Tag Archives: Ethio zone 9 bloggers

የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት ይከበር!

ዞን 9

Zelalem Kibret

የዜጎች ከሀገር ሀገር የመንቀሳቀስ መብት በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ አባል ሆና በፈረመቻቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለማቀፍ ድንጋጌዎች የተጠበቀ ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 32/1 ላይ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ . . . ከሀገር የመውጣት ነጻነት አለው” በማለት ተደንግጓል፡፡ ኢትዮጵያ ፈራሚ አባል የሆነችበት ‘ዓለም አቀፉ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃልኪዳን’ በበኩሉ ማንኛውም ግለሰብ ሕጋዊ ማዕቀብ ካልተጣለበት በስተቀር ወደፈለገው ቦታ የመንቀሳቀስ ከሀገር መውጣትን የሚጨምር መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡ በኢትዮጵያ ህግም ብቸኛ ገደብ የሚያስቀምጠው የኢምግሬሽን አዋጅ ቁጥር 354/2003 በአንቀጽ 7 ላይ “ማንኛውም ሰው ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ ሊታገድ የሚችለው በሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ሲታዘዝ ብቻ ነው” በማለት የመንቀሳቀስ መብት ገደብን በማያሻማ መልኩ ያስቀምጠዋል፡፡

እንደሚታወሰው የዚህ የጡመራ መድረክ አባል የሆነው ዘላለም ክብረት በወንጀል ተጠርጥሮ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በራሱ ተነሳሽነት ክሱ እንዲቋረጥ በማድረጉ ከማሕሌት ፋንታሁን፣ ከአስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ከኤዶም ካሳዬና ከተስፋለም ወልደየስ ጋር ሐምሌ 01/2007 ከእስር ተፈትቷል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የሕግ አግባብ መሠረት ከሀገር እንዳይወጣ የሚያደርግ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ክልከላም የለበትም፡፡ ይሁንና ሕዳር 05/2008 ዘላለም ለቡድኑ የተበረከተ ሽልማትን ለመቀበል ወደ ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ለማቅናት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቢገኝም የጉዞ ሰነዱ (ፓስፖርቱ) ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ ተከልክሏል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች እንደተገለጸው ጦማሪው የጉዞ ሰነዱ እንዲመለስ እና የመንቀሳቀስ መብቱ እንዲከበር ያደረገው ሙከራ ከመጉላላት በቀር ምንም መፍትሔን አላስገኘም፡፡ እንዲያውም በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ መንግሥታዊ አካል መጥፋቱን ለመታዘብ ችለናል፡፡ በዚህም ምክንያት የተለያዩ ዕድሎችን ተጠቅሞ መማርም ሆነ መሥራት እንዳይችል ሁኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንም ይህንን የመብት ጥሰት ‹ጉዳዩ ከአቅሜ በላይ ነው› በሚል ምክንያት ሊያስቆም አልቻለም፡፡

በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ በታኅሣሥ 01/2008 ዓ.ም. ለትምህርት ወደ አሜሪካ ለመሔድ በሞከረችበት ወቅት የጉዞ ሰነዷን ተቀምታ ከሐገር መውጣት እንደማትችል የተነገራት ሲሆን፤ ለምን የጉዞ ሰነዷን እንደተነጠቀች በተደጋጋሚ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት መምሪያ ጥያቄ ብታቀርብም እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ማግኘት አልቻለችም፡፡

እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በጥር 11/2008 ዓ.ም. ወደ ጀርመን ሃገር ለስድስት ሳምንታት የጋዜጠኝነት ልምድ ለመቅሰም ያገኘውን አጋጣሚ ለመጠቀም ያደረገው ሙከራም በተመሳሳይ የጉዞ ሰነዱን ያለምንም ሕጋዊ ምክንያት በመነጠቁ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

ይባስ ብሎም ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ ለስድስት ሳምንታት ወደ ጀርመን ሃገር በመሔድ በጀርመኑ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ የቀረበለት የልምድ ልውውጥ ላይ ተሳትፎ ወደ ሃገሩ ሲመለስ በየካቲት 26/2008 ዓ.ም. በተመለሰበት ወቅት ‹ከሃገር እንዴት ልትወጣ ቻልክ› ከሚል ከባድ ዛቻና ማስፈራሪያ ጋር የጉዞ ሰነዱን ሊነጠቅ ችሏል፡፡

ይህንን ሕገ ወጥ ድርጊት ለማረም ሁሉንም ሕጋዊ መንገዶች አሟጠን የምንጠቀም ሲሆን፤ ሕግ አስፈጻሚው አካል ግን ይህንን ስህተቱን ማረም የሚጀምርበት ተጨማሪ ዕድል አግኝቷል፡፡ ዘላለም ክብረት የዘንድሮው The Nelson Mandela Fellowship ወይም በቀድሞው አጠራር Young African Leaders initiative (YALI) አሸናፊ ሆኗል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ ፌሎውሽፕ የአሜሪካው ፕሬዝዳነት ባራክ ኦባማ ወጣት አፍሪካውያን አህጉራቸውን የሚጠቅሙ መሪዎች እንዲሆኑ የሚያግዛቸውን ክህሎት እንዲጨብጡ በማሰብ እ.ኤ.አ. 2010 ይፋ ያደረጉት መርሐ-ግብር ሲሆን፤ በዚህ ስድስት ሳምንታት በሚፈጀው መርሐ-ግብር በየዓመቱ በርካታ አፍሪካውያን ለራሳቸውም ለአህጉራቸውም ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት ገብይተው ተመልሰዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር አሸናፊ የሆኑት ሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ዘላለም ክብረት በመጋቢት እና ሚያዝያ ወር ቅድመ ሁኔታዎችን አሟልተው በሰኔ አጋማሽ ወደ አሜሪካ እንደሚያቀኑ የመርሐ-ግብሩ የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል፡፡

እኛም ከጊዜ ወደ ጊዜ ጉዳዩ ሕጋዊ መልክ ይይዛልና ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም ነገሮች ግን እየተባባሱ እና የመብት ጥሰቱም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይሄም ድርጊት ዜጎች በሃገራቸው ሕግን አምነው ለመኖር አለመቻላቸው ማሳያም ነው፡፡ በመሆኑም የሚመለከተው የአስፈጻሚ አካል ያለምንም የሕግ አግባብ የጉዞ ሰነዳቸውን ተቀምተው የሚገኙ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች መብታቸው ተከብሮላቸው የጉዞ ሰነዶቻቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱላቸው እንዲያደርግ እና የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንጠይቃለን፡፡

ሕገ መንግሥቱ ይከበር!

ምንጭ፡ https://www.facebook.com/Zone9ers/?fref=nf

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ምስጋና አቀረቡ

በድንገት ከያለንበት ተይዘን እንደታሰርነው አፈታታችንም ግራ የሚያጋባ ነበር፡፡ ተመሳሳይ ክሶች ቀርበውብን እያለ ግማሾቻችን ‹ክስ ተቋርጦላችኋል› ተብለን ተፈታን፣ ግማሾቻችን ደግሞ ‹ነፃ ናችሁ› (ከሳሽ በነፃነታችን ላይ ይግባኝ መጠየቁ እንዳለ ሁኖ) ተብለን ይሄው ወጥተናል፡፡ ቀሪ ክስ ይዘን በዋስ ወጥተን እየተከራከርንም ያለን አለን፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የሁላችንም ዕምነት ግን አንድም ቀን ሊያሳስረን የሚገባ ወንጀል አለመፈፃችን ማመናችን ነው፡፡ መፈታታችን ጥሩ ሁኖ፤ መታሰር በፍፁም የማይገባን ነበርን፡፡ መፃፋችን እና ሕግ እንዲከበር መጠየቃችን ሀገሪቱ አገራችን እንድትሻሻል እና ሁላችንም ዜጎች የተሻለ ህይወት አንዲኖራቸው ከመሻት ባለፈ ሌላ ነገር አልነበረውም/የለውም፡፡ ነገር ግን ይህን በማድረጋችን ተገርፈናል፣ ተዘልፈን-ተሰድበናል፣ ታስረናል ተሰደናልም፡፡ ይህ በፍጹም አይገባንም ነበር፡፡

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

የእኛ መታሰር ፖለቲካዊ ንቃት የፈጠረላቸው ሰዎች እንዳሉ ሲነግሩን ደስ ይለናል፡፡ በእኛ መታሰር ምክንያት ለመጠየቅና ለመፃፍ በጣም እንደሚፈሩ የሚነግሩን ሰዎች ስናገኝ ደግሞ እናዝናለን፡፡ የመታሰራችን ጉራማይሌ ስሜት እንደዚህ ነው፡፡ ሳይገባን በመታሰራችን የነቁ መኖራቸውን በማወቃችን የምነደሰተውን ያክል፤ ሳይገባን በመታሰራችን የተሰበሩና ከተዋስኦ መድረኩ የራቁ እንዳሉ ስናውቅ እጅግ እናዝናለን፡፡
መታሰር በደል ነው፡፡ ብዙ ነገር ያጎድላል፡፡ መታሰር መልካም ነው፡፡ ብዙ ነገር ያስተምራል፡፡ እኛ በመታሰራችን ሀገራችን የበለጠ እንድናውቃት ሁነናል፡፡ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ነፃነት አሁንም ብዙ ዋጋ እንደሚያስከፍል ተረድተናል፡፡ ሕግን መከታ አድርገው የኖሩ ‹ስም የለሽ› ዜጎች ሕጉ ሲከዳቸውና እነሱ ላይ ‹በላ› ሲያመጣባቸው ታዝበናል፡፡ ከሁሉም በላይ ፍትህ የሌለባት ሀገር ለዜጎቿ የማትመችና አገር እንደሆነች አይተናል፡፡
በእስራችን ወቅት የተለያዩ በደሎች በተቋም ደረጃ ደርሰውብናል፡፡ ግን አገር ነውና ከይቅርታ የሚያልፍ አይደለም፡፡ ለበደላችሁን አካላት እናንተ ይቅርታ ባትጠይቁንም፤ እናንተ የፈለጋችሁትን ባለማድረጋችንና ሕግን መሰረት አድርገን በመኖራችን ስላስከፋናችሁ እባካችሁ ይቅር በሉን፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል ግን እናንተ አላችሁ፡፡ ጓደኞቻችንም ናችሁ፤ ዘመቻ አድራጊዎችም ናችሁ፤ ቤተሰቦቻችንም ናችሁ፤ ጠያቂዎቻችንም ናችሁ፤ ጠበቆቻችንም ናችሁ፣ የመንፈስ አጋሮቻችንም ናችሁ ርቀት ሳይገድባች የጮሃችሁልን አለም አቀፍ የመብት ጠያቂዎችም ናችሁ … በመታሰራችን የተረዳነው አንዱ ትልቅ ነገር የናንተን መልካምነት፣ የናንተን አጋርነት እና የናንተን የማይሰለች ድካምና ፍቅር ነው፡፡ እናንተ ባትኖሩ ‹አጭሩ› የእስር ጊዜያችን ይረዝምብን ነበር፤ ‹ቀላሏ› እስር ትከብድብን ነበር፡፡ ምስጋና ለናንተ፤ እስራችን ‹አጭር› – ፈተናችን ‹ቀላል› እንዲሆን አድርጋችሁልናልና፡፡
እናንተ ወዳጆቻችን ለሁሉም ነገር – እልፍ ምስጋና፡፡
እናመሰግናለን!
የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች

በፍቃዱ ሀይሉ በ20 ሺህ ብር ዋስ ከእስር ተለቀቀ

ባለፈው ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አራቱ የዞን ዘጠኝ አባላት መካከል ናትናኤል ፈለቀ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ) በነፃ እንዲለቀቁ ሲወሰን፤ ዛሬ ጥቅምት 10 ቀን 2088 ዓ.ም. በዋለው ችሎት በወንጀለኛ መቅጫ ህግ 257/ሀ እንዲከላከል ተብይኖበት የነበረው በፍቃዱ ኃይሉ በ20 ሺህ ብር ዋስ ከእስር እንዲለቀቅ ተወሰነ፡፡

በፍቃዱ ኃይሉ

በፍቃዱ ኃይሉ

ብሎገርና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ሀይሉ ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም ለልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት የዋስትና መብቱ እንዲከበርለት ጠይቆ በነበረው መሰረት ለዛሬ ጥቅምት 10/2008 ዓ.ም የዋስትናውን ጉዳይ ለማየት ቀጠሮ የሰጠው የልደታ ፍርድ ቤት በ20 ሺህ ብር ዋስ ወጥቶ ጉዳዩን በውጭ ሆኖ እንዲከታተል ወስኗል፡፡
አራቱ የዞን ዘጠኝ አባላት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ በተወሰነበት ወቅት ክሱ ከሽብርተኝነት ወጥቶ በማስረጃነት የቀረቡበት ፅሁፎች አመፅ ቀስቃሽ ናቸው በሚል በወንጀለኛ መቅጫ ህግ 257/ሀ እንዲከላከል የተወሰነበት በፍቃዱ ሀይሉ መከላከያ ምስክሮቹን እንዲያሰማ ለህዳር 27 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

በዞን 9 ብሎገሮችና ጋዜጠኞች ክስ ላይ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን መስማት ጀመረ

Ethiopia-Federal-High-Court-300x194

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆየው የማስረጃ መስማት ውሎ ዛሬ ምስክሮችን በማስማት ተጀምሯል፡፡ በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ ጉዳዬን ያስረዱልኛል ያላቸውን 17 ምስክሮች ያስመዘገበ ሲሆን 15ቱ በፍርድ ቤቱ ተገኝተው ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ አቃቤ ህግ ችሎቱ በዝግ ችሎት አንዲሆን የጠየቀ ሲሆን ምስክሮቼ እና የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለመጠበቅ ችሎቱ በዝግ ሊሆን ይገባል የሚለውን አቤቱታውን ጠበቆች በከፍተኛ ደረጃ ተቃውመውታል፡፡ ምስክሮቹ የጭብጥ ምስክሮች ሳይሆኑ ፍተሻን የታዘቡ የደረጃ ምስክሮች በመሆናቸው እና ስማቸውም በግልጽ ተከሳሾች ጋር ስለደረሰ ምንም አይነት የደህንነተ ስጋት የለባቸውም ከሚለው የጠበቆች ክርክር በኋላ ፍርድ ቤቱ በጉዳዬ ላይ ተወያይቶ ለመወሰን ረፍት ወስዷል፡፡ በዚህም መሰረት የአቃቤህግን አቤቱታ ውድቅ በማድረግ ችሎቱ በግልጽ ሆኖ መስክሮች ምስክርነታቸውን እነዲያሰሙ ታዟል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ምስክሮች አነማን ላይ አንደሚመሰክሩ እና ምን አንደሚመሰክሩ በተጠየቀው መሰረት ፍርድ ቤቱም በጠበቆቹ ስለተነሱት ነጥቦች የአቃቤ ህግን ምላሽ ጠይቋል፡፡ አቃቤ ህግም በዛሬው ዕለት የቀረቡት ምስክሮች በ2ኛ፣ በ3ኛ፣ በ5ኛ፣ በ6ኛ፣ በ7ኛ እና 8ኛ ተከሳሾች ( በስድስቱ የዞን9 ጦማርያን ላይ እና በጋዜጠኛ አስማማው ላይ ) ላይ እንደሚመሰክሩ ገልጾ የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቡድን በብርበራ ያገኛቸው ማስረጃዎች ከተከሳሾች የተገኙ ስለመሆናቸው ያስረዱልኛል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡

ዞን9

በምላሹም መሰረት የአቃቤ ህግ ምስክሮች ምስክርነታቸው ሰጥተዋል፡፡ ምስክርነታቸው ሲሰጡ በነበረበት ወቅት የተከሳሾችን ስም አለማወቅ አንዲሁም የተከሳሾችን መልክ አለመለየት የመሳሰሉት ጉዳዬች የተስተዋሉ ሲሆን ምስክርነታቸውን የሰጡት ሰዎች ስም ዝርዝር እና የምስክርነታቸው ጭብጥ በአጭሩ አንደሚከተለው ነው ፡፡

1.ሙሉጌታ መዝገቡ ለማ – ናዝሬት ነዋሪ ነኝ መአከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፓሊስ ታዛቢ ምስክር አንድሆን ጠይቆኝ በዚያ መሰረት ምስክር ሆኜ ተገኝቻለሁ፡፡ ከአቤል ከኮምፒውተሩ ላይ ጽሁፍ ሲወጣ እና ሲፈርም አይቼ እኔም ፈርሜያለሁ ፡፡ የጽሁፉን ይዘት አላነበብኩም አንዳንድ ቦታ አፍሪካ ሪቪው ኬንያ የሚል ቃል አይቻለሁ የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡

2.በለጡ አበበ ዮሴፍ ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 32 ሲሆን ከፍተኛው ፍርድ ቤት የካ ምድብ ሰራተኛ ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ነዋሪ ሲሆኑ በማን ላይ ለመመስከር እንደመጡ ሲጠየቁ በስም እንደማያስታውሱት ገልጸው በአካል ግን ለይተው አሳይተዋል፡፡ መስካሪዋ በ6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ክብረት ላይ የሚመሰክሩ ሲሆን በተለየ ስም ሲጠሩት ተስተውለዋል
“የሽብርተኝነት ጉዳይ የሚያመለክት ይመስለኛል፡፡ ወደ 70 ገጽ አማርኛና 10 ገጽ እንግሊዝኛ ጽሁፍ ተገኝቷል፡፡ ያየሁትን አይቼ ፈርሜያለሁ፡፡” ካሉ በኋላ ተከሳሹስ ፈርሟል ተብለው ሲጠየቁ መጀመሪያ አላስታውስም ቢሉም እንደገና ሲጠየቁ ግን አዎ ፈርሟል ብለዋል፡፡

3.እታፈራሁ ጌታቸው ወልዴ የሚባሉ ሲሆን እድሜያቸው 36 ነው፡፡ በመንግስት ት/ቤት በአስተዳደር ሰራተኛነት የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ ማን ላይ እንደሚመሰክሩ ሲጠየቁ ፍቃዱ እና…..(ስሙ ጠፍቶባቸው ቆይተው) እ…አጥናፉ ብለዋል፡፡ በአካል ደግሞ በፍቃዱን አሳዩ ሲባሉ አጥናፍን አሳይተዋል፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ማእከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄደው ጽሁፎች ሲታተሙ ማየታቸውንና በፍቃዱ በፍቃደኛነት ሲፈርም ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለጽሁፎቹ ሲጠየቁ “የአማርኛ ጽሑፎች ናቸው፡፡ 60 ገጽ የሚሆን ‹ወያኔ ይውደም› ምናምን የሚል ጽሑፍ አይቻለሁ፡፡ እንግሊዝኛም አለው 10 ገጽ ይሆናል፡፡ በምስል ከውጭ ሰው ጋር ሆነው የሚነጋገሩትም አይቻለሁ፡፡ ይዘቱ ግን ግር ይለኛል፡፡” ብለዋል፡፡ አጥናፍን አስመልክቶ ደግሞ ‹‹የእሱንም በዚያው መልኩ ነው ያየነው፡፡ ዕለቱም ግንቦት 16/2006 ነው፡፡ ኮምፒውተሩ ላይ የነበሩትን ጽሁፎች እዚያ ለነበሩት ሲያሳይ ነበር፡፡ ጽሑፎችን አይቻቸዋለሁ….‹የጨለማው ቀን….የጨለማው ንጉስ› የሚል አይቻለሁ፡፡ ‹ኢትዮጵያ አንድ ናት› የሚልም አይቻለሁ፡፡ ወደ 30 ገጽ ይሆናል፡፡ ሁሉም ፕሪንት ተደርጎ ሁላችንም ፈርመንበታል፡፡››ብለዋል

ሶስቱ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ጠበቆች በሂደቱ ላይ አስተያየት አለን በማለት፣ ዶክመንቶቹ ፕብሊክ ዶክመንት ናቸው በአደባባይ የተጻፉ ጽሁፎቻቸው እና በማንኛውም ቦታ የሚገኙ ስለሆኑ ዶክመንቶቹን ክደን አልተከራከርንም የእኛ ክርክር ዶክመንቶቹ ለወንጀል ስራ የሚበቁ አይደሉም ነውና በዚህ ጭብጥ ዙሪያ ምስክር መስማቱ ያብቃልን የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡አቃቤ ህግ በበኩሉ ሁሉም ምስክሮች አንዲሰሙልኝ እፈልጋለሁ በማለቱ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ያስረዱልኛል ካለ ይቀጥል በማለቱ ምስክሮቹ ቀጥለዋል፡፡ ጠበቆች መስቀለኛ ጥያቄ ሳይጠይቁ ተከታዬቹ ምስክሮች መሰማታቸው ቀጥሏል፡፡

4.አራተኛው ምስክር አፈወርቅ ካሳ ይባላሉ፡፡ የግል ሰራተኛ ሲሆኑ እድሜያቸው 46 ነው፡፡‹‹ቀኑ ሚያዝያ 18/2006 ነው፡፡ የተከሳሹ አስማማው ቤት ጠዋት 3፡00 አካባቢ ሲፈተሸ ታዛቢ ነበርኩ፡፡ ጋዜጦች፣ መጽሔቶች፣ ፓስፖርት…ብዙ ወረቀቶች ላይ ‹‹አዎ የእኔ ናቸው›› እያለ ሲፈርም አይቻለሁ፡፡ እኔም ፈርሜያለሁ፡፡ ቤተሰቦቹም ቤት ውስጥ ነበሩ፡፡ አብዛኛው ያየሁት የግል መጽሄቶችን ነው፡፡ ማህተምም አይቻለሁ፡፡ ደሞ ቢሮው ሄደን ላፕቶፕ፣ ፍላሽ፣ ሲዲ፣ መጽሔቶች አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ የሚፈልገውን እየለየ ፈርመናል፡፡ ወደቢሮው የሄድነው በመኪና ነበር፡፡ ከዛ ደግሞ አድራሻችንን ይዘው ስለነበር ሰኔ 4….አይ 14/2006 ነው መሰለኝ ከማዕከላዊ ተጠርተን ላፕቶፕ ላይ የነበረውን ስዕሎችና የእንግሊዝኛ ንግግሮች ሲወጡ አይቻለሁ፡፡ የእኔ ነው ብሎ ሲፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡›› ብለው ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

5.አምስተኛ ምስክር አጌና አንከና ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 48 ሲሆን ነዋሪነታቸው አ.አ ነው፡፡ የሚመሰክሩት ደግሞ በ3ኛ ተከሳሽ ናትናኤል ላይ ነው፡፡ የምስክርነት ቃላቸው፣ ‹‹ሰኔ 17/2006 ለግል ጉዳይ ማዕከላዊ ነበርኩ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ፖሊስ ጠይቆኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ላፕቶፑ ላይ አማርኛ ጽሑፎች አይቻለሁ፡፡ ጽሑፎቹ የተከሳሹ ስለመሆናቸው አምኖ ሲፈርምባቸው ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ ይዘቱን ግን አላነበብኩትም፤ አልተረዳሁትም፡፡ የገጹን ብዛትም አላስታውስም፡፡›› የሚል የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

6.ስድስተኛ ምስክር ገብረጨርቆስ ገብረመስቀል ይባላሉ፡፡ የ50 ዓመት የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ ምስክሩ በአስማማው ላይ ለመመስከር እንደመጡ ቢናገሩም በአካል ግን ለይተው አላወቁትም፡፡ እንዲያውም አስማማውን አሳዩ ሲባሉ አቤልን አሳይተዋል፡፡

ከፍርድ ቤቱ ውሎ በኋላ አስተያየታቸው የሰጡት የተከሳሾች ጠበቆች አቃቤ ሀግ ያቀረባቸው ምስክሮች ወረቀት ሲፈረም አየን ከማለት ውጪ ምንም አይነት ለሂደቱ ቁም ነገር ያለው ምስክርነት የሚሰጡ አይደሉም ፡፡ ተከሳሾች ተገኘባቸው የተባለው ጽሁፍ የአደባባይ ዶክመንት ከመሆኑም በላይ አልተገኘብንም ብለን ክደን አልተከራከርንም በይዘቱ ላይ ክርክር ስላልተደረገ መስቀለኛ ጥያቄ ለማቅረብም ብዙ አልጨነቅንም ብለዋል፡፡አቃቤ ሀግ የወንጀሉን የመጀመሪያ ደረጃ ጭብጥ የሚያሳዬ ምስክሮችን ያቅርብ አይቅርብ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የማስረጃ ማሰማት ሂደቱ ነገ ይቀጥላል፡፡

በተቃራኒው ምሳቸውን ችሎት ውስጥ የተመገቡት ሁሉም እስረኞች በጠንካራ መንፈስ ሆነው ሲጨዋወቱ እና ሲነጋገሩ ተስተውለዋል፡፡ የችሎቱ ተሳታፌዎች በምስክሮች መደናበር እየሳቁ ነበረ ሲሆን የዞን9 ወዳጆች አጋሮች ቤተሰብና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡

ምንጭ፡-ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ

ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የዞን ዘጠኝ ብሎገሮችና ጋዜጠኞች፤ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ፡፡
ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ለ17ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ልደታ ምድብ 9ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ሸለመ በቀለ “የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስከበሩልንም” በሚል ከችሎት እንዲነሱ በጽሑፍ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተሰየመው ተሻሽሎ ቀርቧል በተባለው የአቃቤ ህግ ክስ ላይ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመስማት እንደነበር ዳኞቹ ቢናገሩም፣ ተከሳሾች አቤቱታ እንዳላቸው በመግለጽ የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ዝግጁዎች አለመሆናቸውን ለችሎቱ ማስረዳት ችለዋል፡፡
ተከሳሾች ‹‹እኛ በሰብሳቢ ዳኛው ላይ አቤቱታ አለን፤ ፍርድ ቤቱ የራሱን ውሳኔ እንኳ አላከበረም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የእምነት ክህደት ቃላችንን ለመስጠት ዝግጁዎች አይደለንም›› በሚል ፍርድ ቤቱ አቤቱታቸውን እንዲቀበል ጠይቀዋል፡፡

ዳኛ ሸለመ በቀለ “ፍርድ ቤቱ ቃሉን አላከበረም›› በሚለው ጉዳይ ላይ መልስ ሲሰጡ ‹‹የእኛን ውሳኔ የማትቀበሉ ከሆነ ጉዳዩን በይግባኝ እንዲታይ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
“ላለፉት ስድስት ወራት በነበረው የክርክሩ ሂደት የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ሂደቱን በአግባቡ በመምራት የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስጠበቁልንም፡፡ በተለያየ ጊዜም ሐሳባችን ለመግለጽ ስንሞክር ክልከላ አድርገውብናል፡፡ አሁን ደግሞ ችሎቱ ራሱ የሰጠውን ትዕዛዝ ራሱ ሽሮ ፈጽሞ ልንረዳው በማንችለውና የመከላከል መብታችንን በሚያጣብብ የክስ ሁኔታ ክርክሩን እንድንቀጥል ሲበየንብን የችሎቱ ሰብሳቢ ወሳኝ ሚና ነበራቸው” ሲሉ ተከሳሾች በሰብሳቢ ዳኛው ላይ ቅሬታቸውን በአቤቱታቸው ገልፀዋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ከችሎት እንዲነሱ የሚጠይቀውን አቤቱታ አይቶ ነገ ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል ሲል ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

%d bloggers like this: