Tag Archives: Addis Ababa City Adminstration

በአዲስ አበባ ሰሚት አካባቢ ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ

በአዲስ አበባ ከተማ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ።

Addis Ababa Poor construction

የአዲስ አበባ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ እንደገለጹት፥ የህንፃ መደርመስ አደጋው ዛሬ ማለዳ 12 ሰአት ላይ ነው በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሰሚት አካባቢ የተከሰተው።

ባለ 5 ፎቅ ህንፃው ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀ ቢሆንም ከታችኛው ወለል ላይ ሁለት ባንኮች አገልግሎት መስጠት ጀምረው እንደነበርም አቶ ንጋቱ ጠቁመዋል።
የመደርመስ አደጋው በስራ ሰዓት ቢደርስ በሰው ላይ ከባድ አደጋ ሊያደርስ ይችል እንደነበርም ነው ባለሙያው ያነሱት።
የባንኮቹ የጥበቃ ሰራተኞች ህንፃው ከመድርመሱ በፊት ከባድ ድምፅ በመስማታቸው ከአደጋው ሊያመልጡ ችለዋል።

ምንጭ፡-ፋናቢሲ

የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ አድማ፤ ታሪክ ራሱን ሊደግም ይሆን?

ብስራት ወልደሚካኤል

የዛሬ 42 ዓመት በየካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም. በቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴ ዘመን በሊትር የ10 ሳንቲም የነዳጅ ጭማሪን (50 በመቶ ጭማሪን)ተከትሎ የታክሲ ባለንብረቶች እና ሾፌሮች የታሪፍ ማሻሻያ ጭማሪ ቢጠይቁ ተቀባይነት በማጣታቸው የታክሲ አድማ ተደርጎ ነበር፡፡ በተመሳሳይ ዕለት የኢትዮጵያ መምህራን ማኀበር በጠራው አድማ የሀገሪቱ መምህራን በሙሉ ስራ አቁመው ነበር፡፡ ይህም እየተቀጣጠለ ከአዲስ አበባ ወደ ሌሎች ከተሞች ሳይዳረስ በሚል የወቅቱ መንግሥት የነዳጅ ጭማሪውን መሰረዙን ይፋ አደረገ፡፡

Addis taxi strike

ይሁን እንጂ ተቃውሞው እንደሰደድ እሳት ተቀጣጠለ፤ከዛም መፍትሄ ይሆናል በሚል የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ፀሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተወለድ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የካቲት 21 ቀን 1966 ዓ.ም. ከስልጣናቸው እንዲሰናበቱ ተደረ፡፡ ይሄም መፍትሄ አልሆነም፤ይልቅ የመምህራን ማኀበርና የታክሲ የተቃውሞ አድማ ወደ ወታደሩ ዞረ፤ከዛም ንጉሱንም ዘውዳዊ ስርዓቱን ላይመለስ እስከነ አካቴው አሰናበተው፡፡ ልብ በሉ ይህ ሁሉ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የነበረ የአዲስ አበባ ታክሲ አድማ ምን እንዳስከተለ፡፡ ይሄ ሁሉ 4ኛ ወሩን ያስቆጠረውና እስካሁንም የቀጠለውን የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ በተጨማሪ መሆኑ ነው፡፡ አሁን ደግሞ በጎንደርም ተቃውሞዎች እያገረሹ መንገድ እስከመዝጋት እንደደረሱ እየተሰማ ነው፡፡

ዛሬ ከ42 ዓመት በኋላ በዘመነ ኢህአዴግ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የመንግሥትን አዲስ መመሪያ በመቃወም የተደረገው የታክሲ አድማ በጠዋቱ ጀምሯል፡፡ ይህ እስከተፃፈበት ድረስም የአዲስ አበባው የታክሲ አድማ እንደቀጠለ ነው፡፡ አድማውም ለ ሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚደረገ የታቀደ ቢሆንም፤ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ ግን አድማው ሊቀጥል እንደሚችል ነው፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ የአዲስ መመሪያ ዋና ሰለባዎች የታክሲ ሾፌሮች በመሆናቸው ነው፡፡

Flyers

New Addis Ababa Transport regulation

እስካሁን ባለው አድማም በከተማው የመንግሥት የመስሪያ ቤት የትራንስፖርት አገልግሎት አውቶቡስ፣ የግለሰቦች የጭነት ተሸከርካሪዎች (በግድ ተሳፋሪ እንዲጭኑ እየጠደረጉ) ከሚሰጡት አገልግሎት በስተቀር የተለመዱት የሚኒባስ ታክሲዎች አድማ መትተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ህዝብ ብዛትና ከተጠቃሚው ብዛት እንዲሁም ቀድሞም ከነበረው የትራንስፖርት እጥረት አንፃር የታክሲዎች አድማ የሚያስከትለው ተፅዕኖ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡መንግሥት በስሩ ባሉ መገናኛ ብዙኃን በጠዋት ዜና እወጃው የአዲሱን የአዲስ አበባ ትራንሰፖርት ደንብ መመሪያ ትግበራ ለ3 ወራት ማራዘሙን ቢገልፅም፤የታክሲዎች አድማ ግን ቀኑን ሙሉ ቀጥሎ ውሏል፡፡

ምንም እንኳ ሀገር አቀፍ ምርጫ ከተደረገ 100 ቀናት ቢያልፉትም፤ የዛ “ምርጫ” ኢህአዴግ 100% የህዝብ ድምፅ “በምርጫ” አሸንፊያለው የሚለው መዝሙር ሳያባራ በየአቅጣጫው ጠንከር ያለ ተቃውሞ መምጣቱ ምናልባትም አማራጭ ሐሳብ ያለመኖርና እንዲኖር ያለመፈለጉ ያመጣው መዘዝም ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በርግጥ የዛ ተዓምረኛው “ የ100% ምርጫ” ውጤት መዘዝ ገና ብዙ ክስተቶችን በመላው ሀገሪቱ ሊያስተናግድ እንደሚችልም ይጠበቃል፡፡

የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ ተቃውሞ አድማ ወደ ሌሎች የግልና መንግሥታዊ ተቋማት አድማሱን አስፍቶ የዛሬ 42 ዓመቱን ታሪክ ይደግመው ይሆን?

Public service Bus as a taxi in Addis

በተለይ ከዓለም ገበያና ሀገሪቱ ነዳጅ ከገዛችበት 365 % (ነዳጁ ከተገዛበት ወደ 4 እጥፍ) ክፍያ የተጫነበት ተጠቃሚው ህዝብ ትክክለኛ መረጃ ቢኖረው ከታክሲ አድማው ይልቅ የተሳፋሪው አለመቅደሙ አስገራሚ ቢሆንም፤የዛሬው የታክሲዎች አድማ ሌላም ቁጣ ይቀሰቅስ ይሆን ወይስ እንደተለመደው በማስፈራሪያ አሊያም ደንብ ቁጥር 208/2003 ተከትሎ ወጥቷል የተባለው አዲሱ መመሪያ ተሰርዟል በሚል ወደስራቸው ይመለሱ ይሆን?

ሁሉንም ጊዜ ያሳየናል፡፡

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል 6 ወር ሲፈረድበት፤ ፋንቱ ዳኜ ከመኖሪያ ቤቱ ተወስዶ መታሰሩ ተሰማ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የአዲስ አበባ ወጣቶች አመራር የነበረውና በአሁን ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወጣት ስንታየሁ ቸኮል 6 ወር እስራት ተፈረደበት፡፡ ወጣት ስንታየሁ ቄራ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ ደህንነቶች ተወስዶ ከታሰረ በኋላ የፌደራሉ ፍርድ ቤት ቄራ ምድብ ችሎት ቀርቦ የአካባቢው የኢህአዴግ ካድሬዎች ከመሰከሩበት በኋላ እንደተፈረደበት ታውቋል፡፡

ስንታየሁ ቸኮል

ስንታየሁ ቸኮል

ፍርድ ቤቱ ለቀረበበት ክስ መከላከያ ምስክር አሊያም የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ቢጠይቀውም፤ ወጣት ስንታየሁ “ከሳሼም፣መስካሪየም፣ፈራጁም ኢህአዴግ ስለሆነ የመከላከያ ምስክር ብዬ ሰዎችን አላንገላታም፣የቅጣት ማቅለያም አላቀርም፤የፈለጋችሁትን ፍረዱ” ሲል ችሎት ላይ መናገሩ ትውቋል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ በችሎት የተናገርውና የቀረበበት ክስ ከዓመት በላይ የሚያስቀጣ ቢሆንም፤ ፍርድ ቤቱ በ6 ወር እስራት እንዲቀጣ መፍረዱ ታውቋል፡፡

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከአንባቢ ውጭ የተደረጉ ጋዜጦችን መፈክር ይዞ

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከአንባቢ ውጭ የተደረጉ ጋዜጦችን መፈክር ይዞ

ስንታየሁ ቸኮል ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም ከቀድሞው አንድነት ፓርቲ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ የፀጥና ደህንነት ኃይሎች ተደጋጋሚ ሲታሰርና ሲደበደብ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ በተደረጉ በተለያዩ የስርዓቱ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የስርዓቱን ድርጊት የሚያመለክቱ ልዩ መፈክሮችን ይዞ በመውጣትም ይታወቃል፡፡

