Tag Archives: Dr. Fikru Maru

ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ እስር ቤት ውስጥ ሆነውም ኢትዮጵያውያንን እንዳግዝ ይፈቀድልኝ የሚል አቤቱታ አቅርበዋል

ጌታቸው ሺፈራው

“እንደ አለመታደል ሆኖ የራሴን እውቀት በቀጥታ ለተተኪ ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ማስተላለፍ ባልችልም በርካታ ሃኪሞችን በራሴ ወጪ ሲውዲን ሃገር ልኬ በማስተማር የዘርፉን እውቀት ወደ ሃገራችን ሃኪሞች እንዲያሸጋግሩ አመርቂ ስራ እየሰራሁ እገኛለሁ፡፡ ” ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ

Dr.Fikru Maru
ፎቶ፡ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ

ቀን፡ 22/02/2010
ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት
የልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት
አዲስ አበባ
ከሳሽ፡ የፌደራል ጠ/አ/ህግ
ተከሳሽ፡ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ ወርዶፋ (በነ ማስረሻ ሰጠ የክስ መዝገብ 13ኛ ተከሳሽ)
ጉዳዩ፡- ሃኪሞችን እና የሆስፒታል አመራሮች በምገኝበት ማ/ቤት በቢሮ በኩል እንዳገኛቸው ለማ/ቤት ትዕዛዝ እንዲሰጥልን ስለመጠየቅ

እኔ አመልካች በዚሁ ችሎት ቀርቤ እየተከታተልኩ በምገኝበት ክስ ምክንያት በማረሚያ ቤት የምገኝ ሲሆን ቀደም ሲል በሲውዲን ሃገር ሰርቼ ያገኘሁትን ገንዘብ እና 40 ዓመታት በልዩ የልብ ሕክምና ያዳበርኩትን እውቀት ይዤ ወደ ሃገሬ በመመለስ በሃገራችን ሁለት የልብ እና የልብ ነክ ሕክምና ሆሰፒታሎችን በማቋቋም ቀደም ሲል በህክምና እጦት ወደ ውጪ ሄደው መታከም ባለመቻላቸው ህይወታቸውን ያጡ የነበሩ የበርካታ ዜጎችን ህይወት መታደግ እንዲችሉ እና ባለፉት 11 ዓመታት ከ50 ሺ (ሃምሳ ሺ) ለሚበልጡ ዜጎች በአነስተኛ ዋጋ ህክምና እንዲያገኙ አድርጌአለሁ፡፡
እነዚህ ሆስፒታሎችን አሁን ድረስ በቦርድ ሊቀመንበርነት እየመራሁ እገኛለሁ፡፡
እንደ አለመታደል ሆኖ የራሴን እውቀት በቀጥታ ለተተኪ ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ማስተላለፍ ባልችልም በርካታ ሃኪሞችን በራሴ ወጪ ሲውዲን ሃገር ልኬ በማስተማር የዘርፉን እውቀት ወደ ሃገራችን ሃኪሞች እንዲያሸጋግሩ አመርቂ ስራ እየሰራሁ እገኛለሁ፡፡

ሆኖም ግን ተጠርጥሬ በእስር ላይ የምገኝ በመሆኑ ይኸው ምትክ የሌለው ህክምና ለዜጎች በተሻለ አኳኋን እንዲሰጥ በአካል በቦታው ላይ ሆኜ መምራት ባለመቻሌ በቋሚነት ህክምና የሚደረግላቸው እና አዳዲስ ህሙማንን በሚመለከት በሆስፒታሉ ያሉ ሃኪሞች አገልግሎት እንዴት መስጠት እንዳለባቸው ለሃኪሞች የተሻለ ሃሳብ /ምክር/ መስጠት እንድችል ፍ/ቤቱ የዜጎችን እጅግ ከፍተኛ ጥቅም ከግምት በማስገባት ቁጥራቸው እስከ አራት የሚሆኑ ባለሙያዎችን በቤተሰብ መጠየቂያ በኩል ቢመጡ የሚሰጠው የመነጋገሪያ ጊዜ እጅግ በጣም አጭር ደቂቃዎች ብቻ በመሆኑ ለማነጋገር አስቸጋሪ መሆኑን ከግምት በማስገባት ከእነዚህ ሃኪሞች እና የሆስፒታሉ አመራሮች ጋር በማረሚያ ቤቱ ቢሮ በኩል ተፈቅዶልኝ ከላይ ለተጠቀሰው በጣም አስፈላጊ ጉዳይ መገናኘት እንድችል እንዲፈቀድልኝ እና ለቂልንጦ ማረሚያ ቤት ትዕዛዝ እንዲሰጥልን በማክበር አመለክታለሁ፡፡
ከሠላምታ ጋር” ሲሉ ጥያቄያቸውን ማቅረባቸው ታውቃል።

በቂሊንጦ ለደረሰው ቃጠሎ ተጠያቂዎች ናችሁ በሚል በሽብር የተከሰሱት እስረኞች ላይ የሚደርሰው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት ቀጥሏል

