ ኑሜሪ አና አሁን ያለውም አል በሺር የይገባኛሉን ጥያቄ ገና ድሮ ባቀረቡ ነበር። ሰብብ ፈጥረን ስለቀድሞ ውለታዋ እና ተቀዋሚዎቻችንን ስለምትገታልን እንዲሁ በነፃ እንቸራት ካልተባለ በቀር እንደ እውነቱ ከሆነስ ሱዳን፥ “ኢትዮጵያ ያዘችብኝ፥ ይገባኛል፤” የምትለው አንዲት ስንዝር መሬት የላትም። ከቅኝ ግዛት ነፃ ከወጡ በሁዋላ የአፍሪካ ሀገራት በሞላ የያዙት ድንበርና ወሰን የቅኝ ገዥዎችቸው አነዚህ ናቸው፤ ብለው ያረጋገጡላቸውን ብቻ ናቸው። ስለዚህ ሱዳን ከሌሎቹ የአፍሪካ ሃገራት በምንም አትለይም። በመሆኑም ከኢትዮጵያ ልቀበል ይገባኛል ልትል የሚያስችላት ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ጥሪኝ አፈር የላትም። ስለ ኦሜድላ ብቻ እንኩዋን ብንዘክር፥ አፄ ኅይለሥላሴ በሱዳን በኩል ከስደታቸው ሲመለሱ ከ 5 ዐመታት በሁዋላ ለመጀመሪይ ጊዜ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሰቅለው የአውለበለቡት ኦሜድላ ላይ ነበር። ይህን በሚያደርጉበት ጊዜም የ እንግሊዝ የቅኝ ገዢ ትልቅ ባለስልጣናት ለ ሰንደቅአላማዋ አክብሮት በተጠንቀቅ ቆመው መሬቱ የኢትዮጵያ መሆኑን ተቀብለው ይመለከት ነበር እንጂ “የሱዳን መሬት ላይ እንዴት ባንዲራ ያውለበልባሉ!” ሲል በንጉሱ ላይ ቅዋሜ አላሰሙም።

ኦሜድላ የኢትዮጵያ ለመሆንዋ ከዚህ በላይ ምን ማረጋገጫ አለ? ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን ይቺ ታሪካዊ ስፍራ ለሱዳን የምትሸለመው? ቀዳማዊ ኅይለሥላሤ ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሲያውለበልቡ ጦሩን እንዲያቀነባብር በእንግሊዝ መንግሥት ተሹሞ አብሮአቸው በሱዳን በኩል የገባው ሜጄር ዊንጌትም ታዛቢ ሆኖ እጎናቸው ነበረ። ንጉሡን ተሽቀዳድሞ አዲስ አበባ የገባው ሎርድ ካኒንግሃምም እሳቸው ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ እንዳውለበልቡ አሳምሮ ያውቅ ነበር። እነዚህም ሁለት ታላላቅ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካዮች ኦሜድላ የኛ ናት አላሉም። የሆነ ሆኖ እውነት እንግሊዝ ከ አፄ ምንይልክ ጋር ተዋውሎ ከነበር እሱው እንግሊዝ የመሬት ይገባኛል ጥያቄውን ያቅርብልን እንጂ ያልተዋዋልናት ሱዳን ምን አገባት? ከሱዳን ሳንዋዋል እንዴት ሱዳን የተዋዋልነው ይከበርልኝ፥ ልትል ትደፍራለች? ይህን ጥያቄ ሊያነሳ የሚችል አንግሊዝ ብቻ ነው። ነበርም። ግን እንግሊዞች አላነሱም። ምክንያቱም ቀላል ነው። የዚህ ዐይነት ውል ከአፄ ምንይልክ ጋር ስላተፈራረሙ። ተፈራርመው ቢሆን ኖሮ መጠየቅ ብቻ አይደለም፥የተፈራረሙበት ቀለም ሳይደርቅ መሬቱን እጃቸው ያስገቡ ነበር። ስላልተፈራረሙ ይህን አላደረጉም። የሱዳንን ነፃነት እንግሊዞች ሲፈቅዱም የተባለውን መሬት የኔ ነበር ብለው ወደ ሱዳን አላዘዋወሩም። አሁን ያለውን መሬት ብቻ ነው ትተውላቸው የሄዱት።አሱም ለሁለት ተከፍሎባቸዋል። ከአንግሊዝ የተረከቡትን መሬት እንኩውዋን በቅጡ መያዝ አቅቶአቸው “የቆጡን አወርድ ብላ የብብትዋን ጣለች፤” የተባለው ተረት በነሱ ላይ ተፈፅሞባቸዋል። የራሳችውን አጥብቀው መያዝ ሳይችሉ የኛን መሬት መከጀላቸው ማስቆጣት ብቻ ሳይሆን ያስደንቃል። እንግዲህ እንግሊዝ ከአፄ ምንይልክ ጋራ መሬትን አስመልክቶ ላለመዋዋሉ ሶስት ማስረጃዎች አሉ ማለት ነው። አንደኛ፥ የተባሉትን መሬቶች ቀደም ሲል እጁ ባለመክተቱ፤ ሁለተኛ፥ ንጎሱ ኦሜድላ ላይ ሰንደቅአላማችንን ሲሰቅሉ አለመቃወሙ፥ ሶስተኛ፥ ሱዳንን ለቆ ሲሄድ ለሱዳን ከተወላት የተባበሩት መንግሥታይ ባፀደቀላት ዳር ድንበር ውስጥ እነዚህን ሁሉ የኢትዮጵያ መሬቶች በካርታም ሆነ በፅሁፍ ባለማካተቱ። በነዚህ ሶስት ማስረጃውች ምክንያት እሩቅ ሳንሄድ፥ ሰነድ ለማግኘት አፈር ሳንቆፍር እና ድንጋይ ሳንፈነቅል ምንይልክ እና እንግሊዝ አንዳችም የመሬት ውል እንዳልተፈራረሙ እናረጋግጣለን። ተፈራርመዋል የሚል እስቲ ሰነዱን ያቅርብልን!! ደግሞም ቢፈራረሙም እንኩዋን ውሉ የቅኝ ገዥዎች ሰለሆነና ምንይልክም ሆነ ማንኛውም መሪ የአትዮጵያ መሬት የግል ንበረቱ ስላልሆነ መሬት ለባእዳን ሰጥቻለሁ ቢል አይፀናም።

አፄ ምንይልክ ተስማምተውበት፥ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግ ያፀደቀውን ነው እኛ በተግባር የምናውለው፤ ሲል ኢህአዲግ ደጋግሞ ተናግሮአል። ይህን መሰረት በማድረግ እኔ ብዙ ምርምር አካሂጄ ሁለቱ አፄዎችና የደርግ ሊቀመንበር የነበሩት ኮረኔል መንግሥቱ ኅይለማርያም ለሱዳን መሬት ለመስጠት የተዋዋሉበት አንድም ሰነድ አላገኘሁም።ምክንያቱም ስላልነበረ። ስለ ሌለም። አሁን በህይወት የአሉት ኮሎኔል መንግሥቱም አንድም የዚህ ዐይነት ውል ከሱዳን ጋር እንዳልተፈራረሙ አበከረው መስክረዋል። ይልቁንም አኔ ያገኘሁት መረጃ፥ አውሮፓውያን መንግሥታት ለብቻቸው ተሰብስበው አፍሪካን ለመቀራመት ያደረጉትን ውል ለአፄ ምንይልክ ነግረው የኢትዮጵያን ነፃነት ግን አንደሚያስጠብቁ ቢገልፁላቸው፥ “እኔ በሌለሁበት እናንተ ተሰብስባችሁ ያደረጋችሁትን ውል በፍፁም አልቀበልም፤ የኢትዮጵያን ነፃነት አናስጠብቃለን ሰለአላችሁት ግን አመሰግናለሁ፤” በማለት ተንኮላቸውን ውድቅ ማድረጋቸውን የሚያሳይ ነው። በነገራችን ላይ፤ አፄ ምንይልክ እንኩዋን ለሱዳን መሬት ሊሰጡና በሰላም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ የነበሩት የውጭ ሀገር ሰዎች መሬት አንዲገዙ አይፈቅዱላቸውም ነበር። አላደረጉትም እንጂ ሶስቱም መሪዎች አድርገውትም እንኩዋን ቢሆን፤የኢትዮጵያን ህዝብ መሬት አንስተው ለባእዳን ለመቸር ምንም መብት አልነበራቸው። ኢትዮጵያ፥ እንዲያስተዳድሩዋት አደራ የተሰጠቻቸው ምድር እንጂ እንዳሻቸው ለፈለጋቸው አገር ገፅበረከት አድርገው የሚለግስዋት የግል ንብረታችው አልነበረችምና። አሁን ያለውም መንግሥት አንዲሁ የኢትዮጵያን መሬት ገምሶ ለባእዳን ለመቸር ከቶም አንድም ህገመንግሥስታዊ ነፃነት ወይም ስልጣን የለውም። በጉልበቱ ካልሆነ በቀር። ረጅሙን ታሪካችንን ወደ ሁዋላ መለስ ብለን ብናስተውል፥ ባለፉት 5300 ዐመታት ኢትዮጵያን የመሩት መንግሥታት ድንበር ከማስፋት በቀር መሬታቸውን እንደ አንጀራ ቆርሰው ለባእዳን ሲቸሩ በፍፁም ተስተውሎ አያውቅም። አሁን ከአለው መንግሥት በስተቀር።

እዚህ ላይ ባድመ ይታወሰናል። ባድመ ባድማው ደረቁ መሬት ከአትዮጵያና ኤርትራ በኩል ወደ 150000 ገደማ ወይም ከዛ በላይ ምስኪን ሰዎች በከንቱ አስጨረሰ። ከዚያ አልጀርስ ላይ ለኤርትራ ይገባታል ይሰጣት፤ ተብሎ ተፈረደላት።ባድመ እስካሁን በ ኤርትራ እጅ ውስጥ አልገባችም። ለምን? የትግራይ መሬት ውስጥ ስለሆነች የማትነካ፥ የማትገሰስና የተቀደስች ሆና ወይስ በሌላ ምክንያት? ሰፊ መሬት አለኝ ብሎ ከማውራት በቀር ለማንም የማይጠቅመውን ጠፍ መሬት አንሰጥም ብሎ ይዞ፥ ለመሬት ብላ ከኛ ላልተዋጋችው ሱዳን ለምለም ምድር ገምጦ ለመቸር መቸኮል ምን ይባላል? ይህ ለሰሚው ግራ ነው። ባድመም በኤርትራ ላትወስድ የቻለችው፥ “ትግራይ ሀገርህ ተወራለችና የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ተነሳ!” ተብሎ በተጠራው የሀገር ማዳን ጥሪ መሰረት፥ “ጉዳዩ እኔን አይመለከተኝም ይህ የትገራይ መሬት ነው፤” ሳይል በብሄራዊ ስሜት የነደደው ቆራጡ የኢትዮጵያ ህዝብ አጥንቱን ከስከሶ፤ ደሙን አፍሶ፤ንብረቱን አጉድሎ ባደረገው ተጋድሎ ነው። ትግራይ ስትወረር የኢትዮጵያ ህዝብ ፥ “ወይኔ ሃገሬ!” ብሎ ደሙን ሲያፈስ ባድመ የመጨረሻው እንጂ የመጀመሪያው አይደለም። ከዛ በፊት ጣልያን ከማንም አስቀድሞ ትግራይን በወረራት ጊዜ በመቀሌ፥ በአምባላጌ፥በአድዋ እና በማይጨው በ 40 ዐመታት ልዩነት ውስጥ ሁለቴ ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍሎአል። ለዚህ ሁሉ ውለታው አፃፋው ይሄ ነውን? እባካችሁ ሰከን ብላችሁ ነገሩን አስቡበት።

ይህ ድርጊት በትውልድ ያስወቅሳችሁአል። ጠንቁ ለልጆቻችሁና ለልጅ ልጆቻችሁ፤ እንዲሁም ለዘራችሁ ይተርፋል። ለስልጣን ያበቃችሁ የትግራይ ህዝብ ሳያቀር በአደራጎታችሁ ያፍርባችሁአል። የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ አቅም ባይኖረው ነገ ሊጠነክር ይችላል። ሳይወድና ሳይፈቅድ መሬቱን ሱዳን አሁን ብትወስድበት እንኩዋን ነገ ሲጠነክር ተዋግቶ ያስመልሰዋል። በዚህ ሳቢያ አሁን ልትጠቅምዋት ያሰባችሁአት ሱዳንም ሰላም አታገኝም። የ እናንተም ስም በክፉ ተነስቶ አፅማችሁም ሲወቀስ ይኖራል። ስለዚህ ሱዳንን በሌላ በሌላ ነገር ካስዋት እንጂ የስንት ሰማአታት ወገኖቻችን ደም እና ላብ የአለማውን መሬታችንን አሳልፋችሁ በብላሽ አትስጡ። ለሱዳን ካሳ፥ አፍንጫዋ ስር የተገነባላት የአባይ ግድብ መች አነሳት? በዚህ የኢትዮጵያ ህዝብ ገንዘቡን በከሰከሰበት ግድብ ከማንም በላይ ተጠቃሚዋ ሱዳን አይደለችንምን? ግድቡ ይበቃታል፤ መሬቱ ይቅርባት። ብቻችሁን ይህን መወሰን ካስቸገራችሁ ደግሞ ፓርላማችሁና የኢትዮጵያ ህዝብ ይምከርበት። ለይስሙላስ ቢሆን ፓርላማ አለ አይደል? እንዲህ ዐይነቱ ትልቅ የሀገር ሉአላዊነት ጉዳይ ሀገር ሳይመክርበትና ህዝብ ሳይወስንበት አንዴት በዝግ ጉዋዳ ይካሄዳል? ባድመ አንዳትወሰድ የተረባረባችሁትን ያህል አና ለኤርትራ አንዳይሰጥ የምትተጉትን ያህል፥ እባካችሁ አሁን ሱዳንን የሚያዋስናትን ሁሉ የኢትዮጵያ ዳር ድንበር ለሱዳን ከመቸር ታቀቡ። በውኑ ከዚህ ከታቀባችሁ፥እናንተም፤ ልጆቻችሁም፥ ዘራችሁም፥ አንዲሁም በመቃብር ውስጥ የሚኖረው አፅማችሁም ከመወቀስና ከመረገም ይተርፋል። ጆሮ ያለው ይስማ። ልብ የአለው ልብ ይበል።

ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ ጂግሳ የ The Hidden and Untold History of the Jewish People and Ethiopians እና የ Heaven to Eden መፃህፍት ደራሲ ነው። ሁለቱም መፃህፍት በ amazon.com ቢፈለጉ ይገኛሉ። አስተያየት ለማቅረብ በ fiktolo@gmail.com ይጠቀሙ።

በእስር ላይ የሚገኙት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት መግለጫ ሰጡ

በእስር ላይ የሚገኙት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት በአዲስ አበባ መርካቶ በሚገኘው አንዋር መስኪድ ባለፈው አርብ ታህሳሥ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሰውን ድንገተኛ የቦንብ ፍናዳታ አደጋን አስመልክቶ ዛሬ አርብ ታህሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በእስር ላይ የሚገኙት የኮሚቴ አባላት ባለፈው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በነበረው ችሎት ከ7 ዓመት እስከ 22 ዓመት የሚደርስ ፅኑ እስራት እንደተፈረደባቸው አይዘነጋም፡፡ ሙሉ መግለጫው የሚከተለው ነው፡-

Dimetsachin Yisemaየአንዋር መስጊዱን የቦምብ ጥቃት አስመልክቶ በእስር ቤት ከሚገኙ የኮሚቴው አባላት የተሰጠ መግለጫ አርብ ታህሳስ 15/2008

ህዝበ ሙስሊሙ ለተንኮለኞች ሴራ ሳይበገር አንድነቱን አጠንክሮ፣ አመለካከቱን አቻችሎ ሰላማዊ የመብት ትግሉን መቀጠል ይኖርበታል!

በአንዋር መስጊድ ቅጥር ግቢ ታህሳስ 01/2008 የደረሰው የቦንብ ጥቃት የዓለም አቀፉ ሕብረተሰብ ትኩረት እንዲሰጠው፣ ድርጊቱም በገለልተኛ አካላት በአስቸኳይ ተጣርቶ ለህዝብ ይፋ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን!
አርብ ታህሳስ 15/2008 /አዲስ አበባ/ኢትዮጵያ

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ሕገመንግስታዊ የመብት ጥያቄያችንን ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ማቅረባችን ይታወቃል። ለጥያቄዎቻችን ተገቢውን እና ፍትሃዊ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ጥያቄውን በሀሰት በመፈረጅ ሰላማዊ ሂደቱን ለመቀልበስ ተደጋጋሚ ጥረት ተደርጓል። የህዝበ ሙስሊሙን የፍትህ ጥያቄን ለማጠልሸት እና በመካከሉ ልዩነትን ለመፍጠር የተለያዩ የፕሮፓጋንዳ ስራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። ለህዝበ ሙስሊሙ ጥያቄዎች መፍትሄ ለማፈላለግ ሕዝብ በወከለን መሰረት በመንቀሳቀሳችን ወንጀለኛነት እና የረጅም እስር ፍርድ እንዲወሰን ተደርጓል። ይህም ሁሉ ሆኖም የሙስሊሙን አንድነት መስበርም ሳይቻል ቀርቶ ለመብቱ መከበር የሚያደርገውን ትግል በተጠናከረ መልኩ እየቀጠለ ባለበት ወቅት እጅግ ጸያፍ የሆነ የቦምብ ጥቃት በእምነት ቤታችን ቅጥር ግቢ ውስጥ መሰንዘሩ እጅግ ያሳዘነን ክስተት ነው።

የህዝበ ሙስሊሙን ጥያቄ ለመቀልበስ የሚደረጉ ሙከራዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ እና የህዝበ ሙስሊሙን ሰላማዊ የትግል ሂደት መንገድ ሊያስቱ እንደሚሞክሩ ደጋግመን ስናስጠነቅቅ ቆይተናል። የሸፍጥ ጥቃቶችን በስውር በመፈጸም ፓለቲካዊ ጥቅም የሚያስገኙ እርምጃዎችን ለመውሰድ የማመቻቸት ተግባር በተለያዩ ሀገሮች የምናየው ክስተት ነው። በሰላማዊ የትግል ሂደታችንም በተለያየ ጊዜ የተረዳነውና ያጋጠመንም ነው። ሆኖም ግን ሙስሊሙ ህብረተሰብ የመከላከል ስራዎች ላይ በልዩ ትኩረት በመስራቱ ሰላማዊ ሂደታችን ለፓለቲካ ግብዓት እንዳይውል እድሉን ነፍጓቸው ቆይቷል። እንግዲህ በአንዋር መስጊድ ቅጥር ግቢ ውስጥ ታህሳስ 01/2008 የደረሰው የቦንብ ጥቃት ቀደም ብለን እንደ ህዝብ ገምተን ስንከላከለው፣ መንግስትም የሀይማኖት ተቋማትን በተለይም የመስጂዶችን ደህንነት ለመጠበቅ በኩል ያለበትን ሀላፊነት በትክክል እንዲወጣ ስናስጠነቅቅበት የቆየነው እንጂ ሌላ አይደለም።

ሙስሊሙ ህብረተሰብ ፍትሃዊና ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ ለመቀጠል ዳግም ቃል እየተጋባ ባለበት በአሁኑ ወቅት እና አማኞች የፈጣሪያቸውን ግደታ ለመወጣት በተሰባሰቡበት ቦታና ሰዓት የቦንብ ጥቃት ማድረስ በእርግጥም የሙስሊሙን ሰላማዊ ሂደት ለማጠልሸት፣ የትግል ወኔውን ለመስበር፣ አንድነቱን ለመረበሽ ዛሬም የማይፈነቀል ድንጋይ እንደማይኖር የሚያረጋግጥ ነው። ከዚህ በመነሳት በቀጣይም በመስጊዶች ብቻ ሳይወሰን በክርስትና እና በሌሎች የአምልኮ ቦታዎችም ላይ ተመሳሳይ ጥቃቶችን በማድረስ በተለያዩ እምነት ተከታይ ኢትዮጵያዊያን መካከል ቅራኔን ለመፍጠር ሙከራዎች እንደሚደረጉ መገመት ከእውነታ የራቀ አይሆንም። በዚህ አይነት የተንኮለኞች ሴራ አገራችን እና ህዝባችን አደገኛ ወደ ሆነ አቅጣጫ እንዲመሩ አንፈቅድም። በመሆኑም ጉዳዩ የዓለም አቀፋዊ ማህበረሰብ ትኩረት እንዲቸረው እና ይህ እኩይ ተግባር በገለልተኛ አካል ይጣራ ዘንድ ሀገር እና ወገን ወዳድ የሆኑ ሁሉ ጥረት እንዲያደርጉ አጥብቀን እንጠይቃለን። በደረሰው ጥቃት ለተጎዱት ወገኖቻችን፣ እንዲሁም ለመላው ሙስሊም ህብረተሰብ እና ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በሁኔታው የተሰማንን ሀዘን እንገልጻለን። ህዝበ ሙስሊሙም በፍንዳታው ጉዳት ለደረሰባቸው ወንድሞቹ እና ለቤተሰቦቻቸው አስፈላጊውን እገዛ በማድረግ እና ከጎናቸው በመቆም አጋርነቱን፣ አንድነቱን እና ከምንም በላይ የትኛውም አይነት ሴራ የማይበግረውን ከፈጣሪው በተዘረጋ የእምነት ገመድ ላይ ያለውን የአንድነት ትስስር በተግባር ሊያሳይ ይገባል።

የህዝበ ሙስሊሙ ጥያቄያች ፍትሀዊ ናቸው፡፡ ሂደቱም ሰላማዊ ነው። በህዝበ ሙስሊሙ መካከል ጥርጣሬን ለማስፈን፣ ክፍፍልን በማምጣት እርስ በርሱ ለማጋጨት የሚፈጸም የትኛውም ደባ የከሸፈ ከንቱ ጥረት ነው። ህዝባችን በዚህ እና መሰል ሴራዎች ሳይበገር አንድነቱን ጠብቆ፣ አመለካከቱን አቻችሎ ሰላማዊ የመብት ትግሉን ከመቼውም ጊዜ በላይ አጠናክሮ እንዲቀጥል እናሳስባለን።

አገራችን ያለችበትን ተጫባጭ የታሪክ ፈታኝ ምእራፍ በመረዳት ህብረተሰባችን ያለአንዳች የብሄር፣ የዘር፣ የሃይማኖትና የጾታ ልዩነት ለፍትህ እና ለሕግ የበላይነት በመቆም ዜጎቿ በሰላም ተሳስበን የምንኖርባት ሀገር ትሆንልን ዘንድ ጠንክረን መታገል ይኖርብናል። ለዚህ ስኬት ከጥረታችን ባሻገር ሁላችንም ፈጣሪያችንን በጽኑ እንለምን። በመተናነስ፣ በጸሎት፣ በሰደቃ እና በመልካም ተግባር ወደፈጣሪያችን አላህ (ሱ.ወ) መቃረብ እንደሚኖርብን ህዝባችንንም ራሳችንንም ሳናስታውስ አናልፍም!
ድል የሚከጀለው ከአላህ እንጂ ከሌላ አይደለም!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምጻችን ይሰማል!
አላሁ አክበር!

ምንጭ፡-ቃልኪዳን ቲዩብ

ጠላት ሰሪዎቹ (The Enemy Makers)

ገመቹ መረራ ፋና

gemechu merera

ብዙውን ጊዜ የራሳችንን ጠላቶች ራሳችን ጠፍጥፈን እንደምንሰራ አምናለሁ። በማድረግም ባለማድረግም (by commission and omission) የምንሰራቸው «ስህተቶች» አሉ። በተለያየ ጊዜ ያቆሰልናቸው ወይም ቆስለው እያየን በቁስላቸው አላግጠን ያለፍናቸው ሰዎች ነገ ወዳጅ ይሆኑናል ብለን የምንጠብቅ የዋሆች አይደለንም። ይሄንን ድርጊታችንን ወይም ተዓቅቦአችንን ተከትሎ የሚመጡብን ችግሮች ከመጋፈጥ ቆም ብሎ ዛሬ ላይ ምን እያደረግኩ ነው ብሎ ማሰብ ሳይበጅ አይቀርም። እስቲ በመጨረሻ ላይ የቆምንበትን/ያለንበትን ሁኔታ ከማየታችን አስቀድመን ጥቂትአብነቶች አንስተን የራሳቸውን ጠላት ጠፍጥፈው የሰሩ አካላትንን እና «ጠላቶቹን» በምሳሌነት እንመልከት፦
1. ጋሳን ፋይዝ ካናፋኒ
ይህ በብዙዎች ዘንድ የአረቡ የምንጊዜም ምርጥ የሥነ-ጽሁፍ ሰው ነው ተብሎ የሚወሰድ ፍልስጤማዊ ደራሲና የነጻነት ታጋይ ከሕልፈቱ በኋላ በ Conference of Afro-Asian Writers የ Lotus Prize for Literatureን አሸንፏል። በልጅነቱ የ1948ቱን የአረብ-እስራኤል ጦርነት ተከትሎ ከትውልድ ስፍራው ከቤተሰቦቹ ጋር ተሰዶ ወደ ሊባኖስ ከዚያም ወደ ሶርያ የኖረው ካናፋኒ በ36 ዓመት እድሜው ሞሳድ ባጠመደው የመኪና ቦምብ ከ17 ዓመቱ የወንድሙ ልጅ ጋር ቢገደልም በትንሹ የሕይወቱ ቆይታ ግን ብዙ ስራ ሰርቶ አልፏል።
Letter from Gaza በመባል በሚታወቀው ለጓደኛው ሙስጠፋ በጻፈው የመልስ ደብዳቤ ካናፋኒ አንድ ነገር ግልጽ ያደርጋል። ይህ ደብዳቤ ሶርያ በስደት እያሉ ብዙ አስቸጋሪ ጊዜያት አብረው አሳልፈው ለነበረውና ወደፊት ሃብታም የመሆን ግብ ሰንቀው ይኖሩ ለነበረው አብሮአደግ ጓደኛው ሙስጠፋ የተጻፈ የመልስ ደብዳቤ ነው። በመጀመሪያው ደብዳቤ አሜሪካ ነዋሪ የሆነው ሙስጠፋ ለካናፋኒ ለኑሮው የሚያስፈልጉትን ሁሉ ነገሮች አመቻችቶ ወደ አሜሪካ (ካሊፎርኒያ- ሳክራሜንቶ) እንዲመጣና የልጅነት ግባቸውን እንዲያሳኩ እየነገረው ነበር። በሲቪል ምህንድስና በካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ ስኮላርሺፕ አግኝቶ ሁሉ ነገር የተስተካከለለት ጋሳን ካናፋኒ ግን ለጓደኛው እኔ ወደ አሜሪካ አልመጣም፣ አንተ ወደ ጋዛ ና እንጂ ይለዋል። «I won’t follow you to “the land where there is greenery, water and lovely faces” as you wrote. No, I’ll stay here, and I won’t ever leave.» በዚህች መስመር እንደተጠቀሰው መቼም ከጋዛ አልወጣም ነበር ያለው። ለምን ይሆን አልመጣም ያለው? ያስብላል።
ናዲያ። ያቺ በጣም አብዝቶ የሚወዳት ናዲያ አይኑን እንደከፈተችለት ይገልጻል። ናዲያ ቆንጅዬ የ13 ዓመት ልጅ ነች። የሙት ወንድሙ ሴት ልጅ። ለበዓል ይኖርበት ከነበረችው ኩዌይት ወደ ጋዛ ሲሄድ የወንድሙ ሚስት እያነባች ልጇ ናዲያን ሄዳ ጋዛ ሆስፒታል እንዲጠይቃት ትለምነዋለች። እናቱ እና የወንድሙ ሚስት የደበቁት ነገር እንዳለ እየተሰማው ወደ ሆስፒታል ክፍሏ ይገባል። የሆስፒታሉ አልጋ ላይ ትልቅ ትራስ ተንተርሳ ጥልቅ ዝምታን በሚናገሩት እና እንባ ባዘሉ አይኖቿ ተመለከተችው። «Her face was calm and still but eloquent as the face of a tortured prophet might be. Nadia was still a child, but she seemed more than a child, much more, and older than a child, much older.» አጎቷን ያየችው ናዲያ በእጆቿ ድጋፍ ቀና ብላ ሰላም ካለችው በኋላ ተኛች። ካናፋኒም አንዲህ ይላታል «ናዲያ ብዙ ስጦታዎች ከኩዌይት ይዤልሽ መጥቻለሁ። ድነሽ ከአልጋ ስትወርጂ እቤት ትመጪና ስጦታዎችሽን ሰጥሻለሁ። ባለፈው በደብዳቤ ጽፈሽ የጠየቅሺኝን ቀይ ሱሪም ገዝቼልሻለሁ። ሱሪውን ይዤልሽ መጥቻለሁ።» ናዲያ ኤሌክትሪክ እንደያዛት ሰውነቷ ተንቀጥቅጦ ዝም አለች። አንባዋ ግራና ቀኝ ወደ ትራሱ ፈሰሰ።
«ሱሪውን አልፈለግሺውም? ምን ሆነሻል?» ብሎ ሲጠይቃት እንደምንም ጥርሷን ነክሳ ከሩቅ የመጣ በሚመስል ድምጽ «አጎቴ!» አለችው። እጇቿን ዘርግታም የሸፈናትን የሆስፒታል ብርድልብስ ገለጠችና በጣቶቿ ጠቆመቸው። ናዲያ እግሯ ከጭኗ መነሻ ጋር ተቆርጦ ነበር!! «ይሄንን ልረሳ አይቻለኝም» ይለዋል በደብዳቤው ለጓደኛው። «ያን ቀን ናዲያ እግሯን ያጣችው ታናናሽ ወንድም እና እህቶቿን ከቦንብና ከነበልባል ልታድን ራሷን ጥላ ከልላቸው ስለነበር ነው ብለው ነገሩኝ። ሮጣ ልታመልጥ እና እግሯን ልታድን ትችል ነበር። ግን ያንን አላደረገችም።» ይልና ከዚያች ቀን በኋላ ሁሉን ነገር በተለየ መልክ ማየት መጀመሩን እና ወደ ሳክራሜንቶም እንደማይመጣ፣ ይልቁንም እርሱ ራሱ እንዲመጣና ለሀገራቸው ትንሳዔ፣ ለህዝባቸው መፍትሄ እንዲሰሩ ይጠይቀዋል። ይሄ መስዋዕትነት ምንን እንደሚጨመር እንግዴህ መዘርዘር አያስፈልግም – ጉዳዩ የእስራኤል እና የፍልስጥዔም ነውና። እስከ ሕልፈተ ሕይወቱ ድረስም ለሃገሩ ሲሰራ ኖሯል። የጋሳን ካናፋኒ ስራዎች ዛሬ በብዙ ፍልስጤማውያን ልብ ውስጥ አለ።
2. ብ/ጄኔራል ታደሰ ብሩ
ጄነራሉ ሙያቸውን ከሚያከብሩ እና ለንጉሱ ታማኝ ከነበሩ ወታደሮቻቸው መካከል ግንባር ቀደሙ ነበሩ። በንጉሱ ጊዜ እንዳገለገሉት አብዛኞቹ ባለሥልጣናት እና ተሿሚዎች ለንጉሱ መልካም አመለካከት እና ታማኝነት የነበራቸው ግለሰብ ነበሩ። ይሄንንም በንጉሱ ላይ የታቀደውን መፈንቅለ መንግስት ባከሸፉበት ስራቸው እንዲሁም ኔልሰን ማንዴላን መጠበቅ እና ማሰልጠንን የሚያህል ትልቅ አደራ በመቀበል አስመስክረዋል። (እዚህ ጋር እንዴት ያንን መፈንቅለ መንግስት ያከሸፈ ግለሰብ በመልካም ይወደሳል የሚል አንድ ጥያቄ ሊነሳ ይቸላል። ነገር ግን እንደወታደር እና ሃላፊነቱ እንደነበረበት ሰው ግዴታቸውን የተወጡ መሆኑ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲገለጽ ነበር። ከውትድርና ሳይንስ አንጻር ከታየና ከወቅቱ ሁኔታ ጋር ከተመዘነ ባይጥምም የሚያስማማ ነው።) የኚህ የተከበሩ ጄነራል ታማኝነት ግን አንድ ቀን ተሸረሸረ።
ከዕለታት በአንዱ ቀን በቤተመንግስት በተዘጋጀ የራት ግብዣ ላይ መኳንንቱ እና መሳፍንቱ እንዲሁም እነጄነራል ታደሰ ብሩ ታድመው ነበር። በራት ግብዣው ላይ ሰው ጨዋታ ይዞ የነበረ ሲሆን ብ/ጄኔራል ታደሰ ብሩ ጨዋታ ይዘው የነበረው ከጠ/ሚ/ሩ አክሊሉ ኃብተወልድ ጋር ነበር። የጨዋታውም ርዕስ ጄነራሉ በወቅቱ ይሰሩት ስለነበረው ስራ ነበር። ጄኔራሉ በወቅቱ በጦር ሰራዊቱ ውስጥ የጀመሩት እና በተለይ ይመሩት የነበረው አንድ ክፍል ነበር። ይህ ክፍል «የፊደል ሰራዊት» የሚባል ሲሆን በሃገራችን የተለያዩ ክፍሎች የመሰረተ ትምህርት ስልጠና ይሰጥ ነበር። በውይይቱ ወቅት ጠ/ሚ/ሩ እጅግ ያስገመታቸውን እና ለጄነራሉ መለወጥ ምክንያት የሆነውን ትዕዛዝ መሰል ምክር ለጄነራሉ ሰጡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አክሊሉ «ታደሰ፤ ኦሮሞ ውቅያኖስ ነው ይውጠናል – ልታስተምረው እንዳትሞክር። እነሱን አንድ ክፍለዘመን ወደኋላ ይዘን መሄድ ነው ያለብን» ነበር ያሉት።
በወቅቱ በዚህ ጊዜ ተመስርቶ የተለያዩ የልማት ስራዎችን እየሰራ የነበረ አንድ ማህበር ነበር፤ የመጫና ቱለማ የመረዳጃ ማህበር። ይህ ማህበር እንደ መቶ አለቃ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ያሉ የተለያዩ ትልልቅ ሰዎችን በአባልነት ያቀፈና የተለያዩ የማህበራዊ ፍትህ እና የልማት ስራዎችን የሰራ ማህበር ነበር። ትምህርት ቤቶችን፣ ሆስፒታሎችን/ክሊኒኮችን እና ሌሎች መሰል የልማት ስራ ይሰራ የነበረው ማህበሩ ለዚህ ስራው የሚረዱ ግብዓቶችን ሊሰጡ የሚችሉ ከመላው ሕብረተሰብ የተውጣጡ ሰዎችን የያዘ ሲሆን በውስጡ ደጃዝማቾችን፣ ኮሎኔሎችን፣ ዶክተሮችን ወዘተ በአባልነት ያቀፈ ማህበር ነበር። ለማህበሩ አባልነት ከተጠየቁት እና የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ከተጋበዙ ሰዎች መሃዘከል ደግሞ ብ/ጄኔራል ታደሰ ብሩ አንዱ ነበሩ። ጄነራሉ ግን ማህበሩ የብሄር ተኮር ፖለቲካ ያራምዳል የሚል ዕምነት ስለነበራቸው ግብዣውን ከአንዴም ሁለቴ ሳይቀበሉ ቀርተው ነበር።
ወደ ራት ግብዣው ምሽት ስንመለስ ጠ/ሚ/ሩ ያንን «ምክራቸውን» ለጄነራሉ ሲለግሱ ያላወቁት አንድ ነገር ነበር፤ ጄኔራሉ በእናታቸው ኦሮሞ መሆናቸውን። በዚህ ጊዜ ነበር እያገለገሉ ያሉት ሥርዓት አባላት ያላቸውን የነቀዘ አስተሳሰብ የተገነዘቡት እና ከዚህ በፊት የገፉትን የአባልነት ግብዣ ተቀብለው የመጫና ቱለማ ማህበርን የተቀላቀሉት። ከዚህ ቀን በኋላ በሥርዓቱ የተገፋ ሕዝብ ላሉት የኦሮሞ ሕዝብ በደርግ እስከተገደሉበት ዕለት ድረስ የታገሉ ሲሆን የማህበሩን የትግል ገጽታ በአንድ ደረጃ ከፍ እንዳደረጉ ይነገራል። (በኦላና ዞጋ የተጻፈውን «ግዞት እና ግዝት» የተሰኘው መጽሃፍ ውስጥ በስፋት ስለጄነራሉ ማንበብ ይቻላል።) ዛሬ የብ/ጄነራል ታደሰ ብሩን ትግልና መስዋዕትነትን የማያውቅና በልቡ ያላኖረ የኦሮሞ ወጣት ማግኘት ያስቸግራል።
(ምንም እንኳን ለዚህ ጽሁፍ ከላይ ከተጠቀሰው የሚበልጥ አግባብነት ባይኖረውም ጠ/ሚ/ሩ በሌላ አጋጣሚም ንጉሱ ዘንድ የቀረቡትን የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሰራተኞች ተወካዮች «ንጉሱ እንኳን እናንተን የማንንም ጋላ ያናግራሉ» ብለው መናገራቸው በ «ኮሙኒስቶችም እኛን ይመስላሉና» ላይ ተጽፎልናል)
3. አህመድ ግራኝ (አህመድ ኢብን አል ጋዛሊ)
አህመድ ግራኝ ለዚያ ሁሉ ዘመቻና በቀል እንዲነሳሳ ምን አደረገው? ለዚህ ምላሽ የሚሆን በቂ ጽሁፍ በተክለ ጻድቅ መኩሪያ የታሪክ መጽሃፍት ውስጥ ይገኛል። (በእኔ እይታ ጸሃፊው እንደአብዛኞቹ የሃገሬ ታሪክ ጸሃፊዎች የሚዛናዊነት ችግር ባስተውልባቸውም በዚህ ጉዳይ ላይ ቅሬታ የሚያስቀርብ ነገር አላየሁም። ስለዚህ አንባቢ አንብቦ ይረዳው አሊያ በሌላ ጽሁፍ እመለስበታለሁ ወይም ባለሙያዎቹ ይጽፉበታል።)
4. የኛ ትውልድ
የኔ ትውልድ ያልኩት በዋነኛነት ይሄንን የCyber ትውልድ ነው። በበይነ-መረብ (ኢንተርኔት) ታግዞ የተለያዩ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በማንሳት ያለማቋረጥ የሚያፈሰው ተዋስዖ አጥፊም አልሚም ሊሆን የሚችልበት አጋጣሚ አይጠፋንም። ስንቶቻችን ለሰዎች እና ለነገሮች ያለንን አመለካከት በCyber ላይ ባየነው እና ባጋጠመን ነገር በአሉታዊ መልኩ ተቀይሯል? ስክሪኖች ይቁጠሩት። ይሄ «የአንተም ልክ ነህ፣ አንተም ልክ ነህ» ምክር አይደለም። ጥያቄ ሊሆን ይችላል።
በሰዎች ሳይኮሎጂ ጥናት «የመንጋ ደመነፍስ» ወይም “tribal instinct” መኖሩን ባለሙያዎቹ ይነግሩናል። ይህ ደመነፍስ በየትኛውም አለም ያለ ሲሆን ራሱን በተለያዩ ቡድኖች መኖር ውስጥ ይገልጣል፤ ክርስቲያን-ሙስሊም፣ ዲሞክራት-ሪፐብሊካን፣ ወዘተ . . .እናም ምንም እንኳን የሚፈጸመው በግለሰቦች ቢሆንም በሌላ አቻ ግለሰብ ላይ ያለማገናዘብ ከሚነገሩ/ከሚደረጉ የቃላት ጥቃቶች ይልቅ በነዚህ አይነት ቡድኖች ላይ የሚወረወሩ ያላግባብ አስተያየቶች የበለጠ ትኩረት አግኝተው ውጥረት ይፈጥራሉ። ቅራኔዎችን ያሰፋሉ። የማይታረቁ ልዩነቶችን ብሎም ጠላትነትን ይፈጥራሉ።
ከነዚህ ንግግሮች ወይም የቃላት ምልልሶች መካከል ግን አብዛኞቹ በውይይት ሊፈቱ የሚችሉ፣ የተለየ እሴት የማይጨምሩ በመሆናቸው በውይይት ሊተዉ የሚችሉ አሊያም ሊለወጡ የማይችሉ እውነታዎች በመሆናቸው ከመቀበል ውጪ አማራጭ የሌላቸው ነገር ግን «ለተቃራኒው» ቡድን እንደመሸነፍ እንዳይወሰድ በእልህ የተያዙ ናቸው። ከነዚህ ውስጥ የታሪክ ልዩነት የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳል ብንል ማጋነን/ሐሰት አይሆንም። አንድ ሰበዝ እንምዘዝ።
የሃገር/መንግስት ምስረታም (State Formation) ሆነ ግዛት ማስፋፋት (Expansion) በሰላማዊ መልኩ ወይም ኃይል ሳይጠቀሙ የሚያሳኩት ነገር አይደለም። ስለዚህ በነዚህ ሂደቶች ወቅት የሚፈጸሙ የተለያዩ ጥፋቶች አሉ። ስማቸው ከተራ ግድያ እስከ ጭፍጨፋ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሊሄድ ይችላል። ይሄ አያከራክርም ምክንያቱም «ጽጌረዳን በሌላ ስም ብንጠራው መዓዛው አይቀየርም።» የሚያከራክረው ጉዳይ ግን ያንን የታሪክ ኹነት የመቀበል ወይም ያለመቀበል እንዲሁም ለአሁኑ ትውልድ ወቀሳ ፍጆታ ማዋል ያለማዋል ላይ ነው።
እዚህ ጋር «አፍቃሬ – የቀድሞ መሪዎች» በእርግጥም አሉ ብለን ብዙ ጊዜ እንዳምን የሚያደርገን ነገር አለ። ያለፉትን መሪዎች የምንከላከልበት (Defend የምናደርግበት) አግባብ ግልጽ አይደለም። ይህ መከላከል የመጣው ከገዢው/ሃገር ከሚያስተዳድረው አካል ቢሆን ኖሮ የሕልውና ጥያቄ የሚያስነሳባቸው ብዙ ሁኔታዎች በመኖራቸው ምክንያቱ ግልጽ ይሆናል። ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን እንደ ግለሰብ በታሪክ የተፈጸፈሙ ድርጊቶችን መካድ ግን (ለያውም ለትምህርት/አካዳሚክ/ ዓላማ ባልሆነበት እና በማስረጃ ባልተደገፈበት ሁኔታ) ባላጋራ/ጠላት መፍጠር እንጂ ምንም የሚያመጣው ለውጥ የለም። እውነቱን ተቀብሎ ያ ስህተት ዛሬ ላይ ጥላውን እንዳያጠላ የሚደረግበት ሁኔታ ላይ መወያየት የተሻለ ረብ አለው።
በሌላ በኩል ደግሞ «የአባት እዳ ለልጅ» የማስተላለፍ አባዜ የተጠናወተው ተዋስኦ ያለመታከት ማካሄድም ተመሳሳይ ውጤት ነው የሚኖረው – ጠላት መፍጠር። በዚህ ዘመን የሚኖር ግለሰብ ተጠያቂነት አሁን ላለበት ዘመን እና ለሚመጣው ትውልድ የተተወ እንጂ ላልነበረበት ጊዜ የሚተላለፍ መሆን የለበትም። ከላይ የተጠቀሰው ያለፈውን ስርዓትና መሪዎች የመከላከል «በሽታው» እንደ ግል ድክመት ሊቆጠር እንጂ ያለፈው አካል ላደረሰው በደል ወይም ስህተት ተጠያቂ የሚያደርገው ሊሆን አይገባም። እነኚህ ሁለቱ በየትኛውም የታሪክ ክርክሮች ውስጥ ሊተገበሩ የሚችሉ ቋሚዎች (Constants) ስለሆኑ መርሆዎች ተደርገው ሊወሰዱ የሚችሉ ናቸው።
ምናልባት ከዚህ አለፍ ስንል በቅርቡ የአውስትራሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር ከእርሳቸው እጅግ በጣም ረዥም ጊዜ በፊት ለተፈጸመው በደል ነባሮቹን የሃገሬዎቹን ሰዎች {the Aborigins} በይፋ ይቅርታ መጠየቃቸው የሚያስተምረን ነገር ይኖር ይሆን? Let’s watch our words and stop making an enemy out of our brethren!!!

ማን አለ እንዳንተ፣ ታማኝ?

በፈቃዱ ዘ ኃይሉ

Befeqadu  Ze Hailu
የሆነ ጊዜ የሰማኋት ቀልድ ትዝ አለችኝ፤ አንዳንድ የተቃዋሚ ተወካዮች ፓርላማ ውስጥ በነበሩበት በዚያ በደጉ ጊዜ ነው አሉ፡፡ አንድ ተወካይ የሻዕቢያ መንግሥት ላይ ሊደረግ ስለሚገባው እርምጃ ሲናገሩ እንዲህ አሉ፤ “አሁኑኑ ገብተን ድምጥማጣቸውን ማጥፋት አለብን፡፡ አለበለዚያ ካደሩ አይቆረጠሙም፤ እነዚያ ወያኔዎችም ያኔ ሲመሠረቱ ሳንጨፈልቃቸው ዝም ብለናቸው ነው ዛሬ አናታችን ላይ…” አሉና ያሉበት ቦታ ትዝ ሲላቸው ድንግጥ ብለው ወደአቶ መለስ መቀመጫ አማተሩ፡፡ አቶ መለስ በጥሞና ያዳምጣሉ፤ ተወካዩ እንደደነገጡ “…ልጨርሰው ወይስ ትጨርሰኛለህ?” አሉ ይባላል፡፡

የሕወሓት/ኢሕአዴግ ወታደሮች አዲስ አበባ ደርሰው “ሲቪል” መንግሥት ከመመሥረታቸው አስቀድሞ “እኩይ” ናቸው በሚል ሲቃወማቸው የነበረ እና እስካሁንም ስክነቱ ያልተለየው አክቲቪስት ታማኝ በየነ ነው፡፡ የታማኝ የአክቲቪስትነት ሪከርድ ከኮሜዲያንነቱ የሚመዘዝ ነው፡፡ በቀልዶቹ ቢጀምርም አሁን ግን በጣም ‹ሲሪዬስ› ነው፡፡

አሁን እነቪኦኤ፣ ዶቸ ቬሊ፣ ኢሳት በየቤቱ እንደሚደመጡት ከደርግ ማክተሚያ ቀደም ብሎ ብዙ ሰው በየቤቱ ‹ድምፂ ወያነ›ን በድብቅ ያደምጥ ነበር፡፡ የፕሮፓጋንዳ ሚዲያዎች አመል ነውና ያው ውሸታቸው አይጣል ነው፡፡ ታዲያ ታማኝ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ቀርቦ የምሩን ሲቀልድ ‹እዚህ ቦታ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር፣ እዚያ ቦታ ደግሞ ይሄን ያክል ሻለቃ ጦር ደመሰስን ይላሉ፡፡ ሲደመር ግን ይሄን ያክላል፡፡ ቆይ እኔ የምለው ወያኔዎቹ የሚደመስሱት ጦር ከጠቅላላ ጦሩ በለጠ እኮ፤ ከየት እያመጡ ነው የሚደመስሱት?› ዓይነት ቀልድ ተናግሮ አላገጠባቸው፡፡ ከዚያ በድምፂ ወያነ መልስ ተሰጠው፤ “ቁጥሩን አዲስ አበባ ስንደርስ እናወራርዳለን” የሚል፡፡ ዛቻ የሽፍትነት ዘመንም አመል ነበረች፡፡
ግንቦት 20/1983 – ኢሕአዴግ አዲስ አበባን ሲረግጥ፣ ሲ ኤን ኤን ካነጋገራቸው ሰዎች አንዱ ታማኝ በየነ ነበር፡፡ “በመሣሪያ ተከበናል፣ ምንም ሠላም የለም…” የሚል ነገር ለጋዜጠኛው ሲነግረው ይታያል፡፡ ታዲያ ታማኝ ሁኔታውን በቀልድ ሲያስታውስ “ጓደኞቼ ከውጪ ደውለው ‹ሲ ኤን ኤን› ላይ አየንህ ሲሉኝ፣ ወዲያውኑ እንግሊዝኛዬ እንዴት ነበር?” አልኳቸው ይላል፡፡

ታማኝ ከአዲሱ ስርዓት ጋር አብሮ መኖር በማይችልበት ሁኔታ የተቀያየመው፣ ካልተሳሳትኩ የወቅቱ ባለሥልጣናት፣ እነታምራት ላይኔ በተገኙበት ስታዲዬም ውስጥ በቀለደው ቀልድ ነው፡፡ እንደማስታውሰው ቀልዱ በማንነት ላይ የተመሠረተ እና ለኢሕአዴግ የማንነት ብያኔ የማይበገር ዓይነት ቀልድ ነው፡፡

ፍቃዱ ማሕተመወርቅ፣ የቀድሞዋ ዕንቁ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ነበር፡፡ በመጽሔትና ጋዜጦች አከፋፋይነትም ይታወቃል፡፡ አሁን መጽሔቱ ተዘግቶ “በታክስ ስም” ፍርድ ቤት እየተመላለሰ ይገኛል፡፡ ፍቃዱ ነጻው ፕሬስ ሲጀመር ጀምሮ ምኅዳሩን ያውቀዋል፤ እናም “እናንተ በደጉ ጊዜ ነው የመጣችሁት” እያለ ይቀልድብኛል፡፡ ያኔ (ማለትም የመጀመሪያው አንቀጼ ላይ ‹ደግ› ባልኩት፣ ለፍቃዱ ግን ‹ክፉ› ግዜ) አንድ ሰው ስርዓቱን የሚያስቀይም ንግግር ሲናገር፣ እንዳሁኑ በሕግ ሥም ፍርድ ቤት አይመላለስም፣ የደረሰበት ይጠፋና ከአራት አምስት ወር በኋላ ተመልሶ ይመጣል፡፡ እንዳይሞት እንዳይሽር ተቀጥቅጦ ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ከዚያ ወዲህ ያሻሻልነው ነገር ቢኖር ፍርድ ቤት የመቅረብ ዕድል መፈጠሩ ነው ማለት ነው፡፡ የሆኖ ሆኖ ይህን ያነሳሁት ታማኝ ላይ የደረሰውም እንዲህ ያለው ነገር ነው ለማለት ነው፡፡

ታማኝ ተሰደደ፡፡ ብዙዎች ሲሰደዱ አቅላቸውን ያጣሉ፡፡ የሀገር ቤት ናፍቆት መመለስ ካለመቻሉ ጋር ተደማምሮ ይሁን፣ የሄዱበት አገር ኢሕአዴግ የማይደርስባቸው ከመሆኑ በተጨማሪ የሚያዩት ነጻነት ስለሚያስቀናቸው አላውቅም ብቻ ጠርዝ ይይዛሉ፡፡ ጥቂቶች ብቻ ሚዛናቸውን በጥፍራቸው ቆንጥጠው ይቆማሉ፡፡ ታማኝ ለኔ ከጥቂቶቹ አንዱ ነው፤ ያውም በረዥም ቆይታ ይህንን ማስመስከር የቻለ፡፡ ታማኝ አሁን አክቲቪዝሙን የሚሠራው ብዙ ጊዜ የቪዲዮ ማስረጃዎችን እያቀረበ ነው፡፡ ቪዲዮዎቹን ዩቱዩብ ላይ ሳያቸው በክምችቱ እቀናለሁ፡፡ ለረዥም ጊዜ የአገር ቤት ጉዳይን እየተከታተሉ፣ ማስረጃዎችን እየሰበሰቡ የመቆየት ፅናት የገቡበትን ጉዳይ ርዝመት እና ክብደት ከመረዳት ይመነጫል፡፡

የማስረጃ ነገር ከተነሳ አይቀር፣ አሁን እነ ታማኝ ማስረጃ ዶት ኮም (masreja.com) የተባለ ድረአምባ ፈጥረዋል፡፡ ድረአምባው በአሁኒቷ ኢትዮጵያ ውስጥ በሕግ የበላይነት ፈንታ ራሳቸው ከሕግ የበላይ ሆነው ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎች ላይ ማስረጃ የሚሰበሰብበት ነው፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ እኔ በይቅርታ አምናለሁ፤ እስከዛሬ አዲሱ ያለፈውን እየቀጣ የመጣበት ዑደት ቢያንስ የእኛ ትውልድ ላይ ቢቆም እያልኩ እመኛለሁ፡፡

ይህንን በተመለከተ ጓደኛዬ ሶሊያና “ይቅርታ ከፍትሕ ጋር መጋጨት የለበትም” ብላ ሞግታኛለች፡፡ ልክ ነች፤ በወቅቱ የሰጠችኝን ምሳሌ ከወቅታዊው ሁኔታ ጋር አዋህጄ ልናገር፤ “‪#‎OromoProtests‬ ላይ ልጇ የተገደለባት እናት የስርዓት ለውጥ ቢመጣ እና ለገዳዩ ወታደር ይቅርታ አድርጊለት ብትባል ፍትሕ ተደረገልኝ ብላ ታምናለች?” በወቅቱ፣ ሶሊም እኔም ጥያቄውን ከመጠየቅ በቀር መልስ መስጠት አልቻልንም፡፡ እርግጥ ነው ልጁ የሞተው የመጣው ለውጥ እንዲመጣ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በምሳሌያችን መሠረት አወዛጋቢው ማስተር ፕላን ቢሰረዝ እንኳን ልጁ የለውጡ እሸት ተጋሪ ላይሆን አልፏል፡፡ ይቅርታ ለአገሪቱ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ያስፈልግ ይሆናል፤ የቤተሰቡን አባል ወይም ወዳጁን ላጣው ግለሰብ ግን ፍትሕ ሆኖ ይሰማዋል ማለት አይቻልም፡፡ የሆነ ሆኖ፣ ለይቅርታውም ቢሆን ማስረጃውን መሰብሰብ አስፈላጊ ነው፡፡ አጥፊው ጥፋቱን እንዳይክድ፣ ይቅርታ ጠይቁኝ ባዩም በማስረጃ እንዲሞግት፡፡

ማስረጃ መሰብሰብ ሕገ-ወጥ መስሏችሁ የምትፈሩ ካላችሁ አትሳሳቱ፡፡ ሕጋዊ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት ራሱ በፀረ-ሙስና ኮሚሽን በኩል አላግባብ የተገኘ ሀብት ካለ በሚል የባለሥልጣናቱን ሀብት ምንጭ ሳይቀር የማጣራት ማንዴት አለው፡፡ ቁርጠኝነቱ ስለሌለ አልተሳካላቸውም፤ እኛ ግን ይሳካልናል፡፡ በየቀኑ ከታችኛው እርከን (ወረዳ) እስከ ላይ ድረስ የምንጠየቃቸውን ጉቦዎች፣ ባለሀብቱና ባለሥልጣናቱ (ሁለቱም አንድ ናቸው) ኢ-ርትዓዊ በሆነ መንገድ የሚያካብቱትን ሀብት፤ ከትላልቆቹ እስከ ትናንሾቹ ሹመኞች በሕዝብ ላይ የሚፈፅሙትን ግፍ፤ ትንንሽሽም፣ ትልልቅም ሠላማዊ ተቃውሞዎች በተነሱ ቁጥር በንፁሐን ዜጎች ነፍስ ላይ የሚሰነዘሩትን የኃይል እርምጃዎች የሚያጋልጡ ማስረጃዎች ባገኘን ቁጥር ለማስረጃ ዶት ኮም በመላክ ለኢትዮጵያችን የወደፊት መልካም ዕጣ ፈንታ ሲባል እንዲከማቹ የበኩላችንን እናድርግ፡፡ ማስረጃዎቹን መሰብሰቡ ሌላው ቢቀር አጥፊዎቹን ስለሚያስፈራቸው በደላቸውን ሊያላሉልን ይችላሉ፡፡
ቪቫ ላ ታማኝ!!!

Source: http://befeqe.blogspot.se/2015/12/Tamagn-and-masreja-dot-com.html