ወጣት ፋንቱ ዳኜ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ ቅስቀሳ ላይ እያለ የተነሳው

ወጣት ፋንቱ ዳኜ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ ቅስቀሳ ላይ እያለ የተነሳው

በተያያዘ ዜና ሰኞ ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ኦዲትና ኢንስፔክሽን ፀሐፊ የነበረው ፋንቱ ዳኜ ሳሪስ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች ተይዞ መታሰሩ ታውቋል፡፡ አቶ ፋንቱ በወቅቱ ሳሪስ ፖሊስ ጣቢያ ቢወሰድም እስካሁን ለምን እንደተያዘ እና እንደታሰረ የተገለፀ ነገር እንደሌለ ለማወቅ ተችሏል፡፡ወጣት ፋንቱ ከቀድሞ የአንድነት ፓርቲ ጠንካራ ወጣት አመራሮች መካከል አንዱ እንደነበር ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

ፖሊስ በ”በሁከትና ብጥብጥ” ተጠርጣሪዎች ላይ ሦስት መዝገብ አደራጅቻለሁ አለ

•እነ ወይንሸት ለሁለተኛ ጊዜ 6 ቀን ተቀጥሮባቸዋል
•”ወይንሸት ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ስታሸብር ነበር” ፖሊስ

ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ላይ “ሁከትና ብጥብጥ አስነስታችኋል፤ ተካፍላችኋልም” በሚል ፖሊስ ባሰራቸው ሰዎች ላይ ሦስት የተለያዩ መዝገቦች ማደራጀቱን አስታውቋል፡፡

protest 2

ሚያዝያ 22 ቀን 2007ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የቀረቡ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ሌሎች በዕለቱ የተያዙ ሰዎችን በተመለከተ ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ እንደገለጸው፣ ፖሊስ የራሱን ቡድን በማዋቀር ተጠርጣሪዎችን በሦስት መዝገቦች ስር እንደየተሳትፏቸው አደራጅቻለሁ ብሏል፡፡ በዚህ መሰረት በሶስተኛው መዝገብ ላይ ያካተታቸውን በርካታ ታሳሪዎች አጣርቶ መልቀቁን የገለጸው ፖሊስ፣ በሁለተኛውና በአንደኛው መዝገብ ላይ ባሉት ተጠርጣሪዎች ግን ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጹዋል፡፡
አንደኛው መዝገብ ላይ በእነ ወይንሸት ሞላ መዝገብ 5 ሰዎች የተካተቱ ሲሆን አራቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፤ አንደኛዋ ተጠርጣሪ ደግሞ ፖሊስ የፓርቲው አባል እንደሆነች የሚገልጸው፣ እሷ ግን አባል አለመሆኗን የገለጸች መሆኗን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ስለሆነም በዚህ መዝገብ የተካተቱት ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ማስተዋል እና የፓርቲው አባል ያልሆነችው ቤተልሄም ይገኙበታል፡፡ ማስተዋል በዛሬው ዕለት ቀደም ብሎ የተሰጠው የቀጠሮ ቀን ስላልደረሰ ፍርድ ቤት አልቀረበም፡፡ ቤተልሄም ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባል ሳልሆን አባል ነሽ እየተባልኩ ምርመራ ይደረግብኛል፤ ሌሊት እየተጠራሁ እመኝ እየተባልኩ ነው›› ስትል ለፍርድ ቤቱ ገልጻለች፡፡

Semayawi-Weyeneshet

በሁለተኛው መዝገብ ላይ ደግሞ 15 ተጠርጣሪዎች ተካትተዋል፡፡ ፖሊስ በዚህ መዝገብ በተካተቱ ተጠርጣሪዎች ላይ ክሱን ሲያሰማ እንዲህ ብሏል፤ “ተጠርጣሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ሲያደርጉ ‹ጠንካራ መሪ እንጂ ጠንጋራ መሪ አንፈልግም›፣ ‹ወያኔ አሳረደን›፣ ‹ፍትህ የለም! በማለት ሁከት እንዲነሳ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡”
የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በምርመራ ወቅት የገጠማቸውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ ያሰሙ ሲሆን፣ በተለይ የሚደረግባቸው ምርመራ ከፓርቲው ጋር የተያያዘ እንጂ ከተጠረጠርንበት ጉዳይ ጋር የተያያዘ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ምርመራው ከጉዳዩ ጋር የሚገናኝ አይደለም፤ ሌሊት ሌሊት እየተጠራሁ ምርመራ ይደረግብኛል፡፡ የፓርቲ አባል መሆን ወንጀል እስኪመስለኝ በፓርቲ አባልነቴ ጫና ይደረግብኛል፡፡ በዚያ ላይ የጤና እከል ገጥሞኛል፤ ህክምና ያስፈልገኛል” ስትል ለፍርድ ቤቱ ያስረዳችው ወይንሸት ሞላ፣ ፍርድ ቤቱ የዋስትና መብት እንዲሰጣት ጠይቃለች፡፡

በሁለቱም መዝገብ የተካተቱት ሁሉም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፖሊስ በበኩሉ በመጀመሪያው መዝገብ ላይ ያሉት እነ ወይንሸት ላይ የምርመራ ስራውን እንዳልጨረሰ በመግለጽ 14 ቀን ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ በተለይ ወይንሸት ሞላ ላይ ፖሊስ፣ “ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ተመሳስላ በመልበስ ስታሸብር ነበር” በማለት ዋስትና እንዳይሰጥና የጠየቀው የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ በሁለተኛው መዝገብ ላሉት ደግሞ 7 ቀን ፖሊስ ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ በሁለቱም መዝገብ ላይ በተመሳሳይ የ6 ቀን ጊዜ በመስጠት ለሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

መንግስት በጠራው ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ወጣቶች እስር አሁንም እንደቀጠለ የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ በትናንትናው ዕለትም ሦስት የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አባላት (አንደኛው አሁን ላይ የሰማያዊ አባል) መታሰራቸው ይታወሳል፡፡
በተያያዘ ዜና ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ሳይጀመርና ከሰልፉ በኋላ ተይዘው የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ቤት ተበረበረ፡፡ ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ትናንት ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ለሁለተኛ ጊዜ ቀርበው የ6 ቀን ቀጠሮ ከተሰጠባቸው በኋላ ምሽት ላይ ቤታቸው መበርበሩንና ንብረቶቻቸው መወሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡

በብርበራው ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በሰላማዊ ሰልፍና በሌሎች አጋጣሚዎች የሚለብሱት የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ የምርጫና ሌሎች ቅስቀሳ ወረቀቶችም ለ‹ምርመራ› ተወስደዋል፡፡
ቤታቸው ለሰዓታት የተበረበረባቸው ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ማስተዋል ፍቃዱ ሲሆኑ ወይንሸት ሞላ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ወረቀቶች፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ ሲዲዎች፣ አርማ የሌለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ (በተናጠል አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የሆነ)፣መጽሐፎች እና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች እንደተወሰዱባት ገልጻለች፡፡ ዳንኤል ተስፋዬ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ በአንድ ላይ ያስጠረዛቸው የፋክትና የአዲስ ጉዳይ እትሞች፣ ሲዲዎችና ካሴቶች ተወስደውበታል፡፡ በተመሳሳይ ኤርሚያስ ጸጋዬ ዴስክ ቶፕ ኮምፒውተር፣ የሰማያዊ ፓርቲ ሰነዶች፣ ሲዲዎች፣ ማስታወሻ ደብተሮችና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች ተወስደውብኛል ብሏል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር ዋስትና የከለከላቸውን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እየወሰደ እየመረመረ ነው፡፡ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ላይ የታሰሩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ጠዋት በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ቀርበው የ6000 ብር የሰው ዋስትና እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር በእስር አቆይቷቸዋል፡፡

ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ጥሶ በአሁኑ ወቅት ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ አስሯቸው የሚገኙትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ እየወሰደ እየመረመረ ይገኛል፡፡ በዛሬው ዕለት ዳንኤል ተስፋዬ ወደ ማዕከላዊ እስር ቤት ተወስዶ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ውስጥ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ምንጮች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡

የት ሂዱ ነው?

ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም

ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም

ዓለም ሁሉ ጠላን፤ በየትም አገር እየሄድን ‹‹የሙጢኝ!›› ከራሳችን መሬት በጉልበት እየተነቀልን፣ ከራሳችን ቤት እየተባረርን፤ ከተወለድንበትና ከአደግንበት አካባቢ እየተፈናቀልን፣ ጭራውን ቆልምሞ እንደሚሮጥ ባለቤቱ እንዳባረረው ውሻ በአገኘነው አቅጣጫ እየሮጥን፣ እጃችንን እያርገበገብን ‹‹የሙጢኝ!›› እንላላን፤ የፈራነውን ሞት በየመንገዱ እናገኘዋለን፤ ሞትን ሸሽተን ሞትን ያጋጥመናል፤ የሞቱ ልዩነት አይታየንም፤ በየመንገዱ የሚያጋጥመው ሞት የውርደት ሞት ነው፤ የብቸኛነት ሞት ነው፤ ዘመድ-ወዳጅ ለቀብር የማይገኝበት ሞት ነው፤ ሠለስት፣ አርባ፣ ሙታመት የማይወጣበት ሞት ነው፤ ባዕድ ምስጥ ያላሳደገውን አካል የሚበላበት ነው፤ የሞት ሞት ነው፡፡

ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ከአገር አስወጥቶ ባዶ መሬት ብቻ ይፈልግ ይመስል የወያኔ ሎሌዎች በማስፈራራት ሁሉም አገሩን እየተወላቸው እንዲሄድ ያቀዱ ይመስላል፤ ጥንት ኢሰመጉ በምሠራበት ጊዜ በየጊዜው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሰዎችን በማስፈራራት ሰላማቸውን ለመረበሽ ወደስደት ወይም ወደወንጀል ተግባር የሚመሩ የወያኔ አባለች ነበሩ፤ አሁን እንደገና ብቅ ማለት ጀምረዋል፤ ሕጋዊ ሥርዓት እየላላ ጉልበተኞች በግላቸው ለዘረፋና ለቅሚያ እየተሰማሩ ይመስላል፡፡
ስለራሴ ላውራ፤ ከእኔ የሚፈልጉት ምን እንደሆነ እርግጠኛ አይደለሁም፤ የሚፈልጉት የምኖርበትን አፓርትመንት እንደሆነም አላውቅም፤ በእኔ ቤት ያለ ሀብት የሚባል ለወያኔ አገልጋዮች የሚጠቅም ሁለት የገብረ ክርስቶስ ስዕሎች ብቻ ናቸው፤ (በዚህ አጋጣሚ እነዚህን ስዕሎች ለመግዛት የሚፈልግ ያነጋግረኝ)፤ ከዚህ ሌላ ለወያኔ ዋጋ የሌላቸው መጻሕፍት ናቸው፤ ስለዚህም አሁን በእኔ ላይ የተሰነዘረው ጥቃት እኔን ወደስደት ለመግፋት የሚደረግ ሙከራ ይሆናል፤ በ1992 ግድም ተሞክሮ ነበር፤ አልሠራም፤ ዛሬ ይበልጥ አይሠራም፤ ለማናቸውም ምክንያቱን በትክክል ለማወቅ ባልችልም በእኔ ላይ ዘመቻ መጀመሩን አንድ በቅርብ ከማውቀው ወያኔ በትክክል ተረድቻለሁ፤ ይህንን ዘመቻ በመምራት ላይ ያለውንም ሰው ማንነት ተነግሮኛል፡፡
ይህ አገር የአንድ ጉልበተኛ ቡድን ነው ብዬ አልቀበልም፤ የአባቶቼና የእናቶቼ፣ የኤቶቼና የቅድማያቶቼ አጥንትና ደም የገነባው አገር ነው፤ ማንም ለስደት አይዳርገኝም፤ ማንም አስፈራርቶ ኢትዮጵያዊነት መብቴን መግፈፍ አይችልም፤ አልፈቅድለትም፤ በግልጽ በማያጠራጥር ቋንቋ ኑሮዬም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም እዚሁ ነው፤ ከኢትዮጵያ አፈር የሚለየኝ የለም፡፡
እኔን ለማጥቃት ላሰፈሰፉት ወያኔዎችና ሎሌዎቻቸው አንድ እውነት ልንገራቸው፤– በፈለጉትና በተመቻቸው መንገድ በእኔ ላይ በጉልበታቸው ግፍ ቢፈጽሙ ነገ በነሱ ላይ የባሰ ግፍ እንደሚደርስባቸው ይወቁት፤ ሁልጊዜም ከሕግ የወጣ ጉልበተኛነት ጉልበተኛነትን ያነግሣል፤ በመግደል ድል ይገኛል ብለው የሚያምኑ ወያኔዎች ትንሽ ቆም ብለው ያስቡ፤ በመሞትም ድል ይገኛል፤ በመሞትም ማሸነፍ ይቻላል፡፡
በእኔ ላይ የዘመተው ወያኔ ወይም ሎሌ ማናቸውም ሥራ ውጤት እንዳለው ማወቅ አለበት፤ አንድ ነገር አድርጎ ምንም ዓይነት ውጤት አያስከትልም ብሎ ማሰብ ድንቁርና ነው፤ ይህ የሳይንስ ሕግ ነው፤ For every action there is a reaction ይላል!