*ለፍርድ ቤት አቤቱታ ማሰማታቸውን ተከትሎ ጨለማ ቤት እንዲታሰሩ ተደርገዋል

dr-fikru-maru

ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ         ፎቶ  ከሲውድን ሬዲዮ

ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም በአዲስ አበባ ቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ተከትሎ ለጠፋው የሰው ህይወትና ለደረሰው የንብረት ውድመት ተጠያቂዎች ናችሁ በሚል የፌደራል አቃቤ ህግ በፍይደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የሽብር ክስ መስርቶባቸው በእስር ላይ የሚገኙት 38 ተከሳሾች ላይ የሚፈጸምባቸው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ቀጥሏል፡፡

ተከሳሾች ታህሳስ 14 ቀን 2009 ዓ.ም በነበረው የችሎት ውሎ ወቅት በእስር ቤት እየደረሰብን ነው ያሉትን ኢ-ሰብዓዊ አያያዝ በተመለከተ አቤቱታ ማሰማታቸውን ተከትሎ ወደ እስር ቤቱ ሲመለሱ ጨለማ ክፍል፣ በጠባብ ቤት ውስጥ ታጭቀው እንዲታሰሩ መደረጋቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በህክምና ላይ የሚገኙት የ66 ዓመቱ ኢትዮ- ሲውድናዊው የልብ ህክምና ባለሙያ እና የ “አዲስ የልብ ህክምና ሆስፒታል” መስራች ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ በእነ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የቀረበባቸው 38 ተከሳሾች፣ የጸረ-ሽብር ህጉን አንቀጽ 3 (1፣ 2፣ 4 እና 6) ስር የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት ተላልፈዋል በሚል አቃቤ ህግ በህዳር 13 ቀን 2009 ዓ.ም በይፋ ክስ እንደመሰረተባቸው ይታወሳል፡፡ ከዚህ ክስ በተጨማሪም ሌሎች 131 ሰዎች ላይ በተመሳሳይ ክስ መከፈቱ ለመንግስት ቅርበት ባላቸው መገናኛ ብዙሃን ተዘግቦም ነበር፡፡

ተከሳሾቹ በምርመራ ወቅት እጅግ የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸው እንደነበር በተደጋጋሚ ይፋ መደረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ ይህንኑ የተፈጸመባቸውን ድርጊት ለችሎት ለማስረዳት መሞከራቸውን ተከትሎ ደግሞ አሁን ላይ በጨለማ ክፍል እንዲታሰሩ ተደርገዋል፡፡

በታህሳስ 14 ቀን 2009 ዓ.ም በነበረው የችሎት ውሎ ዳኞቹ ወደ ችሎት ሲገቡ ሁሉም ተከሳሾች ከመቀመጫቸው በመነሳት፣ ‹‹በእሳት ቃጠሎው ወቅት ህይወታቸውን ላጡ በእስር ላይ የነበሩ ወንድሞቻችን የህሊና ጸሎት እናደርጋለን›› በማለት ጸሎት አድርገው መቀመጣቸውና በወቅቱ ለደረሰው ቃጠሎም ተጠያቂው ያሰራቸው አካል መሆኑን መናገራቸው አሁን ላይ በጨለማ ክፍል ለመታጎር እንደዳረጋቸው ቤተሰቦቻቸው እምነታቸውን ይገልጻሉ፡፡

የተከሳሽ ቤተሰቦች በተከሳሾች ላይ እየደረሰ ያለው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እንዲቆም የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትን ቢያነጋግሩም፣ ‹‹ጉዳያችሁን ወደ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ውሰዱ›› የሚል መልስ እንዳገኙ ታውቋል፡፡ በዚህም የተከሳሽ ቤተሰቦች ጠቅላይ አቃቤ ህግ በማምራት ዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባየንና ምክትል ዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ብርሃኑ ወ/አገኝን አነጋግረዋል፡፡ አቶ ጌታቸው ለተከሳሽ ቤተሰቦች ‹‹ጉዳያችሁን በጽሁፍ አቅርቡ›› በማለት አቤቱታቸውን በጽሁፍ የተቀበሉ ሲሆን፣ በጉዳዩ ላይ ታህሳስ 21 ቀን 2009 ዓ.ም ምላሽ ለመስጠት ቀጠሮ ሰጥተው ነበር ፡፡ ነገር ግን ከቀናት በኋላም ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጥበት ጉዳይ ነው የሚል ሰበብ ምላሽ እንዳላገኙ ተናግረዋል፡፡

ለፍርድ ቤቱ የቀረበው የተከሳሾችን አቤቱታ  ከታች ይመልከቱ

%e1%8b%a8%e1%89%b0%e1%8a%a8%e1%88%b3%e1%88%be%e1%89%bd-%e1%8a%a0%e1%89%a4%e1%89%b1%e1%89%b3

%e1%8b%a8%e1%89%b0%e1%8a%a8%e1%88%b3%e1%88%be%e1%89%bd-%e1%8a%a0%e1%89%a4%e1%89%b1%e1%89%b3-2

ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት

%d bloggers like this: