Category Archives: Social and Culture

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው ተመረጡ፤ ፓትርያርኩ በከባዱ ተገሥጸዋል

their-graces-the-gen-sec-elect-abune-sawiros-and-the-gen-mgr-elect-abune-deyoscoros

ለዋና ጸሐፊነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ የደቡብ ምዕ. ሸዋ ወሊሶ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ(በግራ)፤ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ የደቡብ እና ምሥራቃዊ ትግራይ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ(በቀኝ)

•ፓትርያርኩ፣ የአስመራጭ ኮሚቴውን ዕጩዎች ካልተቀበሉ ነባሮቹን ብፁዕ ዋና ጸሐፊ እና ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጅ ለድጋሚ የሦስት ዓመታት የሥራ ዘመን እንደሚያስቀጥላቸው አሳስቧቸው ነበር፤

•“እነርሱንስ ከምታስቀጥሉ እኔን አንሡኝ፤” ያሉት ፓትርያርኩ፣ ማሳሰቢያውን ተከትሎ በምልዓተ ጉባኤው በተሠየመው አስመራጭ ኮሚቴ የቀረቡትን ዕጩዎች በመቀበላቸው፣ በምስጢራዊ የድምፅ አሰጣጥ ሥርዓቱ መሠረት፣ የብፁዕ ዋና ጸሐፊው እና የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ምርጫ ተከናውኗል፤

•ለቀጣይ ሦስት የአገልግሎት ዓመታት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ ድምፅ ከሰጡት 38 የምልዓተ ጉባኤው አባላት የ22ቱን በማግኘት፤ ለቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊነት የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ድምፅ ከሰጡት 38 የምልዓተ ጉባኤው አባላት የ26ቱን በማግኘት በቅዱስ ሲኖዶሱ ተመርጠዋል፤

•በምልዓተ ጉባኤው በአብላጫ ድምፅ የተመረጡት፣ አዲሱ ብፁዕ ዋና ጸሐፊ እና ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በሚጻፍላቸው ደብዳቤ ይሾማሉ፤

•ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው፥ የቋሚ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊም ሲኾኑ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳዎችን የማዘጋጀት፤ ውሳኔውንና ትእዛዙን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ለሚመለከታቸው ማስተላለፍና በተግባር ላይ መዋላቸውን እየተከታተሉ ስለአፈጻጸማቸው ለምልዓተ ጉባኤው ሪፖርት የማቅረብ ሓላፊነት አለባቸው፤

•የመላዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥራ አስፈጻሚ የኾኑት ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፥ ከፍተኛ የአስተዳደር አካል የኾነው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ባለሥልጣን እንደመኾናቸው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሚወስናቸውን ጉዳዮች በሕገ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ይፈጽማሉ፤ ያስፈጽማሉ፤ መምሪያዎችንና ድርጅቶችን ኹሉ በበላይነት ይመራሉ፤ ማንኛውም ንብረት፣ የገንዘብ ገቢና ወጭ በቤተ ክርስቲያኒቱ የፋይናንስና የንብረት አስተዳደር ደንብ፣ በሕግ ፊት ተቀባይነት ባለው የሒሳብ አያያዝ ሥርዓት መከናወኑን ይከታተላሉ፤ ይቆጣጠራሉ፤ በየዓመቱ በርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም፣ ዕቅድ ክንውናቸውን ያቀርባሉ፤ ሲፈቀድም ተግባራዊ ያደርጋሉ፤

•ፓትርያርኩ የጥዋቱ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ሲጀመር፣ ከመንበራቸው ተነሥተው፡-“አባቶቼ፣ ወንድሞቼ፥ ይቅርታ አስቀየምኋችኹ” ብለው ትላንት በምርጫው ሒደት ላይ ለፈጠሩት መስተጓጎል የተጸጸቱ መስለው ቢታዩም፣ ከጥቂት ቆይታ በኋላ ተመልሰው ደግሞ፤ “ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስንና ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስን አውጡልኝ” በማለታቸው ምልዓተ ጉባኤውን በእጅጉ አሳዝነዋል፤ ይህም ከባድ ተግሣጽም አስከትሏባቸዋል፤

Abune Matias I

•ምልዓተ ጉባኤው ከስሕተታቸው የማይማሩትን ፓትርያርኩን በሚከተለው ቃል ነበር የገሠጻቸው፡- “የእርስዎ መሠረታዊ ችግር፣ ይህችን ቤተ ክርስቲያን አያውቋትም፤ ለ35 ዓመታት ውጭ ስለኖሩ የአህጉረ ስብከቱን ይኹን የቤተ ክህነቱን የየዘርፍ ሥራዎች አያውቋቸውም፤ ባልዋሉበትና ባላወቁት ሓላፊነት በመቀመጥዎ ሕግንና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገው መሥራት አልቻሉም፤ የሚያሳዝነው፥ በዚኽች ቤተ ክርስቲያን ላይ እጁን ያነሣ አካል አኹንም እርስዎን ሾመብን፤ አኹንም ከጀርባ ኾኖ ያበጣብጠናል፤ ወደ ሰላም፣ ወደ ልማት፣ ወደ ዕድገት እንዳትሔድ፤ ዘወትር የብጥብጥ ዐውድማ እንድትኾን እየሠራ ያለ አካል መኖሩን እኛም እናውቃለን፣ ሕዝቡም ያውቃል፡፡”

•ምልዓተ ጉባኤው ለቀጣይ ስድስት ወራት(ከግንቦት እስከ ሐምሌ እና ከነሐሴ እስከ ጥቅምት) በቋሚ ሲኖዶስ አባልነት የሚያገለግሉ የስድስት ብፁዓን አባቶች ምርጫም አካሒዷል፡፡ ከግንቦት እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሰላማ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፤ ከነሐሴ እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2009 ዓ.ም.፡- ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፣ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል እና ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እንዲያገለግሉ በቅዱስ ሲኖዶሱ ተመርጠዋል፡፡
ምንጭ፡-ሐራ ዘተዋሕዶ

ሕገ መንግሥቱን አልተቀበሉም ተብለው ከዳኝነት የተሰናበቱት የሕግ ባለሙያ የጥብቅና ፈቃድም ተከለከሉ

ታምሩ ጽጌ

•ክልከላውን በመቃወም ወደ ሰበር እንደሚሄዱ ገልጸዋል

Ethiopian minstry of Jstice

በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ከ2006 ዓ.ም. ጀምሮ በዳኝነት ሲሠሩ የነበሩትና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ‹‹ለሕገ መንግሥቱ ታማኝ ሆነው አልተገኙም›› በማለት ጥር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ከዳኝነት ሥራቸው እንዲነሱ ያደረጋቸው የሕግ ባለሙያ፣ የጥብቅና ፈቃድም መከልከላቸውን ገለጹ፡፡
የዳኞች የሥነ ምግባር ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ ላይ በተደረገ ውይይትና የአገሪቱ መሠረታዊ ፖሊሲና ስትራቴጂ ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር በተደረገ ውይይት ላይ፣ ባደረጓቸው ንግግሮች ወይም በሰጡት ሐሳብና በ1997 ዓ.ም. ምርጫን አስመልክተው የተናገሩትን በመጥቀስ፣ ‹‹ለሕገ መንግሥቱ ታማኝ አይደሉም›› ተብለው ከዳኝነት ሥራቸው የተነሱት አቶ ግዛቸው ምትኩ ናቸው፡፡ በስምንት ዓመታት የዳኝነት አገልግሎታቸው ዘመን ምንም ዓይነት የሥነ ምግባር ጉድለት ፈጽመው እንደማያውቁ የሕግ ባለሙያው አቶ ግዛቸው ይናገራሉ፡፡

አቶ ግዛቸው ከዳኝነት ሥራቸው ከተነሱ በኋላ በጥብቅና አገልግሎት ሥራ ለመቀጠል ፈቃድ ለመውሰድ ለፍትሕ ሚኒስቴር የጥብቅና ፈቃድና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ጥያቄ አቅርበው እንደነበር ገልጸዋል፡፡
ዳይሬክቶሬቱ የሰጣቸው አጭር መልስ ከዳኝነት የተነሱት ‹‹ሕገ መንግሥቱን አልቀበልም›› ብለው መሆኑን ጠቅሶ፣ ለፍትሕ ሥራ አካሄድ መልካም ሥነ ምግባር አስፈላጊ እንደሆነ በመግለጽ ፈቃድ እንደ ከለከላቸው ተናግረዋል፡፡ አቶ ግዛቸው የጥብቅና ፈቃድና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ጥብቅናውን የከለከላቸው፣ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ፈቃድ አሰጣጥና ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 199/1992 ከሚደነግገው ውጪ መሆኑን፣ የዳኞች አስተዳደር ጉባዔ በእሳቸው ላይ ያስተላለፈውን ውሳኔና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከዳኝነት ያነሳበትን ዝርዝር ማስረጃ ዳይሬክቶሬቱ ሳይመረምርና ትችት ሳይሰጥበት መሆኑን ጠቅሰው ለፍትሕ ሚኒስትሩ አቤቱታ ያቀረቡ ቢሆንም፣ ሚኒስትሩም የዳይሬክቶሬቱን ውሳኔ አፅድቀው እንደከለከሏቸው አቶ ግዛቸው አስረድተዋል፡፡

የጥብቅና ፈቃድ መከልከላቸው አግባብ አለመሆኑንና የጥብቅና ፈቃድ ለማግኘት ሕገ መንግሥቱን አለመቀበል ፈቃድ እንደሚያስከለክል እንደ መሥፈርት አለመቀመጡን፣ ለስምንት ዓመታት በዳኝነት ሲሠሩ አንድም ጊዜ በሥነ ምግባር ጉድለት ተጠይቀው እንደማያውቁና ለዳኝነት ሲመለመሉ በዋና መሥፈርትነት ተቀምጦ የነበረውን ሕገ መንግሥቱን ማክበርና ማስከበር ሲተገብሩ መቆየታቸውን አስረድተዋል፡፡ ነገር ግን ከተመደቡበት የዳኝነት ሥራ ውጪ በተደረጉ ውይይቶች ላይ በሰነዘሩት ሐሳብ ‹‹ሕገ መንግሥቱን አልተቀበልክም›› ተብለው ከዳኝነት ሥራቸው በመነሳታቸው፣ የጥብቅና ፈቃድ ሊከለከሉ እንደማይገባ በመግለጽ ክስ መመሥረታቸውን ጠበቃቸው አቶ ዳማው አስፋው ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ያቀረቡትን የክስ ማመልከቻ ሲመረምር የከረመው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አምስተኛ ፍትሐ ብሔር ችሎትም፣ የሕግ ባለሙያው የጥብቅና ፈቃድ ቢሰጣቸው የሚገናኙት ወይም አገልግሎት የሚሰጡት ወደ ዳኝነት አካሉ ሄደው መሆኑን ጠቅሶ፣ ‹‹ለፍትሕ ሥራ አካሄድ መልካም ሥነ ምግባር ያስፈልጋል›› በማለት የጥብቅና ፈቃድና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ጥብቅና ፈቃድ የከለከለበትን መንገድ ተቀብሎ ጥያቄያቸውን ውድቅ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

ለሕገ መንግሥቱ ታማኝ አለመሆን በየትኛውም ምዘና ለጥብቅና ፈቃድ ክልከላ ሊውል እንደማይችል የሚናገሩት ጠበቃቸው አቶ ዳማው፣ በሥነ ምግባር ደንቡ አንድ ጠበቃ በተደራቢነት የፖለቲካ ሥራ ሊሠራ እንደሚችል አስቀምጦ እያለ፣ ‹‹አንድ የሕገ መንግሥት አንቀጽ እንዲሻሻል ጠይቀሃል›› በሚል፣ ከዳኝነት የተነሳን ሰው በፍትሕ ሥራ ውስጥ ገብቶ እንዳይሠራ ፈቃድ መከልከል ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሕገ መንግሥቱ አንድ ሰው ሙያውን መርጦ መሥራት እንደሚችል ደንግጎ እያለ፣ ‹‹ይህንን አመለካከት ይዘህ ላንተ ፈቃድ አልሰጥም›› ማለት፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 25 ላይ ለዜጎች እኩልነት የሰጠውን ድንጋጌ መቃረንና በዜጎች መካከል ልዩነት መፍጠር መሆኑንም አክለዋል፡፡

የዳኞች አስተዳደር ጉባዔም በውሳኔው ያስታወቀው አንድ ዳኛ በሥራ ላይ ባለበት ወቅት የራሱ የሆነ የፖለቲካ አመለካከት ሊኖረው ቢችልም፣ ያንን አመለካከቱን በዳኝነት ሥራው ላይ ሊያንፀባርቅና ወገንተኛ ሊሆን እንደማይችል እንጂ፣ ከሐሳብ ሊነፃ እንደማይችል መግለጹን ጠቁመዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም አቶ ግዛቸው ከዳኝነት ኃላፊነታቸው ባነሳበት ወቅትም፣ ስለወደፊት የጥብቅና ሥራቸው ምንም ያለው እንደሌለና አንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ከጥብቅና ፈቃድ ጋር ተያይዞ ጥያቄ ሲያነሱ ምክር ቤቱ በዝምታ ማለፉን አስታውሰዋል፡፡ ይኼ የሚያሳየውም በአንድና በሁለት ስብሰባዎች ላይ በተሰነዘረ ሐሳብ ከሁሉም የሕግ ሥራዎች ላይ መነሳት ሳይሆን፣ ጉባዔው ባመነበትና ጠቅሶ ያሳለፈውን ውሳኔ ማፅደቅ ብቻ እንደሆነም አክለዋል፡፡ የሥር ፍርድ ቤት ውሳኔም ሕገ መንግሥቱን የሚቃረንና ተገቢነት የሌለው በመሆኑ፣ አቤቱታቸውን ለፌዴራል ሰበር ሰሚ ችሎት እንደሚያቀርቡ የአቶ ግዛቸው ጠበቃ አቶ ዳማው ተናግረዋል፡፡

ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› ማለት ሊቀር ነውን?

Daniel Kibret

ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርኩን እንደራሴ ሹመት በተመለከተ ለመወያት የያዘው አጀንዳ የመንግሥት ተወካይ ባለበት እንዲታይ መወሰኑን ዛሬ ጠዋት ሰማን፡፡ ከብጹዐን ጳጳሳት በቀር ካህናትና ቆሞሳት እንኳን የማይገቡበት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አማኝ ይሁን ኢአማኒ፣ ሙስሊም ይሁን ክርስቲያን የማይታወቅ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝበት መጋበዙ የደረስንበትን የውርደት ደረጃ የሚያሳየን ነው፡፡

በአንድ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ወሳኝ አካል መሆኑን ስናስበው፤ በሌላ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የሚደረገው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ነው፤ ውሳኔውም በሐዋርያት ሥራ እንደተገለጠው ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› የሚባልበት ነው(የሐዋ. 15፣29) የሚለውን ስናየው ‹የመንግሥት ተወካይ ይኑርልን› የሚለውን ውሳኔ ኢሃይማኖታዊ ነው ያሰኘዋል፡፡ ለአንድ የሲኖዶስ ጉባኤ የመንፈስ ቅዱስ መገኘት አልበቃው ብሎ ነው የመንግሥትን ተወካይ የሚጋብዘው? ‹ሱባኤ ይዘን፣ ጸሎት አድርገን፤ አንድ ገዳም ወርደን፣ ከእግዚአብሔር ጋር መክረን› አይደለም ይሉን አባቶቻችን፡፡ ‹የመንግሥትን ተወካይ ጋብዘን› ነው ያሉን፡፡ እንዲያውም ቀኖናው የሊቀ ጳጳሳቱ(ፓትርያርኩ) ጉዳይ ሲታይ ‹በመቀመጫቸው መካከል አንድ ወንበር አስቀምጠው፣ ቅዱስ ወንጌሉን በዚያ ላይ አኑረው፣ ሊቀ ጳጳሳቱ በፊታቸው ተቀምጦ፣ አንድነት ተነሥተው በሩን ዘግተው ይጸልዩ፤ የተሰበሰቡበትንም ጉዳይ በሥውር(በኅቡእ) ይመርምሩ› ነው የሚለው(ፍ.ነ. ዐ.168)፡፡ እንዴት ተደርጎ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የሚታየው? አግዚአብሔር ያየናል የሚለው ጠፍቶ ታዛቢ ቢያስፈልግ እንኳን የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ለታዛቢነት አይበቁም? ቅዱስ ጳውሎስ ‹በወንድሞች መካከል ሽማግሌ ሊሆን የሚችል አንድ አስተዋይ ሰው በእናንተ ዘንድ አይገኝምን?› (1ኛቆሮ. 6፣5) ያለው ለዚህ ጊዜ አይሆነንም?

በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝ መጋበዙ በአንድ በኩል የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዕልና የሚነካ በሌላ በኩልም ሕገ መንግሥቱን የሚጥስ፤ በመጨረሻም ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚያፈርስ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያለ ማንም ጣልቃ ገብነትና ታዛቢነት የራስዋን ጉዳዮች በራስዋ ሕግጋት፣ ቀኖናና ሥርዓት መሠረት የመወሰን መብት አላት፡፡ አባቶቻችን ከንጉሥ ሐርቤ ዘመን ጀምረው ከግብጽ ሲኖዶስ ጋር ሲሟገቱ የኖሩት ይህን ሉዐላዊነት ለቤተ ክርስቲያናቸው ለማስገኘት ነው፡፡ ጳጳሳትን ለማግኘት የግብጽ ሡልጣኖች መለማመጥ፣ የግብጽንም ፓትርያርኮች መለመን ሰልችቷቸው፡፡ ከግብጽ ቀድማ ክርስትናና የተቀበለች ሀገር፣ የራስዋን ጉዳይ ለመወሰን አለመቻሏ አስደናቂ ስለሆነባቸው፡፡ ከቤተ ክርስቲያንዋ ታላቅነትና ከሀገሪቱ ክብር ጋር ስላልተመጣጠነላቸው፡፡

ዛሬ ያ ሁሉ ተረስቶ መንግሥትን በገዛ ፈቃዳቸው ‹አንተ በመካከላችን ካልተገኘህ አንሰበሰብም› የሚሉ አባቶች መጡ፡፡ ቀደምት አበው ‹አንተ ከኛ ጋር ሁን› የሚሉት ፈጣሪያቸው ነበር፡፡ ዘመን ተቀየረ፡፡ በቀደመው ጊዜ ‹መንግሥት ለምን በጉዳያችን ውስጥ ይገባል?› ነበር ክርክሩ፡፡ ‹አሁን መንግሥት ከሌለ ይህንን አጀንዳ አናይም› የሚባልበት ዘመን ላይ ደረስን፡፡ የፓትርያርክ እንደራሴ ጉዳይ የሃይማኖት ጉዳይ ነው፡፡ እንደራሴውም የሚፈጽመው ሃይማኖታዊ ጉዳዮችን ነው፡፡ የሥልጣን ክልሉም በቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን ክልል ነው፡፡ ታድያ ለምንድን ነው መንግሥት ያስፈለገው? ይህንን ጥያቄ ፓትርያርኩ ጠይቀውት ይሆናል፡፡ እንደመከራከሪያ ቢያቀርቡት አይገርምም፤ ቢያሳዝንም፡፡ የምልዐተ ጉባኤው መቀበል ግን ሕመም ነው፡፡

መንግሥትስ ቢሆን ምን ብሎ ነው ተወካይ የሚልከው? ምናልባት ‹ጠሩኝ፣ ሄድኩ› ካላለ በቀር፡፡ ሕገ መንግሥታችን መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ እንደማይገባ በግልጽ እየደነገገ እንዴት አድርጎ ነው በቀኖናዊ ስብሰባ ላይ የሚገኘው? ውሳኔውንስ ከየትኞቹ የቀኖና መጻሕፍት ጋር ሊያገናዝብ ነው? በጉባኤው የሚኖረውስ ሚና ምን ሊሆን ነው? ምን ዓይነት ወኪልስ ነው የሚወክለው? በየትኛው ሥልጣንና ሕግ ነው የሚገኘው? የዚህ ዓይነቱ አሠራርስ መጨረሻው ምን ይሆናል? በጉባኤው ላይ የሚተላለፈው ውሳኔ የማን ውሳኔ ነው? ‹የእኛና መንፈስ ቅዱስ› ወይስ ‹የእኛና የመንግሥት›? መንግሥትም ጉዳዩን ሊያስብበት ይገባል፤ ‹ሲጠሩት አቤት› ሳይሆን ‹ሲጠሩት ለምን?› መሆን አለበት፡፡

የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ኤጲስ ቆጶስ በዚህ ዓለም መኳንንት ርዳታ አንዳይቆም ያዝዛል፡፡ በእምነቱና በእግዚአብሔር ቃል ብቻ እንዲጸና፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ 176፤ረስጠብ 21) በዲድስቅልያም ላይ ‹ከቤተ ክርስቲያን ሹሞች በቀር ሕዝባዊ አይፍረድ› ይላል (ዐንቀጽ 71)፡፡ ታድያ በምን ሕግ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤውን የሚያደርገው?

ዛሬ እንደዋዛ የሚከፈተው በር ነገ እንዝጋህ ቢሉት አስቸጋሪ ነው፡፡ አንድ አባት የመንግሥት ተወካይ ይገኝልኝ ባለ ቁጥር የሚፈቀድ ከሆነ፤ ነገ ደግሞ ወንድሜ ባለበት፤ እናቴ ባለችበት፤ ሐኪሜ ባለበት፣ ፖሊስ በተገኘበት ይሄ አጀንዳ ይታይ የሚል ነገር መስማታችን አይቀሬ ነው፡፡ ጋባዡም፤ ተጋባዡም ቆመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ መቼም እንደዘንድሮ የእንጦንስና ጳውሊ ራእይ በተግባር የታየበት ዘመን የለም፡፡

ሀገር አቀፉ የ12ኛ ክፍል ዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ተደረገ

(አዲስ ሚዲያ) ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሐሙስ ግንቦት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የነበረው ሀገር አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግቢያ የሆነው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተቋረጠ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር መገለጫውን በድረ-ገፁ እንዳስታወቀው ከሆነ፤ ብሔራዊ ፈተናው እንዲቋረጥ የተደረገበት ምክንያት ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ኮድ 14 የእንግሊዘኛ ፈተና በመውጣቱ ነው፡፡ ሚኒስተሩን አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በመስሪያ ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ሌሎች ፈተናዎች ላለመውጣታቸው ምንም ዓይነት ማረጋገጫ ባለመኖሩ ሁሉም ፈተናዎች እንዲቋረጡ መደረጉን በመጠቆም፤ ተማሪዎችን እና ወላጆቻቸውን ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡

ENEA cancelled press released, 2016

ይሁን እንጂ እንዲቋረጥ የተደረገው የዚህ ዓመት የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ሌላ ፈተና በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚዘጋጅ ከመግለፅ ውጭ፤ መቼ ሊሰጥ እንደተወሰነ የተገለፀ ነገር የለም፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የፈተናውን መቋረጥ አስመልክቶ ዛሬ አራት ኪሎ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤ ፈተናው ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ለምን እና እንዴት ወጥቶ ሊሰራጭ እንደቻለ እና ለተፈጠረው ችግር ማን ኃላፊነት መውሰድ እንዳለበት ከመግለፅ ተቆጥቧል፡፡

ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ እንግሊዘኛ ኮድ 14 ከመፈተኛው ቀን አስቀድሞ ወጥቷል ቢሉም፤ በተመሳሳይ ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. የሂሳብ ትምህርት የተፈጥሮ ሳይንስ እና ማኀበራዊ ሳይንስ የሂሳብ ትምህርት ፈተናም በተመሳሳይ መልኩ ከነ መልሶቻቸው በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨታቸው ታውቋል፡፡ የአዲስ ሚዲያ ምንጮች ከሆነ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጀመር የነበረው ሁሉም የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተናዎች ግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም.በተለይ በኦሮሚያ ክልል ለወራት ትምህርታቸው የተስተጓጎለባቸው ተማሪዎችን ታሳቢ ሳያደርግ የፈተናውን መሰጠት በሚቃወሙና ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ከመፈተኛው ቀናት አስቀድሞ ፈተናውን አዘጋጅቶ ከሚያሰራጨው ትምህርት ሚኒስቴር፤ ሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ ቢሮ እንደወጣ ጠቁመዋል፡፡

NEAEA,Ethiopia

በተመሳሳይም ባለፈው ሳምንት የተሰጠው የ10ኛ ክፍል ፈተናም እንደ 12ኛ ክፍሉ ባይሆንም አስቀድሞ መውጣቱና በተወሰነ መልኩ መሰራጨቱ ቢገለፅም፤ እንደ 12ኛ ክፍል ፈተና በማኀበራዊ ሚዲያ ባለመሰራጨቱ እና በገለልተኛ አካል ይፋ ባይገለፅም፤ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ግን የ10ኛ ክፍል ፈተናም ወጥቶ መሰራጨቱን አስተባብለዋል፡፡ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ከዛሬው መግለጫና የወጣው ፈተናው በማኀበራዊ ሚዲያ ከመሰራጨቱ በፊት ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን በኢቢሲ ዜና እወጃ “ፈተናው ተሰርቆ ወጥቷል የሚባለው መረጃ ሐሰት ነው፤ ስለዚህ ተማሪዎች ለዛሬው ፈተና ተረጋግተው እንዲዘጋጁ” የሚል ማሳሰቢያ መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡

ለፈተናው ቀድሞ መውጣትና በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨት ዋነኛ ምክንያት፤ ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለ5 ተከታታይ ወራት የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን አዲሱ የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ተቃውሞ በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ ክልል የወሰደውን የኃይል እርምጃ ተከትሎ በተፈጠረ አለመረጋጋት ፈተናው እንዲራዘም የቀረበው የተማሪዎቹና የወላጆቻቸው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ የተወሰደ የአፀፋ እርምጃ እንደሆነ ፈተናውን ካሰራጩት አካላት ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ወጥቶ የተሰራጨበትም ሆነ ፈተናው በሀገር አቀፍ ደረጃ ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ሲደረግ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የሽብርተኝነት ክስ ተመሰረተበት

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

Getachew Shiferaw

የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው ክስ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡

በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የዕንቁ መፅሔት አምደኛ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ፣ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መስራች አባልና የጊዜያዊ አስተባባሪው አመራር እንዲሁም አዲስ ሚዲያ ተባባሪ እና በራሱ የማኀበራዊ ገፅ ብሎገር እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- EHRP.